"ሮበርት ፕሪቮስት አዲሱ ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ ማን ናቸው? BBC
የሰላም ያድርገው። አሜን።
• "ሮበርት ፕሪቮስት አዲሱ ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ ማን ናቸው?
ትናንት ከሰዓት በቫቲካን ቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ የተሰባሰበው ሕዝብ የተመረጡት አዲስ ሊቀ ጳጳስ ማን መሆናቸው በይፋ ከመነገሩ በፊት 'ረዥም ሕይወት ለጳጳሳችን' እያለ ድምጹን ጮክ አድርጎ ደስታውን ሲገልጽ ነበር።
የ69 ዓመቱ ሮበርት ፕሪቮስት 267ኛ ሊቀ ጳጳስ ሆነው ሲሾሙ መጠሪያቸውም ሊዮ 14ኛ እንደሚሆን ተነግሯል።
ምንም እንኳ አብዛኛውን የአገልግሎት ዘመናቸውን ያሳለፉት በላቲን አሜሪካ ቢሆንም፣ የሮማ ካቶሊክ ቤተክርስትያን ለመጀመርያ ጊዜ አሜሪካዊ ሊቀ ጳጳስ መሾሟ ነው።
ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ ጵጵስናቸውን ከመቀበላቸው በፊት በፔሩ በሚሽነርነት ለረዥም ዓመታት አገልግለዋል።
በ1955 በስፔናዊ እናታቸው እና የፈረንሳይ እና ጣልያን ደም ካላቸው አባታቸው በቺካጎ የተወለዱት ፕሪቮስት፣ በ1982 ቅስናቸውን ተቀብለዋል።
ከሦስት ዓመት በኋላ ወደ ፔሩ ቢያመሩም ወደ አሜሪካ ለተለያዩ አገልግሎቶች ይመላለሱ ነበር።
የፔሩ ዜግነት ያላቸው ፕሪቮስት ከተገለሉ ማኅበረሰብ አባላት ጋር በመስራት እንዲሁም ልዩነቶችን ለማጥበብ በመጣር ይታወቃሉ።
በሰሜናዊ ምዕራብ ፔሩ የአንድ ቤተክርስትያን መጋቢ በመሆን ለ10 ዓመት ያህል ያገለገሉት ፕሪቮስት፣ በካቶሊክ ሴሚናሪ ውስጥ በመምህርነትም ሰርተዋል።
ሊዮ 14ኛ ሊቀ ጳጳስ ሆነው ከተሾሙ በኋላ በተናገሩት የመጀመርያ ንግግር በሞት ለተለዩት ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ ያላቸው ፍቅርን ገልጸዋል።
"አሁን ድረስ ደካማውን ነገር ግን በብርታት የተሞላውን የሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ ድምጽ ሲባርከን ይሰማናል" ብለዋል።
"በጋራ ከእግዚአብሔር ጋር እጅ ለእጅ ተያይዘን ሁላችንም ወደ ተሻለ ነገር እንሻገር" ሲሉ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ተሰብስቦ ደስታውን ለሚገልፀው ሕዝብ ንግግር አድርገዋል።
በፔሩ በሚሽነሪነት አገልግሎት ላይ ሳሉ፣ ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ በፔሩ ቺክላዮ ጳጳስ አድርገው ሾሟቸዋል።
በምርጫው ላይ በተሳተፉት ካርዲናሎች ዘንድ በላቲን አሜሪካ ጳጳሳትን በመምረጥ እና በመሾም ቁልፍ ሚና ያላቸው የጳጳሳት አለቃ ሆነው በማገልገላቸው በሚገባ ይታወቃሉ።
ሊቀ ጳፓስ ፍራንሲስ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2023 ኤጲስ ቆጶስ አድርገው ከሾሟቸው ከጥቂት ጊዜ በኋላ ካርዲናል አድርገው ሾመዋቸዋል።
• የሊቀ ጳጳስ ሊዮ አመለካከቶች ምንድን ናቸው?
በካቶሊክ ቤተ ክርስትያን ውስጥ ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ ጀምረዋቸው የነበሩ ለውጦችን ያስቀጥላሉ ተብሎ በበርካቶች ዘንድ ይታመናል።
ፕሪቮስት ስደተኞችን፣ ድሆችን እንዲሁም አካባቢን በተመለከተ የሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስን እምነት ይጋራሉ።
ካርዲናል በነበሩበት ወቅት የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስን አቋም ያለምንም ማወላወል ከመሞገት ወደ ኋላ አላሉም ነበር።
የትራምፕ አስተዳደር ሰነድ አልባ ስደተኞችን ወደ ኤል ሳልቫዶር ሲያጓጉዝ ተችተው አቋማቸውን በጽሁፍ ያጋሩ ሲሆን፣ ቫንስ በፎክስ ኒውስ ላይ ቀርቦ የሰጠውን ቃለ ምልልስም እንዲሁ አብጠልጥለው ተችተዋል።
"ጄዲ ቫንስ ተሳስቷል። ኢየሱስ ለሌሎች ያለንን ፍቅር ደረጃ እንድናወጣለት አልጠየቀም" ብለዋል በጽሑፋቸው።
ሮበርት ፕሪቮስት ምንም እንኳ አሜሪካዊ ቢሆኑም እንዲሁም በካቶሊክ ቤተክርስትያን ውስጥ ያለውን መከፋፈል በሚገባ የሚያውቁ ቢሆኑም ቤተክርስትያኒቷን ወደ አንድ ያመጣሉ ተብሎ ተስፋ ተጥሎባቸዋል።
በላቲን አሜሪካ ረዥም ዓመት ማሳለፋቸውን በመጥቀስ ብዙዎች ከአርጀንቲና የተገኙት ሊቀ ጳጳስ የጀመሯቸውን ሥራዎች ያስቀጥላሉ ይላሉ።
ቫቲካን ፕሪቮስት ለረዥም ዓመት በላቲን አሜሪካ ማገልገላቸውን በማስታወስ ከሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ በመቀጠል ሁለተኛው ላቲን አሜሪካዊ ሊቀ ጳጳስ ስትል ጠርታቸዋለች።
በፔሩ በነበሩበት ወቅት ከጾታዊ ጥቃት ጋር በተያያዘ ስማቸው የተነሳ ቢሆንም ያገለግሉባቸው ቤተ እምነቶች እና አብረዋቸው የሰሩ አባቶች ምንም ዓይነት ተሳትፎ የላቸውም ሲሉ ተከላክለውላቸዋል።
አዲሱ ሊቀ ጳጳስ በተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት ላይ ያላቸው አቋም ግልጽ አይደለም። ነገር ግን ወግ አጥባቂ የሆኑ ካርዲናሎች ሳይቀሩ ከሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ የለዘበ አቋም እንደሚኖራቸው ያምናሉ።
ሊዮ 14ኛ ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ የተመሳሳይ ጾታ አፍቃሪ ጥንዶችን መባረክን በሚመለከት መመርያ ሲያስተላልፉ ምንም እንኳ ጳጳሳት ውሳኔውን እንደሚያገለግሉበት አገር ባሕል እና አውድ አንዲተረጉሙ ቢገልፁም ድጋፋቸውን ገልጸዋል።
ባለፈው ዓመት ስለ አየር ንብረት ለውጥ በተናገሩበት ወቅት የያኔው ካርዲናል ፕሪቮስት "ከቃል ወደ ተግባር የምንሸጋገርበት" ጊዜ አሁን ነው ብለው ነበር።
የሰው ልጅ ከአካባቢው ጋር "የተናበበ ግንኙነት" መመስረት እንዳለበት ያስተምራሉ።
በቫቲካን የኤሌትሪክ መኪናዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ እንዲሁም ከፀኃይ ብርሃን የሚገኝ ኃይል ስለመጠቀምም በመስበክ ይታወቃሉ።
ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ፣ ፍራንሲስ ሴቶች ወደ ጵጵስናው እንዲመጡ ለመጀመርያ ጊዜ ውሳኔ ሲያስተላልፉ ድጋፋቸውን ገልፀዋል።
• ቀጣዩ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ማን ሊሆኑ ይችላሉ? አፍሪካውያንስ አሉ?
አሜሪካዊ ካርዲናል ሮበርት ፕሪቮስት
አሜሪካዊው ሮበርት ፕሪቮስት የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተመረጡ
በአሜሪካ ቺካጎ ተወልደው ያደጉት የ69 ዓመቱ ካርዲናል ሮበርት ፕሪቮስት፣ ፖፕ ሊዮ ተብለው የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተመረጡ።
ካርዲናል ፕሪቮስት በፔሩ ጳጳስ ሆነው ከመሾማቸው በፊት በሚሺነሪነት አገልግለዋል።
ሊቀ ጳጳሱ ከእንግሊዝኛ በተጨማሪ ጣልያንኛ እና ስፓኒሽኛ የሚናገሩ ሲሆን፣ በተለያዩ ማኅበራዊ አገልግሎታቸው እንዲሁም አዳማጭነታቸው ይጠቀሳሉ።
ከሁለት ዓመት በፊት እአአ በ2023 ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ የቫቲካን የጳጳሳት አለቃ አድርገው በመሾም ቀጣዩን የጳጳሳት ትውልድ በመምረጥ ውስጥ ቁልፍ ሥልጣን እንዲኖራቸው አድርገዋል።
ካርዲናል ፕሮቮስት ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ ተብለው ለመጠራት መወሰናቸው ተገልጿል።
ለሁለት ቀናት አዲሱን ሊቀጳጳስ ለመምረጥ የተሰባሰቡት የቤተ ክርስቲያኗ ካርዲናሎች ከተሰበስቡብት ቤተ መቅደስ አናት ላይ አዲስ ሊቀ ጳጳስ መመረጡን የሚያሳየው ነጭ ጭስ የታየው ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ነበር።
የሮማ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ካርዲናሎች በምሥጢር በሚሰጡት ድምጽ ለመመረጥ በዕጩነት ከቀረቡት ካርዲናሎች መካከል ሁለት ሦስተኛውን ድምጽ ያገኙት የሃይማኖት አባት ቀጣዩ ሊቀ ጳጳስ ይሆናሉ።
አሜሪካዊው ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ በቫቲካን አዲሱን ሊቀ ጳጳስ ለመምረጥ ለሁለተኛ ቀን የተሰባሰቡት ካርዲናሎች በምሥጢር ድምጻቸውን መስጠታቸውን ተከትሎ ነው አዲስ ሊቀ ጳጳስ መሆናቸ ይፋ የተደረገው።
ድምጽ መስጠት ከሚችሉት 133 ካርዲናሎች መካከል የ89ኙን ይሁንታ ያገኙት ሊቀ ጳጳስ በቅዱስ ጴጥሮስ ካቴድራል በረንዳ ላይ ብቅ በማለት ለሕዝብ ታይተዋል።
በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ የተሰባሰቡ የእምነቱ ተከታዮች ሊቀ ጳጳሱን ሲመለከቱ ደስታቸውን በጩኸት እና በእንባ ገልጸዋል።
ዕድሜያቸው እስከ 80 ዓመት የሚሆን 133 ካርዲናሎች ቀጣዩ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳስ ማን ሊሆን እንደሚገባ ከተወያዩ በኋላ ይሆናሉ ያሏቸውን በዛሬው ዕለት መርጠዋል።
ሚያዝያ 13/2017 ዓ.ም. ሕይወታቸው ያለፈው ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስን የተኩት አባት አሜሪካዊው ካርዲናል ሮበርት ፕሮቮስት ሆነው ተመርጠዋል።
በጣልያንኛ እና በስፓኒኛ ቋንቋ የመጀመሪያ ንግግራቸውን ያደረጉት ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ "ይህ ሰላም የመላበት ሰላምታዬ ለሁላችሁም ልብ እና ቤተሰብ . . . እንዲሁም በዓለም ላሉ ሕዝቦች እንዲደርስ ይሁን" በማለት መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
የመጀመሪያው አሜሪካዊ ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰበው ከ40 ሺህ በላይ ለሚሆነው ሕዝብ ባደረጉት ንግግር "እግዚአብሔር ሁላችንንም ይወደናል፤ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ" ብለዋል።
አዲሱ የሮማ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ "ሰብዓዊነት በእግዚአብሔር እና በፍቅሩ የሚደረስበት ድልድይ ክርስቶስን ይፈልጋል። አግዙን፤ እርስ በርሳችሁም ተረዳዱ። ድልድይ እንገንባ" ብለዋል።
በንግግራቸው በሞት የተለዩትን ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስን ያስታወሱት ተተኪያቸው ለሕዝቡ እርሳቸው እንዳደረጉት ምዕመናኑን መባረክ እንደሚፈልጉ ተናግረው ቡራኬ ሰጥተዋል።
ድምጻቸውን የሰጧቸውን ካርዲናሎች ያመሰገኑት ሊቀ ጳጳስ ሊዮ 14ኛ "እግዚአብሔር ወዳዘጋጀልን ቤታችን ሁላችንም በጋራ እንጓዛለን" ካሉ በኋላ "ለሮማ ቤተክርስቲያን ልዩ ሰላምታ ይድረስ" ብለዋል።
በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተገኙት የእምነቱ ተከታዮች አንድነት እንደሚያስፈልግ አጽንኦት ሰጥተው የተናገሩት ሊቀ ጳጳሱ ሁሉም በጸሎት እንዲያግዛቸው ጠይቀዋል።
• የአዲሱ ጳጳስ ምርጫ
የአዲሱ ሊቀ ጳጳስ ማንነት ይፋ ከመሆኑ በፊት በምስጢር ድምጽ የሚሰጡት ካርዲናሎች እዚህ ውሳኔ ላይ ለመድረስ ሁለት ቀን ወስዶባቸዋል።
ይህም ማለት በዕጩነት የቀረቡት እና ሁለት ሦስተኛው መራጭ የተስማማባቸው አባት ብዙዎችን መማረክ ችለዋል ማለት ነው።
ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ እና ቤኔዲክት 16ኛ ሲመረጡም አብላጫውን ድምጽ ማግኘታቸው የታወቀው በሁለተኛው ቀን ነበር።
ነገር ግን ቤተክርስቲያኒቱን ለረዥም ዓመት በሊቀ ጳጳስነት ያገለገሉት ጆን ፖል ዳግማዊ እአአ በ1978 በሦስተኛው ቀን ነበር መመረጣቸው የታወቀው።
በሲስቴይን ቤተ መቅደስ የተሰባሰቡ 133 ካርዲናሎች ተራማጅ፣ ወግ አጥባቂ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ አንድ ያመጣሉ ተብለው ተስፋ ከተጣለባቸው አባቶች መካከል አንዱን በአብላጫ ድምጽ መምረጥ ይጠበቅባቸው ነበር።
አዲሱን ሊቀ ጳጳስ ለመምረጥ የተሰባሰቡት 133 ካርዲናሎች ከ71 የተለያዩ አገራት የተገኙ ናቸው።
በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ የተሰባሰበው የእምነቱ ተከታይ አዲሱ ጳጳስ ማን መሆናቸውን ለማየት በጉጉት እየጠበቀ ነው።
የካርዲናሎቹ ምርጫ በመላው ዓለም በሚገኙ 1.4 ቢሊዮን ተከታዮች ዘንድ እና በቤተክርስቲያኒቷ ላይ ተጽዕኗቸው የገዘፈ ነው።
በአሁኑ ምርጫ ከተሳፉት 80 በመቶ የሚሆኑት ካርዲናሎች የተመረጡት በሟቹ ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ የተሾሙ ናቸው።
አብዛኞቹም ለመጀመሪያ ጊዜ ሊቀ ጳጳስ የመርጡ ሲሆን፣ አጠቃላይ ዓለም አቀፍ ምልከታም ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።
• ጳጳሱ ሲመረጡ የተደረገው. . .
በዕጩነት ከቀረቡት ካርዲናሎች መካከል አንደኛው አስፈላጊውን ድምጽ አግኝተው ከተመረጡ "ይህንን ቀኖናዊ ምርጫ ተቀብለው የቤተ ክርስቲያኒቱን ሊቀ ጳጳስነት ይቀበላሉ?" ተብለው ተጠይቀዋል።
ተመራጩ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ተብለው ሊጠሩበት የሚፈልጉትን ስም በመምረጥ የጵጵስና ካባ እንዲለብሱ ይደረጋል። የጵጵስና ስማቸውም ሊዮ 14ኛ የሚለውን ስም መርጠዋል።
የቀሩት ካርዲናሎችም ለአዲሱ ጳጳስ እጅ በመንሳት በአገልግሎታቸው ሁሉ ሊታዘዟቸውም ቃል ገብተዋል።
ይህንንም ተከትሎ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰበው ሕዝብ ከቅዱስ ጴጥሮስ ቤተ ክርስቲያን በረንዳ ላይ በላቲን ቋንቋ "ጳጳስ አለን" ተብሎ ይታወጇል።
የአዲሱ ሊቃነ ጳጳሳት ስም ለሕዝቡ ይፋ ሆኖ፣ ጳጳሱ ራሳቸውም በአካል ወጥተው ለሕዝቡ ታይተዋል። አዲሱ ጳጳስም አጭር ንግግር አድርገው ለከተማዋ እና ለዓለም የቡራኬ ቃል አስተላልፈዋል።
በመጨረሻም በምሥጢራዊ ምርጫ ሂደት የእያንዳንዱ የምርጫ ዙር ውጤትን ጳጳሱ እንዲመለከቱ ይደረጋል።
ሰነዶቹ ታሽገው በቫቲካን ቤተ መዛግብት ውስጥ እንዲቀመጡ ተደርገው ከዚያ በኋላ ሊከፈቱ የሚችሉት በሊቀ ጳጳሱ ትዕዛዝ ብቻ ነው።"
አስተያየቶች
አስተያየት ይለጥፉ