#ጎንደር ትናንት ዛሬና ነገ #ጎንደር ከ1624 እስከ 1792 ዓ.ም ድረስ የሀገራችን መዲና ነበረች፡፡

 

#ጎንደር ትናንት ዛሬና ነገ
#ጎንደር ከ1624 እስከ 1792 ዓ.ም ድረስ የሀገራችን መዲና ነበረች፡፡ የጎንደር የከተሜነት ታሪኳ የሚጀምረው በአፄ ፋሲለደስ የንግስና ዘመን የመጀመሪያዎቹ ዓመታት እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይሁንና ጎንደር የሚለው ስያሜ በአፄ አምደፂዩን የንግሰና ዘመን ማለትም ከ1312 አስከ 1342 በዜና መዋዕል ተጠቅሶ መገኘቱ የጎንደርን ዕድሜ ለማሰላት በርካታ ዓመታተን ወደ ኋላ መመለስን የሚጠይቅ እንደሆነ አመላካች ነው፡፡

 
ጎንደር ፋሲለደስ የነገሱበትን 36 ዓመታት ጨምሮ የልጃቸው የፃዲቁ ዮኃንስና የልጅ ልጃቸው የታላቁ እያሱ 75 የንግስና ዓመታት የጎንደር ወርቃማ ዘመናት እንደነበሩ ታሪክ ይዘክራል፡፡
#የጎንደር የጨለማ ዘመን ተብሎ የሚታወቀው ደግሞ አፄ ተክለ ጊወርጊስ ስልጣን ከለቀቁበት ከ1792 ዓ/ም ጀምሮ አንደነበር ይነገራል፡፡
ኢትዮጵያ በዛጉየ ስረዎ መንግስት ማለትም ከ13ኛው ክፍለ ዘመን ወዲህ ቋሚ የማዕከላዊ መንግስት መቀመጫ አልነበራትም፡፡ በአፄ ፋሲለደስ የንግስና ዘመን ጎንደር የሀገሪቱ ዋና ከተማ መሆኗ በኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግስት መመስረት አዲስ ምዕራፍ መክፈት ችሏል፡፡
#የጎንደር ከተማ ከ200 ዓመታት በላይ በተከታታይ ለአስራ አራት ነገስታት መቀመጫ መዲና በመሆን አገልግላለች፡፡
የጎንደር ከተማ ጥንታዊ ስልጣኔ ሰላም የሰፈነበት ህግና ፍትህ የተከበረበት ኪነ-ጥበብና እውቀት ለማስፋፋት እድል የተገኘበት ጊዜ መሆኑን ጥንታዊ የታሪክ አሻራዎች ይዘከራሉ፡፡ የጎንደር ጥንታዊ ስልጣኔ ሲዘከር የኪነ-ህንፃ ጥበብ፣የእደ-ጥበብ ቱርፋቶች፣የንግድ ማዕከልነቷና ዘመናዊ የከተሜነት ይዞታዋ ተጠቃሾች ነበሩ፡፡ የጎንደር የእደ-ጥበብ ውጤቶች ከጎንደር ወርቃማ ዘመን አስከ ዘመነ መሳፍንት ድረስ ከፍተኛ እምርታ የታየበት እንደነበር ይነገራል፡፡ በልብስ ስፊት፣በልኳንዳ፣ በወፍጮ፣ በዳቦ መጋገሪያ፣ በአናጢ ስራ፣ በቆዳ ስራ፣ በህትመት ወዘተ ጎንደር በጊዜው እጀግ የሰለጠነች እንደትባል አስችሏታል፡፡ መፅሀፍት በብቃትና በጥራት ተጠርዘውና ተለብደው ይቀርቡ ነበር፡፡
#የጎንደር ከተማ ታሪክ የማይሽራቸው ትውልድ የሚኮራባቸው የሰውን ልጅ ቀልብ የሚስቡና ለዛሬው ትውልድ የገቢ ምንጭ የታሪክ መዘክርም ሆነው የሚያገለግሉ የኪነ-ህንፃና የኪነ-ጥበብ ውጤቶች ይገኛሉ፡፡ በዘመኑ የኪነ-ህንፃ ውጤቶች መካከል የአፄ ፋሲል ግንብ ዋነኛው ተጠቃሽ ነው፡፡ የአፄ ፋሲል ግንብ በ20ሽ ካሬ ሜትር ስፋትና በ900 ሜትር ርዝመት ላይ በሞራ ግንብ ተከቦ በተንጣለለ ሜዳ ላይ ተመልካች ውብ እይታን ፈጥሮ ይታያል፡፡
#ግቢው አስራ ሁለት ቢሮዎች፣ ስድስት አብያተ-ክርስቲያን፣ ስድስት አብያተ-መንግስታትንና ሌሎች በተመሳሳይ የስነ-ህንፃ ጥበብ የተገነቡ ቀደምት ህንፃዎችን አካቶ የያዘ ነው፡፡ በውስጡ ከሚገኙት ታላላቅ ቤተ-መንግስታት መካከል እድሜ ጠገቡ እረጅሙ የአፄ ፍሲል ቤተ-መንግስት የአፄ ዮኃንስ ቤተ-መንግስት የአፄ አድያም ሰገድ ልጅ እያሱ ቤተ-መንግስት፣ የአፄ ዳዊት ቤተ-መንግስት፣ የአፄ በካፋ ቤተ-መንግስት፣ የእትጌ ምንትዋብና ቋረኛው እያሱ ቤተ-መንግስት ይገኙበታል፡፡ በዚህም ግቢ ተገኝተው ለመመልከት እድሉን የሚያገኝ ሰው በዘመኑ የነበሩትን የኪነ-ህንፃና ኪነ -ጥበብ ውጤቶች ምን ደረጃ ላይ ደርሰው እንደነበር በማሰብ፣ በወቅቱ በነበሩት የጥበብ ፈጠራዎች አድናቆቱን ለመስጠት እንደሚገደድ መገመት ይቻላል፡፡
ሌላው የዘመኑ የኪነ-ህንፃ ጥበብ ውጤት የሆነው የፋሲለደስ መዋኛ አንዱ ሲሆን ከፋሲል ቅጥር ግቢ በስተምዕራብ አቅጣጫ ከቃሃ ወንዝ ዳርቻ የተመሰረተ ነው፡፡ መዋኛው 6 የእንቁላል ግንቦችን 50 ሜትር በ30 ሜትር ስፋት ያለው የመዋኛ ገንዳ አለው፡፡ አንድ ባለ ግርማ ሞገስ የቤተ-ክርስቲያን ፍርስራሽም በግቢው ይገኛል፡፡
#የደብረብርሃን ስላሴ ቤተ-ክርስቲያን ከአፄ ፋሲል ቅጥር ግቢ በስተ ሰሜን ምስራቅ አቅጣጫ 1.5 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ በ1674 ዓ.ም በአፄ አድያም ሰገድ እያሱ አማካኝነት የአራት ማዕዘን ቅርጽ ይዞ የተገነባ ነው፡፡ በ1880ዎቹ በጎንደርና በአካባቢው የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት በድርቡሾች ለቃጠሎ ሲዳረጉ ምንም አይነት ጉዳት ያልደረሰበት ብቸኛው ቤተ- ክርስቲያን ነው፡፡
በአፄ ፋሲል መዋኛ በስተምዕራብ አንድ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው የቁስቋም
“ኮምናሌክስ” በጎንደር ነገስታት የግዛት ዘመን መጨረሻ አካባቢ በእትጌ ምንትዋብ ዘመን እንደተሰራ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በግቢው ውስጥ የቁስቋም ቤተ ክርስቲያን የእትጌ ምንትዋብ አዳራሽና ፍርስራሽ ቅርሶች ይገኙበታል፡፡
#ይህ ቤተ ክርስቲያን በወቅቱ የክርስትና ሃይማኖትን ለማጥፋት በድርቡሾች በተደረገው ዘመቻ የተቃጠለ ሲሆን በአፄ ሃይለ ስላሴ አገዛዝ ዘመን ንጉሱ ለሃይማኖታቸው ካላቸው ፅኑ እምነትና ቀና አመለካከት የተነሳ ቅርሱ እንዲታደስ ተደርጓል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ በአሁኑ ወቅት ጥንታዊነቱን ጠብቆ ታሪክን እየዘከረ ይገኛል፡፡
#ከቤተ ክርስቲያኑ ፊት ለፊትም የእትጌ ምንትዋብ አደራሻና የአባይን መነሸ ለማየት የመጣው የእስኮትላንዳዊት ጀምስ ብሩስ ቤተ መንግስትና የመኖሪያ ቤት ፍርስራሽ እንዲሁም የቋረኛው እያሱ እዮአብር የእትጌ ምንትዋብ አፅሞች ይገኙበታል፡፡
#ከፋሲል ግንብ በስተ ምዕራብ አቅጣጫ 280 ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው የኪነ-ህንፃ ጥበብ ውጤት ደግሞ ራስ ግንብ ነው፡፡ ይህ ቤተ መንግስት ምቹና በማን እንደተሰራ ግልፅ የሆነ መረጃ ባይኖርም አንዳንድ ጽሁፎች ላይ እንደተጠቆመው በአፄ ፋሲለደስ ዘመነ መንግስት ድርጅት ራስ ቢትወደድ ወልደ ጊወርጊስ ለተባሉ ለጦር መሪ እንደተሰራ ይገለፃል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በእትጌ ምንትዋብ ዘመን እንደተሰራ ይነገራል፡፡ በእትጌ ምንትዋብ ዘመን አዛዥ የነበሩት ራስ ሚካኤል ስሁል ይኖርበት እንደነበር የታሪክ መዛግብት ይናገራሉ፡፡ ከዚህ የተነሳም የራስ ሚካኤል ግንብ ተከትሎም ይጠራል፡፡
#ይህ ህንፃ በጣሊያን ወረራ ጊዜ ለጀኔራሎች መኖሪያ፤ በአፄ ሃይለ ስለሴ የግዛት ዘመን ደግሞ ለዕራሳቸው ማረፊያ ከዚያ በኋላም በደርግ ዘመን ለስርዓቱ አዳጋ ናቸው ተብለው የሚጠረጠሩ ለዕስራት የሚዳረጉበት ቦታ እንደነበር ይነገራል፡፡
#በዚህ ታሪካዊ ህንፃ ውስጥ በርካታ ታሪካዊና ባህላዊ ቅርሶች የሚገኙ ሲሆን በተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እጅ የሚገኙ ቅርሶችን ለማሰባሰብና ለማስቀመጥ ጥረት በመድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ቅርሱ ከፈረንሳይዋ ቬንስስ ከተማ በተገኘ ገንዘብ ድጋፍ ተጠግኖ የባህል ሙዜም እንዲሆን ጥረት ተደርጎ ወደ ባህል ሙዜምነት መቀየር ተችሏል፡፡
ከአፄ ፋሲል ግቢ በስተ ሰሜን አቅጣጫ 3 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወለቃ የተባለው የፈላሻ መንደር ይገኛል፡፡ ፈላሻ የሚለው ስያሜ ከአይሁዶች ወደ ኢትዮጵያ መምጣታቸው ጋር የተያያዘ ስያሜ ነው፡፡ ወለቃ የሚለው ስያሜም “ወርቅ” እና ወርቅና እቃ የሚሉ ሁለት ቃላትን በመገጣጠም የተገኘ ነው፡፡ የአካባቢው ስያሜም በቦታው የሚመረተውን ምርት ለማድነቅ እንደተነገረ ነዋሪዎች ያስረዳሉ፡፡
#በዚህ መንደር አይንን የሚስቡና የሚያማልሉ ባህላዊ የሸክላ ስራዎች በማምረት የምትታወቅ ሲሆን ከ1985 ዓ.ም ጀምሮ “ፕላውሸር” የተሰኘ የሴቶች የእደ-ጥበብ ማሰልጠኛ ማዕከል በማድረግና የዕደ-ጥበብ ውጤቶችን በማምረት ላይ ትገኛለች፡፡ ጥንታዊዩ የአዲስ አለም /ሰላም ቤት/: የሽህ አሊ ጎንደር የመቃብር ስፍራ ነው፡፡ የጥንታዊ ንግድ ማዕከልና የእስልምና ሙሁራን /አለም/ መፍለቂያ ቦታ ነው፡፡ ሽህ አሊ ጎንደር በአፄ ቴድሮስ ዘመን የነበሩ ታላቅ ወሎየ ናቸው፡፡
#በከተማዋ በእንፋሎት መታጠቢያነት የሚያገለግለው ደሮ ቤት ወይም የወሸባ ግንብ እና ጥንታዊ የደፈጫና የሰበጢት ድልድዮች ታሪክን እየዘከሩ ትውልድን በትውልድ እየተኩ ዘላለም ይኖራሉ፡፡ በከተማዋ ከ60 በላይ ጥንታዊና ታሪካዊ አብያተ-ክርስቲያነት የጥበብ የቅርስና የባህል ማዕከል ናቸው፡፡ በከተማዋ 18 የሚደርሱ መስጊዶች የሚገኙ ሲሆን የመጀመሪያው ቃደ መስጊድም ከታሪካዊነቱ አኳያ የቱሪዝም መስብ ሆኖ ይገኛል፡፡ የከተማዋ የቱሪስት መስቦች የሃገር ውስጥና የውጭ ሃገራትን ቱሪስቶችን ቀልብ በመስበር ለከተማ አስተዳደሩ የገቢ ምንጭ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡ የአባቶችን ዘመን ተሸጋሪ ታሪክን ዘካሪ ተጨባጭ ቅርሶችን ጥለውልን አልፈዋል፡፡ እንዚህን ዘመን ተሸጋሪ ቅርሶችን የአሁኑ ትውልድ ሊንከባከባቸውና ወደ ቀጣዩ ትውልድም ሊያስተላልፋቸው ታሪካዊ ሃላፊነት አለበት፡፡ ጎንደር በሲራራ ንግድ ማዕከልነቷም ትታወቃለች፡፡ #ማዕከላቸውን ጎንደር ከተማ ያደረጉ ሶስት ዋና ዋና የሲራራ ንግድ መስመሮች እንደነበሩ የታሪክ ድርሳናት ያመለክታሉ፡፡ መነሻውን ጎንደር አድርጎ በወገራ ደባርቅ ማለትም ተከዜ ሽሬና አድዋን በማለፍ በመፅዋ ደርሶ የሚመልሰው መስመር ነው፡፡ የሲራራ ንግድ መስመር ደግሞ በይፋግ፣ በጎጃም፣በሶ ገቢያ አድርጎ አባይን በመሻገር አናሪያ ከፋና ጀንጃሮ ድረስ የተዘረጋው መስመር ነው፡፡ በድምር የከተማዋን ታሪክ ስንመለከት የጎንደር ከተማ የሃገራችን የኪነ-ህንፃ፣የኪነ-ጥበብ የንግድና የሌሎች ማህበራዊ እሴቶች መፍለቂያ እንደነበረች መገመት አይከብድም፡፡ ይህ ደግሞ የከተማዋን የሃገር ውስጥና የውጭ ሃገር ቱሪስቶች ቁጥር በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ በማሳደግ ላይ ይገኛል፡፡ የጎንደር ከተማ ካለበት የቱሪስት መስብ ሃብቶች በተጨማሪ ምቹ የአየር ጠባይና የተፈጥሮ አቀማመጥ ታታሪና ስራ ወዳድ ህዝብ ያላት ከተማ ነች፡፡
#የከተማዋ መልካም ምድር አቀማመጥ ከባህር ወለል በላይ በአማካይ 2260 ሜትር ከፍታ ላይ በተራራ መቀነት ስር ትገኛለች፡፡ የአየር ንብረቷ ወይና ደጋ፤ አመታዊ የዝናብ መጠኗ ደግሞ 1172 ሚሊ ሊትር ነው፡፡ የከተማ አስተዳደሩ በ6 የክፍለ ከተማ በ25 የከተማና በ11 የገጠር ቀበሌዎች የተደራጀች ሲሆን በማዕከላዊ ስታስቲክስ መረጃ ትንበያ መሰረት 390,644 ህዝብ እንዳለ ቢገለፅም በከተማዋ ያለው የህዝብ ብዛት ከ700 ሽህ በላይ እንደሚሆን ይገመታል፡፡
#የጎንደር ከተማ ለኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ምቹና ተስማሚ ስትሆን ከአዲስ አበባ በ748 ከባህር ዳር 180 ኪ.ሜትር ከጎረቤቷ ሀገር ሱዳን በ180 እና ከአስመራ ደግሞ በ540 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡ ከተማዋ ምቹ የኢንቨስትመንት አማራጭ ያላት ሲሆን ባለሃብቶች በከተማ ውስጥ በማንፋክቸሪንግ፤ በሆቴል፤ ቱረዝም ፤በኮንስትራክሽን ፤በማህበራዊ አገልግሎትና በንግድ ትራንስፖርት ተስማርተው ይገኛሉ፡፡ በከተማዋ ኢንቨስትመንት ፈቃድ መስጠት የተጀመረው በ1998 ዓ/ም ጀምሮ 1700 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ወደ ስራ ገብተዋል፡፡በቀርብ የኢንቨሰትመንት ፈቃድ የወስዱት ፕሮጀክቶች ወደ ስራ ሲገቡ ከ141ሽ923 በላይ ዜጎች የስራ እድል ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በከተማዋ በርካታ ሆቴሎች ለውጭ ሃገርና ለሀገር ውስጥ ቱሪስቶች አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡ በሃገር አቀፍ ደረጃ በተካሄደ የሆቴሎች የደረጃ ውድድር በከተማዋ 6 ሆቴሎች ባለ ሶስት ኮከብ፤ ባለሁለት ኮከብ ደግሞ አንድ ሆቴል ይገኛል፡፡
#በመሰረት ልማት በኩል የውኃ፣የመብራት፣ የመንገድ፣ የቴሌኮሙኒኬሽንና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን በከተማዋ ለማስፋፋት ጥረት ሲደረግ ቆይቷል፡፡ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ በሁሉም የመሰረተ ልማቶች በሚሰጧቸው አገልግሎቶች የህብረተሰቡን ፍላጎት አርክተዋል ለማለት ባያስደፍርም መሰረተ ልማቶችን ለማሟላት እየተደረገ ያለው ርብርብ በተሻለ ደረጃ ላይ ይገኛል ማለት ይቻላል፡፡
#ከመሰረተ ልማቶች አኳያ መሰረተ ልማት ግንባታንና የንፁህ መጠጥ ውኃ አቅርቦትን ስንመለከት በክልሉ መንግስት በተመደበ 74 ሚሊየን ብር የአንገረብ የንፁህ መጠጥ ውኃ ግድብ ተገንብቶ አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከ8 ጥልቅ ጉድጓዶችና ከአንገረብ ግድብ በቀን በአማካኝ 10 ሽ ሜትር ኪዩብ ውኃ በማምረት ለንዋሪው የንፁህ መጠጥ ውኃ በማቅረብ ላይ ይገኛል፡፡ ይሁን እንጂ የአንገረብ ግድብ የንፁህ መጠጥ ውኃ #በአካባቢው የሚገኙ 8ጥልቅ ጉድጓዶች በአካባቢው ተፅኖና በተፈትሮ የውኃ መጠን መቀነስ ምልክቶች እየተስተዋለበት ይገኛል፡፡
#በዚህ ዙሪያ ውኃ ህይወት ነውና የአካባቢው ኗሪዎች የግድቡን ህልውና መጠበቅ በዙሪያው ችግኞችን በመትከልና በመከባከብ እንዲሀም ወደ ግድቡ ሊገባ የሚችለውን ቆሻሻ በማቃጠል ከብክለት መከላከል የሁሉም ኃላፊነት ሊሆን ይገባል፡፡
ትግላችን ይቀጥላል ።
G.A.T

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።