ለክፉ ነገርስ ችርስ መታመም ነው።

ነገር ማጋጨቱን ብናቆምስ?
„ሰው ሳይወድቅ በፊት ልቡ ከፍ ክፍ ይላል፤
ትህትናም ክብረትን ትቅማለች።“
መጽሐፈ ምሳሌ ምዕራፍ ፲፰ ቁጥር ፲፪
ከሥርጉተ©ሥላሴ
26.08.2018
ከጭምቷ ሲዊዘርላንድ።



·        
ነገረኝነት በረከተ። መዋጋት እና ማዋጋት እለታዊ አጀንዳችን ሆነ። በዚህ በጠ/ ሚር አብይ አህመድ ከጋዜጠኞች ጋር የነበረው የመጠይቅ እና የወይይት ክ/ ጊዜም ይህን ስመለከት አዘንኩኝ።

ምን አለ ስለ ኢትዮጵያ - ኢትዮጵያዊ አጀንዳ ቢኖረን። ምን አለ በዚህ መሰል ብሄራዊ ጉባኤ እንኳን ቀና ቀናውን ብናስብ። ምን አለ ስለ ወደፊቱ ተስፋችን ምን ብንደርግ እንዴትስ ተደጋግፈን ይህን ያገኘነውን ዕድል ከፍ ወደ አለ ደረጃ እንዴት እናሸጋግር የሚል ትኩረት ቢኖረን።

የሚገርመኝ በአንዲህ ዓይንት ቴሌቪዥናዊ ውይይት ላይ ልጆችን እርግፍ አድርገን እንረሳቸዋለን። በጹሁፍ ላይ፤ በድህረ ገፆች ውይይት ሙግት ላይ የዛሬ ልጆች ብዙም ግድ አያሰጣቸውም አክሰሱን ቢኖራቸውም። ትልልቆችም ቢሆኑ ማድመጡን እንጂ ማንበቡን አይወዱትም፤ ጥቂት ሰው ነው ማንበብ የሚሻው። ነገር ግን በቴሌቪዥን ከሆነ ያዳምጡታል።

የሆነ ሆኖ እኔስ እላለሁኝ በዬትኛውም ሁኔታ እና በዬትኛውም አጋጣሚ የቴሌቪዥን መግለጫዎች፤ የራዲዮን ውይይቶች፤ የቃለ ምልልስ ሂደቶች ሁሉ ልጆችም ሊያደምጡት እንደሚችሉ እያሰብን ቢሆን እመርጣለሁኝ። ልጓም ልናበጅለት ይገባልም ለአንደበታቸውን እላለሁኝ።

ልጆች ዛሬ ሁሉም አጋጣሚ ስላላቸው ሁሉንም ነገር ለመወሰድ ጭንቅላታቸው ባዶ ሌጣ ወረቀት ማለት ነው። ጥቁርም ሲጻፍበት ጥቁር፤ ነጭም ሲጻፍበት ነጭ።

የሚገርመው ነገር ከዛ ሁሉ ጠያቂ አንድም ሰው፤ አንድም ነፍስ ስለ ትውልድ የሞራል ቀረጻ አንዳችም ጥያቄ አልተነሳም። ቋንቋ ፉክክሩም ከጥበብነቱ ይልቅ አቅጣጫው ሌላ ነው። ቋንቋ የጥብብ ቤተሰብ ነው። ጥበብ ደግሞ በፈቃድ የሚከውን እንጂ በፉክክር ወይንም በመግዛት እና በመገዛት እሳቤ፤ በእልህ እና ከማን አንሼ በመሆን መንፈስ አይለካም። ጥብብ መለኪያው ዲካ የለውም እና።በጥበብ ውስጥ ለመኖር የውስጥ መሻትን ይጠይቃል። 

ወደ ቀደመው ምልስት ሳደርግ ልጆቻችን እኮ እያመለጡን ነው። መንፈሳቸው የእኛ አይደለም፤ መንፈሳቸው እንደ ትሩፋታችን አይደለም። መንፈሳቸው እንደ ትውፊታችን አይደለም ሊሆንም አልቻለም። እጅግ ሰቅጣጭ ነገሮች ይደመጣሉ፤ ይታያሉ። ተማረ በሚባለውም፤ ባላተማረውም በእኔ ቢጤውም። በዛ ሰሞናት ሥርዓት አልበኝነት ተቋማዊ ይሁን እስከ ማለት ደፈርን እኮ!መቼስ ለክፉ ነገር ችርስ መታመም ነው - እንደ እኔ።

ነገን ማሰብ በቁስ ከሆነ ኪሳራ ነው፤ ከንቱነትም። ነገን ማሰብ በመንፈስ ብቃት ከሆነ ግን ትርፍ ብቻ ሳይሆን የትውልዳዊ ድርሻችን መቅድም ነው።

በዛ ላይ የሉላዊ ቤተሰቦች ነን። ዛሬ ዓለም ታስፈራለች። ዓለም ለክፉ ነገሮች ክፍት ናት ቧ ያለች። መጠኑም ሰፊ ነው … ቁመቱም ረጅም ነው … አለም ለከንቱ ነገር ትማርካለች፤ አለም ለፍርሻ ትደላለች፤ አለም ለጠብ ምቹ ናት። አለም ወደ ገደል ማግስትን ለመልቀቅ የሰላች ናት። ነገረ ዓለም ታስፈራኛለች።

ዓለም ለበጉነት ጠባብ ናት፡ ዓለም ለትሁት መንፈስ ጥብቆ ናት፤ ዓለም ለደግነት ወረደ አጭር ናት። ዓለም ለፍቅር ቁመናው ጉርድ ናት። ዓለም ዳምናለች። ዓለምም ታደክማለች።
ዓለም ዛሬ በቅጽበት ሁሉንም ክፉ ነገር የመመገብ ሙሉ አቅም አላት። ዝንቅንቁንም፤ ቅልቅሉንም፤ ድቅድቁንም፤ ጭላጩንም፤ ስርክራኪውንም፤ ግርድፉንም፤ ሽርክቱንም፤ ስለሆነም ዓለምን ማጣሪያ ልናበጅላት ይገባል።

የዓለም የማጣሪያ ወንፊቱ ደግሞ ሚዲያ ሊሆን ይገባል። የሚዲያ ሰው ሲኮንለት ብዙ ክፉ ነገርን ነገርን ማሸነፍ ይችላል። ሚዲያ የልብ ስታዲዮም ነውና። ግን በቁመናው ልክ ነው ወይ ሲባል? እኛው እራሳችን ሚዛን ላይ ማስቀመጥ ነው።

አብሶ እንደ ኢትዮጵያ ላለ አገር፤ አብሶ እንደ እኛ ላለ የሰው ልጆች መገኛ፤ አብሶ እንደ እኛ ሃይማኖተኛ ህዝብ የዓለም ከንቱነት ልታሰቀናን፤ ልትማርከን፤ ልንወዳጃት አይገባም። ዓለምን የማረምም ታላቅ ተልዕኮ አለብን።

ሰው ከተፈጠረባት ህዝብ ይሄ ይጠበቃል። ግን እኛ የዓለም ከንቱን ታዳሚነትን ፈቅደን ከሆነ ለትልዕኳችን ጸርነታችን እኛው ነን ማለት ነው። ሰው መሆን መቻል ማለት እንደ ተፈጥሮው ሞራል ለመሆን መወሰን፤ መቁረጥ፤ ሆኖ መገኘት ማለት ነው። 
 
ቀደም ባለው ጊዜ ሆድ የሚያስብሱ መከራዎች ስለነበሩ ነው። አሁን መከራ የለብንም ለማለት አይደለም። አሁን የሚታዘዝ // ለመታዘዘ የሚፈቅድ ሙሴ አላት አላዛሯ ኢትዮጵያ። ስለዚህም ይህን ሙሴ ለማገዝ መትጋት ማለት ለእኔ ራስን ማሸንፍ መቻል ነው። 

ኢትዮጵያን ከወደቀችበት እረግረግ እናንሳት ለሚል መሪ እኔም ማለት የሚቻለው ከኖርንበት ሸር እና ተንኮል ተላቀን ነው። እውነት ለመናገር በዚህ በጋዜጠኞች ጉባኤ ላይ ያዘንኩባቸው ነገሮች ነበሩ። ስለምን ነው በመርዝ ከተነከረው የቂም በቀል ለመውጣት የማንፈቅደው? ስለምን ነው ከኢጎ አርበኝነት ጋር ለመፈታት የማንፈቀደው?

ስለምን ነው ከ10/12 ዓመት በፊት ስለነበረው የቁርሹ እድምተኛ ዛሬ ካለው የምህረት እና የይቅርታ ዓውደምህረት ጋር ቀላልቅለን ወይንም ሰብርቀን ለመጓዝ የምናስበው? እውነት ለመናገር በዚህ ለመቀጠል ያስቡ ሚዲያዎች እዬተንጠባጠቡ ይቀራሉ። አያድጉም። በፍጹም ሁኔታ መለወጥ ያስፈልጋል።

ኢትዮጵያንም ለመምራት ማስብ ብቻውን ግብ አይደለም። ከበሽተኛው የቂም እና የቁርሾ መከራም እራስን ማዳን ይጠይቃል። ብዙ ሰው በቀረበው ጥያቄ እና በተሰጠው መልስ ረክቶ ሊሆን ይችላል። እኔ ግን ከጠንካራው ጎን ይልቅ ደካሞችን ማንሳት ነው የሚበጀን ባይ ነኝ። ስለሆነም በሚዲያ ሰዎች ያዬሁት ሰብዕና ዝብርቅ የሞራል ጉዳይ ላይ ነበር አትኩሮቴ። እርግጥ ነው አብዛኞቹ ሴቶች ያቀረቡት ፍሬ ነገር እና ጭብጥ እንዲሁም ክሽን ያለ አቀራረብ አርክቶኛል።

የሆነ ሆኖ በጥቅሉ ሳዬው ግን ከጥላቻውም፤ ከቂሙም፤ ከበቀሉም፤ ከበላይነት መንፈሱም አልተወጣም። ጋዜጠኛው፤ ጸሐፊው ወይንም የሚዲያ አሰተዳዳሪውም ከዚህ መውጣት ካልቻለ ነገ ለእኔ ኮረኮንች ነው።

እርግጥ ነው ሚዲያ ሳይንስ ነው ሙያም ነው፤ ያደላቸው እድሜ ሙሉ የሚማሩት እንዲያም ሲል በመኖርም ክህሎቱ ሊገኝ የሚችልም ነው፤ ግን ራስን ቢያንስ ለሚዲያ ዲስፕሊን ማስገዛት ያስፈልጋል፤ ይህ ጉባኤ ብሄራዊ ብቻ አልነበረም፤ ዓለምአቀፋዊም ነው።

ዓለም ዛሬ ኢትዮጵያ አጀንዳዋ ሁናለች። ለዚህም እስኪ ገርመኝ ድረስ በዝምታ ውስጥ የባጀው የጀርመን መንግሥት ሰሞኑን አንድ እርምጃ ወሰዷል። ዝምታው እስኪገርመኝ ድረስ ያልኩት ጀርመን የእናት ያህል ነበር የኢትዮጵያ ጉዳይ አጀንዳው የነበረውና ነው። አብሶ የ ሉላዊ የመቻቻል እናት ጠ/ ሚር አንጄላ ሜርክል። 

ወደ ቀደመው ምልስት ሲሆን ያ እርምጃም ኤርትራንም ጨምሯል እጅግ አስደሳች ዜና ነው፤ ከዚህም ባለፈ ኤርትራውያን ስደተኞች ወደ አገራቸው መመለስ እንደሚችሉም የውጭ ጉዳይ ሚ/ሩ በኩል መግለጫ ተሰጥቷል። ይህ እንግዲህ ለእኔ የሰማይ ስጦታ ነው። ልዑል እግዚአብሄር በቃችሁ ሲል እንዲህ ነው። አንተ ሰላም ስለመሆንህ እርግጥ የምትሆነው ጎረቤትህ ሰላም ሲሆን ነውና።

„ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር / አብይ አህመድ አርብ ማምሻውን የጀርመን የውጭ ኢኮኖሚ ትብብርና ልማት ሚኒስትር የሆኑትን ክቡር / ጌርድ ሙለርን በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል“

የማታስቧቸው የፖለቲካ ሰዎች ያልሆኑት ሁሉ አስደንጋጭ የሆኑ መረጃዎችን እንድታብራሩላቸው ይጠይቋችኋዋል አሁን አሁን። ስለምን? ዓለም ኢትዮጵያ ላይ መልካም ተስፋው ማቆጥቆጥ ስለጀመረ ነው። ኢትዮጵያ በቸርነት መስመር ላይ እንደሆነች ስለተረዳ ነው።
 
ለዚህ ስለመብቃታችን ልዑል እግዚአብሄርን አምስግናለሁኝ፤ ነገር ግን እኛ የአብይ መንፈስ ከሚታትርበት ጋር እንደ ጋዜጠኛ፤ እንደ ጸሐፊ አብረን ነን ወይ ስል ያዬነው ነው። በይቅርታ እና በመንፈሱ ውስጥ ቀዳሚ ሊሆን የሚጋባው፤ የይቅርታ አንባሳደር ሊሆን የሚጋባው ታላቁ አካል የሚዲያዊው ቤተሰብ ሁሉም ነው ማለት ባልችልም ግን ዝንባሌው እምጠብቀው ዓይነት አልነበረም። የተነሱ ጥያቄዎችም እንዲሁ። ረዝመታቸው ጭብጣቸው ጅረታቸው እና ቅርንጫፎቻቸውን አክሎ ... 

አንዳንዱ ጥያቄ ኢትዮጵያን ልክ እንደስካንድናብያ አገሮች ሁሉ የማዬት ዝንባሌ አይቻለሁኝ። እነዚህ አገሮች በተፈጥሯቸውም ጦርነት አያውቋቸውም፤ ስለዚህም በሰላም ውስጥ መኖራቸው ብዙ በረከት አስገኝቷቸዋል፤ ደም ያልፈሰሰበት ምድር መሆኑ በራሱ እኮ የሚፈጥረው ሳቢ የምርቃት ትሩፋት አለ። ደም ሲፈስ እርግማን ይመጣል። እነኝህ የሰላም አገሮች ግን እርግማን የለባቸውም። ለዚህ ነው ባለፈው ጊዜ ዶር አብይ አህመድ ስካንዳንብያ ቢፈጠሩ ኖሮ ስል ያጠዬቅሁት።

መንፈሱን በፍጹም አልተረዳነውም። ኢትየጵያ የነበረችበት ብቻ ሳይሁን አሁንም ያለው የፖለቲካ ቀውስ፤ የኖርንበትን የኢኮኖሚ ድቀት፤ ባዶ ካዝና ስለመረከባቸውም፤ ለጠ/ ሚኒስተርነት ቦታውም አዲስ ስለመሆናቸው፤ እሱም ብቻ ሳይሆን ያለው ቢሮክራሲያዊ መስመር ጋር አብሮ ስለመቀጠሉም የተስተዋለ አይመስልም።

አዲስ ለመገንባት በታሰበው የሚዲያ መንፈስ ሳይቀር የአግላይነት እንጂ የአቃፊነት ሁኔታ አላዬሁኝ። ታይተው የማይታወቁ ነገሮች አበረታች ፈንጣቂ ሲጀመሩ ሊበረታቱ ነው የሚገባቸው፤  በአገር ግንባት ሆነ በአመራር ሬድ ሜድ አይጠበቅም።

ዜጋ የክት እና የዘወትር የለውም። የዜግነት ሩብ እና ሲሶ የለውም። ይህ የመነጠል፤ በቂም ነክሶ የመያዝ የሶሻሊዝም ፍልስፍና ደግሞ ዛሬ ሙት በቃ ተፈርዶበታል። እርግጥ ነው ቅሪተ አካሉ የለም ማለት ባይቻልም። 

የሆነ ሆኖ ቁም ነገሩ ራስን ከዘመኑ ጋር አስማማቶ መጓዙ ላይ ነው። የሰው ልጅ እንደ ችሎታው ብቻ ሳይሆን እንደ ተመክሮውም አገሩን ሊያግዝ የሚችለበት መስክ ለመጀመር መታሰቡ በራሱ የለውጥ ሐዋርያነት ነው - ለእኔ። 

ሌላው ያላደረገውን አዲስ መንፈሳዊ ዕሳቤ፤ አቃፊ፤ አሳታፊ የእኔ ባይነትን የሚያፋፋ ጅማሮ ሊበረታታ ይገባል። ሙያ እና ሙያተኛ መቼ እና መቼ ተገናኝቶ ነውና ኢትዮጵያ ላይ። የፖለቲካ ድርጅት መሪነት ራሱ እኮ ፈቃድ እና ተነሳሽነት ብቻ ነው። መሪነት ደግሞ ሁለገብ ዕውቀት አነሰም በዛም ይጠይቃል፤ ይህ ሆኖ በማያውቅባት ኢትዮጵያ ዛሬ ተወልዶ ያፍራ ማለት ከዬትኛው ፕላኔት ነበሩ ያሰኛል? ትንሽ ሰፋ አድርጎ ማዬት፤ ትንሽ ላቅ አድርጎ መመልከት ይገባል።

በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ውስጥ ተማሪው ወደ ዩንቨርስቲ ሲመደብ ፍላጎቱ ተጠይቆ፤ ስብዕናው ተመርምሮ አይደለም። ብዙ ውጥንቅጥ ያለባት አገር ናት። እነኝህ ሁሉ በጀንበር እፍ ተብለው ሊወገዱ ሊቀረፉ የሚችሉ አይደሉም፤ ባለው ነገር አቻችሎ ለመጓዝ የተሻለ የ አሰራር ስልት ቅዬሳው ጅምር ነው ውጤቱ ደግሞ የሂደት ጉዳይ ነው። 

እስከ አሁን ሽግግሮች ሁሉ ከስሜት ያለፉ አልነበሩም። እንዲያውም ሃይልም አለበት፤ በስሜት ይገናባሉ በስሜት ይፈርሳሉ፤ እንደ ፈጣሪ ቸርነት ነው ኢትዮጵያም እንደ አገር ህዝቧም እንደ ዜጋ የኖረው እንጂ መሰረት የያዙ ጥናታዊ፤ ምክክራዊ ስራዎች ተከውነውባት አያውቅም። ለዚህም ነው ሁልጊዜ ከዜሮ እንደንጀምር እንገደድ የነበረው። አሁንም ሺህ ሚሊዮን ጊዜ እርምጃ እርምጃ የምንለው ያለውን የ እዮባዊነት ጥናታዊ አመራር እና አዲሳዊነት ካለማጤን የመነጨ ነው። 

ዛሬ ላለው ጅምሬ አቅም ማወጣት የሚያስፈልገውም አዲሳዊ ዕሳቤ ዕይታው ካለ እርሾ የተጀመረ ስለመሆኑ ከልብ ሆኖ መመርምር ያስፈልጋል። በማፍረስ ለኖረች አገር፤ በበቀል ለኖረች አገር፤ በይቀርታ እና በምህረት፤ እንዲሁም በፍቅር እና በትህትና፤ በተጨማሪም በቸርነት እና በትእግስት ወጣ ገባውን አስተካክሎ፤ ዥንጉርጉሩን ፍላጎት ተቀራረቢ የማድረግ ተልዕኮ ይዞ መነሳት እርሾ አልነበረውም። ለሁሉም አዲስ ነው። ምን አልባት ክብደቱ ይሄው ይመስላል …

ይህ ጅማሬ ጠቃሚነቱ፤ ፍሬያማነቱ ዛሬ አይታይም በጽናት - በትጋት - ቀጣይ ካደረግነው ኢትዮጵያ የስካንድናብያ አገሮች ዕድል ሊገጥማት ይችላል። ኢትዮጵያም የሚሸሹበት አገር ሳትሆን የሚመጡበት፤ የሞፈሯት አገር ሳትሆን የሚመኟት አገር ትሆናለች። በዛ ላይ ልዑል እግዚአብሄርም ከልቡ ይወዳታል፤ የአስራት አገሩ ናት እና።

ስለሆነም ትውልዱን መቅረጽ የሚያስፈልገው በዚህ ትሁት ርጉ - ቅናዊ - አክብሮታዊ - አዲሳዊ - መርሃዊ - ይቅርታዊ - ምህረታዊ ጉዞ ሊሆን ይገባል … ሚዲያ ይህን መስራት ከተሳነው ቢዘጋ እመርጣለሁኝ … 

እውነት ለመናገር እኔ ህዝቡ በነብስ ወከፍ የሚሰጠው የውስጥ የመለወጥ ምላሽ እጅግ ያበረታታል፤ አብሶ ብዙ ያልተባለለት የመከላከያ ሰራዊቱ ጅማሬ እንኳን እንደ እኔ ይበል የሚያሰኝ ነው … 
እኔ እንደሚታዬኝ ከሆነ በ ኡለታዊነት ያለው ሚዲያውም የግል ይሁን የመንግሥት በአዲስነት መስመሩን „ሀ“ ቢለው ማግስትን ማልማት ይቻለዋል። ከጊዜ ጋር መጓዝ ደግሞ የተጓዡን ስኬት በከፊል ያበሥራልና .... 

ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚሰጢር።
የኔዎቹ ኑሩልኝ።

መሸቢያ ጊዜ። 

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።