ጦርነት ትርፉ ሁለመናን ማሳጣት ነው።

ዎህ! በተመጠነ ሁኔታ!
„ኖን። መንገዳችን እንመርምርና እንፈትን።
   ወደ እግዚአብሄር እንመለስ።“
ሰቆቃው ኤርምያስ ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፵
ከሥርጉተ©ሥላሴ
27.08.2018

ትውልዳዊ ድርሻ እንደ ወርቅ የሚፈተንበት አዲስ የተጋድሎ ዘመን። 

  • ምርኩዝ።

Ethiopia: አብዲ ኢሌ በአዲስ አበባ ከተደበቀበት በይፋ በቁጥጥር ስር ዋለ

  • ·       የወግ ገባታ።

ከድካም የሚያሳርፍ ፈቃደ እግዚአብሄር ነው። የቅድመ ዓለም የማዕከለ ዓለም የድህረ ዓለም ንጉሥ ክርስቶስ በቃችሁ ሲል እንዲህ ቸር ወሬ ያሰደምጣል። የኢትዮ ሱማሌ ነገር የተከደነ የጭንቅ አውዴ ነበር።

ምክንያቱም ልጅ እያለሁ ነበር የኢትዮጵያ እና የታላቋ ሱማሌ ህልምን እውን ለማድረግ ሲያድ ባሬ ጦርነት የከፈተብን። ያን ጊዜ ቀበሌ ላይ የእናቴ ተሳትፎ እጅግ የሚገርም ነበር። ከት/ቤት ስመለስ ቁልፍ ለማምጣት ወደ ቀበሌ ስሄድ የኢትዮጵያ እናቶች ትጋት እጅግ ድንቅ ነበር። አቤት እንዴት ደስ ይል እንደነበር የነፃነት መሻት ዓውደ ዝማሜው ... 

በመደዳ ምጣድ ተጥዶ ገብስ ሲቆላ፤ በመደዳ ሙቀጫ ተዘጋጅቶ ሲሾኮሾክ፤ በመደዳ ገብስ ተዘርግፎ ሲበጠር፤ ሲለቀም ታምር ነበር። ሌሎችም መሰናዶዎች ጎን ለጎን ሲከወኑ ... እናቶቻችን እኛን ወደ ት/ ቤት ሸኝተው እቃቸውን ይዘው በጥዋቱ ልክ እንደ መደበኛ ሥራ ወደ ቀበሌ ይገሰግሱ ነበር።

ወንዶችም ገብሱን ከመኪና በማውረድ፤ ለሥራ በሚያመች መልኩ ከባባድ እቃዎቸን በማቀራረብ፤ በማደራጀት፤ በ እንጨት ፈለጣ፤ ውሃ በማቅረብ... ወዘተ ይሳተፉ ነበር።

ትውናው አገር ማለት ምን ማለት እንደሆን ታላቅ ተቋም ነበር። የውጪ ወራሪን ለመመከት የነበረው ትጋት እና ማዕደኝነት ይህ ነው ተብሎ ለመግለጽም ቃላትም እራሱ ሊሸከመው አይችልም ማለት እችላለሁኝ። ኮ/ መንግሥቱ ሃይለማርያም እስከ ካቢናቸው ተፈትናው ያለፉበት አውደ ድላችን ነበር። 

ለሁለተኛ ጊዜ የዓድዋን ድል በደማቅ የአሸናፊነት ሰንደቃችን አረንጓዴ ቢጫ ቀዬ ሰንደቃችን በዓለም የታሪክ መዝገብ በድንቅ ህዝባዊ ተጋድሎ እና ሙሉ ተሳትፎ የተዘከረበት ገድል ነበር። ሠራዊታችን አየር ሃይላችን፤ ምድር ጦራችን የደህንነት አካሎቻችን ሁሉም በወል ሆነው አገሬ ኢትዮጵያ ብለው ታሪክን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን እንደገና የወለዱበት ወቅት ነበር። አዬሩ ድባቡ አጀንዳው ሁሉም አገሬ  ኢትዮጵያ ነበር ... ፊከራው፤ ቀረርቶው ወኔው እልሁ የተደፈርን ብስጭቱ ...    

እርግጥ ነው የጦርነቱ ድባብ አጅግ አስፈሪ ነበር። ት/ ቤትም ቢሆን ስጋቱ ከባድ ነበር። አገራችን በእብሪተኛው ሲአድባሬ ብትሸነፍ ያ ሲታሰብ ጨለማ ነበር። እና ተስፋውና ተስፈኛውም ለማገናኝት ብሄራዊ ጥሪው በሁለገብ ማዕዶት ተሳትፎ እንደዛ ጎመርቶ ሲካሄድ እጅግ ያስመካ ነበር። ጦርነት እጅግ አስከፊ ነገር ቢሆንም። 

አብሶ በጦርነት ውስጥ፤ ጦርነት በሚካሄድባቸው ቀዬዎች ላደግን ልጆች ጠባሳው ከባድ ነው። የሥነ - ልቦናው ብቻ ሳይሆን በመማር ማስተማር ሂደቱም ተጽዕኖው እጅግ ረቂቅ እና ውስብስብ ነው። በመኖር ትርጉም እና በነፈስ ትልም እንዲሁ ... 

የአገር ውስጡም ቢሆን የወያኔ ሃርነት፤ የሻብያ እና የደርግ ውጊያም እንዲሁ ሥራአለም ሆኜ ታድሜበታለሁኝ። ባጠቃላዩ ጦርነት ማሳጣት ነው ትርፉ። እርግጥ ነው ከውጪ ወራሪ ጋር በተደረገው ጦረነት አገራችን ተርፋላች። ግን ደም ተገብሮበት ነው። ዛሬ የተገኘው በትናንቱ እርሾ ላይ ነው። እርሾ አልባ አገር አትፈጠርም። የሆነ ሆኖ ከጦርነት አመድ ብቻ ነው ትርፉ። ከጦርነት አሸናፊው ቂምና በቀል ብቻ ነው። በጦርነት ጠፊው ደግሞ ትውልድ ነው።

ይህቺ አላዛሯ ኢትዮጵያ በዚህ ዓመትም በሴራዊ ድር ዘንድሮ በቀዝቃዛ ጦርነት ስትታመስ ነው የባጀቸው። አብሶ ኢትዮ ሱማሌ ላይ በአቶ አብዲ ኢሌ አመራር የተፈጠረው ግዙፍ የህዝብ፤ የሃይማኖት የጥቃት ዘመቻ ጭራሹን እያገረሻ እና እየታደሰ፤ ታክቲኩን እዬቀያዬረ እና እያዘነጋ  ያለማባራት ብዙ ነገሮችን ማሳጣቱ ለእኔ ኢትዮ ሱማሌ ታላቅ የስጋት ቀጣና ነበር።

እጅግ አድርጌ የምፈራው አካባቢ ቢኖር የጅጅጋን፤ የኡጋዴን አካባቢ ነው። የቀውሱ ተሻጋሪነት ብቻ ሳይሆን የጭካኔው ዓይነትም ከሰብ ዘሎ አውሬነት ስለሆነ እጅግ አሳሳቢ፤ አስደንጋጭም ልብ ተጥሎ ሊተኛለት የሚችል አልነበረም። የሚገርመው ያን የሱማሌ ወረራ ፍዳ እና መከራ በመቀበል የተማገደው ማህበረስብ እና ቀዬ ነው ሀገር በቀል በሆነ ሴራ ደግሞ ማገዶ ሆኖ የባጀው። 

የሆነ ሆኖ ሰሞናቱ አላዛሯ ኢትዮጵያ ከከወነቻቸው በድንቅነት ከባህረ ህሊናዊ ሰሌዳ ሊመዘገብ የሚጋባው ሂደት ኢትዮ ሱማሌ ክልል አዲስ አማራር የመረጠበት ሂደት እና ክልሉን ለማረጋጋት የኢትዮጵያ ሠራዊት የፈጸመው ወገናዊ ተግባር ነበር። በጠቅላይ ሚ/ር ቢሮም የተከወነው ስልታዊ ጥበባዊ አትኩሮታዊ ክዋኔ አንዱ የታሪካችን ፈርጅ ነው። 

ለእኔ መጋቢት 18/ 24 ቀን 2010 ዳግሚያ ትንሳኤው የምለው ይህን ችግር እጅግ በሰከነ፤ እጅግ በበሰለ የቅራኔ አያያዝ እና የሃይል አሰላለፍ ለመፍታት የተሄደበት መንገድ ከድንቅ በላይ መሆኑ ነው።

ስለ ነፃነት፤ ስለ ዴሞክራሲ፤ ስለመጪው ምርጫ፤ ስለቀጣዩ ትውልድ ወሳኙ ማዕከላዊ ቦታ አዲስ አባባ ሳይሆን ለእኔ ኢትዮ ሱማሌ ክልል ነው። መረቡ፤ ንክኪው፤ ጅረቱ መጠነ ሰፊ እና እጅግ ትብትብ ነበር። እና ጭንቅ ላይ ነበር የሰነበትኩት። በተለይ አመራሩ ስለሆነ ችግሩን አምንጪው፤ ከሌላው ካደባው አፈንጋጭ ቡድን ጋር ሆኖ በቅንብር በቅጡ በተደራጀ አመራር ጥቃቱ ይከወን ስለነበር እንቅልፍ ያሳጣኝ፤ ያሰጋኝም አምክንዮ ነበር።

ክብር ለልዑል እግዚአብሄር እና ሁሉንም ነገር እንዲህ ረብ አደረገልን። ካህሊነ ንጉሥ ክርስቶስ ሁሉ ይቻለዋል። የቀውሱ ግብረ ምላሽ እና የቀጣዩ የተስፋ አቅጣጭ አጅግ አስጊ ነበር። ለእኛ ብቻ ሳይሆን አፍሪካ ቀንድን ይዞ እስከ መካከለኛው ምስራቅ አፍሪካ የሚዘልቅ የመከራ - የሟርት - የምሾ ነጋሪት መለከት ነበረው።

ብልህ መሪ በቀውስ አፈታት ላይ ሙያውን የተካነ ሙሴ ፈጣሪ ሰጠንና፤ አጋሮችም ቅኖችም ታክለው፤ ጥበብ የእግዚአብሄር ነው እና በበረከቱ ጎብኝቶን፤ አዲስ አመመራር ተቀዬረ። ለዛውም በጥበብ። ከመሪ ደረጃ በስብዕዊ መብት የሰከኑ፤  በአክቲቢስት ደረጃ ዓላማቸውን እና ግባቸውን ያወቁ ታታሪ በውስጥነት ደረጃ አዲሳዊ አመራር ጋር ውህድት የፈጠሩ አጋዥኛ  ሁኔታዎች መፈጠራቸው ተመስገን ነው። በአክቲቢስት ደረጃም ኢትዮ ሱማሌ እጅግ የታደለ ነው። ብቻ ልዑል እግዚአብሄር ተማለደን።

አሁን ደግሞ ይሳካላችሁ፤ ተስፋችሁ መሰረት ይያዝ ሲል ልዑል እግዚአብሄር ዛሬ አቶ አብዲ ኢሌ በህግ ሥር እንደሆኑ ዜናው ነገርን። ይህ መቸም ታላቅ የምሥራች ነው። እሳቸውም ቢሆን እንደ ቀደመው ጊዜ በበቀል እና በቂም ጥንስስ ሳይሆን፤ ተጠያቂ የሚሆኑት በህግ አጋባብ ስለሆነ ላጠፉት ጥፋት ተጠያቂነታቸው በሥርዓት እንደሚከውን ተስፋ አድርጋለሁኝ።

የትም አገር፤ የትም ዓለም፤ ማንም ከህግ በላይ አይደለም። ሁሉም ሰው ከሚኖርበት አገር ህግ በታች እንጂ በላይ አይደለም። ከዚህም በተጨማሪ እንደ ሉላዊ ዜግነትም ሁሉም ግሎባላዊ ዜግነት ያለው ሰብ እና ፍጥረት ከዓለም አቀፉ ህግ ሥር እንጂ በላይ አይደሉም።

ስለዚህም ህግን ላከበሩ፤ ህግም መብታቸውን አይነፍግም፤ ህግን ለተለላፉ ደግሞ ግዴታቸውን እንዲወጡ ይገደዳሉ። መብት አለኝ ግዴታ ግን የለብኝም በዬትኛውም የዜግነት መኖር ውስጥ ተፈጥሮ አያውቅም እና ዳኝነቱ ድንጋጌያዊ ይሆናል። የተበደለን የሚክስው ህግ ብቻ ነው። ህግ ሥራ ላይ እስከዋለ ድረስ በዳይም ተባዳይም እኩል የዜግነት ግዴታ እና መብት ይኖራቸዋል። የእኩልነቱ አፈፃመም መሰረቱ ህግ ነውና።

አቀጣጣይ፤ ቆስቃሽ እና ቀውስ ናፊቀኒትን አጀንዳቸው ላደረጉ ደግሞ ዛሬ ጥቁር ማክዳቸውን ለብሰው ድንኳናቸውን ጥለው ይሆናል። በብዙ ስውር ፍላጎት የተጠመዱ አጀንዳዎች መኖራቸው አሊ አይባልም። ይህን ቀውስ በማራገብ ደረጃ ሚደያዎችም ቤተኞች ነበሩ። 

ዛሬ በጣምራ ያ የስውር አጀንዳ ቅስም አከርካሪ በተወሰነ ደረጃ ተስብሯል ብዬ አስባለሁኝ። ብዙ በቀውሱ ተስፋ የሰነቁ መፍንቀለ ለውጥ ሰውር አጀንዳዎች ዛሬ የሽንፈታቸው የመጨረሻው ባይሆንም የመጀመሪያው መርዷቸው ነው።

ለዚህ ነው እኔ ቀጨር መጨሬውን፤ ቅል ቋንቋራውን፤ አርቲ ቡርቲውን፤ እንቶ ፈንቶውን፤ ዝባዝንኬውን ትቶ የአብይን ሌጋሲ አጀንዳ ማድረግ ካሰብነው የሚያደርስ ሰጋር በቅሎ ነው የምለው።

መተጋት ያለበት ይህን ንጹህ መንፈስ በሁሉም መስክ አግዞ እና እረድቶ አዲስ የ እኩልነት የፍትህ ሥርዓት መፍጠር ከማስቻሉ ላይ ነው መሆን ያለበት። ሥርዓት ነው የማግስት አደራጅ እና መሪ መሆን የሚችለው። ስለሆነም ሽግግሩን የእኔ የሁላችን የጋራችን ማለት ራስን ከማሸነፍ ይነሳል። 

አዲሱ ዓመት ዘንድሮ ኢትዮጵያ ላይ እጅግ ለረጅም ጊዜ  ከአገር ውጪ የነበሩ ወገኖች ሁሉ ከቤተሰቦቻቸው ጋር የሚገናኙበት፤ አብረው የሚያሳልፉብት ልዩ ቅኒያዊ መንፈሳዊ ዘመን ነው። የልብ የልባቸውን፤ የሆድ የሆዳቸውን በህይወት ካሉት ቤተዘመዱ ጋር ገጥ ለገጥ ተገናኝተው ሳቅ የሚያዋጡበትም ነው። ተመስገን! ይህንስ ማን ክፉ ብሎት … ይህን ዕድል እንኳን ከመጤፍ ያልቆጠሩት እንደተጠበቁ ሆነው ...  

አምና ይህን ጊዜ የነፃነት አርበኞችም ቢሆኑ ካቴና ውስጥ ነበሩ። ዘንድሮ ደግሞ በነፃ አዬር ውስጥ ናቸው ብቻ ጉዳዬ ማለታቸው እስከምን ስለመሆኑ ወፊቱ ትጠዬቅ

መገናኘት፤ መተቃቀፍ፤ መሳሳም፤ አብሮ መሳቅ፤ አብሮ ማዕደኛ መሆን፤ ነገን ማሰብ፤ ትናንትን መርሳት፤ ቁርሾን መጠዬፍ ዛሬን አስብሎ ለሰጠን ልዑል አምላክ ምላሽ ዋጋ ነው። የተመስገኑ ፍሬ ነገርም ይሄው ነው።

ዛሬም ስለቁርሾ፤ ዛሬም ስለበቀል የሚያስቡ ነፍሶች እውነት ለመናገር አገር የገቡበትን መሰረታዊ ዓላማ እና ለዚያ ያበቃቸውን የፈጣሪን ጥበብ መተላለፍ ይሆናል። ከካቴና ጋር የተፈቱትም ቢሆን እንዲሁ። 

አሁን በዚህች ቅጽበት ራያ ላይ፤ ወልቃይትና ጠገዴ ላይ በርጥብ ጢስ አፈና ማገዶነት አለ … እነሱ ሲታሰቡ ደግሞ ጥቅጥ ያለ ጨለማ ነው።  

በጥቅሉ ሲታይ ግን ለዚህም ቢሆን ልዑል እግዚአብሄር እኛ ባላሰብነው፤ ባላቀደነው፤ ባላደራጀነው መንገድ ነው ሃዲዱ ቧ አድርጎ ምህንድስናውን የተካነው … 

ስለዚህም ዋጋው የሚካካሳው ከዛ ከኖርንበት ጥቁር የጥላቻ ነቀርሳ መፈወስ ስንችል ብቻ ነው። በቀለኛውም፤ በዳዮችም በቃን ወገኖቻችን መበድል ሲሉም ነው። መዳን የፈጣሪ ቢሆንም ከራስ ጥረት ውጪ ግን አይደለም። እንድን ዘንድ እንጸልይ ልዑል እግዚአብሄርም ይርዳን። አሜን!

ልዑል እግዚአብሄር እኛን ስለሰጠን እናምስግነው።

ዓራት ዓይናማው መንገዳችን የአብይን ሌጋሲ ማስቀጠል ነው!

የኔዎቹ ቅኖቹ ኑሩልኝ።
መሸቢያ ጊዜ።





አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።