የጎንደር እናት ደግማ ድንኳን ጥላ እንደትተከዝ ለወያኔ ምርኩዝ መሆን አለመታደል ነው።

የጎንደር እናት ደግማ ድንኳን
ጥላ እንደትተከዝ ለወያኔ 
ምርኩዝ መሆን አለመታደል 
ነው።
„ሰነፍ በልቡ አምላክ የለም ይላል።“
መዝሙር ፲፫ ቁጥር ፩“
ከሥርጉተ©ሥላሴ
 11.11.2018
ከጭምቷ ሲወዘርላንድ።

የሚገርሙኝ ነገሮች መብዛታቸው በአዎንታዊነት ቢታዩም ዕንባን በማስቀጠል ከሆነ ግን አሉታዊ ነው። አሁን የቅማንት ጉዳይ ይገርመኛል  በአሉታዊነት። የቅማንት እናትም ጎንደሬ ስለሆነች 50 ዓመት ሙሉ ዓውዱ የጦርነት ስለነበረ ያው በሁሉም መስክ ተጠቂ ናት። 

ዛሬ የቅማንት እናት ተመስገን ብላ ዎህ በምትልበት ጊዜ ሻማው በማንቀላፋት ላይ ባለው የወያኔ ሃርነት ትግራይ ሹማምንት ጋር በመሆን የእናትን ጡት መውጋት አለመታደል ነው። አያሳፍርም ወይ የጎንደር ልጆች አሁን እርስ በእርሳችሁ ስትዋጉ። ማፈሪያ!ለዛውም የ አብይን ካቤኔ ሰላም ለመንሳት መጣር? ውርዴት ነው። 

27 ዓመት ሙሉ አንበርክኮ ሲገዛ- ሲሰነጥቅ፤ ሲተረትር፤ ሲሸነሽን፤ ሲዘርፍ፤ ሲወር፤ ነቅሎ ሲወሰድ፤ አፈር ሲጭን፤ እንጨት ሲጨን፤ የጎንደር ልጅ በግባ ግቢቱ እዬገባ ሲያድን ሲመነጥር ከኖረ አውሬ ጋር አብሮ መሆን ከህፍረቶቹ ሁሉ የላቀው ነው። ለዛውም ጎንደሬ የተባለን ሲያሳድድ ከነበረ ማህበረ ደራጎን ጋር ሆኖ የራሱን ወገን መዋጋት እጅግም አሳፋሪ ድርጊት ነው። ባይገባቸው እንጂ ቅማንቶች በዬሄድንበት ስንሳደድ የምንኖረው ጎንደሬ በመሆናችን ነው።

ያ ማንነት የሚሸመትም የሚቀናም አይደለም። ሙዚቀኛው ቃናውን፤ ስንኙን ካልተካነበት አይደምቅለትም። የነፃነት ትግል አደረጋለሁ የሚለው ካለጎንደር ማጣፊያው አጥረዋል።

ጎንደር በሰው ሰውኛ ከሆነ የሚተረጎመው ብዙም ልብ ሰቃይ ጉዳይ ላይኖርበት ይችላል። በመንፈሳዊ ህይወት  የዕድምታ ሚስጢር ከሆነ ግን ጎንደር ዲያቆን ዳንኤል ክብረት እንዳለው ከምድር በላይ ብቻ ሳይሆን ከምድርም በታች የማናውቃቸው ረቂቅ ሚስጥራት አሉበት። መስህቡ፤ ተመስጦው የላይኛው ነው። 

ጎንደር እኮ የአባታቸውን ህልፈት ተከትሎ ጎጃም ድረስ ሄዶ አጤ በካፋን ለምኖ አምጥቶ ያነገሠ ህዝብ ነው። የሚገርም ህዝብ አኮ ነው። እኔ ራሱ ቅራኔ ውስጥ ገብቼ እምሟገት ሰለ ኢትዮጵያዊ ወገኖቼ ብቃት ነው። ስለዬትኛውም ዜጋዊ ብቃት። እንጂ ሥርጉት ምን ይቀርባታል። ምን ችግርስ አለው እንዲያውም የሚቀናው ጸጥ ብሎ ከርሞ ብቅ ሲባል ነው። 

የጎንደር ሰው እኮ ከዬት መጣህ? ማነህ? ምንድን ነህ ሃራሙ ነው። ይህን ትውፊት እዬተጋፋ ነው የቅማንት የዘመኑ ሊሂቃን አካባቢውን የጦር ቀጣን ለማድረግ ከወያኔ ሃርነት ትግራይ ጋር አብረው እዬሠሩ የሚገኙት። አሁን ያምሳሉ፤ ያተራምሳሉ።

ለዛውም በላ ኢትዮጵያ ካሉት ክልሎች ሁሉ የብአዴንን ያህል ጥያቄያቸውን ያዳመጠ አንድም ክልል የለም፤ በሱማሌ፤ በኦሮምያ፤ በሀረሬ ሚሊዮን አማሮች ይኖራሉ ግን አንዳቸውም ልዩ ዞን አልጠዬቀበትም። የአማራ ውሃ ልክ እስከዚህ ድረስ ነው። በአማራ ክልል ኦሮሞዎች ልዩ እውቅና፤ ትግራይ የሚገኙ አናሳ በሄረሰቦች ግን ትዝ ብለዋቸውም አያውቁም ፈጽሞ። 

ሌላው የብአዴን የፌድራል ይሁን የክልል ውክልና አሰጣጥ እና የሥራ ክፍፍል ደግሞ ለሌለው ብሄረሰብ ያደላ ነው። ሌላ ቦታ ይህ አይደፈረም እንዲህ ዓይነት ጉዳይ። የጤና ጥበቃ ሚነስተሩን ሪኮሞንድ ያደረገው ብአዴን ነገር ግን የትግራይ ሰው ናቸው ሙሉ ለሙሉ። ሌላውም እንዲሁ ...

የሆነ ሆኖ ወደ ቀደመው ምልሰት ሳደርግ የቅማንት ብሄረሰብ ባለበት በአጋጣሚ እኔ ሥራ የጀመርኩት ጭልጋ ነበር። ውስጣቸውን አሳምሬ አውቀዋለሁኝ ሳምነቱን ሙሉ ከእነሱ ጋር ነበር እማሳልፈው። እነሱን የማደራጀት አብሮ የመኖርም ዕድሉ ነበረኝ።

የምኖርበት ቤት አከራዬም የቅማንት ባላበት ነበሩ። ቋንቋውንም አሳምረው ይናገሩት ነበር። እኔም ተምሬው ነበር። እትሸት ቤተሰብ ሲመጣም የሚያነጋግሩት በቅማንተኛ ነበር። የወንድማቸው ልጅ እቴነሽ አብራ ታድግ ነበር ከሷ ጋርም የሚነጋገሩት በቅማንትኛ ነበር። ሠራተኛቸውም ቅማንት ስለነበረች የሚያዟት በቅማንትኛ ነበር። 

የቀደሙት የቅማንት ብሄረሰብ አባሎች እኔ ፈጽሞ አንዲት ቅንጣት ሳሃ ላወጣባቸው አልችልም። ሙሉ ስብዕና ነው የነበራቸው። ሴራ የሚባል አያውቁም ከሴረኛ ጋርም አይተባበሩም፤ አደብም ነበራቸው። ቋንቋውንም ገበሬ መንደር ሲናገሩ አውቃለሁኝ። አልተከለከሉም። ሁለት ትላልቅ ሆቴል የነበራቸው የቅማንት ባላህብቶች አይከል ከተማ ነበሩ።

ሌላ አሁን ተጨቁነን ነበር ለሚሉት የጓድ መላኩ ተፈራ አራጊ ፈጣሪ አማካሪ የነበረው በዛ በጭንቅ ጊዜ ማነው? ጓድ የሖንስ አፈወርቅ አልነበረምን? ይህን በዘመኑ የነበሩ የኢህአፓ ታጋዮች የሚመሰክሩት ነው። ይህ ሰው እኮ የጎንደርን ሰው ወጣት ያሰመነጠረ ነው።

በዬትኛውም የመንግሥት አካላት፤ በዬትኛውም የህዝባዊ ድርጅቶች አካላት፤ በዬትኛውም የሙያ ማህበራት፤ በዬትኛውም የኢሠፓ መዋቅር ቅማንቶች በአቅማቸው በልቅናቸው ልክ ነበሩበት ለጥፋቱም ለልማቱም። ቀድሞ ነገር ጎንደር ላይ ሰው ከዬት መጣህ ተብሎ ተጠይቆ አይውቅም። ይህ ውርዴም ነው። ትውፊቱ ሰው የአግዚአብሄር/ የአላህ ፍጡር ነው። 

ደግሞስ እነሱ አካላችን እኮ ናቸው። ማንስ ትዝ ብሎት ቀድሞ ነገር ያውቅ እና ነው። በማህበሩ፤ በዝክሩ፤ በሰንበቴው፤ በሰርጉ፤ በእድሩ፤ በቁቤው በጎርብትና ምን ልዩነት ኖሮ? ጎረቤቶቻችንም ቅማንቶች ነበሩ በመከባባር ነው የኖርነው። 

እኔ እንዲያውም "ፊድል" ከልጆች የግጥም መጸሐፍ ላይ አንዷን አመስግኜ ጽፌያለሁኝ። የልጅነት ጊዜዬን ሳወሳሳ። ልክ እንደ ቤተሰቦቼ ማለት ነው። መጸሕፍት ቋሚ ቅርስ ነው።

ነገረ ጎንደር በሚስጢራት የለማ ነው። ፈላስማው ዘር ያዕቆብ እኮ ትግራይ ሲያስድዱት ሰላሙን ፈልጎ መጥቶ የተቀመጠበት ጎንደር እንፍራዝ ነው። ቅዱስ ያሬድም እንዲሁ። ሌላው ቀርቶ የንግሥት ማክዳን እና የንጉስ ዳዊት ፖስተኛ ስም የሚጠራ ቦታ እንኳን ሊቦ ውስጥ አለ። 

አሁን ትናንት ጠ/ሚር አብይ አህመድ እንደ ነገሩን ደግሞ የፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ አያት ጎንደር ነው የተቀበሩት፤ የመህመድ ግራኝ ዘመንም እዛው ጎንደር ላይ ነው ያከተመው ግራኝ በር ደንቢያ ላይ።

ጎንደር ለሁሉም ሳቢ እና አቃፊ የሆነ ሰብዕና ያለው ህዝብ የሚኖርበት ቀዬ ነው። ልቅናው የመነጨው እኮ አቅፎ፤ ደግፎ፤ ፈቅዶ፤ ተቅብሎ ማኖር በመቻሉ ነው የብዙ ሚስጢራት ሊቃናት ባለቤት መሆን የቻለው። 

እንዲያውም ሥመ - ጥር የሆነ ሰው ከገጠም ልጅም ቤተሰብ ታጭቶለት ጎንደር እንዲቀመጥ፤ በጋብቻ አስሮ የማስቀረት ይትበሃል ሁሉ አለ እንኳንስ የቅማንትን ብሄረሰብ ሊገፋ ቀርቶ። ምን ይሆን ልዩነታችን? አንድ እኮ ነን። 

ህም! ተገለን ኖርን? የኢሠፓ አንደኛ ጸሐፊ ሰክሬታሪ የቅምንቷ ባላባት ማን ነበረች ጓድ ማሬ ካሰኝ አልነበረችንም? የኢሠፓ አንደኛ ጸሐፊ የፕሮቶኮል ሹም ጓድ ሰማልኝ እምሬ አልነበረምን? ከሁለቱ የስልክ ኦፕሬቶሮች ዋነኛዋ ታማኝ የምትባለው እና መሪዋ የቅምንት ሴት አልነበረችም? የጎንደር ክ/ አገር የኢሠፓ የፋይናንስ እና የጠቅላላ አገልግሎት የመምሪያ ሃላፊ ጓድ የሖንስ አፈወርቅ አልነበረንም? የክ/ አገሩ የኦዲት ኮሚሽን ምክትል ሃለፊ አቶ ተስፋሁን አዱኛ አልነበረምን? ስንቱ ይዘርዘር? 

አውራጃ አስተዳደሪዎች፤ አውራጃ የፓርቲ ተጠሪዎች፤ የወረዳ አስተዳዳሪዎች፤ የወረዳ የፓርቲ ተጠሪዎች የመምሪያ ሃላፊዎች ቅማንቶች አልነበሩበትንም? የህዝባዊ ድርጅቶችን እና የሙያ ማህበራትንማ ቤቱ ይቁጥረው። 

እኔ የህዝባዊ ድርጅቶችን እና የሙያ ማህበራት ጉዳይ ሃላፊ ስለነበርኩ መለኪያ ብቃት ብቻ ነው የነበረው። በዚህም ነው ደግሞ የምታውቀው። ያልሞቱ ያልታመሙ ሰዎች ጎንደር ይኖራሉ። እነሱ ይመሰክሩታል። በእኔ ቤት የክት እና የዘወትር ሰው ተፈጥሮ ከሆነ። ሌላውም ይህንኑ ነው የሚያደርገው።

ከዬትም ይምጣ ምንም ይሁን ለቦታው ከመጠን ቦታውን ይይዛል። የሚጎድል የሥነ - ምግባር ነገር ቢኖር እንኳን ኳችነቴን አሟልቼ ብቁ አድርገው/ አደርጋት ነበር። እኔም ዓርት ዓይናማ ኳች ጓድ ገ/መድህን በርጋን የመሰለ ድንቅ የሙያ አባት ስለነበረኝ።

መሬት አይቆረስም ተገፍተን ነበር፤ ተጨቁነን ነበር፤ ተገለን ነበር ሲሉ ቅማንቶ። የጋሽ ነጋ ፋርማሲ የእማማ አበቄለሽ ጠጅ ቤት፤  እኔ የተከበሩ ድንቅ የ አገር ዋርካ  ካሰኝ አለማዬሁ ድርጅት የሁላችን አልነበረንም? ሁላችን ሄደን አንገለገልም ነበርን? ስንቱ ይዘርዘር? እሙሃይ አበቄለሽ የሁላችን ትውፊት አይደሉምን? ክቡር ካሰኝ አለማዬሁ ትውፊታችን አይደሉምን?  

እኔ አንደማስበው የቅማንት ሊሂቃን በጎንደር ላይ ራሳቸው የቀኑ ይመሰለኛል። የጎንደርን ትውፊት ማክስል ፈለጉ። 

ከፈለጉ እኮ ከልካይ የላቸውም መቀሌ ላይ ካለው ጽ/ቤታቸው ሄደው መጠቃለል ነው የሄሮድስ መለስ ዜናዊን ነፍስ ይማርልን ብለው¡ጎንደር ሲመጡብሽ በለቅሶ ሲሸኙብሽ በለቅሶ ብዬ አንድ ጊዜ አዕምሮ ጋዜጣ ላይ ጥፌ ነበር። ጎንደርን የረገጠ ጭንቁ ሽኝት ላይ ነው። መላቀስ ነው። ከ ኤርትራ እኮ እናቴን ለማዬት አዲስ አበባ የገባች ጎረቤታችን አለች።

ማህባው ፍቅር እኮ የተፈጥሮ ነው ጎንደር ላይ።  
ወያኔ ሃርነት ትግራይ እንኳንስ የዛሬ ተለጣፊዎችን ቅማንቶች ቀርቶ በአባቶቻችን ትጋት የ እርሻ ካፒታልስ ሰቲት ሁመራ ላይ አቆጥቁጦ በነበረበት ወቅት በቅጥር የእርሻ የጉልበት ሠራተኛነት ለጉሮሮ የበቁት፤ በኋላም ነፃነት ሲሉ አብረው ግብር አበር ለሆኗቸው ለወልቃይት እና ጠገዴ ሰንቅ እና ትጥቅ ረዳታቸው እንኳን አልሆኑም። 

ለሻብያም ላደራጃቸው፤ ላሰለጠናቸው፤ ክህሎቱን ላዋሳቸው አልሆኑም። የበሉበትን ወጪት ሰባሪ ማተበቢሶች ቢኖሩ የትግራይ ወያኔ ሃርነት የማንፌስቶ ማህበርተኞች ብቻ እና ብቻ ናቸው።

ለኦሮሞ ህዝብ እኮ ጠንቁ ኋነዋል ዛሬ ላይ። ስንቱን ሺህ ወገን በሰሞናት ብቻ ከአቶ አብዲ ኢሌ ጋር በመሆን አፈናቀሉ? ስንቱን አሰሩ? ስንቱን አገቱ? አማራስ መቼም የተለመደ ነው። አማራ ለዬዘመኑ ዒላማ ነውና። 

የሆነ ሆኖ እኔ ማዕት ከሰማይ እንዳይተዘዝ ሁሉ እፈራለሁኝ ስለቅማንቶች ሳስብ። የእኔ ጉዳዬ የድምጽ አልባዎቹ የኢትዮጵያ እናቶች ጉዳይ ስለሆነ ቅማንትም አንዷ ስለሆነች ስለዚያ ሳስብ ይበርደኛል።
  
አሁንም ለጎንደር እናት ሌላ ምሾ፤ ሌላ ወይታ፤ ሌላ ስቃይ ጠሪ ሆነዋል የቅማንት ሊሂቃን። ጥያቄያችሁ እራሱ ቋት የማይገፋ ነው። መጨረሻችሁ ደግሞ የሰማይ ቅጣት ነው። 

ተለይታችሁ ታዩታላችሁ … ማዕረግ ተገፎ፤ ክብርን አውልቆ የሚገኝ የሥነ - ልቦና ጥቅም ከተገኜ ይታያል። አማራ እንደሆን ዛሬ ባለጥንድ ድርብ ነው እንደ አባት እናቶቹ። ብቻውንም አይደለም። 

አታዩም ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂን ናፍቆታቸውን ለመወጣት ከእርቁ በሆዋለ ለአራተኛ ጊዜ ነው የመጡት። ነገን ያዬ … ምን አልባት ባልተጠበቀ ሁኔታ በኮንፌዴሬሽን የሚኖር መልካም ዜና ይኖራል። ኤርትራውያንም አሁን ናፍቆታቸውን ለመወጣት በገፍ ነው ወደ ኢትዮጵያ እዬገቡ ነው የሚገኙት።

ከመለዬት መራቆት እንጂ ልምላሜ አይገኝም። ለጥቂት ሰው ስልጣን ተብሎ የቆዬን ታሪክ መበከል ጉዳቱ ለራስ ለቅማንት ህዝብ ነው። ጎንደር ሆነ አማራ የሚቀርበት አንዳችም ነገር የለም። የጎንደር ክብሩ ወደ ቦታ የተመለሰው ሐምሌ 5 ቀን ነው።

ከዚህ ክብሩ ጎንደርን ንቅንቅ የሚያደርገው አንዳችም ምድራዊ ሃይል የለም። ሥጦታው የሰማይ ስለሆነ ባልተሰበ እና ባልታቀደ ሁኔታ የሚሆኑን ነገሮች ሁሉ ልብ ላለው ዕለታት በሚስጢራት ሙላት የሰከኑ ናቸው።

ማስተዋል ይሰጠን ፈጣሪ!
የኔዎቹ ኑሩልኝ።
መሸቢያ ጊዜ።



አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።