አማራ ከእንግዲህ ማረጃ ልኳንዳ ቤት አይደለም።

         ጊዜ ምስክር ነው።
                                                 ከሥርጉተ ሥላሴ 15.06.2018 (ከጭምቷ ሲዊዘርላንድ)

„እግዚአብሄር ዓለቴ፤ አምባዬ መድሃኒቴ ነው። እግዚአብሄር ጠባቂዬ ነው በእርሱም እታመናለሁኝ። ጋሻዬና የረድኤቴ ቀንድ መጠጊዬና መሸሸጊያዬ መድሃኒቴ ሆይ ከግፍ ሥራ ታድንኛለህ።“  (መጽሐፈ ሳሙኤል ምዕራፍ ፳፪ ቁጥር ከ፩ እስከ ፫)



  • የዕውነት ማህደር።

በእስር ላይ ብሆንም ግንቦት 7 አንድም ጥይት በኢትዮጵያ ምድር እንዳላጮኸ ነው የማውቀው።አንዳርጋቸው ጽጌ ለቢቢሲ
June 14, 2018

መነሻዬ ይሄ ነው። የሰማዕቱ ጎቤ እና ጓዶቹ ገድል በዓለም አደባባይ ስለተናኜ ደስ ይለኛል፤ ግን የተከበሩ አርበኛ አንዳርጋቸው ጽጌን ተከትለው የሄዱ የውጪ ኑሯቸውን የተዉ አርበኞች ሜዳ ላይ ተሰዉ ዜናንም ሰምተናል። አርበኛ አንዳርጋቸው ጽጌን ሊገድል ነው ሲባል ጎንደር፤ ፊት ለፊት ውጊያ አድርገን ሞቱ ሲባል የጎንደር አርበኞች፤ ተጋድሎው ህዝባዊ ሲሆን የግንቦት 7 ነው፤ ይህ ውስብስብ የፖለቲካ ትርምስ እንዴት ነው የሚፈታው? ግንቦት 7 እንዲታመን ነው ወይንስ ግማሽ ውሸታም ነው ለማለት ነው? ወይንስ ቅይጥ መንፈስ ለመፍጠር ነው አልገባኝም። እርግጥ ነው በአንዲት የውጊያ ግንባር ፊት ለፊት ገጥሞ ውልቅልቁ ወጥቶ አባላቶቹ እጃቸውን ሰጥተው ቃለ ምልልስ አዳምጠናል። ከዚህ የተረፈው ግን የጎበዝ አለቆች የ አማራ አርበኞች ተጋድሎ ነበር። አርበኛ ጎቤ ሲሳዋማ ቀረ እኮ ሰበር ዜናው። ያ ተለውጦ የነዳጅ ቦቴ በመንፈስ ቅዱስ ሰረጋላ ፍንዳታ ነው የተደመጠው .... 

በሌላ በኩል በዓለም አቀፍ ደረጃ ይህ የማፈረስ እዬነጠሉ ሰውን መግደል የተወገዘ ስለሆነ ይህን ነጻ ለማውጣት ይሆን? በዚህ በተመሰጠረ ፖለቲካዊ የለገመ ቁስል ነው ስሜን ጎንደር የታረደበት። በሌለበት፤ ባልነበረበት፤ በማያወቀው አጀንዳ ተጠያቂ ሆኖ አሁንም በእስር የሚማቅቀው አማራ ነው። ጎጃም እና ጎንደር። እኔ አብዛኛውን እትብቴ የተቀበረበትን ቦታ እንደ ምቾተኞች በመንፈስ ሰረጋላ ሳይሆን በእግሬ ተጉዥ የበላውን በልቼ ከሰኔሏ ኩርምት ብዬ ተኝቼ አቅበት ቁልቁለት ወጥቼ ስላደራጀሁት ከአንዱ ቀበሌ ወደ ሌለው ለመሄድ እንኳን ምን ያህል ጊዜ እንደሚያስፈልገው አሳምሬ አውቀዋለሁኝ እንኳንስ ከኡምንሃጀር ሸህዲን በመንፈስ ሰረገላ ጥቃት ሊፈጸም ቀርቶ። ውጪ አገር ያለውን ጀርባውን ፎቶ እያነሳህ ጎንደር ግን በይፋ እንዲታጨድ ተፈረደበት። የጦር ሰራዊት ማስልጠኛ ወልቃይት ላይ መሠረትን? ወያኔስ ከዚህ በላይ ምን አደረገ አስደረገ?  ዛሬ ደግሞ አዲሱ ተስፋ አብን መከራ ጥራኝ ብሎ በሁሉም ቦታ ውዳሴ ከንቱን በዛ መከረኛ አማራ ደም ላይ ያሳውጃል። 

ከጎንደር ከተማ ቋራ በእግር ለመሄድ ብርቱ ሂያጅ ከሆነ በእግር የ7 ቀን ጉዞ ነው። ለዛውም ተዋጊ ቀን አይሄድም ሌሊት ነው የሚጓዘው። ጫካም ገብቼ አይቸዋለሁኝ። ገድል መግባት፤ በወንዝ ሙለት መወሰድም አለ በላይ ከዘነበ በጨለማ ስለማይታይ ሙላቱ እኔ እራሴ አንድ ጊዜ መገጭ ላይ ገጥሞኝ ነበር ይህ መከራ። ዲሲ ላይ ተሁኖ ሲለቀቅ የነበረው የኢሳት የሞገድ የውጊያ ድል እና ግባቱ ተመስገን ነው ዛሬ በተወሰነ ደረጃ ለሌላ የፖለቲካ ትርፍም ቢሆን መደቡን ይዟል። ልኩን ቢመረውም ተጎንጭቶታል። ደማቸውን ከልብ ያደረጉትም እንዲሁ ታሪክ አልቦሽ ፈሰው ቀርተዋል። ጣማራ ጦር ነው። ዕንባ በዚህ የፖለቲካ እንቆቅልሽ ፍርዱን ይሰጥበታል። ፊቴ አመል እስኪያወጣ አልቅሻለሁኝ። ዕውነት እራሱ ነው ድርጅቱን እንዲህ ታሪክ አልባ አድርጎ ውልቅልቁን ያወጣው። 

ውሸት ቢያውል እንጂ አያባጅም። መባጃው ሞት ተሰንቆ ጎንደር የታረደበት ታሪክ ይሄው ነው። የጎንደር ልጆችም የመረረ የሃሳብ ታገድሎ የገጠማቸው በዚህ አመክንዮ ምክንያት ነው። ከራስ በላይ ንፋስ ምንም ስለሆነ። ነፃ ሳልወጣ ልቅር በሃሰት ፕሮፖጋንዳ ጎንደር ሲታጨድ ቁጭ ብዬ የሚዲያ አድማቂ እና አጨብጫቢ ከምሆን፤  በአለ ማህያ ሆኜ ሱፍ እና ከራባት አንጠልጥዬ ሙገሳ ከሚቸረኝ። መርዝ ጠጥቼ ብሞት እመረጣለሁኝ። አሁን ጎንደር ጉሙ እዬገፈፈለት ነው እድሜ ለዘመነ አብይ። … በግራ በቀኝ ካለ እዳው መሰቃዬቱን መስካሪዎቹ በርከት ብለዋለታል። ጎንደር ታሰረ ጎንደር ታረደ እሱን አግልሎ አጀንዳ ቀርጾ፤ ማናፌስቶ ጽፎ ለተደራጀ ለግንቦት 7 ሲባል። ይሄ የትም ቦታ ላይ አይደለም የሆነው በጅሉ ጎንደር ላይ እንጂ። አሸብሻቢዎች የጎንደር ህብረቶችም ለዚህ ነበር የተጉት። እዛች የአንድ ቀን አቧራውን አራግፎ እንዲንቀሳቀስ በቀሰቀሰው በጎቤ ጀግንነት የተርበተበተው ሻብያ ጦርነት ጀመርኩኝ ብሎ ሲያውጅ ጦር አዛዡ ደግሞ አውሮፓ ላይ ነበሩ  … 

ተራራ ላይ ተንጠልጥሎ የነበረው እዬተንጠባጠበ ይታያል። ይህ የእዮር ታዕምር እንጂ የሌላ የሰው አይደለም። ተመስገን! ለስልትም ስለመሆኑ መቼውንም ቢሆን የሚዘናጋ መንፈስ አይኖርም። ተገኝተናል። ከበሳል ፖለቲከኛ ታክቲክ እና ስትራቴጅ በዚህ መልኩ ሊቀርብ እንደሚችልም ሚዛን ላይ መስቀመጥ ግድ ይላል። ስለምን? የ2009 ርዕሰ አንቀጽ ያስተላለፈው መንፈስ ስላለ። አሁን እርግጥ ነው ተነስቷል ብልሆች ግን ይዘውታል። ስሜን ኢትዮጵያን ያገለለ መንግሥት ለነበረው ህልመኛው ግንቦት 7 መቋደሻው፤ የሰው ብርንዶ አቅራቢው ጎንደር ነበር። ግንቦት 7 ጎንደርን የጎንደርን ልጆችን ለመስጨፍጨፍ የተፈጠረ ድርጅት ነው። ለዚህ ነው ዓርማውንም ሥሙን ስንሰማው ያመናል የሚሉት የጎንደር ልጆች። ከእንግዲህ በፈለገው ዓይነት እና መንገድ ሥም እና ዝና በቅድስተ ቅዱሳን መንፈስ ቢመጣ የመንፈስ እርቀ ሰላም የለም። ከጎንደር በላይ የሚበልጥብኝ፤ ከጎጃም በላይ የሚበልጥብኝ ምንም ማንም ስሌለ። ኦቦ ለማ መግርሳ የልቤ የምላቸው አክብረውን እበራችን ድረስ ስለመጡልኝ ነው። ስለሆነም እኔ ሥርጉተ ሥላሴ ለማውያን ነኝ። አብያውያን ነኝ። ገዱውያን ነኝ። አንባቸዋውያን ነኝ።   
  • የአማራ መከራ በግንቦት 7 ሥም የሚታወቁት ብቻ …


"አማራ መሆናቸው ከወንጀል ተቆጥሮ በፋሽስት ወያኔ ታፍነው የተወሰዱና በተለያዩ የሕወሓት ማሰቃያ እስር ቤቶች የሚሰቃዩ" ዛሬ ከደጀ ሰላሜ ከሳተናው ድህረ ገጽ ያገኘሁት ነው። 
ይሄ እንግዲህ የታወቀው በዝርዝር ያለው ነው። በዬቤቱ በሚገኘውው አስር ቤት፤ በክንፈ ማሰልጠኛ ጣቢያ፤ በባዶ ስድስት ያለውንማ ፈጣሪ ይቁጥረው። ብቻ እዮር ፍርዱን ዳኝነቱን ይስጥ አቅማችን፤ ትምህክታችን እሱ ብቻ ነው። ማን አለን እና ለእኛ።

"ግንቦት 7 ዘረረው፤ ደመሰሰው፤ እስረኞችን አስፈታ፤ ሰላዮችን ገደለ፤ እንዲህ ያለ ንብረት አወደመ፤ ማስለጠኛ ተከፈተ" እዬተባለ በግንቦት 7 ሚዲያዎች ሁሉ በራዲዮው እና በቴሌቪዥን ጣቢያቸው ሲተረክ የነበረው የመከራ አዋጅ ዛሬ እንግዲህ ከዬትኛው መደብ እና ወገን ይመደብ እንደሆነ እዮር ይፈረደው። አስርጎ አስገብቶም ከሆነ ሌላው የታሪክ ግድፍት ነው። ብቻ ቃለ ምልልሱ ድርጅቱ "አሸባሪ" ከሚለው መንፈስ የራቀ ዓላማ ያለው እንደሆነ ለማጠዬቅ ነው። የሆነ ሆኖ የታረደው ጎንደር እንጂ ሌላው አይደለም። የሞቱት የእኛ ወንድሞች ናቸው። የሌላው ቤተሰብ እማ ምን ሆኖበት። ያስተምር፤ ይዳር፤ ይኳል። ቀልድና ቁም ነገሩ እንዲህ እና እንዲህ ሆኖ ይጣፋል። የራስን የዕትብት መንደርና ዞግ ሰላማዊ አድርጎ በሰው ቁስል ነበር ጨዋታው። ሌላማ ከጠፋ ዋላ ምን ይሁን ይባላል። ምንስ ካሳ ተጠይቆ በምንስ ካሳ ይወራረዳል። የሰው ሃብት፤ የታሪክ ሃብት፤ የእውነት ልቦና ሃብት ነው የከሰመው። የተዘረፈው በማንአለብኝነት። ታሪካችን፤ ተጋድሎችን ደማችን ነው የተቀማው። በደም የተገነባው ሠራዊታችን ነው የተዘረፈው። በግፍ!

ይህ አልበቃ ብሎ አሁን ደግሞ አዲሱ የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ እንላከለካለን እያለን ነው። መልሶ ይሄን ህዝብ ለሞት እና ለእስራት ለወያኔም ሳቢያ አምራች ሁኗል። ለዚህ ነው ሰሞኑን ትግራይ ኦን ላይን ግልጽ በሆነ ሁኔታ የጻፈው። አብን የአሁኑ ጉዞው አብሶ ለጎንደር እና ለጎጃም መጥፊያ እንጂ መዳኛ አይደለም። ሞት ተደገም ... ተከለስ እያለን ነው።

ግንቦት 7 ማጣፊያው ሲያጥረው ነው „አንድ አማራ“ ብሎ አዲስ የሲኦል ጥሪ ተላጠፊ ፈጠረ። አገር ቤትም በቀስተዳመነ መሥራቹ በፕ / መስፍን ወ/ ማርያም የኦህዴድ ጥንካሬ ሲያሰጋው ሰማያዊ ላይ ሄዶ ቁብ ያለው። አቅም የለም። በቃ በዚህ የለበጣ ፖለቲካ አገር ታመሰ ታረሰም። ለዛም አገራዊ ንቅናቄው ይሳካል ተብሎ ነበር ይሄ " አንድ አማራ" የሚል እንኮሸሽሌ የተፈጠረው። በሽግግር መንግሥት አራት ኪሎ ላይ ለመኮፈስ ሲል ተጨማሪም  ከደቡብ "አረንጓዴ ፓርቲ" ብሎ፤ ከወጣቶች "የአማራ ክንፍ" ብሎ ፈጠረ በራሱ አባሎቹ። አማራ አልተወከለም ለሚለው ተዋያዮች አድርጎ ለማቅረብ። በለስም ወፍም አልቀናውም ለማ እና ገዱ መንፈሱን ማርከሻ ሰርተው ወፊቱ ሌላ ዜማ ስታዜም ደግሞ አሁን ተፈልጎ የተገኘው ይሄው አዲሱ የአማር ብሄራዊ ንቅናቄ ነው። ውጪ ያሉትማ ይተዋወቃሉ። በሃሰት ክስ በገፍ የአማራ ልጅ ለእርድ እንዲቀርብ ተግተው የሰሩት የግንቦት 7 ሚዲያዎች ቢሆኑ እንዴት እና በምን ሁኔታ ይቅርታ ሳይጠይቁ እሁን ከእነሱ ጋር አብን ቃለ ምልልስ ማድረጉ ልብን ይቀረድዳል። ለዚህ ነው የወልቃይት የጠገዴ የማንነት ኮሜቴ አባላት ሰብሰብ ብለው የተቀመጡት። በዚህ አቋማቸው እንዲቀጥሉ ይነገራቸዋል። ቀልድ የለም። 

በዚህ ዘመን ይህን ማስተዋል ያልቻለ ዕብን መደራጀቱም፤ መሰባሰቡም፤ ባለራዕይ መሆኑም ለአማራ የሚፈይደው አንዳችም ነገር የለውም።  የሞት አዋጅ ነው። ታጥቦ ጭቃ። በመደራጀቱ አቶ ኤፍሬም ማዲቦ ዛሬ ሳይሆን ቀደም ብለው ከአውስትርልያ መልስ "የአማራ መደራጀት ለኢትዮጵያ አደጋ ነው" ብለው እዬገለጹ፤ በሌላ በኩል ደግሞ "በመሬቱ አለን እዬተዋጋን ነው፤ ወታደራዊ ማሰልጠኛም አቋቁመናል፤ አማራ አሁን መዳረጀቱን የመረጠበት ጊዜ ትክክል አይደለም" ማለት ምን ማለት እንደሆን መመዘን ያልቻለ ድርጀት ነገን በደም እንዲበቅል ከመሆን አያመልጥም። ዛሬም ቢሆን ድርጅቱ ከአማራ እራስ አልወርድ ብሎ ተጨማሪ የማፍረስ ፕሮፖጋንዳውን ይፋ አውጥቶ እዬተናገረ ስለምን ቃለ ምልልስ ከኢሳት ጋር ማድረግ እንደ አስፈለገ ሁሉ እጅግ ግራ ያጋባል። አማራነት አሞሌ ጨውነት ማለት አይደለም። ከብት ነው አሞሌ ሲይ የሚሰገበገብ። ሚዲያ ዛሬ እድሜ ለዩቱብ በአንድ ቀን መመሥረት ይቻላል። ምንም ጥገኝነት አያስፈልግም። 

ለእኔ የአቶ ኤፍሬም ማዲቦ ጉዳይ እና የትግራይ ኦን ላይን ውግዘት ተመሳሳይ ነው። ይህ በጥንቃቄ ሊያዝ እና ሊመረመር የሚጋባው ብልህ ጉዳይ ነው። የአማራ ሊሂቃንም ቢሆኑ ከድርጅት በፊት ለነፍስ ወከፍ የህዝባቸው ህልውና መቆርቆር መሟገት ይኖርባቸዋል። ይህ በአማሰራረቱ ሁለት አምክንዮን ይዞ ይመጣል ደስታ እና መከራ።
እኔ በግሌ አማራ መሞት፤ መከሰስ፤ አካል መጉደል፤ መታሰር ካለበት በራሱ አጀንዳ ይሁን ብዬ እስከ ጠ/ ሚር ቢሮ ድረስ አመልክቼ አዲሱ የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ ደግሞ ያ ርህህርና በሌለው ሁኔታ „ግንቦት 7 በዚህ እና በዚያ ጥቃት“ መፈጸሙን አስታወቀ በማለት አንድም ሪፖርተር መሬት ላይ ሳይኖር በጅሎች ትክሻ የነበረውን ትውና ልባችን ያውቀዋል። ዛሬ ሄዶ ከዛ መወሸቅ ነገ መከራው ከተቻለ ጥሩ ነው፤ መልካም ጉዞ ብሎ የሚመጣውን ከማዬት ሌላ ምንም የለም።

ቀድሞ ነገር ግንቦት 7 ለማን እንደ ተፈጠረ ለምን እንደተፈጠረ እኮ እኛ ባሰብነው በተጋንበት፤ "ጉዲት" የሚል ሥም እስኪሚሰጠኝ ድረስ ራሳችን በሃሳብም ደረጃ በማገድንበት መስመር አለመሆኑን እድሜ ለሐምሌ 5 የአማራ የህልውና ተጋድሎ ሁሉንም አይተናል። ያን ጊዜ ዘጋርድያን ሳይቀር ታዝቦ ጎንደር ሚዲያ የሌላት ከተማ ሲል ነበር የዘገበው። 

አቤቶ የጎንደር ህብረት "ከዞብል" እያለ ሪፖርት ሲቀርብ የነበረው እዛው አሜሪካ ላይ ተሁኖ እንደነበር አሳምረን እናውቃለን። አንድም የአማራ ድርጅት፤ አንድም የአማራ ታገድሎ ታታሪ፤ እንድም የአማራ ተቶርቋሪ ባልተጠዬቀበት ይግባኝ የለሽ ፍርድ VOA. ESAT. ሲያስተላልፉት የነበረውን ዘጋባ ያደመጠ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ሳቢያ ይፈልግ ስለነበረ አጋጠመኝ ብሎ አነደደው ጎንደርን ባልተወለደ አንጀቱ። ባገኘው በእጁ ባለው መሳሪያ ሁሉ ረሸነው ጎጃም እና ጎንደርን አማራን ነጥሎ። የተጋድሎውን ተስፋ ለማክሰል በፈንጅ ደበደበው። 

ዛሬ በዛ ደም የተገኘ ድርጅት ቃለ ምልልስ ተድራጊ ሲታገለው የነበረውን ተለጣፊ ድርጅት አድንቂ ሆኖ አረፈው። ነገ ደግሞ ውህደት እንጠብቃለን በምስሉ ካደራጀው ከአንዱ ጋር። „ዓይጥ ለሞቷ የድመት አፍንጫ ታሸታለች።" "እጸድቅ ብዬ ባዝላት ተንጠልጥላ ቀረች" ነው። ግንቦት 7 ለመጀመሪያ የሠራዊት አባሉ ለአርበኛ ዘመነ ካሴም፤ ባዶ እጁን ሄዶ ቤት ለእንግዳ ላለው  ኢትዮጵያ አርበኞች ግንባር፤ በቅንጅት ጊዜም ባላቸው ላይ ተዳብሎ የፈጠረውን የዘመን ትርምስ እና ውድቀቱን ቁጭ ብለን እያዬን ነው። አሁን እንኳን ትንሳዔን ሲያውጅ ብለልሁ ኦቦ ሌንጮ ለታ ጉም አደርገውት አፍንጫህን ላስ ብለውት ነው የሄደው። 

ቀጣዩ የአብ ጉዞ ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ውህደት ይጠበቅ ይሆናል፡፤ ምን አለ አማራ ይሙት ...። ምን አለ አማራ የመሞከሪያ ጣቢያ ነው።  አማራ እያለም አስታዋሽ የለውም እንኳንስ ሞቶ ማን ያስተዋሰው ያ ሰማዕት ሳሙኤል አወቀን ማን አስተወሰው? ነፍሱን ኑሮውን ለሰጠው ትናንትን እንርሳ ሲባል ዕውነትን እንርሳ ማለት አይደለም። ለጎንደር ግንቦት 7 ከተፈጠረ ጀምሮ ታሪኩን የቀማ እና በድብቅ ሴራ ያረደው ድርጅት ነው። የእነ አበጀ በለውን፤ የእነ አርበኛ "አብርሃም" እንግዳን፤ የእነ ጄ. ሃይሌ መለሰን፤ የእና መስከረም አታላይን ድርጅት ዋጠው። የተለመደ ነው ባዶ እጁን ሄዶ መኢህአድን እና ኢዴፓን ውልቅልቃቸውን እንዳወጣው ቀስተደማና። ሲገድልም ማህበራዊ መሰረታቸውን አሳጥቶ ነው። ያ በብሄራዊ ደረጃ ስለነበር መስዋዕትነቱ ሁሉም ቦታ ስለገበረበት ይሁን። አንድ ብሄር ወይንም አንድ አካባቢ ብቻውን አልቀለጠበተም። አሁን ግን ጎንደር እና አማራ ብቻ ነው። በገዳይ ሪከርድ ሰባሪ ጎንደር፤ በተገዳይ ሪከርድ ሰባሪም ጎንደር። ዘመን ይፍታው። ለክፉ ቀን ላወጣው ጎንደር የግንቦት 7 መሥራች የሸለሙት ይህን ነው። ብልሁማ አንዲት እናት እርጎ ካለሂሳብ ጨመሩልኝ ብሎ ጋብቻ አስወስኖ ዝምድናውን ፈልጎ ይሄው ዛሬ የሚሊዮኖችን ቀልብ ገዝቶ በ እለቱ ፍቅርን ከነማተቡ አተረፈ። ለዚህ ነው አሁን ጎንደር ለአብይ ካቢኔ ጸሎት በተደሞ እና በወል ላይ ያለው። ብልሆች እንዲህ ናቸው ይሉኝታ የሚያወቁት። የኪዳን ቀለበቶች፤ የዘመን አዋራዎች። 

ለወያኔ ሃርነት ትግራይ ብቻ ሳይሆን ለግንቦት 7 እኔ መጠዬቅ የምሻው „ጎንደር ምን አደረገ ነው“ የዛሬው ሊቀ ሊቃውንትነት እኮ የጎንደር መሬት አደራ አውጪነት ነው። የጦር አዛዥነትም የጎንደር አንበሶች የመሠረቱት የ ኢትዮጵያ አርበኞች ግንባር ነው። በጥርስ የተያዘነው ደግሞ እኛ ጎንደሮች በተለይም አማራዎች ነን። እዚህ እንኳን ድርጅታቸው ነው የሚያስድደን። ሌላ ዘር ያለባቸው የተሻለ ዕድል አላቸው … ግን ምን አደረገ ጎንደር? ሻብያ የባድመን፤ የናቅፋ ገንዘብን ውድቀት ቁንጫኑን ለመወጣት ጎንደርን መማገድ ነው። ትግራይ ላይ አይሞክራትም ከ20 ሺህ ያላነሰ ሰራዊት አደራጅቶ እያጋባ እያዋለደ … 

  • ውሸት እርኩሰት ነው።

በውሸት ፖለቲካ ቋጥኝ ለቋጥን ሲቧጥጥ የነበረ ድርጅት አቅም አለኝ ብሎ ጎንደርን ለሞት አሳልፎ ሲሰጥ፤ የአማራ ተጋድሎ መሰረታዊ ጥያቄ „የነፃነት ሃይል“ በሚል ሲጠቀለል በሸታ ላይ የወደቁ መላ የጎንደር እናቶች በዕንባ ብዛት አንጀታቸው ሲታረስ አብዛኞቹ ሲሞነኩሱ ለአብን ምኑም አልነበረም። ምን አስቸኮለው ከንቱ ውዳሴን ለመሰብሰብ። በጥቅሉ ለተጋችሁ ሁሉ እናመሰግናለን ቢባል ምን በነበረ። በሌላ በኩል ሞት ደግሶ በግራ በቀኝ ሲያዋክበው ለነበረ ሚዲያ እንዴት እዛ እስር ቤት ውስጥ ነፍስ እያለ እንዲህ ያለ ቃለ ምልልስ ይሰጣል። ስለምንስ ታሰበ። እውነት ለመናገር አረመኔነት ነው። ጥፍር ሲወልቅ፤ ሲንኮላሽ፤ ትዳር ሲበተን፤ ከሥራ ሲፈናቀል ማነው ለአማራ ህዝብ ድምጹን ያሰማለት? ማን? ተጋድሎውን እውቅና የሰጡት SBS OMN BBN HEBER MERATE አዋዜ ብቻ ነበሩ። አማራ ተጋድሎ ለማለት የደፈሩት። እስከ አሁን ይህ ባልተደፈረበት ሚዲያ ሽርክና ይመራል፤ ይጎፈንናልም። እነዚህ ሚዲያዎች ሥማቸው ተጠርቶ መመስገን ነበረባቸው - በምሥረታው ላይ። 

ቀሪዎቹ እንደ አቅማቸው የአማራ አንደበት የሆኑ በሥሙ የተደራጁ ነበሩ። ለእነሱ ምስጋና አያስፈልጋቸውም መደበኛ ሥራቸው ነው የሠሩት። ትውልዳዊ ድርሻቸወም ነው የተወጡት። ከድህረ ገጽም ሳተናው እና ዘሃበሻ ብቻ እና ብቻ ናቸው በትጋት የሠሩት ዛሬም። ጀግኖቻችን ሲፈቱ እንኳን ደስታቸው አልነበረም። ዘሃበሻ እና ሳተናው ብቻ ናቸው የዘከሯቸው። ክብር ለእነዚህ አማራጭ ሚዲያዎች። ሌሎቹ የሃዘን ቀናቸው ነበር የግንቦት 7 ፕሮ ሚዲያዎች ሁሉም። ሳጅን በረከት ስምዖን ሲለቁ የአማራ ክልላዊ መስተዳደር ጽ/ ቤት በስልክ ተጣደፈ ብሎ የዘገበው የግንቦት 7 ትንሳኤ ራዲዮ ነው። ለነገሩ „ትንሳኤ“ የቅንጅት መንፈስ ነው። የፈጠረውም መንፈስ ነበር። የተመረጠበት ይሄ ስያሜም ያን መንፈስ አመጣለሁ ነው። የኩሬውሃ¡Stagnate አማራ ገዳዩ ሥልጣን ለቀቀ ብሎ ድንኳን ጥሎ ሊያለቅስ? ውጥንቅጥ።


የአማራ እና የኦሮሞ አንድነት እና ትብብር ሲኖርም ደስታቸው፤ ፍሰሃቸው አልነበረም። ግስጋሴው ከ „ከእርምጃ ወደ ሩጫ“ ጉዞው ሁሉ አስፈሪ ስለነበር በቀጥታ ወጥተው ነበር የታገሉት። „እንዳያማም ጥራው እንዳይበላም ግፋው“ የነበረ ወጣ ገብ አቋምም ጉድ ነበር የታዬው። „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነውን“ ታግለውታል እኮ። እሰከ አሁን ድረስ። አማራ በታሪኩ እንደ ኦህዴድ ያለ ድርጅትም እንደ ቲም ለማ ያለ ቅን ንጹህ መንፈስም ፈጽሞ አያገኘም። ተግቶ የተሠራውም አማራ ከተቀረቀረበት ቀና ይላል መንፈሱ ጥግ ያገኛል ተብሎ ነበር በቲም ለማ ላይ አሉታዊ መረጃዎች ሲወጡ እዬተለቀሙ ፖስት ሲደረጉ የነበረው። ሌላ ምንም ሳይሆን የአማራ ትንሳኤ በመንፈስ ደረጃ ቀን ይወጣለታል ተብሎ ስለታሰበ ነበር። ይህን ያልገባው የእኛው የአማራ ሊሂቅ፤ ተንታኝ፤ ታታሪ፤ ድርጅት ደግሞ ከቲም ለማ ጎን መቆም ሲጋባ ዛሬም እዬወጣ ጉሹን ይለቀዋል። ሌላ ልቅልቅ ትንታና ሲያሰማ ቃለ ምልልስ ሲያደርግ ይደመጣል። ጥቅሙን የማያውቅ ማህበረሰብ ቢባል አማራ ብቻ ነው።

ልብ ከዬት ይገዛ፤ ህሊናስ ከዬት ተምጦ ይወለድ? አማራን በህሊናው የማይጠላ አማራን በህሊናው ያላገለለ እሲከ አንድ ሊሂቅ ይቅረብ። ያን ጊዜ ተዋቸው ይደራጁ ወንጀል አይሁንባቸው ብለው የጻፉት የመከካለኛው ምስራቅ አፍሪካ ሊቃውነቱ አቶ የሱፍ ያሲን ብቻ ናቸው። አንድ ዕጣ ነፍስ። ፖለቲከኛው ጆዋር መሃመድም ፊት ለፊት ወጥቶ ብትንትን አድርጎ ሞግቷቸዋል። በሚዲያውም ታታሪዎችን ለረጅም የአዬር ጊዜ እንዲያገኙ አድርጓል። አጋርነቱን ገልፆል። የኞቹማ ጎንደርን ያስቀቀሉ ናቸው ... እሩጉሞች!

ዛሬ ባላለቀው ወደፊትም በማያልቀው ተጋድሎ ሥም የተፈጠረ ጮርቃ ድርጅት „አንድ አማራን“ አመስጋኝ ሆኖ ማረፉ አልበቃ ብሎ ከኢሳት ጋር ቃለ ምልልስ አድራጊ ሆኖ አረፈው። ግንቦት 7 ላያተርፍ አይከስርምብልጠት የተፈጠረበት መርከቡ ነው። አቅም ያለውን እዬሄዱ ማደን ስትራቴጂው ነው። አብን በአማራ ደም ቀለደ። በዘር መቀለድ። በዕንባ መቀለድ። ቀልዱ ቀጥሉም … ካዋጣችሁ የዛሬ ሞቅ ደመቅ ብሎ የተካሄደው ጉባኤ ነገ ሬት ካልሆነስ መልካም ነው። ደስ ብሏቸው ነው ቃለ ምልልስ ያደረጉላችሁን? ወዳዋችሁ ሙተው? ምጥ!

  • ይህ ምን ልዩነት አለው? 


እኔ እምጽፈው ለቅኖች ለንጹሃን ህሊና ላላቸው ብቻ ነው። ቅኖች ደግሞ ጥቂቶች ናቸው። ቻቻታ፤ ሁከታ፤ ኳኳቴ አያሰኛቸውም። ተደብቀው ነው የሚኖሩት። እዩኝ እዩኝም አይሉም። ማንም ዜጋ ሰለ ሰው ልጅ የሚያገባው፤ ስለተፈጥሮ ጭንቅ ጥብብ ለሚል ከግንቦት 7 ከፍተኛ መሪ ሃሳብ እና ከትግራይ ኦን ላይን ሃሳብ ጋር ምን ያህል ጋብቻ እንዳለ ይሄን አንብቦም አዳምጦም መመዘን ይቻላል። የወሎ ጭፍጨፋ እና የአቶ ሞላ አስገዶም ድርጅት  የአቋም መግለጫ የቅርብ ጊዜ ስለሆነ ፊርማው ስላልደረቀ ወደ ዛ መሄድ አይስፈልገኝም። የራሱም የግንቦት 7 አባል ጋዜጠኞቹ ስለሞገቱት። የትናንቱ የአብአን በአንድ በኩል ቃለ ምልልስ ተድራጊ ከኢሳት ጋር፤ በሌላ በኩል „ አንድ አማራን“ አመስጋኝ እስኪ ይሄ መንፈስ እና የወያኔ ሃርነት ትግራይ መንፈስ ምን ልዩነት አለው? ፍርድ ለራስ ነው?

አቶ ኤፍሬም ሌጄቦን አንድ በሏቸው! (ሐይሉ አባይ ተገኝ)

june 11, 2018

Establishment of National Movement of Amhara and its danger for Ethiopia

Tigrai Online, June 11, 2018

  • „በማን ላይ ቆመሽ እግዜሩን ታሚያለሽ"

አብን የማን ተጋድሎ ውጤት ነው? የማን ደም ነው የወለደው? እንኳንስ አብን እስረኞችን ያስፈታው የአማራ ተጋድሎ እና የኦሮሞ ንቅናቄ አብዮቶች ብቻ ናቸው። ይህ አሁን የተገኘው መተንፈሻ ኢትጵያን ወደ ነበረበችበት ክብር የመለሰው እኮ ተጋድሎውን ውስጣቸው ባደረጉ በለማ ገዱ መንፈስ የተገኘ ድል ነው። የታሪክ ሌቦች እማ እድሜ ለዘመን አሽሉኳቸዋል።

ዛሬን አብን የሰጠው ማንም እና ማንም ሳይሆን አማራ በተጋድሎው ኦሮሞ በንቅናቄው ከሁለቱም ከአብራኩ በወጡ አንበሶች በለማ በገዱ በአብይ በአንባቸው ያልተቋረጠ ከወያኔ ሃርነት ትግራይ የገነገነ የእፉኝት መንፈስ ጋር የሞት የሽረት ትግል አድርገው ነው። ይህ ድል ደም ተገብሮበት በሃሳብ ስንት ጉግስ ተካሄዶበት ነጥሮ የወጣ ድል እንጂ በኢሳትም በግንቦት 7 የተሰጠ ችሮታ አይደለም። ይህ የለወጥ መንፈስ በቂ ድጋፍ እንዳይኖረው ተግቶ ተሰርቶበታል፤ ተቋርጦ ተጋድሎዎቹ መክነው ታሪካቸው እንዲከስም በትጋት እና በታታሪንት የሰራውም ኢሳት ነበር። ከፋክት ጋዜጠኛው „አናስደንግጣቸው“ ከጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና በስተቀር። ሁሉም ተረባርበውበታል፤ ቴሌቪዥኑ ራዲዮወኑ አልበቃ እያለ ብራናውን እያጨናነቁ ሞት እና ሁከትን ሲያበረታቱ መንፈስ እናዳይሰባሰብ ጥርጥራሬን ሲዘሩ ነው የከረሙት። በአቋራጭ እንጂ መሬት ላይ ሥራ ሠሮት አልተለመደም አልተኖረበትም። ከተደራጀው ቁብ - ዋጥ - ነበሩን ናድ - መንበር መረከብ ይሄው ነው ሂደቱ። 

ኦህዴድ የኦሮሞ ድርጅት ባይሆን ኖሮ ተመራጭ ነበር። ዕድሉ ከተገኘ ደግሞ አሰናብቶ ንግሥና። አቅም የለም። ሃሳብም የለም። ፖለቲካ ፓርቲ በራሱ ሃሳብ መቆም ካልቻለ ሲፈጠር ነው የሚሞተው። ሁልጊዜ ተጽዖኖ ፈጣሪ ተማጥነህ እንዴት ይሆናል? ይመስገነው ፈጣሪ BBC ሚስጢሩን ከእነ አስኳሉ አግኝቶታል አወያዩ ቅኔ ነው። ጨዋታው ገብቶታል። ከልቡም ተከታትሎታል ጠቅላላ የታሪኩን ሆድ እቃ። አቅሙን ተረድቶታል። እርግጥ ነው አሁን አንድ ቅርብ መስመር መገኘቱን ልብ ያላልነው እንዳይመስላችሁ በማን መንጠላጠል እንደታሰበ ... ተጽዕኖ ፈጣሪ ፍለጋ እድሜ ልክ ከመባዘን ልክን መጥኖ መንቀሳቀስ በበጀ። ካልሆነ ደግሞ መተው። ቅብዕ የፈጣሪ ስለሆነ ... 
  • ችሮታ ከማንም ተጠማኝ አይደለም የዛሬው ለውጥ። 

ዕውቅና ላለመስጠት ቢፈለግም እውነቱ ግን እውነት ነው። በዬትኛውም አገር ቤት አለሁ በሚል ተፎካካሪ ድርጅት እና መልካም ፈቃድም የተገኘ አይደለም ዛሬ ያለው ድል። ጥሪውን በተቀበሉ የዘመን የሰዋዊነት አንበሶች የተገኘ የሰማይ ስጦታ ነው። እነ አብን ታስራችሁ የተፈታችሁት በአዲሱ አብይ ካቢኔ በጠ/ ሚሩ ልዩ ትእዛዝ ነው። ስክነት ያሰፈልጋል። ሁላችንም ኑሯችን ገብርንበታል። ቅራኔ ውስጥ ፈቅደን ወደን ስለ ዕውነት ብለን ለእነሱ እንዳደረግነው ሁሉ እንደ ቀደመው ሁሉ ተማግደንበታል። እነሱም እውነት ይዘው ጫካ ሲገቡ ለሞት የሄደ አይወቀስም አይነቀስም ሊደገፍ ይገባል ብላ ሥርጉተ ሥላሴ ሞግታለች። ዛሬም እማደርገው የማዬው ዕውነት ስላልሆነ ብቻ ነው።

በሂደቱ እራሱ ግንቦት 7 እስከ ሚዲያው ሳይነሳ ግን የሁሉም መከራ መሥራች እና ፊታውራሪ በሆነው በወያኔ ሃርነት የግፍ አገዛዝ ላይ በትጋት ተሰርቶበታል። ዓለም ዐቀፍ ማህበረሰቡን ከተለመደው ውጪ በሆነ አቤቱታ አስጨንቄያቸዋለሁኝ። ስለምን ነው በርሊን ላይ የተከበሩ የግሎባል የመቻቻል እናት የጀርመን ጠ/ ሚር አንጅላ ሜርክል ሰላማዊ ሰልፉን ወጥተው ከነ ካቢናቸው የተመለከቱት፤ ኢትዮጵያ ሲሄዱም ኢህዴግ ያቀረበላቸውን ጥሪ አልቀበልም ብለው ተፎካካሪዎችን ያነጋገሩ፤ ሴቶችም እንዲገኙ አበክረው የገለጹት፤ ዶር መራራ ጉዲና ከእስር ሲፈቱ በኢንባሲያቸው ላይ የክብር አቀባበል ያደረጉላቸው፤ እስረኞችን በሚመለከት በቀጥታ ለቀድሞው ጠ/ ሚር ለአቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ስልክ የደወሉት፤ በማን አቅም በምን አቅም፤? በቅርቡ እኮ ቅልጥ ያለ ሰላማዊ ሰልፍ ተደርጓል በርሊን ላይ ለዛውም የግንቦት 7 ዓርማ ተይዞ። ያው ጅብ ከሄደ ነው ግንቦት 7 ፍጥረተ ነገሩ …  ወጡ እና ጠ/ ሚሯ ተመለከቱት? ዕውቅና ሰጡት?

የሬቻ  እልቂት እና የተባባሩት መንግስታት የቀድሞው ጸሐፊ Ban Ki-moon ባን ኪሙን ወጥተው በአደባባይ ትግሉን ስለምን ተቀላቀሉ? የወጣት ንግሥት ይርጋ፤ የወ/ሮ ታደሉ ከልጃው ሬሳ ላይ ተቀምጠው መደብደብ፤ የኮንሶ ልጅ በቤቱ ውስጥ ከነፍሰጡር አራስ ልጅ ጋር በእሳት መንደድ የባህርዳሩ፤ የአንባጊዮርጊስ ፤ የሬቻው አስቃቂ እልቂት የሰው ልጅ ከሚችለው በላይ ስለነበረ በማይደፈር አቤቱታ፤ ሆኖ የማያውቅ ተቀባይነት ተገኜበት። ዛሬ አብን ሹሞቹን ሲመርጥ የታታሪት ንግሥት ይርጋ ተቀምጣ ያዬነውን አይተናል። የታታሪት ንግሥት ይርጋ ፎቶ፤ የኮንሶ እናቶች ፎቶ፤ የባህርዳር፤ የአንባ ጊዮርጊስ፤ የሬቻ እልቂት ፎቶ ተልኳል።

የወንዶች የፖለቲካ አለም ዓመት ድገሙ ብሏል። ከሰማያዊ ፓርቲ ጥወራ ከመሄድ አጀንዳዋ አማራ የሆነችው ወጣት ንግሥት ይርጋ ቁንጮ ነበረች። ወጣትም፤ ሴትም ብቁም። የእናንተ ነገር እንደ ቀስተደመና ፓርቲ ወረቀት ፍለጋ ነው የሄደው።  ለነገሩ ለመልካም ነው። ከእንዲህ ዓይነት ካልጠራ ጉዞ እንድትዘፈቅብኝም አልሻም። ው መሆን ይበቃል ህዝብን ዝቅ ብሎ ለማድመጥ - ለማገልገልም። ሥርጉተ ሥላሴ ቆራጣ ዲግሪ የላትም። አልተማረችም ዩንቨርስቲ ገብታ። ግን እኔ ነኝ ያለውን ሚዲያ፤ ሊሂቅ ትሞግታላች፤ ጎንደርም ኮከቡ የነበረች ልጁ ናት። ግንባሯን የማታጥፍ፤ ልብ እንዲገጠምላት መቼውንም የማትፈቅድ። ባለመሟሯ የቀረ የጎደለ ነገር የለም። „ሳይንቲስ ለመሆን ሰው ብቻ መሆን ይበቃል“ ብለዋል ክብርት ወ/ሮ ጽዮን ተክሉ። ባለዶክተር ማእረጉማ እዬተዬ ነው። አብይን ለመተርጎም፤ መንፈሱን ለማጥናት አቅም አልተገኘም። ከሁሉም ቀድማ የሞገተች ያሸነፈችም ያልተማረችው ሥርጉተ ሥላሴ ናት። ዲግሪ የሌላት።

ትጉህ ወጣት ንግሥት ይርጋ ከዚህ ዋቢ አላት ሥርጉተ ሥላሴ የምትባል። ፎቶዋ ከጀርመን ጠ/ ሚር ቢሮ፤ ፎቶዋ ከተባባሩትም መንግሥታት አለ። የሰማዕታትም። ሰው መሆን ይበቃል ራስን ለነፃነት ለመገበር። ገበሬ መንደር ከዬትኛው ዩንቨርስቲ የተመረቀ መሪ ይገኝ ይሆን?  ስለምን ሰው ሰውነቱ ሳይሆን መለኪያው ሌላ ስለሆነ፤ ወረቀት። ጎንደርን ጎጃምን አታለካልኩት በሽታሽቶ እንዲያልቅ ተፈርዶበት አሳሩን በልቷል። በነሳጅን በረከት፤ በነሳጅን አዲሱ ለገሰ፤ በነሳጅን አለምነህ ዋሴ … ያ ከበቂ በላይ ነው ….



በምን አቅማችሁ ነው እናንተ ዕውቅና ሰጪስ ነሺስ የምትሆኑት? በምን? በልክ መራመድ ያስፈልጋል። ሂደቱን ተከታትላችሁት ቢሆን ኖሮማ እንደ አንበሳው ጀግና እንደ ኮ/ ደመቀ መኮነን ክውን ባለ፤ ልቅም ባለ፤ ጥርት ባለ ሁኔታ ትጀምሩት ነበር። አማራ ተጋድሎ እኮ መሪ አለው አንበሳ ኮ/ ደመቀ መኮነን የሚባል ወያኔ ሃርነት ትግራይ የሚይርድበት፤ ወጣት ንግሥት ይርጋ የምትባል ሳተናዊት ወጣት፤ አቶ አታላይ ዛፌ የሚባል አንደበተ ርቱ ልባቸው ሩቅ ነው። መንፈሳቸው ጥልቅ ስለሆነ ካገኙት ኪዎስክ ያገኙትን ሎተሪ አይገዙም። ያደጉበት ሙያ በልብ ነው። ጎንደርን አታለካልኩት። መከራው አላለቀም። ጎጃምን አታለካልኩት መከራው አላለቀም።



መነሻውን ያለወቀ መድረሻውን አይታዬውም። BBC የሰጣችሁ ክብር በቂ ነበር። ለማንም ያልተሰጠውን ዕውቅና ነው የሰጣችሁ። ይህ ደግሞ „በአንድ አማራ ፓርቲ“ ችሮታ ተጋድሎ ሳይሆን ከውስጣቸው አማራነት በበቀለ በጠሩ ታጋይ ድርጅቶች የተገኘ ሰብል እንጂ ከሜዳ የታፈሰ አልነበረም። "አንድ አማራ ፓርቲማ" ለአማራ ሞት ወያኔ ሃርነት ትግራይን ለስልጣን ያበቃ መንፈስ ነው። አሁንም ሌላ መንፈስ ሊጎልት ሲሰናዳ ኦህዲድ በቆረጣ ገብቶ ጉድ አደረገልኝ። ለእነሱም ተረፈ። ተመስገን!

አልሰማችሁም አሁን ያለው መንግሥት አማራ እና ትግሬ እዬገዛ ነው ሲባል? የት ነበራችሁ? ምስጋና ሲላክ ለማን ነበር የተላከው? የአወሮፓ ህብረት በ2013/14 ያወጣው ጥልቅ ዶክመንተሪ ነበር። የወያኔ ሃርነት እና ጦሱን በቅጡ የዳሰሰ። 

ያ ማለት ለኢትዮጵውያን ዕንባ ተጠያቂው የወያኔ ሃርነት ትግራይ ነው ማለት ነበር። ያ ውሳኔ ተገልብጦ በ2016/ ለ2017 የዕቅድ መነሻነት አውሮፓ ህብረት የቀረበው ሪፖርት 5 ጊዜ ኦሮምያን፤ 2 ጊዜ ኦጋዴን ሲያነሳ አማራ ቃሉን እራሱ አልተጠቀመበትም። እጅግ በጥንቃቄ ነበር የተሰራው፤ እሰረኞች የኦሮሞ ልጆች ብቻ ነበሩ የተጠቀሱት። አንድም የአማራ ተጋድሎ አንበሶች አልነበሩበትም። እኔም ጽፌበታለሁኝ። ሳተናው አርኬቡ ላይ ይገኛል። ወያኔ ሃርነት ትግራይ ጥበብ የለውም በግልጽ ነው አማራን የሚገድል፤ የሚያሳድድ። ሌላው ግን ሥልጣን እስኪይዝ መሬት ስለሚያስፈልገው መሰረቱን በስልት ጎራረደው - አስቀድሞ።

ማድመጥ ያሰፈልጋል። ይሄን የቆሸሸ የጥላቻ ዘር ነው ለማጠብ ሌት እና ቀን ቅኑ ጠ/ ሚር አብይ አህመድ መንፈስ እዬተጋ ያለው። ዛሬ በወያኔ ሃርነት ትግራይ ህሊና ውስጥ ያለው ጥላቻ ያህል በሌላውም የለም ማለት መሽቶ አይነጋም ማለት ነው። እኛ አይኑረን። እነሱ ግን በጥርሳቸው እንደያዙን ነው። በተሳሳተ መረጃ፤ ዘጋቢው አሜሪካ ተቀምጦ ከዳባት፤ ከአንባ ጊዮርጊስ፤ ከስማዳ፤ ከማርቆስ እዬተባለ ሲዘገብ ነበር። ሁሉም መነሻውም መድረሻውም „የነጻነት ሃይሉ ነው“ በቃ በዚህ ነው አማራ የታረደው። ይህ ድርብ ዓላማን ያነገበ ሲሆን አንደኛው የአማራ ተጋድሎን „አማራ ነኝ“ ለማፈን፤ ሁለተኛው „የወልቃይት እና የጠገዴ ጥያቄ አዳፍኖ ለማስቀረት፤ ሦስተኛው አማራ ለዬትኛውም መንግሥት የሚመች አለመሆኑን ለማስገንዘብ። አራተኛው የባድመ ጦስ አማራ እንዲቃጠልበት ነው። ይሄን እያዬን እንደገና መከራን መወር የሞተ አስነስቶ ዲሞ ያስወጣል። ስከኑ። ጥልቅ ጥልቅ አትበሉ። ከዋናው ለዚህ ካበቃችሁ መርሃዊ ጉዳይ ተነሱ። 

አማራ አማራ ነኝ እንጂ አፋር - ጉምዝ - ከንባታ ወላይታ ነኝ ብሎ አይደለም ደም የገበረው ጎንደር እና የጎጃም አማራ። ዕውነቱ ይሄው ነው። አትሸጡት ዓላማውን። ቅዳሜ ገብያ ጎንደርን የመሠረተ የታሪክ አንባ ነው የነደደው። ልብ ይስጣችሁ። የሃሳብ አቅም ከሌላችሁ ስለምን ለሁለተኛ ግብር አማራውን ታዘጋጃላችሁ? አንድ የፖለቲካ ድርጅት የሃሳብ ደሃ ከሆነ የፖለቲካ ድርጅት ሥም መፍጠር እርባና የለውም። ኦህዴድ አኮ ከዚህ ያደረሰው የሃሳብ ዲታ ስለሆነ ነው። አምጡ!
ኢሳት ቃለ ምልልስ ያደረገላችሁ አብን ውስጥ እኔ አለሁኝ ለማለት ነው እንደ ለመደበት ግንቦት 7። ስለምን አዲሱን የኢንጂነር ይልቃልን ፓርቲ አልጠዬቀም ኢሳት? ጋዜጠኛ ሲፈታ በአደባባይ ግንቦት 7 ነኝ ተብሎ እንዲወጣ የሚያደርገው ያሰራችሁዋቸውም የእኔን ዓላማ ሲያሳኩ የነበሩ ናቸው ነው። እሰረኞች በለማ ገዱ ተጋድሎ ሲፈቱ በሁሉም ቦታ አለን ነው ያሉት በአደባባይ ወጥተው። ይህም ማለት የፈታችሁትን መልሳችሁ እስሩ ነው። የኛዎቹን ናቸው ስለምን ፈታችሁ ነው። ኮ/ ደመቀ ዘውዱ ሲፈቱ አሰራችሁት ፈታችሁት አካሉን ሳታጉድሉ ተብሎ ነው የተፃፈው። የቀረ አለ ጨምራችሁ እሰሩ ነው። 

ኦህዴድ በትረ ሥልጣኑን ሲረከብ ቄሮም ውስጥ እኛም አለነ ሲባል ኦህዴድ ወስጥ እኛም አለን ነው። አሁን ሁሉም አበቃ የአብይ ካቢኔ የግንቦት 7፤ የቀስተዳመነን የቅንጅትን አዕምሮ ሲፈታ ደግሞ ውሸቱ ወላለቀ። ወጌሻ አልቦ። ሌላው ቀርቶ ኦህዴድ እና የገዱ መንፈስ ያን ያህል እዬታገሉ ከውስጥ መረጃ እዬተባለ እነሱን ከግንቦት 7 ጋር ለማለካለክ የነበረው ጥረት ምን እንደሚፈለግ ሁሉ ግራ ያጋባል። ግንቦት 7 ጤነኛ መንፈስ የለውም። ስለምን የተጠጋውን እሱ ብቻ ነው የሚያወቀው? ጸጥ ያለ የፖለቲካ መረጋጋት አይታይበትም ... 

ስለዚህ አብን ላይ ደግሞ አለሁኝ ለማለት ቃለ ምልልስ አደረገ የመክፈቻ ንግግሩ ውስጥ „አንድ አማራ“ አጀንዳ ሆኖ ወጣ። ሰው ስንት ጊዜ ይሞኛል?! ሰው ስንት ጊዜ ይታለላል?! እንድታውቁት አምሻው ጎንደር ከእንግዲህ በማንኛውም ሁኔታ በዚህ የለበጣ የገድያ ማህበር ገብቶ አንደማይዘፈቅ ነው። አብን በጠራ መስመር እራሱን ወቅሶ ተሳስተናል ከልተደመጠ አንዷ አምትፋለማችሁ ሥርጉተ ሥላሴ ትሆናለች። በጎንደር ቀልድ የለም። በጎንደር ድርድር የለም። ጎጃምም ነፍሴ ነው። ታጭዷል 43 ዓመት ሙሉ። ቀና ያሉ ልጆቹ ሁሉ አፈር ገብተዋል። ባድማውም አፈር ለብሷል። እስኪ በዬከተማው የተካሄደውን ስብሰባ ተመልክተቱ ሁሉ ከነማህባው፤ ከወዙ ነው ያለው ጎንደር ግን ድቅቅ ብሏል። ወዝ ያላቸው ልጆቿ ተመጠዋል በአፓርታይድ የወያኔ ሃርነት ትግራይ አገዛዝ እና በሻብያ ሴራ። ጦርነቱ ባድመ ላይ ሳይሆን ጎንደር ላይ ነው የተጠናቀቀው። አሁን ተመስገን ነው። ዕልባት ተሰጥቶታል። 

የአንጋች ብቻ ሳይሆን የመንፈስ ሽፍቶችን ጎንደር ከእንግዲህ አታስተናግድም ከጎጃም ደም መላሽ ህዝብ መንፈስ በስተቀር። አሁን ተመስገን BBC UN አውቆታል የአማራ ተጋድሎን። ዕውቅናም ሰጥቶታል። የኬኒያ ሙሁራንም ሳይቀሩ በአማራ ተጋድሎ ላይ በሚገባ ተወያይተውበታል። አዲሱን ጠ/ ሚር በማምጣት እረገድም ድርሻውን አጉልተውታል። ዛሬ እድሜ ለጉጉል። 

ቢፈልጋችሁ ለምን የአማራ ድምጽ አልከፈተም ኢሳት። የከፈተው እኮ የኦሮሞ እና የትግሬ ድምጽ ነው ለዛውም ኦሮሞ OMN የመሰለ ሚዲያ እያለው። በአማርኛ የሚያስተላልፈው ኢሳት የሥራ ቋንቋ ስለሆነ ብቻ ነው። ለዚህ እማ ETV፣ EBC፣ ENN፣ FANA ዝግጅታቸው በአማርኛ ነው። መልካም ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ባምንም እዛው ኢሳት ውስጥ። ከጭንቅላት ውስጥ ጥላቻ ካለ በዬሁኔታው መጋለጡ አይቀሬ ነው። ከሁሉ በላይ የግንቦት ዬ7 መንፈስ ከራሱ ማንፌስቶ ውጪ አማራን ያቀርባል ተብሎ አይታሰብም። አማራ እና ትግሬ መግዛት ይባቃቸዋል ከእንግዲህ ተራው የሌላ ነው ብሎ እኮ የተነሳ ድርጀት ነው። ዘመን እንዲያስተምረው ብመኝም በዬዕለቱ የማዬው ነገር ታጥቦ ጭቃ ነው። 

በራሱ ሃሳብ መቆም የተሳነው በቃናው መዝለቅ ያቀተው፤ በተከበረው ቁመና ልናገኘው ያልቻልነው ድርጅት ነው ግንቦት 7።  … ትንሳኤነቱ አክትሞ አሁን ካከተመ ድርጅት ጋር ነፍስን ማንጠላጠል የአስተሳሰብ ድህንት ነው። ይልቅ አሁን ቅንጀት ሲፈጠር ድረስለን፤ ግንቦት 7 ሲታሰብ ድረስልን ተባለው መንፈስ አገር አድን ሲፈጠር ድረስልን ሳይባል ከፍረስቱ ማግሥት ዕድሜ ለአብይ መንፈስ የነፍስ ማደሪያነት የግንቦት 7 አዕምሮ መልሶለታል … የእሱ አለመኖር ነበር ይህን መሰል ትርምስ የተፈጠረው። አቅምን አውቆ መመጠን፤ ቢሆንስ ብሎ ማሰብ ይገባ ነበር። አገርን ያህል መሪ ለመሆን … 

ዛሬ ቢታለፍ እያንዳንዱ ሰከንድ ፈተና ይዞ ስለሚመጣ ለዛ ብቃትን ሳይመጥኑ አውራነትን ማሰብ አውደደቁ የከፋ ነው … የታዬውም ይሄው ነው። ስልትም ቢቀያዬር ልብ ተሸልሞ ስለታዬ ትእግስት ሲያልቅ ፍቅር ይሰደዳል ተብሎ ስንበቱ ባጀ ... አሁን ተመሰረትን ስትሉ እነ አብን በጠራ መስመር ካለሆነ ጎንደር መታረጃ አይሆንም ...  ይሄን እንድታውቁት።

„ልብ ያለው ሸብ!“

ቅኖቹ ሚዛኖቹ የጡሁፌ ታዳሚዎች ዕለቱ በኑሩልኝ መሪነት በዚህው ይጠናቀቅ።


አክብሪያችሁ። መሸቢያ ጊዜ።   

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።