ፍቅር ቁጥር አይደለም።

          የፍቅር ተፈጥሯዊ መርህ
               ቁጥር አይደለም።
                                         ከሥርጉተ ሥላሴ 03.06.2018 (ከገዳማዊቷ ሲዊዘርላንድ።)
                       „የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሄርን መፍራት ነው። ሰነፎች ግን ጥበብን ተግሳጽን ይንቃሉ።“
                                        (መጽሐፈ ምሳሌ ምዕራፍ ምዕራፍ ፩ ቁጥር ፯)

ፍቅር ቁጥር አይደለም፤ አንድ ሁለት ሦስት እዬተባለ በጥቁር ሰሌዳ ላይ በጠመኔ የሚጻፍ። ፍቅር መስፈሪያ የለውም። ፍቅር ዳርቻ ዲካ የለውም። ፍቅር ስፋት እና ቁመት የለውም። ፍቅር ቅርጽም ፎርምም ሊወጣለት አይችልም። ፍቅር አልፋ እና ኦሜጋ ነው። ፍቅር ነፍስ ነው። ፍቅር ደም ነው አብሮ የተፈጠረ። አብሮ የሚኖር። ልባም ከሆንክ ለትውልድ የምታወርሰው ቋሚ ቅርስ ነው። ትውልድንም የምታስቀጥልጥበት የህሊና ርስት ነው። ፍቅር ደም ነው። ቀዝቃዛም ለብ ያለም ሳይሆን ሙቀቱንም ቅዝቃዜውንም ለመለካት መሳሪያ ያልተሰራለት አንተም እራስህ የማታውቀው፤ ደረጃውን መመዘን መስፈር መመትር የማትችለው።

ነገር ግን ፍቅር ተቀብሮ የኖረ የሚያሳዝን ብቻ ሳይሆን ሳንጠቀምበት በመቅርታችን፤  እራሳችን ስናጠፋበት የኖርንበት የረቂቅ ሚስጢራት ቅምር ውጤት ሆኖ በተቃራኒው፤ ባልሆነ መንገድ ነው እትጌ ዓለም መጪ ስትል  የኖረችው።

ወደ ሰው ሰብዕና ስንመጣ አንድ ሰው በልቡ ያለውን፤ ከደሙ ውስጥ ያለውን የፍቅር ተፈጥሮ የማያውቅ ፍጡር ከሆነ፤ አውጥቶ ለመጠቀም የማይተጋ ሰው ከሆነ የነቃው ህሊና ድፍን የሆነበት ሰው ነው። ይህም ብቻ ሳይሆን ከሰዋዊ ተፈጥሮ አውሬያዊ ተፈጥሮ የተጫነው ነው።

ፍቅር ደምነቱ ለመጠቀም ፈቃድ ሲኖር ብቻ ነው ደማም የሚያደርገው፤ በስተቀር ገጽ እራሱ ውሃ ሲሄድበት የከረመ አለት ነው የሚመስለው። ወይንም የተላመጠ አገዳ። ፍቅር ለሁሉም እኩል የተሰጠው ጸጋ ቢሆንም ተጠቃሚዎች ግን እጅግ አናሳዎች ናቸው። ለዚህም ነው ዓለማችን ወደ ጉማዊ ቀለም እዬተቀዬረች አስፈሪ እና አስደንጋጭ እዬሆነች የመጣችው።

ዓለምን ወደ ብርሃማነት ለመለወጥ ራሷ ዓለም ያላት አማራጭ አንድ ብቻ ነው። እሱም በዓለም አቀፍ ደረጃ ፍቅርን እንደ አንድ መደበኛ የትምህርት ዓይነት ዕውቅና መስጠት ነው። ይህ እስከ አልሆነ ድረስ በዬዘመኑ በሚፈጠሩ - ሰብአዊ እና - ተፈጥሯዊ ክስተቶች ከአሁንም በባሳ ሁኔታ ዓለም ወደ ጨለማ የምታዘነብልበት መንገድ ክፍት ይሆናል።

በተለይ አሁን የሰው ልጅ ከሰው እና ከሰው ግንኙነት ይልቅ ከስልክ ከኢንተርኔት ጋር ያለው ግንኙነት እጅግ በሚያስፈራ ደረጃ እያደገ ነው። የዲጅታል ዓለም ሥልጣኔው ድንቅ ቢሆንም የሰው እና የሰውን ግንኙነት ግን በእጅጉ እዬቀነሰው ነው። በአንድ አውቶብስ ውስጥ 30 ተጓዦች ቢኖሩ አብዛኞቹ የሚጫወቱት ከቴሌፎናቸው ጋር ብቻ ነው።

በዚህ አግባብ የቤተሰብ እሴትም እዬቀነሰ መምጣቱ አይቀሬ ነው። ሰው ማሽን አፍቃሪም አምላኪም እዬሆነ ነው። ካለ ስልክ መኖር ዛሬ ሰው አይችልም። አንድ ሳምንት ሁሉም ኔት ቢቆም ብዙ ሰው ሆስፒታል ይገባል።

እርግጥ ነው እነዚህ በዓለም የሚታዩ ጉዳዮችን የሚያመጣጥኑ የፍቅር ዕውነተኛ ሰዎች ቢኖሩም በቁጥራቸው ጥቂት ከመሆናቸው በላይ የተደራጀ የመሰባሰቢያ ጋላሪ አልባ በተበተነ ሁኔታ ላይ ነው ያሉት።

ስለሆነም ይህን የአስፈሪውን የዓለም ጉዞ ለመመከት ይቸግራል። ከባድም ነው። የፍቅር ተፈጥሮ ምርምር የሚደረግበት አንድም ስልት ዓለም የሌላት በመሆኑም መጪው ጊዜ እጅግ አስፈሪ ነው።

ስለዚህም ዓለም የፍቅር ተፈጥሮ የምርምር ማዕከል በማደራጀት እና በመምራት ወሳኝ እርምጃዎችን መውስድ ይጠበቅባታል።

ዓለም የፍቅርን ተፈጥሮ መርሆዎች የምታሰለጥነበት አንድም ተቋም የላትም። አብራ የምትመክርበት ፎርም የላትም። አብራ የምትወያይበት ማህበር የላትም። የፍቅር ተፈጥሮ መርሆዎች ዓለም አጀንዳዋ አይደለም። ሆኖም አያውቅም።

በፍቅር ተፈጥሮ መርሆዎች ላይ ያተኮሩ፤ ሰብሰባዎች፤ ሰሚናሮች፤ ወርክ ሾፖች፤ ፓናል ዴስከሺኖች ዓለም የላትም። ምድረ በዳ ናት ዓለም። ዓለም ዓይኗን ጨፍና ነው የምትሄደው። እንዲያውም ለእኔ ዓለም ከወገብ በታች ያለች አንገትም ጭንቅላትም የሌላት ምስል ብቻ ሆና ከላይም ከታችም ተቆምጣ ነው የምትታዬኝ።
  • ·       እንደዚህ።

የዓለም ምድር በዳነት ራሱ መሪ አልባነት ነው። የፍቅር ተፈጥሮ በተለምዶ እንጂ እንደ ሙያ ዕውቅና አላገኝም፤ ተቀባይነት አላገኝም። በቂ ሽፋን አላገኝም። ጤናው አልተጠበቀለትም። 

ስለሆነም ዓለም ጭንቅላት የሌላት ብቻም ሳትሆን ከወገብ በታች ወርችም እግርም የሌላት ፕላኔት ናት።
የፍቅር ተፈጥሮ የሚማሩት፤ የሚመረቁበት፤ የሚፈላስፉበት፤ የሚመራመሩበት ሆኖ ሳለ ግን ዓለም ዓይኗን ጨፍና ትጓዛለች። ስለዚህ የዓለም ውበት ለእኔ ተቀብሮ ነው ያለው። ስለምን? ዓለም ከፍቅር ተፈጥሮ ልታገኝ የሚገባትን ንጥረ ነገር ዕውቅና ስላልሰጠችው። ስላለከበረችው። ሰላሙ እንዲጠበቅ ስላልተጋችለት። 

ዓለም ለፍቅር ተፈጥሮ መርህ ፊቷን አዙረበታለች። የመኖር ጠቅላይ አዛዥ ጄኒራሉ የፍቅር ተፈጥሮ እና መርሁ ሆኖ ሳለ፤ ነገር ግን ዓለም ልግጫ ላይ ነው ያለችው።
እቴጌ ዓለም ከአክራሪነት ጋር የምታጠፈውን ጊዜ፤ መዋዕለ ንዋይ እና መንፈሳዊ ሃብት ጭንቅላትን ለመቀዬር በሚያስችል ሁኔታ ብታፈስበት ምንኛ ጥሩ በነበር። 

አትከላከል ማለቴ አይደለም። እዬተከላከለችም ቢያንስ በስካይፒ እንኳን ስለምን ለማወያዬት አትፈቅድም ከጭካኔ መሪዎች ጋር። ምን ይቀርባታል። ሶርያ እኮ ፈርሳለች። ናይጀሪያም፤ አፍጋንም እንዲሁ። ዘላቂውን መፍትሄ የሚያመጣው ተተኪውን በሰዋዊ በተፈጥራዊ ፍቅር ለማነጽ ሥራ መጀመር ሲቻል ብቻ ነው።

ትናንት ይሄ ስላልተሰራ ጭካኔ ዓለምን አስፈራት። ዓለም ጨካኞች እንዳይኖሩ ከፈለገች ቢያንስ ለቀጣዩ ትውልድ በፍቅር ተፈጥሮ ላይ የተጋ ተግባር መጀመር አለባት።
ስለሆነም ዓለም ስለፍቅር ተፈጥሮ የትምህርት መማሪያ መሳሪያዎችን Curriclum Guidelines፤ የሥርዓተ ትምህርት መመሪያዎችን አሰናድታ ለመምህራኑም የማስለጠኛ ተቋም ከፍት፤ የታላቁን የሰላም ሙሴ ፍቅር ተልዕኮውን ይወጣ ዘንድ መቁረጥ ይኖርበታል። ይህን ብትፈጽም እንደተናፈቀች እንደ ተወደደች መኖር ትችላለች።  ለዓለም ከሰው ቁጥጥር የሆኑ የተፈጥሮ አዳጋዎች ይበቋታል እኮ።

አሁን እኮ በሚያሰፈራ ሁኔታ እራሳቸውን የሚያጠፉ ሰዎች በርክተዋል። እንሙት ለሚሉትም ህጋዊ ድርጅት አለ። „መሄድ ለሚፈልጉ አንክለክልም“ የሚል። እዚህ ሲዊዝ አለ። በፎቶውን ሳዬው በጣም ጭር ያለ የሞት መቃብር ያህል የሚከብድ ነው።
አንዲት ቋንቋ ት/ ቤት ያገኘሁዋት ጓደኛዬ አሜሪካ ተወልዳ ያደገች ሲዊዝ ለመኖር ወስና ት/ ቤት አገኘኋዋት። 

እንደ እኛ ጀርመንኛ ፊደል እዬቆጠረች፤ ተዛ ለተከታታይ ቀናት ቀረች እና ምን ሆነሽ ነው የቀረሽው ስላት „አጎቴን ልሰነባት ነው፤ ትንሽ ጊዜ ልስጠው ብዬ ነው አለችኝ።“ የት ልሄዱ ስላት „ልጅም፤ ሚስትም የለውም ወደ ሞት እሄዳሁኝ ብሎ አመለከተ ሂደቱን አጠናቀቀ ዛሬ ይሞታል። ከሰሞኑ ቀብሩ ይኖራል“ አለችኝ። ደስ ብሎት ስለሚሄድ አላለቀስኩኝም አለችኝ። አሁን ከዚህ ላይ ሞትም ደስታ ሆነ ማለት ነው። ያስፈራል። ያን ቀን መተኛት ሁሉ አልቻልኩም ነበር። 
  
ወደ ቀደመው ምለስት ሲሆን --- እኔ ፍቅር ስል የሁለት ተቃራኒ ጾታዊ ግንኙነት አይደለም። ሙሉ ስብዕናን የሚቀርጽ በተፈጥሯዊነት መንፈስ ውስጥ ያለ ሰዋዊነትን ሙሉዑ የሚያደርግ ማለቴ ነው። የተፈጠረ ነገር ሁሉ ፍቅር እንዲያመነጭ የፍቅር ታታሪ እንዲሆን ከማሳናዳት ጀምሮ ያለውን ሁሉ ያካታል።

ለሰው ልጅ ደስታ ሊሰጡ የተፈጠሩት ሁሉ ፍቅር ናቸው። ተራሮች ፍቅር ናቸው። ወንዞች ፍቅር ናቸው። የሰው ልጅ ፍቅር ነው። እንሳሳት ፍቅር ናቸው፤ የዛፎች ውዝዋዜ ፍቅር ነው። ብሄራዊነት ፍቅር ነው፤ ቀንና ሌሊት ፍቅር ናቸው። መኖር ፍቅር ነው። መተንፈስም ፍቅር ነው። ወቅታት ፍቅር ናቸው። ዘመናት ፍቅር ናቸው። ልጆች ፍቅር ናቸው። ጤናም ፍቅር ነው። ማመስገንም ፍቅር ነው። መመስገንም ፍቅር ነው። ስጦታ መስጠትም ፍቅር ነው። ስጦታ መቀበልም ፍቅር ነው። መታመንም ፍቅር ነው፤ መታመንን መቀበል ፍቅር ነው። ተስፋም ፍቅር ነው። ተስፋ ማድረግም ፍቅር ነው። አይ ፍቅር ነው ይሁንም ፍቅር ነው። እሺም ፍቅር ነው እንብኝም ፍቅር ነው። ማዬትም ፍቅር ነው። ማድመጥም ፍቅር ነው። መታዬትም ፍቅር ነው። መደመጥም ፍቅር ነው። መናገርም ፍቅር ነው። ማናገርም ፍቅር ነው።

በፍቅር ተፈጥሮ ውስጥ ሰላም ብቻ ነው የሚገኘው። በፍቅር ተፈጥሮ ውስጥ መረጋጋት ብቻ ነው ያለው። ፍቅር ባህታዊ ነው። በብትህና ጸጥታው ለሌላው ስለመጨነቅ፤ ስለማሰብ፤ ሃዘን ደስታውን ስለመጋራት ይታሳባል። የፍቅር ሰው አንዲት ድንቢጥ ሞታ መንገድ ላይ ቢያገኛት አንስቶ ይቀብራታል። ፍቅር ስለ ሰው ፈገግታ፤ ሳቅ እና ነፃነት መጠበብ የተፈጠረበት ነው።  

ፈጣሪ አምላክ የሰጠንን ታላቅ የመኖር ጸጋ ወደ ተግባር እንቀይረው ዘንድ ይርዳን አሜን።

ልዑል እግዚአብሄር እናት አገራችን ኢትዮጵያን ይጠብቅልን። አሜን።

Seregute Selassie YouTube
Kenebete ቀንበጥ

ኑሩልኝ የልቦቼ ሥርጉተ© ሥላሴ።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።