ነገ ቀጥ ብሎ ቆሞ የተጠረገ ልብን ከሊቃናት ይጠብቃል!

መኖርን ለማሰብ መሆንን መቀበል።
„ጎለመስሁ አረጀሁም፤ ጻድቅ ሲጣል
ዘሩም እህል ሲለምን አላዬሁም።“
መዝምሩ ዳዊት ፴፮ ቁጥር ፳፭
ከሥርጉተ©ሥላሴ
 26.11.2018
 ከጭምቷ ሲዊዘርላንድ።

ኑርልን አሜኑ! ክፉ አይንካብን ተስፋችን! አሜን!

·      ቅድመ ዕሳቤ።

መኖር በነፃነት ልክ ይለካል። መለካትም በመኖር ልክ ይለካል። ነፃነትም በመኖር ልክ ይለካል። ነፃነት የአራት ፊደል ቅምረት ቢሆንም የሰው ልጅ መፈጠርን የሚገልጽ ታላቅ ቁምነገር ነው። የሰው ልጅ የተፈጠረው ለነፃነት ነው።

የሰውን ልጅ የፈጠረውም ነጻነት ነው። ሰውነት እራሱ ነፃነት ነው። ስለሆነም የሰው ልጅ የተፈጠረበትን ነፃነቱን ሊጠብቅ ነው የተፈጠረው። የሰው ልጅ የተፈጠረውም ነፃነቱን ሊኖርበት ነው የተፈጠረለት። የሰው ልጅ የተፈጠረበት ምክንያትም በመፈጠር ነፃነት ነው። እግዚአብሄር አምላካችን የነፃነትም ፈጣሪም ንጉሥም ነው። ጌታ ቢባል ነፃነት የሰጠን የፈጠረልን እሱ ብቻ ነው ጌታ።

ምድርም ለነፃነት የተፈጠረች ናት። ህዋም ለፃነት የተፈጠረ ነው። ተፍጥሮም ለነፃነት የተፈጠረ ነው። ጠባቂ ወታደራቸው ደግሞ ፍቅር ነው። ፍቅር የአግዚአብሄር  አካል የሌለው የቃሉ አገልጋይ የመንፈስ ድርጁ ሠራዊት ነው። ወልጋዳን መንፈስን የሚጋራ፤ የሚሞረድ። ሸካራውን አለስልሶ፤ ኮረኮንቹን የሚጠርግ። 

ፍቅር ነፃነት ካገኜ ነፃነት ህልው ይሆናል። ነፃነት ህልው ከሆን ፍቅር ህልው ይሆናል። ሁለቱ በአንድ ሲዳመሩ ሰላምን ለዛውም የውስጥን ይፈጥራሉ። ሰላም ሰው ሰራሽ አይደለም። መዳህኒታችን እዬሱስ ክርስቶት የምድር ተልዕኮውን የመጨረሱ ዋዜማው የውስጡን ሰላም ትቶልን ስለመሄዱ አብስሮናል።

የውስጥን ሰላም የተሰጠንን ስጦታ የምናውከው ደግሞ እኛው እራሳችን ነን። ነፃነቱን በመንሳት። ሰላም አገር፤ ቀዬ መንደር ውላ እንዳታድር አዋኪዮዋቿ እኛው እራሳችን ነን። ስለምን? የፍቅር ተፈጥሮ ሆነ የነፃነት ሥጦታን ስለማናውቅበት። በትርጉም ሲቃና ጥበበ ቢስ ስለሆን። የከንቱነት ጃንደራባ ስለሆን።

·      ስጠት።

ነገ ጠ/ሚር አብይ አህመድ ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ገጥ ለገጥ እንደሚወያዩ አዳምጫለሁኝ። ሸጋ ነው። ሸጋነቱ ግን የልብ ለልብ ሃዲዱ ነፃነቱ የትኑን ያህል ይሆን ነው መሰረታዊ ጉዳዩ። የተጠረገ ልብስ ተዬት ይሸመት ይሆናው ጉዳዩ። ነፃነት በመስጠት እና ነፃነትን በማወቅ እረገድ የሰፋ ልዩነት መሬት ላይ ስላለ። ከሳሹም ተከሳሽ ነው፤ ተከሳሹም ከሳሽ ነው። ሁለቱን የሚያገናኝ መስመር ነገ ለመሥራት ነው አጤው ቅንነት ብሄራዊ ጥሪውን የላከው። ስምነቱ ህሊናዊ ከሆነ እስዬው ነው። ስለምን? መኖርን ለማሰብ መሆንን መቀበል በኢትዮጵያ ፖለቲካ ጋዳ ስለሆነ።

አሁን ወለጋ ትናጣለች አሉ በአቶ በቀለ ገርባ እና በልጅ ጃዋር መሃመድ፤ ማዕከላዊ መንግሥት ላይ ደግሞ የዘመኑ የሚዲያ ኮከብ የፖለቲካ ሳይንቲስቱ ዶር መራራ ጉዲና ወጋ ጠቀም በሆነው ጠቃጠቆ ቋንቋቸው ይነሳሉ ይወድቃሉ። ይህ ዘመን ለውጥ ማንን ደላው ቢባል እሳቸውን ነው። ማንን አስመቼ ቢባል እሳቸውን ነው። ምቾታቸው ምኞታችን የታገልንለትም ቢሆንም ግን ለነፃነት ሊሰጡት የሚጋባው ክብር ብሄራዊነቱ ላይ ስለመሆኑ ወፊቱ ትጠዬቅ?

ታች የሚያነኩር አለ፤ ላይ ደግሞ ቅኔው እና ጉሹ ተቀላቅሎ በቅይጥ መጁን ይዞ ይፈጫል። የለማ መንፈስ ህውከት እንዲንጠው፤ የለማ መንፈስ ሰላም እንዲያጣ ተግታው ተቀናጅተው እዬሠሩበት ነው። 

ለማን ያህል ታላቅ የዘመን ነባቢት የዴሞክራሲ መርህ  ፍጹም አክቲቢስት ዛሬ በግራ በቀኝ ተወጥሮ መፋነፈኛ እጥቷል። ለማን ያህል ራስን አሳልፎ ለህዝብ ይሁንታ የሰጠ ሊቀ ሙሴ መከራውን ያበሉታል በደቦ ሴራ።

ለምን? የለማ መንፈስም የፖለቲካ ሳንቲስቱን እኩያ ሙያዊ ክህሎት አለውና። ኢትዮጵያ በታሪኳ አንድ የፖለቲካ ሳይንስ ግዙፍን ብሄራዊ ችግር ለማሸገር ገድል ፈጽሟል። የራሱን ክብር እና ልዕልና መንፈሱ ለፈቀደው ፈቅዷል። ያ መንፈስም አኮራው እንጂ እጀ ሰባራ አላደረገውም። መቅኖ ያጣው የ ኦሮሞ ሊሂቃን መታመስም ድምጡ ከዚህ ከማድረግ አቅም ቅናት የመነጨ ነው። በላማው እና በ አብዩ መንፈስ ቅናት ቤቷን ሰርታለች። 

የሆነ ሆኖ ደፋር እርምጃ በሰማይ ታምራት አንድ ድንቅ እና ብርቅ ኢትዮጵያዊ መንፈስ ቢኖር ዶር ለማ መገርሳ ናቸው። ዶር ለማ መገርሳ የፖለቲካ ሳይንስ ሊቀ ሊቃውንት ሲሆኑ ማስተርሳቸውን የሠሩበት መስክ ሉላዊም ነው።

አመራራቸው ከግል ኢጎ የዳነ ሲሆን ብቃታቸው በጥበብ እና በስልት በማድረግ አቅም እና ክህሎት ነው። ይህ ሊጎረብጥ የህሊና ሪህ ሊሆን ግድ ይላል። የተሻለ፤ የመጠቀ ምድር ስትፈጥር ቁርጥማት ነው የአንጎል። የሸሩ ጥንስስ ይህ ነው። እርምጃው ብቃቱ ልቅናው የዶር ለማ መገርሳ እዮራዊ ነውና። እነሱ ቢሆኑ እከሌ ለዚህ ቦታ ብሎ መወስን ቀርቶ አያሳቡትም። ሲበቅል የታዬ አንድም አዲስ ሊሂቅ አልታዬም። ያው በዞረ ድምር ነው ሥም አይቀዬር ነገር ከዛው እንደ ኩሬ ውሃ ሃሳቡም ህልሙ በተለመደው ላይ የሚገኘው። 

የለማ መንፈስ የፖለቲካ ሳይንቲስትነቱ መሬት ላይ በ ዕውንት መንበር ሲከሰት ራዳ ሆነ፤ ንውጠት ሆነ፤ ያልተመቻቸው ኦፌኮኖች በጥዋቱ ከእስር መፈታት ማግስት እረፍት ነስቷቸው የሁለተኛ ጊዜ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ጥሰው በመሄድ የለውጡን ሞተር አከርካሪ ለመስበር ተግተው ነበር። ያን ጊዜ ነው አማራሩን በሙሉ አሽመድምደውት ወለጋ ላይ  የመጡት። የዝና ሽሚያ ነበር ያጣደፋቸው እንጂ እንቆምለታለን የሚሉት የ75 ሺህ በላይ ወገን አልበረም። 

ሙለውን አቅም መተርተር ባይቻላቸውም፤ ባይሳካላቸውም ያገቱት መንፈስ ግን አለ። ነፃነቱን የቀሙት ወገን ግን አለ። አሁን ትግሉ በዚህ የለውጥ ሂደት ቁንጮውን ለመዘወር ህልም ነው ኦሮምያን እያመሳት ያለው። አማራ መሬትም በወፍ በረር አንድ ተደላድሎ የተቀመጠ መንፈስ አለላቸው። ቤተኛ ነው የዚህ ትርምስስምስ።

ሌላው በሚመለከት የግራኝ ግራኝ መንፈስ ደግሞ ሌላው መከራ ነው። ግራኝ ግራ ስል ርዕዮት ዓለሙን ማለቴ ነው። የዚህ ቅኝት በጎ ለማሰብ አልተፈጠረም። ትውልድን ማባከን ዋንኛው መሰረታዊው ተልዕኮ ነው። አንጋቹ በዬዘመኑ ይታጨዳል አክተሩ ደግሞ ይተውናል በዬዘመኑ የሚዲያው ባላባት ተደራዳሪ ሆኖ ይታያል። መፍጠር የለም ማብቀል የለም። 

አሁን ይህን የዘበጠ መከራ ለመግራት ነው በመሆን ውስጥ እንዲሆኑ የተፈጠሩት እነዚህ ትልቅ ጆሮ፤ ግዙፍ ልብ የፈጠረላቸው ቅኖች እዬታተሩ ያሉት። ደመቀ፤ ገዱ፤ ለማ፤ አንባቸው፤ አብይ፤ መንፈሳቸው ጻዕዳ ነው። እኔ እንደ ሥርጉተ ሥላሴ ይሳካላቸዋል ብዬ አስባለሁኝ። ስለምን? ቢባል ይህንም ያደረገው እነሱን ድንቅ መንፈስ ኖሯቸው በርቀት ቤተኛ እንድንሆን ያደረገው ሃይለ እግዚአብሄር እዮር ስለሆነ። ለእነሱም ጥበቡን ያጎናጸፋቸው የሚያምኑት አማላካቸው ስለሆነ። ፈጣሪ ከቅኖች ጋር እንጂ ጠጠር ወይንም ጎማ ልብ ካላቸው ጋር አይደለምና።

ከሦስት ቀን በፊት አንድ የእኔ ቢጤ ለአብይ መንፈስ ቀናዒ፤ የአብይን ጻእዳ መንፈስ እንደ እኔ የመሰጠው በጀርመንኛ ቋንቋ  እንደ ቀደሙት ብዕሮቹ አንድ ጹሑፍ ጀባ ብሎናል ጠ/ሚር አብይን ለአፍሪካ እንደ ፕሮስተሪካው ፈልሳፍ ጎርባቼብ እና አንደ ቀድሞው ፕ/ ባራክ ኦባማ መንፈሱን ድልድይ ሠርቶታል።

 ጀርመኖች ታላቅነታቸውን የሸለማቸው የፕሮስተሪካ ፍልስፋን መሆኑን ያከበሩታል። የኤርትራና የኢትዮጵያን ግንኙነት ከዚህ አንጻር ያዬ የጸሐፊ እድምታ ነው እኔ ሳስበው።

በሴቶች የፖለቲካ ዕውቅናም በልዩ ሁኔታ ተመስጧል - ጀርመናዊ ጸሐፊው። ምስጣውን በእዮራዊ ቀለም አቅልሞታል፤ ብሩሕ ፈጣን አዕምሮ ሰብዕና ያለው ይላቸዋል ዶር አብይ አህመድን። እጅግ የሚገርሙ እጅግም የሚመሰጥ የውስጤ የሆኑ መንፈሶቹን አጋርቶናል። ከዳካር ነው። የትም ይኑሩ ጀርመኖች ልባቸውን ለመስጠት፤ ወይንም ሊታገሉት የሚገባ ዕብለትም ሲኖርም እንዲህ ናቸው። ይህን ያህል የጀርመን ጸሐፊዎችን ልብ ያገኘ መንፈስን ተባበረን እንጣል ነው አሁን ግብግቡ። በክንብንቡም በግልቦሹም።  

David Signer, Dakar 23.11.2018
ይህ ባለህሊና ጸሐፊ አቶ ዳቢድ ሲግናር ለዚህ ቀደመም ልብን የገዙ  ጹሁፍ በአብዬ ሌጋሲ ላይ ጽፏል። ድንቁ ነገር ለጀርመንኛ  ቋንቋ ተናጋሪዎች ይህን መሰል ጠንካራ ጎልበታም እቅም ያለው ቅኔያዊ ጹሑፍ ዲፕሎማሲያዊ ትርፉ እጅግ ረቂቅ ነው። የኦሮሞ ሊሂቃን አልገባቸውም እንጂ የዓለም ቀልብ በድንበር አልባ የት እንዳለ ማዬት ስለተሳነቸው እንጂ አብይን የሚያህል ገናና መንፈስ እንዲህ በኮሽ ኮሽ ማሰናከል ፈጽሞ አያቻልም። እነሱኑ እራሳቸውን ጠልፎ ይጥላቸዋል።  

እኔ ልበ ብርሃን ለሆኑ የአገሬ የተፎካካሪ ፓርቲ መንፈሶች ሁሉ እምለው ሁሉም ቀርቶ የኦሮሞ ተፎካካሪዎችን ለጊዜው እነሱ ቁንጮ ነን ባዮች ናቸው እና እነሱኑ ተወት እንድርገው፤ በዬዘመኑ የለመዱት ነው የማሰናከል ሴራ እና ሌሎች ተፎካካሪዎች ግን ነገ ልባቸውን አጥበው፤ ንሰሃ ገብተው ወደ ስብሰባው አዳራሽ ቢገቡ ምርጫዬ ነውይታጠቡ!እነሱ የማይኖሩበት መንግሥት ለመፍጠር ነው አሁን እዬታማሰ ያለው ሂደት የሚነግረን።

በሌላ ቋንቋ ወያኔ ሃርነት ትግራይን በሙሉ አቅሙ እና መንፈሱ የሚተካ ሌላ ግዞት ነው እዬታጨ ያለው። ይህን ጊዜ ልብ ብለው ጥሞና ወስደው፤ ተደሞ አድርገው የነፃነት ነጣቂዎችን አጀንዳቸው ሳያደርጉ የአብይ ሌጋሲ ስለሚቀጠልበት ሁነት በብስለት መነጋገር ይኖርባቸዋል ብዬ አስባለሁኝ። ተመክሯቸው ይህን ማስበል ይኖርበታል ብዬ አስባለሁኝ። 

እነኝህ የሥርዎ መንግሥት ምኞቶኞች እዛ ውስጥ ሲገኙ ያው በሾላ ድፍን ነው። መሬት ላይ ደግሞ እዬታዩ ነው፤ በየደረሱበት ሁሉ ፍርሻ ነው። በዬደረሱበት ሁሉ እጅግ ሰቅጣጭ የሆኑ ብክሎች ነው ያሉት። ምን አድርጊ ተብላ እንደሆን የኦሮሞ እናት አይገባኝም። በቀን ከ600 በላይ ነፍስ የቀበረች እኮ ናት። እነሱ ትግላቸው የገበርዲን እና የከረባት ነው የለማ አብይ መንፈስ ደግሞ ሰው መሆን መቻል ነው።

በዚህ ሂደት በግርግር የወያኔን የ27 ዓመት የበላይነት በሙሉ አቅም ተረክቦ ሰጥ ለጥ ብሎ የኢትዮጵያ ህዝብ እዬተገዛ እንባውን እንዲቆጥር ነው የኦሮሞ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ምኞት እና ህልማቸው። ኦዴፓም ውስጥ ሊኖር ይችላል። ይህን ፈጣሪ ብቻ ነው የሚያውቀው። 

መቼም ዶር ለማ መገርሳን ምን መሬት እንዳበቀላቸው ይገርመኛል። ይህን ሁሉ ችለው እነሱን ክብር ጸጋ እንዲኖራቸው ደግሞ ይታጋሉ። የሚገርም ተፈጥሮ። ያሰባሰቧቸው እኮ እራሳቸው ናቸው ሌት እና ቀን ታትረው። አሁን ደግሞ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መንፈሱን ግሪደር ጠምደው ሲንዱ ውለው ያድሩላቸዋል። 

ይህ ነው አሁን እነ ሦስቱ ጥምርት የጉዞ አቅጣጫ። የጦር ጄኒራል አላቸው፤ ባለቅኔ ጄኒራል አላቸው፤ የትዕቢት ጄናራል አላቸው፤ ራሱን ጠ/ሚር አድርጎ የሾመ መሪም አላቸው። ስለዚህ ሌላው ተፎካካሪ ይህን መንፈስ ላለመጋራት የጠራ እና ቁልጭ ያለውን መንፈስ መከተል ስልቱ ስትራቴጂው ሊያደርገው ይገባል።

ይህ ማለት ምን ማለት ነው? በጥቃቅን ነገር ሆድ ሊብሰው አይገባም። ጉልህ ጉዳይ ቢሆንም ጊዜ ሰጥቶ ማዬት እና እነማንን ሊጠቅም እንደሚችል ከልብ ሆኖ ጉዳዩን በማድመጥ እለፈኝ ለጊዜው ማለት ይገባል። ምክንያቱም በጥርሳቸው የያዟት እነሱ ኢትዮጵያ ከሃሳብ በላይ ስለሆነች። ኢትዮጵያ ጥበብ ስለሆነች። ኢትዮጵያ ከዬትኛውም ጥንብር ስርክራኪ ፍላጎት በላይ ስለሆነች ነው።

ሊረሳ የማይገባው መሰረታዊ ጉዳይ ኢትዮጵያ አምላክ ያላት እና ጠበቂ ያላትም ስለመሆኑ ማመን እና መቀበል ይጠይቃል። ይህ ለውጥ በምክንያታዊ ተጋድሎ ከሆነ የአማራ ተጋድሎ ጥንካሬ ያመጣው ነው። ቀድሞም „የፈራ ይመለስ“ ብሎ ጀግንነትን የጠራ ነው የአማራ መሬት። ስለዚህ ለውጡ ለሁሉም እንጂ የተወሰነ ሊሂቅ ብቻ የሚፈነጭበት ከቶ ሊሆን አይገባም። ይህን በመንፈስ አቅም ማሸነፍ ይቻላል። ትኩረቱ በጉልሁ ምክንያታዊ በሆነው የነፃነት፤ የፍቅር እና የውስጥ ሰላም ተኮር በማድረግ።

በተረፈ አሁን ኢትዮጵያ መሪ፤ ኢትዮጵያ ሙሉ አቅም እና ክህሎት ያለው መንግሥት አላት ብሎ ማመን ቀዳሚው ነገር ነው። መንግሥት የሌለው፤ መሪ የሌለው የጃውርውያን የበቀላውያን የዳውዳውያን መንፈስ ብቻ ነው።

ስለዚህ ብልህነት የሚለካው ከዕውነቱ መነሳት ሲቻል ብቻ ነው። ዕምነቱ ግን ፌክ መሆን አይገባውም። ሚዲያ ላይ ሌላ፤ ለምዕራብውያን ሌላ፤ ለካድሬዎች ሌላ የተዥጎረጎረ ከሆነ ግን እራስን መሽርሸር ስለመሆን 
ልብ ሊባል ይገባል። አስፍስፈዋል ነጻነቱም፤ ሰላሙንም፤ ፍቅሩንም ለመቀመታ።

ትናንት አንድ ጹሑፍ ከጸሐፊ አቶ ግርማ ካሳ አንብቤያለሁኝ፤ ዶር ለማ መገርሳ አጣብቂኝ ውስጥ ስለመሆናቸው። ዶር ገዱ አንዳርጋቸውም እንሱ አለውቁትም እንጂ የጃውርውያን መንፈስ አቅም ያለው በሙሉ ቁመና አለ እዛው አማራ መሬት ላይ። አቶ ንጉሡ ጥላሁን ዓይነት ሰው አለበት። ቀላል ሰው አይደሉም።

እሳካሁን ድረስ በሰማሁት ቃለ ምልልስ ጠ/ሚር አብይ አህመድ  በሥማቸው ሲጠሩ ሰምቼ፤ አዳምጬ አላውቅም፤ በሌላ በኩል „አገሪቱ“ እንጂ „ኢትዮጵያ“ ሲሉ አዳምጬ አላውቅም። 
እርግጥ ነው በሳቸው ዕምነት እና የነበረኝ ተስፋ ሰለተሟጠጠ 
አሁን ከሆነ አላዳምጣቸውም። ምን ሊሠሩልኝ? እኔ ኢትዮጵያዊ መንፈስ እንጂ በቀን ሲሠራ ሲፈርስ ወሎ የሚያድር ባለግራጫማ ስብዕና የፌስ ቡክ አርበኛ አይደለም የአገሬ ጌጥ ብዬ አማመልከው።

የሆነ ሆኖ በቀደመው የአቶ ንጉሡ ጥላሁን ቃለ ምልልስ በዚህ ማህል ልባቸውን ህሊናቸውን መንፈሳቸውን ውስጡን ለማዬት የሚያስችሉ ፍንጮች አሉ ልብ ላለው ሰው። እርግጥ ነው አቶ ንጉሱ ጥላሁን ከወያኔ ሃርነት ትግራይ ጋር ንክኪ አላቸው ብዬ በፍጽምና አላምንም። እሳቸው አብይ አይመጥንም ከሚሉት ወገኖች ናቸው ከእነ በቀላውያን ጃዋወርውያን ወዘተ …

ስለዚህ የዶር ገዱ አንዳራጋቸው የሥራ እና የማድረግ አቅም በራሱ አንጻራዊ ነፃነት ነው ያለው፤ ቀን ምን ሌት ምን መሆኑ እሱ አንድዬ ብቻ ነው የሚያወቀው። አቶ ንጉሡ ጥላሁን ያህል ከባድ ፈተና አለባቸው ዶር ገዱ አንዳርጋቸው። አማራ ክልል የሚኖረው ህዝቡ ግን ሰማይ ከፍ ምድር ዝቅ ቢል ጃዋርውያን አይሆንም። ሲያምራቸውም ይቅር። ሱባኤው ድዋው አብይ ላይ ነው። አብይ ሰላማችን ነው ንግርቱ።

ቀድሞ ነገር መንፈስን ለማቅረብ እንኳን የሚቻል አይደለም ነገረ እሳቸው። የአቀራረብ ቀላልነት እንኳን የላቸውም። ቅልል ብሏችሁ መግባባት የሚያስችል ሰብዕና የላቸውም። ይከብዳሉ።

ይተዋወቁ አይተዋወቁ ወይንም ይጠባባቁ አይጠባበቁ አላውቅም ሁለቱ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው እና አቶ ንጉሡ ጥላሁን። ብአዴን እና አቶ ንጉሡ ጥላሁን ምን ያህል ልባዊ ህላዊ ትስስር እንዳለቸውም ወፊቱ ትጠዬቅ።
በዚህ መሰል ስብዕና የሚፈጠሩ ሰዎች በዓለም ውስጥ ጥቂት ናቸው። አዎንታዊ ከሆኑ ጠቃሚ ናቸው አሉታዊ ከሆኑ ግን እጅግ አደጋ ነው። 
እና እኔ አማራ ክልል ላይ ልቤን ጣል እማደርግበት ሁኔታ በውነቱ የለም።
ከአማራ ክልል ይልቅ ወደ ፌድራል ቢሄዱ እሳቸው የተሻለ በሆነ ነበር።

ትንሽ እራቅ ቢሉለት ለዛ አሳረኛ ህዝብ። ሳጅን በረከትን ሸኝቶ ሌላ የመርግ መንፍስ ተሸካሚ ባይሆን ባይ ነኝ። አባ ኮስተርነታቸውን አልነጥቃቸውም ስለማምንበት፤ አባ ኮስተር አቶ ንጉሡ ጥላሁን እንደ ቀላል ሰው ዬሚታዩ አይደሉም። ሊንክ ናቸው ለረቀቁ ፖለቲካዊ ውስብሰብ ኩነቶች። ግንኙነታቸው ጥልቅና ሰፊም ነው። ሁሉ ይፈልጋቸዋል ለመሻገሪያነት። ግን እሳቸው ልባቸው ለጃውርውያን 
ያደላ ነው።

ልባቸውን እንኳንስ እኛ ለሳቸውም ጋዳ ነው። አሁን እኮ ነው ዶር መራራ ጉዲናን ከመሼ፤ ጀንበር ካዘቀዘቀች እያወቅናቸው የመጣነው። ከስንት ዘመን በኋዋላ።

እርግጥ ዶር መራራ ጉዲና በቀደመው ጊዜ ምንም ዓይነት ፕሮቶኮል የማያስፈልጋቸው ቀለል ያለ ሰብዕና ነበራቸው። ቤተሰባዊ። እኔ በህይወቴ ሊሂቅ ቀለል ብሎኝ ስሞግት እሳቸው የመጀመሪያው ናቸው። አይከብዱም ነበር። እንግዲህ እኔ ባወቅኩባቸው ዘመን ነው አሁን እናቴ ሌላ ፍጹም ሌላ ሰብዕና ነው ያላቸው። ከአውሮፓ ህብረቱ ጉባኤ እድምታ ወዲህ። በለስ ከቀናቸውም ቀጣዩ ጠ/ሚር እሳቸው ይሆናሉ ነው ምን አልባት „ጠ/ሚር¡ አቶ በቀለ ገር ከፈቀዱላቸው ወይንም ጄኒራላቸው አቶ ጃዋር ከፈቀደላቸው“

በፖለቲካ ህይወት ውስጥ መኖርን ለማስብ መሆን ያስፈልጋል። ነፃነት ዕውነት ይፈልጋል? ነፃነቱ ተገኜ አሁንስ ከማነኮር ተቆጥብን? ነፃነት ሰጪ ቢኮንስ በምን ያህል ሚዛን ይሆን የሚሰጠው? ገና ከምርጫ በኋዋላ እኮ የክብርት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳ ቀጣይነት ዕጣ ወሳኞቹ እንማን እንደሆኑ እዬተነገርን ነው? ለነፃነት ታግለህ ነፃነቱ በሚያሰገኘው ፍሬ ዩዜጎችን ተስፋ ማሽመድመድ ነው የታያዘው። ስለዚህ በነፃነት ውስጥ መኖር እራሱ ከባድ ስለመሆኑ ነው እኔ እያዬሁ ያለሁት። 

ሌላው በሚሰጠው ነፃነት ልክም ላይ ቅናቱ፤ መሰናክሉ፤ ሸሩ እና ደባው ፊት ለፊት ሳይሆን ተሰውሮ እዬተከወነ ነው። እና ፍላጎታችን እና ውስጣችን አልተገናኝም። ራሱ ውስጣችን አድርሻው አይታወቅም።  
ቀን ይገናል ማታ ሲናድ ይታደራል። ከወያኔ ሃርነት ትግራይ ይልቅ አሁን የዳማ ተጨዋቾች የኦሮሞ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ሆነው ነው የማያቸው። ልባቸውነ ጠርገው መቀረብ መቼውንም የማይታሰብ ነው እዬሆነ ባለው ጭብጥ ተርጓሚነት። 

የነገ ስብሰባ የሚያስፈልገው የተጠረገ ልቦና እንጂ ገበርዲን፤ ከረባት
 እና ሳምሶናይት ወይንም የቃላት የዳማ ጨዋታ አይደለም። 
ልባምነትም፤ ሴራን አሸምድምዶ ኢትዮጵያን የ አፍሪካ ቀንዲል ማድረግ። ቃሉ ዕውነት ዕወኑቱ ኪዳን ለማድረግ ማመን፤ መወሰን፤ መቁረጥ። ባሉት ልክ መሆን። ዶር ለማ መገርሳ እኮ ባሉት ልክ ሆነዋል፤ ስልጣን በ አፍጢሙ ይደፋ አሉን አደረጉት። እሳቸውን አቻ የሚሆን ንጹህ ሊሂቅ ኢትዮጵያ ትሻላች። ሱባኤዋም ይኼው ነው።
  • የኔዎቹ ጸሐፊ ዳቢድ ከዳካር የጻፋቸውን የቀደሙ ዕይታዎቹ ይህን ይመስላሉ። ጀርመኖች የወጣላቸው ባለቅኔ ናቸው። ቋንቋቸውም 
  • ቅኔ ነው። የትርጉም አሰጣጡ እና አፈጣጠሩ እጅግ ይመስጣል፤ ችግሩ እዬተፈቀረ አይደፈሬ መሆኑ ነው። እኔን ያሸነፈኝ ቋንቋ።
Die Äthiopierinnen auf dem Vormarsch
Tauwetter zwischen Eritrea und Äthiopien
David Signer, Dakar21.6.2018, 17:28 Uhr
Der neue Ministerpräsident sorgt für frischen Wind in Addis Abeba
David Signer, Dakar 6.6.2018, 15:49 Uhr“
·      እርገት።

                              „የጻድቅ አፍ ጥበብን ያስተምራል፤
                               አንደበቱም ፍርድን ያስተምራል።“
                                መዝሙረ ዳዊት ፵፮ ቁጥር ፴

                   ኢትዮጵያዊነት ገናና ማንነት ነው!
                   ኢትዮጵያዊነት የሰላም ሥጦታ ነው!
                   ኢትዮጵያዊነት የነፃነት ጸጋ ነው!

የኔዎቹ ቅኖቹ ኑሩልኝ።
ያቻላችሁ ፌስ ቡካችሁ ላይ ሊንኩን ለጥፉልኝ።

መሸቢያ ጊዜ። 

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።