ዕውነትን መወገን ትውልድን ያንጻል። ለእውነት ቀጠሮ አያስፍልጋትም!

ቋንጣ።
„ምን እንኳን በለስም ባታፈራ፤ በወይን ሐረግ ፍሬ ባይገኝ፤
የወይራ ሥራ ቢጎድል፤ እርሾችም መብልን ባይሰጡ በጐችም
 ከበረት ቢጠፉ፤ ላሞችም በጋጥ ውስጥ ባይገኙ እኔ ግን
 በእግዚአብሄር ደስ ይለኛል፤ መዳድኃኒቴ አምላክ ሐሤት
 አደርጋለሁ።“
ትንቢተ ዕንባቆም ምዕራፍ ፫ ከቁጥር ፲፯ እስከ ፲፰

ከሥርጉተ©ሥላሴ
 28.11.2018
ከገዳማዊቷ ሲወዘርላንድ።




·      ፍታ።

ሴት ልጅ ሁነኛ ክንድ ሳይኖራት ፖለቲካ ውስጥ ተሳትፎ መጀመር እኔ ባለኝ ተመክሮ እንደ እብደት ነው እማዬው። መከራ ብቻ ሳይሆን መኖርን የሚቃማ አሳር ነው። የማ ቆጨው በራስ ውሳኔ ስለሚሆን ብቻ ነው እንጂ ነገር ሴት የፈተና ተፈጥሮ ነው ያለው። 

እንዴት አደራችሁ ዋላችሁ አመሻችሁ ውዶቼ አዱኛዎቼ። መቼም  ለኢትዮጵያ ሴቶች አዲስ ዘመን ቦግ ብሎ ብሩኽ ሆኖ ወጥቷል - ዛሬ ላይ። „ለእግዜር አይቀርበት ለሰው አይቀርበት ሰሌ ከሰራው ቤት እኛ ገባንበት“ ይላል የጎንደር ሰው ሲተርት።

ገና ተወዳድራ ብታሸነፍ ተብሎ አንዲት ነፍስ ስንት ፍዳ ተከፈለ። ስንት መከራ ታዬ። ሥሟን የሚያነሳ የሚዋሳም አሳሩን ከፍሏል፤ ዕውቅናው ተቀባይነቷ እዬጎላ ሲመጣ ይህቺ ሽንብራ ከሰነበተች ዓይነት በሴራ ደቦ ከፖለቲካ ትግል የተገለለች ቅን ነፍስ እነሆ ዛሬ  የኢትዮጵያ አሉ የሚባሉትን የፓለቲካ ድርጅቶች ሊቀ ሊቃውንታትን ጉባኤ ከጠ/ሚሩ ጀምሮ የስብሰባው መሪ ሆና ጉብ አለች። ቅብዐ ያለው ነፍስ እንዲህ ነው። የፈለገው ነገር ቢገደብ፤ አጥር ቢሰራ፤ ክትር ቢበጅ ቅብዕ ካለ አይቀሬ ነው። ቅኖችም እንዲህ ሲገኙ መገናኛውን በቅኔ ዘጉባኤ ይቃኙታል እንዲህ ... 

አሁን የዛሬ ዓመቱን ጉግስ ላሰበ ሰው ዛሬ የክብርት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳን የሊቀ ሊቃናትን ጉባኤ ሰብሳቢ ሆኗ ሲያ ምን ይል? ራሱ ፈጣሪ መሬት ወርዶ የሠራው ነው እኮ። በተለዬ የብረት መዝጊያ የሆነ ዘመድ፤ የብረት መዝጊያ የሆነ ማኒፌስቶ ጥግ የሚሆንለት፤ ብረት መዝጊያ የሆነ የማያስነካ የሚዲያ ደጅን ለሌለው ነፍስ ለዛውም ለሴት ፖለቲከኛ፤ አለኝ የሚለው ሁነኛ ባለቤት ለሌው አቅም እንዲህ መዳህኒአለም በጥበቡ የሠራው ታምር እንሆ በምድሪቱ ተገለጠ። 
ደስ ብሎናል ደስ ይበላችሁ ባለቤት የሌላችሁ ዜጎች በሙሉ። 
ለዚህ ነው ባለፈው ዓመት ሽንጣችን ገትረን የሸሩን ጣሻ እዬጣስን
 ማስበልም ቡቃያ ማዬትም የማያወቀውን የኢትዮጵያ ባህል ጋር ፊት ለፊት ወጥተን የሞገትነው። እንዲህ ዘመኑ በታምራቱ ይመራ ዘንደስ ስላለመን። 

·      ሬን ሲንቃኘው።

ዛሬ ይህን ጹሑፍ ለመጻፍ ያነሳሳኝ ሊንኩ ይሄ ነው። http://www.zehabesha.com/amharic/archives/92670#comments
የብርቱኳን ዉለታ አለብን
November 22, 2018 
ጋዜጠኛ ሳዲቅ አህመድ የብርቱካን ውለታ አለብን ሲል የጣፈው አጭር ማስታወሻ እንደ ኤ.አ. በ22.11.2018 ዘሃበሻ ላይ ተለጥፎ አንብቤዋለሁኝ። ጉዳዬ ከዚኸው ጹሑፍም ላይ ነው። መቼ ነው ውለታው የሚወዳደረው ዛሬ በተሾመች ማግስት ወይንስ ትናንት?የሆነ ሁኖ ውዶቼ መሰል ገጠመኝንም ተያያዥ ጉዳዮችንም እግረ መንገዴን አነሳለሁኝ ዛሬ። 

እስከ ዛሬ የት ነበር ነው የደሞው ቁም ነገሩ። ይህን የማድረግ አቅሟን በይፋ በአደባባይ ልታሳይበት ከምትችልበት ደረጃ ባትደርስ ኖሮ ላይነግረን ላንሰማው፤ አንገቱን እንደደፋ ሊቀር ነበርን? 

እሷ ባትፈቅደው እንኳን ሌላው ይቅርና ጠ/ሚር አብይ አህመድ ሰሜን አሜሪካ ላይ ሲገኙ እሷም በስብሰባው እንደታደመች እና „የፖለቲካ ነጋዴ“ አለመሆኗን አበክረው ገልጠው ነበር። ፎቷውም ከዶር ለማ መገርሳ እና ከዶር አብይ አህመድ ጋር አብሮ ወጥቶ አይቸዋለሁኝ። ማጠናከሪያ ምስክርነት መሰጠት ከመሼም ቢሆን ያን ሰሞንም ይቻል ነበር። 
ቢያንስ ከስሜን አሜሪካኑ የጠ/ሚር አብይ ልዑክ ጉዞ ከዚያ በኋዋላ እንኳን ይህን ውለታዋን ለመግለጽ ምን ብዕሩ ላይ ካቴና ተተበተበበት። በቃ እንደተከደነች ብትቀር ተከድኖ ሊቀር ነበርን ያደረገችው ቀና ተግባር? በዛ ወጀቡ ባዬለበት እንደዛሬ ሳይሰክን በሉላዊ ዓለም እስላማዊ አክራሪነት በተፋፋመበት ወቅት ነበር ድምጻችን ይሰማ ንቅናቄውን አህዱ ያለው። ፈታኝ ጊዜም ነበር።

ድርብ ንብርብር ፈተና እና ተጋድሎ ነበረበት፤ የአቅም መቅኖ ይሻም ነበር። ለፖለቲካ ትርፋ ትርፍ ሳይሆን እንደ ዜጋ ሁሉም የድርሻውን መወጣት፤ አይዟችሁ ሊለው የሚገባበት ወቅት ነበር።

ዓለም እራሱ ወያኔ ሃርነት ንቅናቄውን የከሰሰበትን መሰረታዊ አምክንዮ ችል ሊለው ባለመቻሉ ነበር ጉዳዩ በታቀደ ሁኔታ ተጠንቶ ነጣነቱ የተቀዳጀው ንቅናቄው። እና ለዚህ ጊዜ አይዟችሁ ያለች እህት ለዛውም አንስት ሊቅ እንዴት እንዲህ እንደ አልባሌ ቋንጣው ዛሬ ይነገረናል? አዝናለሁኝ።

በሌላ በኩልም የሚያስፈራ ምንም ነገር አልነበረም። ወላጅ እናቷ 
ወ/ሮ አልማዝ እራሱ ሁለት ጊዜ አሜሪካ ተጉዘው ልጃቸውን እንዳዩ ከአንደበታቸው ሰምቻለሁኝ። ግንኙነቱ ከነበረም መረጃው ይኖራል ብዬም አስባለሁኝ። ስለዚህ ዕውነቱ በጊዜው ቢነገር ሊያመጣ 
የሚችለው ለነጻነት ትግሉ አቅም እና ጉልበት ነው። 

እርግጥ ነው የሴራ ፖለቲካ መከራ ግዞት ነውና ወከባም በግራ በቀኝ ቢኖርም እሷ ውጪ አገር ነው የምትኖረው፤ የምትሠራበት ድርጅት ሆነ ያላት ሉላዊ ዕውቅና ጥበቃውም አለ። ተማላ ሰው አይደለችም እንደ ሌላው ያገኘ እርግጥ ጭፍልቅልቅ የሚያደርጋት።

ስለዚህ ጋዜጠኛ ሳዲቅ አህመድ ምን ነክቶት ነው ድርጊቱን በፈጸመች ጊዜ የተደራጀ ሚዲያ ያለው አካል ሆኖ ሳለ ስለምን ልዩ ዘገባ ሰርቶ አላስደመጠነም ነበር? ሞጋች እኮ ይሆን ነበር ያ ቅን ነፍስ አደባባይ መልካምነቱ ቢገለጥ ይፋ ቢሆን ኖሮ።

መንገድ ሳት አድርገው ይጠራጠሩ የነበሩ ወገኖችንም ቅጥ ያስይዝ 
ነበር። ጉዳዩ እኮ ጋዜጠኞችን ሁሉ ፈትኖ ነበር እኮ። ስላለፈ ቀላል
ነውን? ስላልተናገርነው ቀላል ነበርን? እኔ እራሱ ስንት ዓይነት ፈተና አስተናግጀበታለሁኝ "እኔ ድምጻችን ይሰማ ነኝ" ብዬ ስለወጣሁኝ፤ ማንፌስቶዬ የተግባር አቅም እንዲኖረው አልነበረም እንደዛ ደፍሬ የወጣሁት። ማንፌስቶ የፖለቲካ ድርጅት ቀርቶ የምንም ማህበር አባል አልነበርኩኝም። ነገር ግን እኔኑ የሚመስለው የነጻነት ዕጦተኛ ነፃነት ስለጠዬቀ ስለምን እንግልት እስር ስደት ይገጥመዋል ነበር ጉዳዩ።
   
የኢትዮጵያ ህዝብ እኮ ተስፋው እኛው ነው የነበርነው። አገር ቤት
ያሉት ተቃዋሚ የሚባሉት በራሳቸውም ድክመት፤ በሳጅን በረከት ስሞኦን የተደራጀ እና የተቀነባበረ የደህንነት መረብም የፈረሱት ፈርሰዋል፤ አንዳዶችም መንፈሳቸው የተዘረፈው ተዘርፈው በእንሱ 
ልክ ተመትረው የእነሱ ጋሼ ጃግሬ ሆነዋል። በካድሬነት የተሰማሩትም ባለማህያ ናቸው። አሻም ያሉትም እንደ አቶ አንዱአለም አራጌ ዓይነቶች ካቴና በልቷቸው ምን ሆነው እንደወጡ ተመልከታናል። ነፍሳቸውን የሰጡም አሉ።


 በርካቶች ተሰደዋል፤ ተጀመሩ የተባሉት ከሁለት ከሦስት ተሰንጥቀዋል፤ አቶ ሌንጮ ለታ እንዳሉት የተጽዕኖ ፈጣሪዎች ቡድን እንጂ ፓርቲ የሚባል ተስፋ የሚጣልበት አልነበረም አገር ቤት። ስለዚህ ለኢትዮጵያ ህዝብ መንፈሱ የእኛ በግልም በጋራም የምናደረገው ጥረት እጅግ ወሳኝ ነበር። ልዩ የተስፋ መቅኖ ነበር። አይዟችሁ እኮ እንዴት ቀን የሚወጣ ረቂቅ የመንፈስ ስጦታ ነው። እርግጥ ነው የሚታይ የሚጨበጥ የሚዳሰስ አይደለም። አይዟችሁ የጥንካሬ የጽናት አቅም ነበር እኮ።

ለዛውም ስሟ ገኖ የወጣው የክብርት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳ በስቃዩ መንፈስ ውስጥ የአጋርነት ተሳትፏዋ መኖር ታላቅ መጽናኛው ነበር ለንቅናቄው ሆነ ንቅናቄውን በቅንነት ለሚዩት ወገኖች፤ አንድም ምስክር ማስረጃ ሰነድም ነበር። እዚህም ውጭ ብቻችን ለምንፍጨረጨረውም ታላቅም ክንድ፤ ታላቅም ተጨማሪ ሃይል መከታም ነበር። እና ስለምን ይህ ነገር ተዳፍኖ ቆዬ?

አሁንም ተገለጠም ተዳፈነም እሷም እሷነቷን እምታስመሰክርበት ከፍ ካለ መንበር አንባ ላይ ናት። ዕድሜ ለኦሮሞ ፕሮቴስት እና አንተ እራስህ ለተመሰጥክበትት ላጎላኸው ለቀደስከው ከጎኑ ለቆምክለት ለ ጎንደር የ አማራ የህልውና ገድለኛ እና ምሩቅ ተጋድሎ። ዕድሜ ለልባሞቹ መንፈሱን በአደራ ተረከብው ከዚህ ላደረሱት አምስቱ ሐዋርያት።



አብሶ የገዱ ቡድን ቃልኪዳኑን ጠብቆ ከውጥኑ እስከ መጨረሻው እግብ እንዲደርስ የራሱን ክብር እና ዝና፤ የአማራን የህዝቡን ልቅና እና ታሪክ ለብሄራዊ ጥቅም በማዋል ለቆረጠው ጀግና፤ ዕድሜ ለአቶ ደመቀ መኮነን ከፉክክር ሳይገቡ ኢጎን ድል ነስተው መንገዱን ለቀዬሱት፤ ዕድሜ ለማስተዋል ዓይነ ህሊና። ዕድሜ ያ ቀንበጥ የተቀናጀ የለማ የገዱ መንፈስ እና ያበሰለ የተጋድሎ ቅንጅት ከግብ ይድርሳል ለሁሉም ተስፋ ይሆናል ብለው ሌት እና ቀን ለባተሉት ለተጉት ብርቱ ቅኖች።

አሁንማ ምን ገበር፤ ምን ጥላ ምን ከለላ ሲያስፈልጋት ነው ለክብርቷ?  ለእሷ ታሪክ ይጠቅም የነበረው በወቅቱ በጊዜው መረጃው ይፋ ቢሆን ነበር። እኛ እኮ ከፍቶናል ድምፆዋ በመጥፋቷ። 

ቢያንስ በዚህ መሰል ተሳትፎ እንዴት አትኖርም ብለን ስለምናስብ። እሷ በመሰረተችው ፓርቲ እኮ የታሰሩ፤ የተንገላቱ ሁለመናቸውን ያጡ ወገኖች ነበሩን። ሌት እና ቀን የሚያለቅሱ እናቶች ነበሩን። እሷን የደገፉ መንፈሷን የተቀበሉ እህቶችም ፍዳን ከፍለውበታል። መረጃው በወቅቱ ወጥቶ ቢሆን ኖሮ ያ ብልህ የሆነ የተስፋ ዋቢ ይሆን ነበር መረጃው ወቅቱን ጠብቆ ተሰጥቶን ቢሆን ኖሮ። በህይወት መኖር ብቻ ሳይሆን ማለፍም እኮ አለ።  


መቼ ነው እናመስግንሻለን መባል ያለባት ዛሬ ስትሾም? ቋንጣ! ይህ ቀን ባይመጣስ እኛም ይቅር የድምጻችን ይሰማ የዛ ድንቅ አብዮት ምዕት አርበኞችስ ህሊና ይህን ጉዳይ ሰምተው ድዋ ቢያደርጉላት ስንት ትርፍ ነበረው? ዝናብ ሲቀር እንኳን ድዋ እንዲያደርጉ  የእስልምና አቨው ይጠያቃሉ እኔ ተወልጄ ባደግኩበት በጎንደር። እኔንም የጠበቀኝ ያቆዬኝ የሼኾች / የሀጂዎች ትጋት ነው።   


የሆነ ሆኖ ወቅቱን ያለፈ መረጃ በመስጠት ረገድ ይህን መሰል ሁኔታ በአማራ ተጋድሎም ላይ ተከስቷል። የጎንደር ህብረት ለኮ/ ደመቀ ዘውዱ ገንዘብ ረዳሁኝ ብሎ አፉን ሞልቶ ደረቱን ገልብጦ ሲቦተልክ ነበር። 

ነገር ግን ገንዘቡ ለካንስ ለኮ/ደመቀ ዘውዱ አልተሰጣቸውም ነበር። ይህን ደግሞ የአማራ ህዝብ ዕንባ ጠባቂ ጋዜጠኛ እና ጸሐፊ ወጣት ሙሉቀን ተስፋው ያውቅ ነበር። እኛ ደግሞ አናውቅም ነበር ይሰጥ አይሰጥ። እራሱ ጋዜጠኛ ሙሉቀን ተስፋው ከጎንደር ህብረት ጋር እስከዚህ ድረስ ግንኙነት እንደ ነበረውም አናውቅም። ማወቁ ይጠቅም ነበር። ሚዛናዊ መሆን ስለሚያስፈልግ። 

የሆነ ሆኖ ኮ/ደመቀ ዘውዱ ይፈታሉ ተብሎ አልታሰበም ነበር መሰል
ያ የሃሰት መረጃ ሲሰራጭ፤ ያልበሉትን በሉ ተብሎ ሸፍጥ ሲሰራ ተባጀ። አሁን የተጋድሎው ፍሬ አፍርቶ ከእስር ኮነሬል ደመቀ ዘውዱ ሲለቀቁ ገማናው ወጣ። ኮ/ደመቀ ዘውዱ ሃቁን በገለጹ ማግስት የአማራ ታገድሎ አክቲቢስትና ጋዜጠኛ እንዲሁም ጸሐፊ ወጣት ሙሉቀን ተስፋው ያልተሰጣቸው ስለመሆኑ ዕውቀት እንደ ነበረው ጻፈ። ምን ያደርጋል። 

የሰይጣን ጆሮ ይደፍን እና ይህ ኮ/ አንድ ነገር ሆነው ቢሆን ኖሮ ጎንደር ህብረትም በውሸት ማምረቻው ይቀጥል ነበር፤ ኮ/ ያልበሉትን ዕዳ አጽመ ርስታቸው ተሸካሚ ትሆን ነበር፤ ነፍስም በአጸደ ገነት እንዲሁ።

ለምድነው መረጃ በወቅቱ ፍሰቱን ጠብቆ የማይሰጠው?ማን ተፈርቶ? የማን ፈቃድ ነው ይጠበቅ የነበረው? ዕውነት እኮ ወገኑ ዕውነት ብቻ ነው። ይህ ማነን ነው የሚጠቅመው ማነን ነው የሚጎዳው? ዕውነትን ነው የሚጎዳው። ዕውነት ነው የሚያለቅሰው፤ ዕውነት ነው የሚታረደው። በወቅቱ መረጃው ቢሰጥ ከብዙ የመንፈስ ድቀቶች ይዳናል። መቼም ይህ ቀን አይመጣም ብሎ ዕውነትን ማፈን ለራስም ህሊና ዕዳ ማስቀመጥ ነው።

የሆነ ሆኖ የጹሑፌ መሰረታዊ ጉዳይ መልካም የሠሩ ሰዎችን ወገኖች እናመሰግናለን ለማለት ቆጥቋጦች አንሁን። ትንሽ መንፈሳችን ዘለግ አድርግን እንሰብ። ትውልድ አለኝ የሚለው ሮል ሞዴል ሰው ያስፈልገዋል። በተለዬ ሴቶች በቀንበጣቸው ሲለሚቀነበጡ በተከታታይ በርከት አድርጎ ሊሂቃን ሴቶችን ማውጣት አልተቻለም። ቢሞከርም አሳር አበሳ ነው የሚጠመደው።

አሁን ትናንት የ80 ፓርቲዎች ውክል አካላት ስብሰባ ነበር። ምን ያህል ሴት ሊሂቃን ተሳትፈዋል? መራራ ነገር ነው። የዛሬ 20 ዓመትም ዛሬም በአንድ እግራችን እያነከስን እንራመዳለን።

ሴቶች ወደፊት ሲመጡ ይታዋቃል የተፈጥሮ አደረጆች ናቸው። ስለዚህ ሳንክ ተፈልጎ ቀብሮ መተውም ብቻ አይደለም አፈርም ተረባርቦ ማልበስ አለበት። ይህ ከሊቅ አስከደቂቅ ተመስጥሮ የተያዘ ጉዳይ ነው። በስንት ዘመን አንዲት ጥሳ የወጣች ዕለት ደግሞ የደመር / የምሾ ማዕልት ነው። የኢትዮጵያ ቀጣይ ትውልድ በተለይ ሴቶች በመላጣ ነው ያሉት። አሁን አማራ መሬት ላይ ተነሳች ወደቀች ወጣት ንግሥት ይርጋ ብቻ ናት። ስብሰባ ሳይ እሷ ብቻ ናት ያለችው። በዚህ 27 ዓመት ሴት አልተወለደንም?

ለዚህ ይሁን ነበር የብርቴ ተሳትፎ ቢገለጥ ጠቃሚ የሚሆነው። 5 ዓመት ተከዘኖ ዛሬ ስንት ወጣት ሴቶች አቅም አግኝተው ሊወጡ ሲችሉበት ጠቃሚው ተምሳሌት ሾለከ ዕድሉ። አላተረፍንበትም።

ቀን ሲያልፍ ሳይሆን ምስጋናው አብነቱ መነገር ያለበት በወቅቱ ነው
አዲስ ቡቃያ ማማረት ስለሚችል። ለሴቶች ታገዮች ባለቤት የሌላቸው ማለቴ ነው በጥቁሩ ቀን ሲማቅቁ በመከራቸው ቀን ነው ምስጋናው እሚጠቅመው የነበረው።
አይዟችሁ የሚያስፈልገው በዛ በታደፈነ ድንብልብል መከራ ውስጥ ተቀበረው እንዲኖሩ ሲፈረድባቸው ነበር። አሁንማ ባወላቸው / አናባቢያቸው ዶር አብይ አህመድ አሉላቸው። ደግነቱ ይህን አክብረህ መጻፍህ አምናን ሳስበው ለዛሬ ያደረሰ አምላኬን አመስግኘዋለሁኝ። ሂደት ነው ውጤትን የሚሳይ።

እዮባዊነት ነው ተስፋን የሚያቀበል የሚያበቅልም። ፖለቲካ የሰው ነፍስ ማደሪያ ነው ለጋህዱ ዓለም፤ ውሳኔም አቋምም መጥኖ እና ለክቶ የሚያተርፈው ላይ አቅምን ማዋልን ይሻል። ጥድፊያ ችኮላ ተስፋን መትከል እንጂ የበቀለን እውሃ እያጠጡ ማለምለም እንጂ ሳንክ መፍጠር እንደ እኛ በረቂቅ ሴራ ለተተበተበ የፖለቲካ ባህል አይሆንም። ዙሮ ዙሮ አፋኝን ያደልባል ትውልድን ያባክናል። ይህ ለውጥ ባይቀናው ተሰናክሎ ቀርቶ ቢሆን ኖሮ ዛሬን ማግኘት አይቻልም ነበር።

የሆነ ሆኖ አሁን እንደ ቀደመው እንደ ተፈጠረችበት ቅብዕባም በሯ ከፈት ባለች ጊዜማ ሁሉም ፈላጊ፤ ሁሉም አክክባሪ፤ ሁሉም ተቆርቋሪ፤ ሁሉም የ አደረ መልካም ነገርን መስካሪ ተርጓሚ  ነው። ለቅኖች ደግሞ የዘወትር ጽላታቸው ነው አቅሟ ሆነ ትትርናዋ።

ሰው በፈተና ውስጥ ሆኖ በሚያደርገው ተገድሎ ጎልቶ ሲወጣ ትውልድም የሚገናበው የሚበቅለውም እንዲህ ነው። እንደ እከሌ መሆን የሚል ትልቅ ብሂል ነበር - ትውፊት። ፈተና ነው የጠራ መስመር የሚያስዘው የሚያነጥረውም። 

መልካምነትን በወጉ በሥርዓቱ የተገባውን ቦታ ስንሰጠው ማግሥትን ለመገንባት የራስን ዕዳ አወራረድን ይባላል፤ በሌላ በኩልም እብለትን ደግሞ ያልተገባውን ክብር ስንነጠቅው ዕውነት ያፈራል፤ ሃቅ ያጸደያል። ተቀብራ መቀረቷ ፍሰሃ የሆናቸውም እውነት ስታፈልቅ ይማሩበታል። በምንም ፈተና ውስጥ ለነፃነት ያደረች ነፍስ በዬትኛውም ቀዳዳ ለተነሳችበት ጉዳይ አቅሟን ለማዋል መፈቅዷ ይመሳከር ነበር፤ ያን ጊዜ ተነግሮን ቢሆን ኖሮ። ሌላው ቀርቶ ጹሑፍ ላይ እንኳን ሥሟን ለማንሳት እኔ ሰላሟን እንዳላውከው እሳቀቅ ሁሉ ነበር። በምትችለው መትጋቷ መረጃ ኑሮኝ ቢሆን ደግሞ ከስጋት እድን ነበር። 

ሌላው እንደ ዛሬው ፌስ ቡክ አልነበረም እንጂ አንቱ የተባሉ የሴት አንበሶች ነበሯት አላዛሯ ኢትዮጵያ። አንድ ነገር እርሾ አልባ አይነሳም።  የኢትዮጵያ ሴት ሊሂቃን ዘመን አልሰጣቸው ብሎ እንጂ ሁሉንም መሆን የቻሉ፤ ሁሉንም በጥበብ ያበጁ ሙሉ እና አኩል የተጉ ግን ውክልና ቀርቶ እንደ ዜጋ የማይታዩ ትርፍ ነበሩ። 

የኸው የብርሃናት ዘኢትዮጵያን የእቴጌ ጣይቱን ሃውልት አዲስ አበባ ላይ ለማቆም ስንት ሰሃ አለበት። በስንት ሺህ አመት አንዲት ሃውልት ብርቅና ድንቅ ሆነ ይኸው በዬዘመኑ ደጅ ይጠናበታል። እነ ንግሥት ማክዳ፤ እነ እቴጌ ሰበለ ወንጌል፤ እነ እቴጌ ተዋቡ፤ እነ እቴጌ ምንትዋብ ስንት ዓለም አቀፍ ገድላትን ሰርተዋል።

በእኛ ትውልድ እንኳን የኢሠፓን ትቼ እራሴ የነበርኩበት ድርጅት ስለሆነ በኢህአፓ እንደ ጦር የምትፈራ የኢህአፓዋ አርበኛ ጽኑዋ አያልነሽ ልዩ ተስፋ ነበረች ለነጻነት ተጋድሎ። ወያኔ ሃርነት ትግራይ ስልጣን እንደያዘ በዱር በገደሉ ስታርበተብተው ነበር መውጫ መግቢያ ነስታ። 

በዚህ ታዬች በዚህ ወረደች አያልነሽ ነበር ገጠር ዜናው ሁሉ እኔም 
እዛው ጫካ ስለነበርኩኝ አጀንዳ የነበረች መሆኗን አሳምሬ አውቃለሁኝ። በልዩም አለች የካቴና እራቷ፤ አርበኛ ወ/ሮ እማዋያሽም ገድል ፈጽማለች። አርበኛ እማዋይ የቅንጅት መንፈስ የፈጠራት አይደለችም የኢሠፓ ፍሬ ናት። ምን ለማለት ነው ካለ እርሾ የሚነሳ አንዳችም የተጋድሎ መስክ የለም። ሁሉም ከቀደመ ትውፊት ትራስ ነው አህዱ የሚለው በዛ ላይ የደም ውርርሱም አለ - ትወፊቱ። በተጨማሪም እዮራዊ ጥሪም አለ።

·      ክ ውሳኔ ነው።
ሌላው ጋዜጠኛ ሳዲቅ አህመድ ያነሳው „ብርቱኳን የምርጫ ቦርድን መምራቱ ቢያንሳት እንጂ አይበዛባትምና ልብ ያለው ልብ ይበል።“ ብሎናል እኔ ደግሞ አያንሳትም  የተገባትን ቦታ ነው የተሰጣት ባይ ነኝ። ይህ ቦታ ትወልድ የሚገነባበት ልዩ የመንፈስ ቦታ ነው። የመጀመሪያው የዴሞክራሲ የውሃ ልክ መሰረት የሚጣልበት ህሊናዊ ማሳ ነው።

ይህ ቦታ የዴሞክራሲ የፊደል ገበታም ነው። ሁሉም ሀ ሁ ለሉ ሰሱ መሙ ብሎ የሚቆጥርበት። ህግ እና ሥርዓት በአላዛሯ ኢትዮጵያ መፈጠራቸው መሬት ላይ የሚፈተንበት ነው። ዕውነት ለባለ ዕውነት ቤተኞች የሚሆንበት የመስረት ድንጋይ ነው። ታላቅ ተቋም ነው። ተቋሙ ሚሊዮኖች የተሰውበት ቁልፍ ተግባር የሚከወንበት የውሃ ልክ ነው።
አሁን ባለው የዚህ ምስቅልቅል ዘመን የእርጋታ መሰረታዊው መሳሪያው ተገኝቷል ብዬ አስባለሁኝ። ረብ ብሏል አሁን ሁለመናው። ምክንያቱም በሽታው ከታወቀበት ቦታ ላይ መዳህኒት ስለተገኜ። 

የለውጡ ዓይን ኮንፓስም በተጨማሪነት ተፈጥሮላታል ከህሊናው ውስጥ። አንጎል ሳይሆን ህሊና ያለው ነፍስ እንዲህ ነው እሚያስበው እንዲህ ነው ባለው ልክም የሚገኘው። ዛሬ ለዛሬ በቂ ቦታ እና ሃላፊነት ነው። ነገ ደግሞ የራሱ ዕቅድ እና ፕላን አለው። በህልምም ያልታሰበ ቦታ እና ሃላፊነት ነው የተሰጣት። የከበረ ቦታ የሁሉም ኒዩክላይ ነው። አናት!

ይህ ቦታ ብዙ ነገሮችን አስታራቂም ነው። ቦታው እራሱ የምህረት ዓዋጅ ነጋሪ ብቻ ሳይሆን የእርቅም ሰነድ ነው። ላይ ላዩን ለማይጋልብ የነፃነት ራህብተኛ ይህ ውሳኔ የልባችን ቁልፍ ከነመፍቻው ሸልሞናል።

ለላው መጨመር ባይካፈም ዛሬ በያለው ያለው ትናንት በየለው ሳይኖረው ቢሆን የበለጠ የመንፈስ አቅም ይፈጥር ነበር። ብዙ በሰባራ ሰንጣራ ሸሮች የተገለሉ፤ የተበቱኑ፤ ብዙ ተስፋ ያጡ መንፈሶችንም ይሰበስብ ነበር ያን ጊዜ ይህ ብልህ መረጃ ቢወጣ ኑሮ። ብዙ ተስፋ የቆረጡ ነፍሶች ጤናቸውን ያጡበት ብዙ ረቂቅ ጉዳዮች አሉ።  
ብዙ ትጉሃንም ራሳቸውን ጠልተው ዘግተው የተቀመጡበት ጉዳይ ወዘተረፈ ነው።

ይህን ሳያዩ ያለፉም አሉ እንደ አንበሳው ጠሐፊ እንደ ጎመራው ያሉ ባለቅኔ፤ እንደ ትንታጉ እንደ ጋሼ ሙሉጌታ ሉሌ … እንደ ደፋሩ አቶ 
አሰፋ ጫቦ … እንደ ሰማዕቱ የኔሰው ገበሬ፤ እንደ ሰማዕቷ የሺ ብሬ ደስአለኝ፤ እንደ ሰማዕቱ አሰፋ ማሩ፤ እንደ ሰማዕቱ ፕ/ ስዩም እምሩ ስንቱ ይዘርዘር …

ዕውነት በአንድም በሌላም ቀኗ ቢረዝምም፤ ብታደክምም ተደብቃ ብታለፋም፤ አልፎ አልፎ ተጨክኖባት ብትሸፈንም ጊዜ፤ የዕውነት አምላክ በጊዜው ይገልጠዋል። ይህንም ዛሬንም ፈጣሪ አላህ አነሳስቶህ መጻፍህ መልካም ቢሆንም እጅግ የዘገዬ ነው ባይ ነኝ። ቋንጣም ነው።

ለወደፊቱ ግን መልካም ነገሮችን መቆጠቡ አያተርፍም። ማንም 
ይክፋው ማንም ደስ ይበለው፤ ማንም ይድላው ማንም ይጎርብጠው ከእውነት ጎን የቆመ ቢያንስ አምላኩ፤ አላህ ይኖርለታል። ስለሆነም ዋጋው የሚከፈለው መስዋእትነት ሳይሆን ትውልድ ፈጣሪነቱ ነው እውነትን ወግኖ ማጉላቱ የሚጠቅመው። 

ለመንፈስም አማራጭ ተስፋ ማቅረብ የጽድቅ ጉዞ ነው። ይህን የሚፈሩት፤ ይህ የሚያርዳቸው ይኖራሉ፤ ግን ትውልዱ ትውፊቱን
 በዚህ መልክ ባሊህ እንዲለው መግራት አለበት።

ምክንያቱም ድህነታች የመንፈስ ነውና። ድህነታችን ቅኖችን የመንከባከብ፤ ለቅኖች አቅም የማዋጣት አቅሙ ፍላጎቱ የለንም። 
በሌላ በኩል በመሰከርን ቁጥር እኛ የሚቀርብን የለም። ስለምን? ለእኛ ያለው እኛኑ ነውና የሚጠብቀው፤ እኛን ካለገኘ በስብሶ ይደፋል እንጂ ለማንም አይሆንም። ስለሆነም ቸርነትን በዓይነ ሙሉነት ማጋባት እንደ ጋዜጠኛ የዕውነት ወገንተኝነት መርህ ሊሆን ይገባል እንላለን ከዚህ ከኮሽ አይሏ አገር ተሲዊዚና። ቀን ቢሞላ እና ቢጎደል ለጋዜጠኛ ዕውነቱን ማውረስ ነው ህሊናው ሊሆን የሚገባው።

አብይ ለእኛም ለሴቶች አናባቢ ነው።

ክብረቶቼ ይህ ጹሁፍ ታህሳስ 26 ቀን 2017 የተጻፈ ነው። የክርሲማስ ዕለት ማለት ነው። የዛሬ ዓመት "አብይ ሰብዕናው ያልተሟላ፤ ልምድ የሌለው ተጠማኝ፤ ጀማሪ ፖለቲከኛ፤ ወያኔ የፈቀደው" ወዘተረፈ ይባልበት በነበረበት ወቅት፤ ዛሬ ደግሞ ራሱን አንግቶ ሁሉን እያፋጠጠው ይገኛል። ከተመስጌን ጋር „ልብ ያለው ሸብ“ እንበል እንደ ጎንደሮች። 

ለእውነት ቀጠሮ አያስፈልጋትም! 

ሴቶች የተፈጥሮ አደራጆች ናቸው!
የኔዎቹ ኑሩልኝ።
መሸቢያ ጊዜ።   



አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።