ከብርት ፕሬዚዳንት ሳሀለ ወርቅ ዘወዴ ትውፊት ናቸው!

መልካምነት ይበጃል።
„ወደ ደጋግ ሰዎች የሚላኩ ሪቂቃን የሆኑ መላዕከት ብርሃን ናቸው።“
መጽሐፈ መቃብያ ከልዕ ምዕራፍ ፳ ቁጥር ፲
ከሥርጉተ©ሥላሴ
04.11.2018
ከጭምቷ ሲዊዘርላንድ።

                      ዋው! የኮ/ ጎሹ ወልዴ ክብር አከበርኩት። ምኞቴም ተሳካ ተመስገን!


የጭብጤ መነሻ አሉታዊ ነገሮች አቅም ማግኘት አይገባቸውም ነው። ክፉ ነገር ይወረናል። ክፉ ነገር ይገዛናል። ክፉ ነገር ያሰተዳድረናል - ፈቅደንለት። ቀና በሆኑ ጉዳዮች ላይ እንኳን ስምምነቱ ያን ያህል ነው። ታዲያ በዬት ታልፎ መልካም ነገሮች ሥር ይኑራቸው። ፍሬስ እንዴት ያፈሩ?

መልካሞችን መልካም ለማለት ካልተደፈረ፤ መልካም ያልሆኑት መልካም አይደለም ማለት ካልቻልን ታዲያ እኛ ሰው መሆናችን ከምኑ ላይ ነው?

እውነት ለመናገር አሉታዊ ነገር ወረራው መልካሞችን እንዳናይ ሸብቦናል። መለዬት አልቻልንም። በጣም ጥሩ የሆኑ መልካም ነገሮች ይታያል ኢትዮጵያ ውስጥ። እጅግ የሚመስጡ ጥሩ ነገሮች አሉ ኢትዮጵያ ውስጥ አሉ፤ አሁን ሴቶችን የፖለቲካ ዕውቅና በመስጠት እረግድ ሉላዊ አብዮት በአብነት እዬተካሄደ ነው ልብ ላለው ልበ ህሊና ብርሃን ላለው፤ እነዚህ አቅም እንዲያገኙ፤ እንዲራቡ፤ እንዲበራከቱ መትጋት ቀርቶ ደግመን ደጋግመን ከክፉ ነገሮች ጋር ልውስውስ አድርገን ግርዶሽ ሰርተን፤ ዝንቅንቅ አድርገን መልካምነትን የተፈጠረበትን ቀን እንዲረግም እናደርገዋለን። ግን ስለምን?

የሰው መለያው እኮ ክፉ እና ደጉን የሚለይበት ህሊና ስላለው ነው። ያ ህሊናው እንኳንስ መልካም ነገሮች እያሉ ወደ መልካም ነገር የሚወስዱ ጥሩ ዜናዎች፤ ውጥኖች፤ ጅምሮች፤ ፈሎች፤ ቀንበጥ ሃሳቦች እንኳን ሲኖሩ እነዛ ሃይል ብርታት አግኝተው የመልካም ነገሮች ቤተኛ ይሁኑ ዘንድ ልናበረታት መቻል ሲገባ ክትር ሰሪዎች መሆነ ከቶ እኛ ሰው ነን ሊያስብል ይችል ይሆን?

ትውልድን በመልካም አስተሳሰብ መቀረጽ ካልተቻለ እኮ ነገ የለም። ነገ የለም ማለት እኛ ታሪካዊ ድርሻችን አልተወጣነም ማለት ነው። እኛ ታሪካዊ ድርሻችን አልተወጣነም ማለት ደግሞ በመኖር ሂደት ወስጥ ያልነበርን ነን ማለት ነው። ሰው ራሱን በራሱ ውስጥ ለመስረዝ እንደምን ይፈቅዳል?

የሰው ልጅ ማሽን አይደለም። የሰው ልጅ የሚኖርበት ዓለም ብዙ የሚጎድለው፤ ብዙ ነገር ጉድፍ ያለበት ነው። ማጣሪያው ግን የራሱ ነው። ያ ማጣሪያው ሰው ነኝ ብሎ ማመን መቻሉ ይመስለኛል። ሰው ነኝ ብሎ ካመነ ደግሞ ፕላኔታችን በመልካም ነገሮች እና መልካም ባልሆኑ ነገሮች ውስጠት የከተመች መሆኑን አምኖ መቀበል ነው። አምኖ መቀበል ብቻ በቂ አይደለም መልካም ለመሆን ከመልካም ነገሮች ጋር መሰማማትን ይጠይቃል።

የአንድ ሰው መልካምነት ለማህበረሰቡ ተቋም ነው። ሁሉ ሰው መልካም ለማስብ ቢችል ዓለም ግራጫ አትሆንም ነበር። መልካምነት አይከፈልበትም፤ ወጪ አያስወጣም፤ የራስን ሥነ - ልቦና፤ የራሰን ሥነ - ህሊና መግራት ብቻ ነው የሚያስፈልገው። ይህ ለማድረግ ጦር ማዘዣ ጣቢያ አያስፈልግም። ምክንያቱም ሰው ራሱን ማስተዳደር አቅም አለው እና።

የሚጠቅሙት፣ የሚበጁት፣ መልካም ያልሆኑ ነገሮችን አለመደገም ነው። መልካም የሆኑ ነገሮች ላይ አትኩሮትም አክብሮትም በመስጠት ፈቅዶ መልካም ነገሮችን ማራባት ነው። መልካም ያልሆ ነገሮች ተጽዕኖ ቢኖራቸውም ተጽዕኖው የዲያቢሎስ ስለመሆኑ በመገንዘብ መልካም ላልሆኑ ነገሮች ተባባሪ፤ ሰሪ፤ አደራጅ ሳይሆኑ መልካምነትን ማጉላት፤ በዛም ለመኖር መፍቀድ የራስን ህሊና ንጹህ ያደርጋል። መልካምነት ትውልድን ለመገንባትም ዋንኛው አብሪ መንገድም ነው።

አሁን የክብርት ፕሬዚዳንቷን ሹመት ፕ/ መስፍን ወ/ማርያም ተቃውመው ጽፈዋል። እኔ ብዙ የዓለም ሚዲያዎችን ተከታትያለሁኝ። የግል ሾው ሁሉ ያሉ ያላቸው በተለዬ ሁኔታ አትኩሮት ሰጥተውታል። እኒህ ጀግና ሴት ሃላፊነትን ሳይሸሹ ሕይወት የምትሰጣቸውን ፈተና ፈቅደው በመቀበል ዓለም አቀፋዊ ግደጃቸውን የተውጡ የዓለም ሴቶች እጬጌ ናቸው። የኢትዮጵያ ስለሆኑ ይህን ሁሉ ማዕት ፕሮፌሰር መስፍን አቅርበውባቸዋል።

ክብርት ፕሬዚዳንቷ ወ/ሮ ሳህለ ወርቅ ዘውዴ የሉላዊ ዓለም እምቤትን ጉዳይ ሳስብ ጠ/ሚር አንጂላ ሜርክልን አሳታወስኩኝ። በሶሻሊዝሙ ጎራ ነበር ያደጉት። ዘመናቸው በፈቀደው የፖለቲካ ሁኔታ ተሳትፈዋል። ዛሬ ዕድሉን ስላገኙ የዓለም ብቸኛዋ ገናና፤ ታዋቂ፤ እጅግ በርቱ፤ አጅግ ተወዳጅ፤ የሉላዊ ዓለም የመቻቻል እናት መሪ መሆን ችለዋል። ዓለም ከሶሻሊዝም ጎራ ተኮትኩተሽ ያድግሽ ነው ብሎ ፊት አልነሳቸውም። አክብሮት አልነፈጋቸውም። ይልቁንም ይህ ሉላዊ እውቅና አብነታቸው፤ አርያነታቸው አገራቸውን ጀርመንን ታላቅ ተደማጭ ሃያላን እና ተወዳዳሪ አገር እንድትሆን አደረገው።
  
ክብርት ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴም በዬሥርዓቱ ሙያቸው፤ ዕውቀታቸው፤ ፈቃዳቸውን ያከበረው አለም ቡሙለ ነው። እኒህ የእኛዊነት ልዕልት ሃላፊነትን እንደ ሌላው ሳይሸሹ አላዛሯ ኢትዮጵያ በጠራቻቸው ቦታ ሁሉ እዬተገኙ፤ ዕድሜያቸውን ሳያሾልኩ፤ ተመክሯቸውን ሳያስተጓጉሉ፤ ዕውቀታቸውን በተጨማሪ እና በተከታታይ ባገኙት ዕድል እያበለጸጉ ዛሬ እዚህ ደርሰዋል። በሳቸው አቅም ክህሎት ዙሪያ ሉላዊ ዓለምም የበኩሉን ድርሻ ተውጥቷል። ተጠቃሚነቱን ደግሞ ለእኛ በስጦታ አበርክቶልናል። ይህ መቼም የሰማይ ዕድልም ነው። 
  
እኒህ የተግባር እምቤት የሆኑት ሊቀ ሊሂቃን የህይወት ጥሪያቸውን ሳያደናቅፉ፤ ሳይሸሹት፤ ሳይፈሩት የተሰጣቸውን ሃላፊነት ለመወጣት በወሰዱት ቆራጥ እርምጃ በሦስቱ ሥርዓቶች ፈተናዎችን ተሻገረው፤ ተስፋ ሳይቆርጡ በጽናታቸው ውስጥ ሆኖው እዚህ ደረጃ ላይ መድረሳቸው እግዚአብሄር ምን አስቦ ነው ብሎ ማሰብ ይገባል። 

እኒህ ብጡሊት እሴታዊት አንስት ትውፊትም ናቸው። ቅብዕ የሰው ሳይሆን የፈጣሪው የልዑል እግዚአብሄር ነውና። ለዚህ ቦታ ብዙዎች ታጭተዋል። ፈቃደ እግዚአብሄር ግን የድምጽ አላባዎችን የኢትዮጵያ እናቶች ዕንባ ይታበስ ዘንድ ይህን ፈቀደ። አላዛሯ ኢትዮጵያ ከዕውቀት በላይ ናትና ሚስጢሯን ገለጠች።  

ዛሬ ለማ ጻድቁ አብይ ቅዱሱ የሚሉት ፕ/ሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም እኮ እነ ዶክተር አብይ እና ዶር ለማ እኮ መልካምነትን ስለፈቀዱ እንጂ ከወያኔ ሃርነት ጋር የሰሩ ለዛውም በደህንነት ዘፈርፍ የታታሩ ናቸው። መልካም ሲሰሩ መልካም ሰሩ ማለት፤ ክፉ ሲሰሩ ደግሞ ክፉ ሰርተዋል ብሎ መውቀስ የተገባ ነው። እኒህ ስምጥር ሴት እኮ የተባበሩት መንግስታት ሁለተኛ ሰው ናቸው። ለቀጣዩ የጸሐፊነት ቦታ ልወዳድር ቢሉ እንኳን የሚችሉ ናቸው። እኒህ ሴት ከዓለም ድንቅ ሴቶች ተርታ የተመደቡ ናቸው ተወደደም ተጠላም።

ትውፊትነታቸው ቢያሰመስግን እንጂ የሚያስወቅስ ሊሆን አይገባም። ጥንካሬያቸው ቢያስከብራቸው እንጂ እንዲህ ከፍ እና ዝቅ ሊል ባልተገባ ነበር። የመቻል አቅማቸው አንቱ ቢያሰኛቸው እንጂ እንዲህ  አፍ መሻሪያ የቁርሾ ማወራራጃ ባልሆነ ነበር። ክህሎት ማወራረስ ያለመደባት አላዛሯ ኢትዮጵያ አሁን የተጀመረው አዲስ የባህል ቅምረት እንግዳነት እንዲህ አዋቂ የሚባለውን ሁሉ ያዳልጠዋል። 

ቀድሞ ነገር እና ለማ አብይም ከዚህ ደረጃ ይደርሳሉ ብሎ ቀደሞ የደገፈ ከሳተናው ድህረ ገጽ እና ከሥርጉተ ሥላሴ በስተቀር ማንም አልነበረም። ይህ ደግሞ ተረገጡ ታሪክ ነው። ልክ የዛሬ ዓመት ነው ተጋድሎው የጀመርነው።

በማፍርስ በማስር ለሚያምኑት ሲኦል ሰብዕናዎች ሁልጊዜም ትውልድ ተከታታይ ታሪክ ሳይኖረው በተበጣጣሰ ሥነ - ልቦናው በዘብርቅ መዋቅር፤ በቅጥ የለሽ ብከንት እና ወና የሚያደርግ ተለምዶ መቀጠሉ ህልማቸው ነው። አሁን በዬትኛው ዘመን በዬትኛው ጊዜ መንግሥት የሰጠውን ሃላፊነት ማን ምን አደረገ ብሎ ቢጠዬቅ መልሱ ጥብቆ ነው።

ዘወትር ሃላፊንት ሲመጣ እንደ ሚዳቋ ሲፈረጥጥ የኖረው ሁሉ ማናቸውንም ብሄራዊ፤ አህጉራዊ እና ሉላዊ የሆነ ብቃትን በአደባባይ ያስመሰከሩ ዕንቁ አንስት ጋር አላዛሯ ኢትዮጵያ ለዓይነ ሥጋ መብቃቷ የህሊና ሪህ ፈጠረ። የራስ ተሰማ ናደው ሴራዊ ህልም መቅኖ ይኸው ነው ትርክቱ። መልካምነትን በሳንጃ መውጋት። ቀን ሲክቡ ማታ ሲንዱ ማደር። መንፈስን ማፈረስ የትጋታቸው አውራ ነውና።

ዛሬ ላለው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ስክነትን -  እርጋታን - አደብን - እዮባዊነት ስለሚጠይቅ ነው እኔ የአብይ ለማ ካቢኔ ኮነሬል ጎሹ ወልዴን አማካሪ እንዲሆኑ ስወተውት የባጀሁት። ልምዱ፤ ክህሎቱ፤ ትውፊቱ፤ ተወራራሽ መሆን ከቻለ ነገን ለማለም፤ ነገን ለማደራጀት አንድ ተፈላጊ እና አዋጪ መንገድ ነው። በዬዘመኑ እራሳቸው ፕ/ መስፍን ወልደማርያም በአማካሪነት በቤተመንግሥት ቤተኝነት ተሳትፈዋል። 

ተቃዋሚ በሚባሉትም በግልጥም በሥውርም አሁንም ይሳተፋሉ፤ እኛ በማናውቀው ሁኔታም እንደ ሥርጉተ ሥላሴ ግንዛቤ ከውጭ መንግሥስታት ጋርም ግንኙነት አላቸው ብዬ አምናለሁኝ። አሁንም አሉ እሳቸው። የሰይጣን ጆሮ ይደፈንና ኩዴታ ሆነ ሌላ ነገር ቢፈጠርም ከዛ ጋር ሆነው ያቦካሉ ይጋግራሉ።

በሦስቱም መንግሥታት ነበሩበት። እሳቸውን የወነጀለ የለም። አማራ የለም፤ አልተፈጠረም እያሉ እንኳን አላዛሯ ኢትዮጵያ ተሸክማቸዋለች። ይህ ለውጥ ጎንደር ላይ መፈንዳቱ እና ማስበሉን ቁጭ ብለው ተመልከተውታል። ያ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ባዶ ምንም የሌለው እያሉ የሚያብጠለጥሉት ህዝብ ነው ሁሉንም ነፃ ያወጣው እሳቸውን ጨምሮ። ይህን ቁጭ ብለው እንዲዩት ዕድሜም እንዲሰጣቸው በ2016 ጽፌም ነበር ምኞቴ ነበር ይህን አሳክቶልኛል ልዑል እግዚአብሄር። ተመስገን!

ስለምን መልካም ለመሆን እንደማይፈቅዱ ግራ ቢገባኝም ይህን የመሰለ ዕድል አላዛሯ ኢትዮጵያ ስታገኝ ደስ ሊላቸው ሲገባ ይልቁንም ተቺ ሆነው አረፉ። መተቸታቸው መብታቸው ቢሆንም ትራስ አድርገው የተነሱበት መስመር፤ የቆጠቆጣቸው፤ ያንገበገባቸው ብሉ ጉዳይ ግን እሳቸውም ያውቁታል እኛም አሳምረን እናውቀዋለን። ቢነዱ ራሳቸውን አጭሰው ከበሸታ ከመውደቅ ውጪ ፈቃደ እግዚአብሄርን መገደብ ከቶውንም አይችሉም። አላዛሯ ኢትዮጵያ እናት ስላገኘች ደስተኛ ናት።

ሌላው ጠ/ሚር አብይ አህመድ ለሁለቱ ክብርታት አንስታት ሊሂቃን በአጽህኖት የተናገሩት ነገር ነበር። ለዚህም ነው ለሽ ብለው ሰነባብተው ተጽዕኖ ለማሳደር ፕ/ መስፍን ወልደማርያም ቦንባቸውን የጣሉት። ገዢ መሬት ነበር ይህ የዶር ሙላቱ ተሾመ የአሸኛኘት ዝግጅት።

እኔ ለጠ/ሚር አብይ አህመድ እምገልጸው ሁለቱ ክብርታት ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ሆኖ ወ/ሮ ማዕዛ አሸናፊ የከፍተኛው የፍትህ መንፈስ ቢኮሯቸው እንጂ የሚያሳፍሯቸው አይሆንም። እነዚህ ሁለት ሊሂቃን አንስታት አገር የመምራት ጠ/ሚር የመሆን ሙሉ ክህሎት ያላቸው ብቁ ሴቶች ናቸው። 

እንዲያውም እኮ ከቦታው ከሃላፊነቱ በላይ አቅም ያላቸው ሴቶች ስለመሆናቸው ልባችንም ልባቸውም ያውቀዋል። ዓለም አድንቆታል።
  
እነዚህ ብቁ ሊሂቃን አንስታት በተለዬ ሁኔታ ሊታዩ የሚገቡ የኢትዮጵያ ትናንትን ከሰጡን ከቀደምቱ ሴት ሊቀ ሊሂቃን ተርታ የሚቀመጡ አንቱ ናቸው። ሁሉም አላቸው። 

ጠ/ሚር አብይ አህመድ አምነው ለሰጧቸው ሃላፊነት በጽናት ከጎናቸው በመሆን፤ እርግጠኛ በመሆን፤ ካለምንም ጥርጣሬ፤ ካላምንም ትርፍ ንግግር፤ ካለምንም ስጋት፤ ካለምንም ቅደመ ሁኔታ ተስፋቸውን መጠበቅ ይኖርባቸዋል ባይ ነኝ - በትሁት መንፈስ። እኔም ራሴ በዛ የራት ግብዣ ባደረጉት ንግግር በቃናው የተሰማኝ ነገር ስላለ። 

ገና ሥራው ስልለተጀመረ ቅደመ ማስጠንቀቂያው ብዙም አስፈለጊ አይደለም፤ ግደፈት ቢኖር እንኳን ሴቶችን ከሆነ በጓዳ ምክክሩን ማድረግ እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው። ይህ መሰል አብዮት አህጉራዊም ሉላዊም ሰለሆነ አብነቱን እንዳያጎሳቁለው ብርቱ ጥንቃቄ ማድረግን ይጠይቃል።  

አንድ ዕውነት ለጠ/ሚር አብይ አህመድ ልነግራቸው አምፈለገው እኔ የሴቶችም አደራጅ ስለነበርኩኝ፤ በኋዋላም የገበሬ እና የሠራተኛ አደረጃም ስሆን ሴቶች ስለነበሩበት፤ በስተመጨረሻም የህዝባዊ ድርጅቶችን እና የሙያ ማህበራት አደራጅም በነበርኩበት ጊዜ ከዬድርጅቱ ሴቶች አሉ፤ እንደገናም የሴቶችም ድርጅቶች በዛ ውስጥ እንደ አንዱ ስለነበር ሴቶች ጽኑ ደጋፊ ካላገኙ አደይ አበባ ማለት ናቸው። እርግፍ አድርገው ትግሉን ያቁሙታል። 

ይህን በጠ/ሚር ለማ አብይ ጥሪ አገር ቤት እንደምትገባ የሚነገርላትን ዳኛ ወ/ት ብርቱካን ሜዲቃሳን ማዬት ብቻውን ይበቃል። ፈተናው አይሎ፤ የሴራው መርብ ተወሳስቦ ታገላት፤ ተጋፈጠች በመጨረሻ እርግፍ አድርጋ ሁሉን ትታ ተቀመጠች።

በዚህ ባላፉት ዓመታት ስንት ምስቅልቅል ሁኔታ ተፈጠረ፤ ሰው የሚያስፈልግበት ገሪ፤ መሪ፤ መካሪ የሚያስፈልገብት ጊዜ ነበር። ያ የባከነ ጊዜ ነበር ለአንድ የነፃነት ታጋይ።

የደረጃ ጉዳይ የለም ለአንድ የነፃነት ታጋይ። የትም ቦታ በዬትም ሁኔታ በር ሲዘጋ በመስኮት፤ መስኮት ሲዘጋ በጣሪያ፤ ጣሪያ ሲዘጋ በምድር ለእነዛ ለድምጽ አልባዎቹ የኢትዮጵያ ሴቶች መጮኽ ወሳኝ እና ቀጠሮ የማያስፈልገው ጉዳይ ነበር። 

ብዙ መከራ ችለን ነው ሁለመናችን አድቀቅን ካለ አንድ ረዳት እና ደጋፊ ነው የምንሳተፈው። ክብር ዝና ወዳሴ ላይኖር ይችላል። ወቀሳ ውግዘት ግልት ይኖራል። ውስጥ የቆሰለበትን ለመፈውስ ድርሻን ለመወጣት መሰናክሎችን እዬረቱ፤ መሰናክሎችን እዬታገሉ፤ ለዛሬ ቀን መድረስ ግድ ይላል። ይህ ቀን ባይፈጠረ ምን ሊኮን ነበር? በቃ እንደ ተሰወሩ መቅረት?

ምን ለማለት ነው ሴቶች ወደ ትግሉ ፈቅደው ሲመጡ እንዲመጡ የመሰከረላቸው አካላትን አንገት ላለማስደፋት መጣር ግዴታቸው ሲሆን በሌላ በኩል ዕውቅና የሰጣቸው አካል በጥዋቱ ተስፋ ካጠባቸው ተነሳሽነታቸው ሰባራ ነው የሚሆነው። አድዮ አባባ ናቸው ሴቶች።

እነኝ ሁለት የኢትዮጵያ ሊሂቃን ክብርት ፕሬዚዳንቷ ሳህለወርቅ ዘውዴ እና ክብርት ወ/ሮ ማዕዛ አሸናፊ ፍላጎታቸው እንደ ፋፋ ይቀጥል ዘንድ ክፍተት እንዳይፈጠር ብርቱ ጥንቃቄ ያስፈልጋል። የቃላቱ ቃና፤ የአገላለጹ ዘይቤ ብርቱ ጥንቃቄ ይሻል። ማበላለጥ ባያስፈልግም የሁለቱም ክህሎት እኮ አለ ከሚባለው ካቢኔም በላይ ነው። አህጉራዊ ሉላዊም ነው። ሰብዕዊ ተፈጠሯዊም ነው። 

እነኝህ ሁለት አንስታት ለለውጡ ፒላርም ናቸው። ዕድለኛም ናቸው ጠ/ሚር አብይ አህመድ እነኝህ ሁሉት ሊቀ ሊቃነት ይሁንታ ሰጥተው እሺ ብለው ሃላፊነቱን መቀበላቸው በራሱ ልዩ ሽልማትም ነው። ታሪክ እኮ እንዲህ ነው የሚሠራው።

አሁን በአለው ሁኔታ ለሁለቱም የቅርብ አለኝታ መከታ፤ ጋሻ፤ ዕውቅና ሰጥተው ለሃላፊነት ያጯቸው ጠ/ሚር አብይ አህመድ ብቻ  ናቸው። ስለዚህ ከሳቸው የፀና አመኔታ ይፈልጋሉ ሁለቱም ሊሂቃነ አንስት። ክብርት ፕሬዚንዳንቷ አትኩሮታቸው ተብትኖ ነበር ንግግር ያደረጉት። ውስጤ እያዘነ። ያ ቅጽበታዊ የአትኩሮት መበተን ምንጪ ከምን እንደሆን እኔ ይገባኛል። በዚያ መሰል ሴሪሞኒያዊ የአህዱ ቀን ለዛውም በርዕሰ የተግባር ዋዜማ ላይ አንዷ ቃል ብዙ ትርጉም አላት ተስፋን ለማስቀጠል ወይንም ለማጠንዘል።

በዚህ ላይ በክብርት ፕሬዚዳንቷ ላይ ጦር የመዘዙ፤ ለአሉታዊነት የማይደክማቸው፤ የማይታክታቸው፤ በቃኝን የማያውቁ የራሳቸው መንገድ እና ዓላማ ዬያዙ አዛውንት የፖለቲካም ሰው ፕ/ መስፍን ወ/ማርያም አንድ አሉታዊ ጹሁፍ አስነብበውናል። ያ ከወቄት ግባ ባይባልም ነገር ግን ዕውቅና የሰጠው አካል እርግጠኛ ስለሆነበት የብቃት አቅም በጽናት ከሁለቱ አንስት ሊሂቃን መራሂታት ጎን መቆም ግድ ይል ነበር። ወቅቱ ተገናኘ። 

መልካምነት ሲዳብር፤ ሲጎለምስ፤ ሲፋፋ ክፉዎች ደግሞ ሴራቸው ሲከሽፍ ከሚሸርቡት የሴራ ጥልፍ ጋር ቤተኛ ላለመሆን መጠንቀቅ ይገባል።

ክፉ እንቅልፍ የለውም። ደግ ሰው ግን ሰላማዊ እንቅልፍ አለው። መልካምነት የውሰጥ ሰላምን የሚያሰከብረው ለራሱ እራሱ ዘብ አደር በመሆን ነውና። ከመልካምነት ትርፍ እንጂ ኪሳራ የለውም።

 በሌላ በኩል ክብርት ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ድጋሚ ቃልኪዳን መግባት አያስፈልገዎትም ነበር። ይህቺ ሃላፊነት ለርስዎ ምን ሆና ነውና? ብሄራዊነት በማስደም ነው እንጂ ደረጃው እኮ የዓለም የሰብዕዊነት እናት ነዎት፤ ለሰብዕዊነት ጀማሪ ሀሁ ቆጣሪም አይደሉም። አላዛሯም ኢትዮጵያም እናት አግኝታለች - በእርግጠኝነት። የማያሳፍሩ አነገትም የማያስደፍሩ። እውነት ለመናገር ትውልዱም ዕድለኛ ነው።

ክብርት ሆይ!

መሆነዎት የወረት፤ የዕለት ሳይሆን በሁለገብ ልቅናው የዘለቀ የዳበረ የክህሎት ልዕልትነተዎት ዓለም የሚያውቀው የአደባባይ ሚስጢር ነው። ሹመቱም ችሮታ ሳይሆን በትግለዎት፤ በጥረተዎት ልክ እንዲያውም አይደለም። የአድማጩ ሙግት ያንሰወታል ቦታው ነው። የእኔ ደግሞ ማገርነት፤ ባላነት፤ አጋርነት፤ ቤተኝነት፤ እንዲሁም አላዛሯ ኢትዮጵያ የፈገችዎት ቦታ እና የእዮር ፈቃድ ይህ ስለሆነ በጸጋ ደስ ብሎኛ ነበር የተቀበልኩት።

በጣም በእርግጠኝነት እጅግም በሆነ እርግጠኝነት አላዛሯ ኢትዮጵያ ከእርሰዎ ስለሚጠበቅበዎት ድርሻም ሆነ ውጤት መንፈሷ ያምነወታል። ሚሊዮን ቅኖችም እንዲሁ። ከመሬት ተነስተው አይደለም ይህን ሃላፊነት ያገኙት። ይህ ዕውቅና ለሰጪውም እጅግ አስከብሮታል። እጅግም የዓለም ሚዲያ አምድም ሆኗል። ክብርም ሞገስም ግርማም ጸጋም ያገኙት የጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድ የማስተዋል ህሊና እና ልበ ብርሃንነትም ጭምር ናቸው። ዴሞክራሲ እኮ የሚለካው ለሴቶች በሚሰጠው የዕውቅና ልክ ነው።

በሌላ በኩል በዚህ ሥርዓት ውስጥ በልጅነት ጀምሮ በህሊናዬ ጸንሻቸው የምኖረው ኮ/ጎሹ ወልዴ የተገባው ክብር ስለተሰጠልኝ እጅግ ሐሤት አግኝቻለሁኝ። የሰው ፍላጎት ማለቂያ የለውም እና በቀጣይነት የጠ/ሚር አማካሪ እንዲሆኑ ፈጣሪን አብዝቼ እለምነዋለሁኝ። አላዛሯ ኢትዮጵያ ይህን ዕድል እንዳያመልጣት ኮነሬሉ ለማናቸውም ፖለቲካዊ፤ ማህበራዊ፤ ባህላዊ፤ ታሪካዊ፤ ትወፊታዊ ሁኔታዎች አይከን ናቸውና።

በመጨረሻ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ዶር ሙላቱ ተሾመ እና የነፍሳቸው አካል ዬሆኑት ባለቤታቸው ወ/ሮ ማዕዛ አብርሃ ላደረጋችሁት መልካም ነገር ሁሉ ልዑል እግዚአብሄር ከእናንተ ጋር ይሆን ዘንድ እመኛለሁ። ረጅም ዕድሜም እመኛለሁኝ። መልካምነት እንዲህ ነው። 

ክፉነትን ሴረኝነትን አድማዊነትን በማክሸፍ ከለውጡ ጎን መሰለፋችሁ እናንተም የለውጡ አካል ስለሆናችሁ እንኳን ደስ አላችሁ።

ማገናዘቢያ ምርኩዝ።

Ethiopia's first female president: Sahle-Work Zewde
Published on Oct 25, 2018
Published on Oct 25, 2018
Foreign Affairs CS Monica Juma weighs in on Ethiopia's first female President
2,141 views
Published on Oct 26, 2018
Published on Nov 3, 2018

Ethiopia has female president

Published on Oct 28, 2018
Published on Oct 26, 2018
https://www.youtube.com/watch?v=iZjUrxmW5zw

ፕሮፌሰር መስፍን ኢትዮጲስ ላይ “ኑ ተከራከሩኝ!” ብለዋል። አሳማኝ መረጃ ያለው ካለ ይቅርታ እጠይቃለሁ ብለዋል

https://www.ethiopianregistrar.com/amharic/archives/59541

ሴቶች ጥበብ ናቸው!
ሴቶች የተግባር እመቤቶች ናቸው!
የኔዎቹ ኑሩልኝ።
መለፊያ ጊዜ።


አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።