የደብርዬ¡ ምሾ ይሁን፤ የአስተዛዛኞች ዓላማ እና ግብ ግን አልገብቶም!

እንኳን ደህና መጡልኝ።
ዝብርቅርቅ።

„አቤቱ እጅህ ከፍ ከፍ አለች፤ አላዩምም፤ ነገር ግን
በሕዝብህ ላይ ያለህን ቅንዓት አይተው ያፍራሉ፤
እሳትም ጠላቶችህን ትበላላች“
 ትንቢተ ኢሳያስ ምዕራፍ ፳፮ ቁጥር ፲፩
 ከሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
15.01.2019
ከእመ ብዙሃን።

·       ሟሻ …

ውዶች ክብሮቼ እነ ናፍቆት የአገሬ ልጆች እንዴት ናችሁ? ደህን ናችሁ ወይ? ውይ ዛሬ ፏ ፍንተው ብሏለኝ አዬሩ፤ እትጌ ልዕልተይ ጠሐይ መጥታ ትፍነሸነሻለች - ታፍነሸንሻለች፤ ለነገሩ የዚህ ዓመት ክረምት ቀለል ያለ ነው። ምን ትፈሪያለሽ ብባል ክረምትን ነው የምላችሁ፤ አገር ቤት እያለሁ አብሶ አዲስ አባባ ኗሪ በነበርኩበት ጊዜ ክረምት እህቶቼ በፈረቃ ይመጡልኝ ነበር፤ ሆዴ ርብሽብሽ ነው የሚለው፤ በተለይ ነጎድጓድ አልወድም። በዬአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ እንዲህ የያዝነው ዘመን ዓይነት ሲመጣ ደግሞ ሳንክ አይጠፋም። ብቻ ጠሐይ ካለች ተስፋ ነው። ተስፋ ደግሞ ያጀግናል።

·         ተዚህ ላይ ዕለቱንስ አብረን ብናዘክር።

ዛሬ ጥር ሥላሴ ነው። የጎንደሪት የልጅነት ጊዜ ታወሰኝ፤ የዋሾ ሜዳ፤ የማርገጃው ወይራ…  ዓይኔ ዕንባ አቀረረ። አያቶቼ ነዳይን ፍሪዳ አርዳው በቁርጥ የገና ጾምን እንዲፈቱ የሚያደርጉበት ዕለት ነበር ዛሬ - ትውፊቱ እንደዛ ነበር።

ሸንበቆው ተሰንጥቆ፤ እንደ ካራ ይዘጋጃል፤ ጤፍ እንጀራው ዘንጠፍ ብሎ ታጥፎ በአዋዜ ቁርጥ ለሚፈልግ ቁርጥ፤ ጥብስ ለሚፈልግ ጥብስ አደግድገው መላከብርሃናቱ አያቴ እና ታናሽ ወንድማቸውም መላከብርሃን ነው አሱም እንግዶቻቸውን ነዳያን ያስተናግዳሉ፤ እህታማቾች ደግሞ ለቅዳሴ የመጣውን ቤት ለእንግዳ በማለት ደስ ብሏቸው ያሰተናግዳሉ፤ በዬቤታቸው፤ ላይ ቤት ታች ቤት ዙሪያ ገባው እንግዳ - በእንግዳ። አስተናጋጁም መላ ቤተሰቡ የልጅ ልጅ ልጁ ነው። ቤተሰቡ ሙሉ ነው። ዛሬም ተተኪው እንዲሁ ሙሉ ነው። 

በሃይማኖታቸው የበረቱ የሥላሴ አጋልጋዮች ናቸው፤ የዛሬዎቹ የልጅ ልጆችም …
ያን ጊዜ ፊት ለፊት ሰፊ ድንኳን ለነድያን ይዘጋጃል፤ ዋነኞቹ እንግዶች እንሱ ናቸው። ነጭ ለባሹ እንኳን አደረሳችሁ ብሎ በፈቀዱ ነው የሚመጣው፤ ነዳዩን ግን ይህ ቀን በዛሬው ቋንቋ ቪአይፒ እንደሚባለው ናቸው ተጋባዦች ተከበሪዎች እነሱ ናቸው።

ዋናው እልፍኙ ማህሌት ያደሩ የጎንደር ተደምጠው የማይጠገቡት ሊቀ -ሊቃናት የቆሎ ትምህርት ጊዜያቸውን እያነሳሱ በቅኔ ይዘክሩታል፤ አንዲያምስ ሲል ይተራረባሉ…  አቤት የእኛ ቤተሰብ ይህን ቀን የነበረው ተድላ እና ደስታ፤ ነዳያን በሙሉ የሚወርዱት ምርቅታ … ልጅ ይውጣላችሁ፤የወለዳቸሁት ይባረክ፤ የያዛችሁት ይለምልም ነበር የሚባለው።

·       ዛሬም የሰጠ አይንሳ ፍሪዳው ቢቀር ወዙን አሳርፎ ለሚሄድ የአብርሃሙ ሥላሴ እንግዳ ቤት ክፍት ሆኖ ይጠብቀዋል … እርግጥ ነው ቦታው በሙሉ ተምርቶ አዲስ ነዋሪ በብዛት አለበት ግን አብዛኛው የሥላሴ አገልጋይ ስለሆነ ከእኛ ቤተሰብ በተጨማሪነት ትውፊቱን የማሰቀጠል አቅም ይኖረዋል ብዬም አስባለሁኝ።

·       ሸምግልና።

ወደ ተነሳሁበት ምልስት ሳደረግ ሽምግልና ጥሩ የሚሆነው አድማጭም ፈፃሚ ሲኖር ነው። ሽምግልና ለኢትዮጵያ የባህል ትውፊት የመሠረት ድንጋይ ነው። ነገር ግን ሽምግልና ለኢትዮጵያ ፖለቲካ ባህል ብዙም ይረዳል ብዬ አላስብም። ሰሞኑን ብህሬዊ ሽማግሌዎች ወደ እንደልቡ አየዋ ህውሃት ሠፈር ጎራ ብለዋል። ዶር/ ደብርጽዮንም ኮንፒተራቸውን ፊት ለፊት አስቀምጠው አብዩን ልምሰል መቼም ተለመዷል ሰፋ ያለ ንግግር አድርገዋል።

ያው እንኳን ለዚህ በቃን ማለት የሚቻል ይመሰለኛል። የብሶት ፖለቲካ ለተጋሩ መሳፍንትም ቤት ለእንግዳ ያለ ይመስላል። እኔ ወደ መልሱ መሄድ የሚያስፈልግ አይመስለኝም። ያልገባኝ የሽምግልና ጉዞው ዓላማ እና ግብ ነው። አልገብቶም! አልበገ

ቅጥንቡሩ የጠፋ ነገር። ተጫኑ ነው ጭነታችሁን አራግፉ ይሆን ለኢትጵያ ህዝብ የሚባለው?ነው ጭነቱ አላደከማችሁም እና ተጨማሪ ጫን ተደል ይታከል ይሆን? ወይንስ ከአፈርኩ አይመለስኝ ባዩ እያያ ህውሃት ትንሽ ሃፍረቱን ገለጥ ገለጥለጥ የሚደርግለት አዬር ፈለገ ይሆን? የአቶ ዳውዱ ኦነግ ሦስተኛ ወገን ለሞራሌ ያስፈልገኛል እንዳለው … ብቻ የሽምግልናው ፍሬ ነገር ሳስበው ከአለው ውስጠትም ውጭተም ሲሰላ የውርንጫ ድካም ዓይነት ሆነብኝ …

ምክንያቱም የግራ ፖለቲካ ኢንትሪጋም ስለሆነ ሽምግልናውን ያባጭለው ይሆን እንደሆን እንጂ ፍሬ ያፈራበታል ብዬ አላምንም። ኦነግ እና ኦዴፓ እኮ ይህን መሰሉ መከራ እኮ ነው እያመሳቸው ያለው። በመገንጠል ውስጥ ያለ የግራ ዝንባሌ በአብሮነት ውስጥ ያለ ሰውኛ ተፈጥሮኛ አይዲኦሎጂ ምን እና ምኑ ይገናኝ?ተቀዶ አይሰፋ ነዶ አይደለም? 

በሌላ የመኖር ጉዳይ ሽምግልና ሊሠራ ይችላል በፖለቲካ አመለካከት አቋም ንድፈሃሳባዊ ፍልስፍና ግን መታሰቡ ራሱ ይገርመኛል። ሞክረነዋል ለማለት አብሶ ለዲፕሎማት ቋንቋ ከሆነ ያው እንደ አንድ ጊዜ ማካሄጃ ሊሆን ይችላል፤ አይዲኦሎጂን ቀይር አትቀይር ከሆነ ግን ራሺያም ቻይናም ኪዩባም ተሸንፈው ወደ አንድ ቋት ይጠቃለሉ ነበር።

እና ሽምግልና አይዲኦሎጂያዊ ችግርን ፈጽሞ አይፈታም። ዕለታዊ ግጭት አይደለም እና፤ አይዲኦሎጂያውዊ ችግር። የመንገድ የጉዞ ካርታ መርህ ነው፤ መርህን የሚረታ ደግሞ በመርህ መንገድ ብቻ ነው። ለዛውም መርህን ለሚያውቅ የፍልስፍና ባለሟል። ሽማግሌዎች ደግሞ ከአይዲኦሎጂ ጋር ቀረቤት የላቸውም። ራሱ የህውሃት የአይዲኦሎጂ መስመር እኮ የትም ዓለም የለም እንዲህ ግራዎ ፍልስፍና በዞግ የተመሠረተ ግራዋ ነገር ጨጎጎት ልበላውን? 

ለዚህ እኮ ነው በአካሄድም፤ በአወሳሰንም፤ በአፈጻጻም መስመረ ቢስ የሆነው። ከሌላ አገር ጋር ተምክሮዎን ለማመዛዝን፤ ለማዋዋጥ፤ ወይንም በዚያ ድጋፍ መረጃውን አጠናቅሬ በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ላፍታታው የማይባልበት። በዓለም ደረጃ ተሞክሮ የሌለው የፈለስ ሄሮድስ መለስ ዜናዊ ጃርታዊ መንገድ ነውና።

·       መለዬት ያቀተኝ።

ከሰሞናቱ የአገር ሽማግሌዎች ከቦታ ቦታ መዘዋወራቸው የአገራቸውን አዬር መመገባቸው መልካም ነው።  በሌላ በኩል  የእርቅና የምህረት የይቅርታ የሰላም አማጭ ኮሚሽንም ተቋቁሟል። እርግጥ ነው ጥናታዊ ተግባራቱ ሞጋች ተግባራት ዘለግ ያለ ጊዜ የሚሻ መሆኑ ብቻ ሳይሆን አባላቱን ለአንድ ተልዕኮ ለማሰለፍ፤ በህዝብ አመኔታ በማስግኘት ረገድ ራሱን የቻለ ፈተና አለበት። ከተልዕኮው በላይ። ቲም ወርክ ከባድ ነገር ነው። ድብልብል መንፈሶች ተለግተው እንዴት የመፍትሄ ቋትን ማመንጨት እንደሚቻል? ታጋሽነትን እና ታታሪነት ቅንነትን ራስን ይቅርታ ከመስጠት ጀምሮ የሚጠይቅ ግዙፍ ጉዳይ ነው። ለዚህ እነማን እንደሆኑን አንድ ዜና አዳምጫለሁኝ። ከተሳካላቸው ጥሩ ነው። 

በዚህ ማህል ደግሞ አንድ የሰላም ቡድን በዬክልሎች እዬተዘዋወረ መሆኑን እያየን ነው። ትንሽ ዝብርቅርቅ አለበኝ። ተደበላለቀ። ይኽኛው ጊዜያዊ ስትራቴጂ ይመስላል … ግን በቅድሚያ ይህ ቡድን ግቡን ያውቀዋልን? ያውቀዋል ስል ቻሌንጁን የመቋቋም ምን አቅም አለው? ይህ እኮ አንተም ተው አንቺም ተይ ዓይነት የሚሆን አይደለም … በፍጹም ከተለመደው ውጪ ነው። የህሊና ተግባር ለዛውም የነቃው ክፍል ውሳኔን ለማመንጨት በዚህ መስመር የሚሆን አይመስለኝም።

ህውሃት በ100 ዓመት ህልም እዬተጓዘ እያለ የሚፎካከረኝ አይመጣም ብሎ ሲያቅራራ በ27ኛው ዓመት ህልሙ ቁልቁል ወርዷል። የእነዚህ የሽማግሌዎች ተግባራት ህልሙን ከፍ አድርገን ወደ 50 ዓመት እንምጣው ወይንስ በበቃህ እናሰናብተው እንደሆን አይገባም።
ሽማግሌዎች አቅሙም የላቸውም የአይዲኦሎጂን ችግር የመፍታት። ምክንያቱም የአይዲኦሎጂ ባለሙያዎች ስላልሆኑ። በዛ ላይ ህውሃት ሃይማኖት የለውም። ማተበቢስ ነው። ፈርሃ እግዚአብሄር አልፈጠረለትም። እንዲፈጥርለትም አይፈቅድም። ባህሉ የፖለቲካው ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ነው ሃይማኖቱ። 

መሪዎቹ ደግሞ የቡድኑ የሃይማኖትም ናቸው። ራሱ ፈርሃ እግዛብሄር ከሌለው ቡድን ጋር በምን አግባብ ሊግባቡ? የገሃዱ ዓለም የፍልስፍና፤ የፖለቲከ ሳይንስ ጠበብቶች ወይንም ዓለም አቀፍ ግንኙነት ያጠኑ ወይንም ህግ ያጠኑ ቢሆኑ እንኳን የቡድኑ አባላት ለመደማመጥ የሚያስችል የቋንቋ ሃዲድ ሊኖራቸው ይችላል። አሁን እኮ እኔ ሳስበው ዱዳ የሆነ ነገር ነው የሚታዬኝ።

·       ዱዳነት።

ዱዳነት ቃል አለማወቅ፤ አለመናገር፤ አንደበት አልተመታሰር ብቻ አይደለም። እኔ አሁን በኢኮኖሚ ዘርፍ፤ በህክምና ዘርፍ፤ በሜትሮሎጂ ዘርፍ፤ በኮዲንግ ዘርፍ፤ በምህንድስና ሙያ ዘርፍ፤ በኤልቶሪኒክስ፤ በፊዝክስ፤ በግራፊክ፤ በአካውንቲንግ ዘርፍ ወዘተ... ለሙያዎች ሁሉ ዲዳ ነኝ። የማውቀው አንዳችም ነገር የለም። ስለዚህ እያንዳንዱ ሙያ የራሱ የሆነ ሜቶሎጂያዊ ቋንቋ አለው። ያ ቋንቋ ለእኔ ባዕድ ነው። አልናገረውም፤ አላውቀውም፤ ቢነግሩኝም ትርጉሙን ፈቺ መዝገበ ቃላት ፍለጋ እሄዳለሁ ማለት ነው።

አሁን ለተሰዬሙት ብሄራዊ ሽማግሌዎችም እንዲሁ ነው። ረጅም ንግግር ውይይት ተካሄዷል። ምን ይሁንልን ህውሃት እንደሆን እራሱ ግርም እያለኝ ነበር ያዳምጥኩት። ለመሆኑ ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነትን ትልቁን የድርጅቱን የመኖር የህልውና ፒላር እነዚህ ወገኖች ቃሉን ራሱ ሰምተውት ያውቁታልን? የህውሃት ባህል የሚባለው ዴሞክራሲያዊ ማዕካላዊነትን ነው። ዲሞክራሲያዊ ማዕካላዊነት አንድ የማሌ ፍልስፍና ዘርፍ ነው። የደረጃጃት መርህ ነው የሚባለው ለዘርፉ ...  

ከዚህ አለፍ ሲልም የግራ ፍልስፍና ነው ንደፈ ሃሳቡ 27 ዓመት ሙሉ ሽግግሩን ሳይጨርስ እንደ ኩሬ ውሃ የታገተው አብዮታዊ ዴሞክራሲም ምን ማለት እንደሆን ያውቁታልን ሽማግሌዎች? እንኳንስ እነሱ 7 ሚሊዮን የኢህአዴግ አባላት ምን ማለት እንደሆን ያውቁታልን የሚመሩበት ርዕዮትን ሁነ የአደረጃጃት መርሃቸውን ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነትን? እንኳንስ 7 ሚሊዮኑ የኢህዲግ አባላት፤ የተወካዮች ምክር ቤት ያውቁታልን? እንኳንስ እነዚህ የአገር ሽማግሌዎች ቀርቶ ህግ ተርጓሚ የሚባለው የፌድሬሽን ምክር ቤት ያውቁታልን?

·       ውሃ መልኩ ምን ይመስላል?

ውሃ ቀለም አለውን? ውሃ መልኩ ለመሆኑ ምን የመስላል? ውሃ የምን እና የምን ኮንፓውንድ እንደሆን አንድ የእኔ ቢጤ ሰው ብትጠይቁት ከሰማይ ይመጣል፤ ወይንም ከምድር ይፈልቃል ነው የሚላችሁ? አሁን የሰላም ልዑካን የተባለውም ቡድን ይህን መሰል ፈተና ላይ ነው የወደቀው። እራሱ ይህን ቡድን የማቋቋም ዓላማው አይደለም ለፈጻሚዎች ለራሳቸውም የገባቸው አይመስለኝም። ለእኔ አልገባኝም እና።

እኔ አያድርግብኝ እና ሽማግሌ ብሆን የዚህ ኮሚቴ አባል ብሆን ብዬ ሳስበው ትርጉም አይሰጠኝም። መቋቋሙ ራሱ። ትርጉም የማይሰጠኝ አብዮታዊ ዴሞክራሲን በእርቀ ሰላም ማረቅ ወይንም ማስታረቅ እንደማይቻል ስለማውቀው። በፖለቲካ የሚሳተፉ ብዙ ሰዎችን እዚህ አገር አውቃለሁኝ፤ አባል እና ደጋፊ አባል ልዩነቱን አያውቁትም አይደለም ዘርዘር ያለ ድርጅታዊ የፓርቲ አደረጃጃት እና መርሁውን ቀርቶ። ለዚህ ነበር እኔ የሞባይል ጽ/ቤት ስል የነበረው። 

አገር ይጎብኙ ጥሩ ነው። ከማህል አገር ወጣ ብለው ህዝቡን ያግኙት መልካም ነው። አይን ለዓይን ይተያዩ ፍቅር በዓይን ይገባል ይስማማኛል፤ ነገር ግን የግራ ዝንባሌን አርቆ አይዲኦሎጂን አስቀይሮ ወጥ አካል ኢህአዴግን ለማድርግ ማንዴቱም የላቸውም። በመሸነፍ እና በማሸንፍ ያለ የተጋድሎ ዕውነት ይጠይቃልና።

 በሌላ በኩል ይህ ለውጥ በዬትኛውም መንግሥታዊ አካል፤ ሃይማኖታዊ ተቋም፤ የፖለቲካ ድርጅት የመጣ አይደለም። ለውጡን ያስመጡት የኦሮሞ የግንጫ እና የአማራ የጎንደር አብዮት ናቸው። ስለሆነም „ኦሮማራ“ ያመጠውን ጽንሰት አምስት አገላጋዮች አገላገሉት። አገላጋዮች እራሳቸው በቀኝ ያለውን የኦሮማራ መስመር የማስቀዬር መብት የላቸውም። የህውሃት የበላይነት ይቁም ነው እና መሪ መፈከሩ።



·       ምልሰት ለጥቅርሻነት።

የለውጡ ፈርጦቹ ይሁን እንደ ቀደመው ተጨማሪ ጊዜ ለህውሃት ጌትነት ይሰጣው ቢሉ እንኳን ኦሮማራ አብዮት አይፈቅድም። ኮፒ ራይቱ የኦሮማራ ነውና። ስለዚህ የሚደክሙት የውርንጫ ድካም ነው። እኔ ሽርሽር አድርጌ ነው የተመለከትኩት። ፋይዳ ላለው ነገር ነው መድከም ወጪም መውጣት ያለበት። ወጪው ራሱ አላስፈላጊ ነው።

·       ምሳሌት።
 
ለምሳሌ የቅድሰት ኦርቶዶክስ ተዋህዶን እርቀ ሰላም እንዬው። የቅኖና፤ የዶግማ ችግር አልነበረበትም ልዩነቱ። የነበረበት የመንግሥት ተጫኝነት ነበር። ያ የመንግሥት ተጫኝነት ሲያበቃ ወይንም ሲያከትም ለ7 ቀን የታቀደው በ3 ሰዓት ተጠናቆ ሰላምን ዓወጀ። እርግጥ ቅን ሙሴያዊ መንፈስም ያለው መንፈስ ቅዱሳዊ ሥጦታም ፈቀደ እግዛአብሄርም አለበት። 

ይህ ብቻ አይደለም እኔ ዛሬ ብጹዑ ወቅዱስ አቡነ ማትያስን አባታችን ነው የምለው። ከህውሃት መሳፍንታት ጋር እሳቸው ያሉበትን የፎቶ ሾፕ ቅንብር ከብሎጌ ውስጥ አውጥቼዋለሁኝ። ለአንዲት ቅንጣት ደቂቃ ተለያይተው የቆዩበት ዘመን ትዝ ብሎኝ አያውቅም። ስለምን? የሽምግልናው አስፈላጊነት ወቅት ሂደት እና ውጤትን ከውስጤ ለመቀበል የቅኖና የዶግማ መፋለስ አለመኖሩን ስለተቀበልኩት። የማስታረቁ ዓላማ ግብ የተሰተካካለም ስለነበር።

ከዚህ ባሻገር ያለው የአይዲኦሎጂ ልዩንት ግን እንደ ቋሚ የፖለቲካ ድርጅት ሠራተኝነቴ የሃሳብ ልዩነት እንጂ የአይዲኦሎጂ ልዩነት ሊፈታ የሚችለው የወደቀው አይዲኦሎጂ አዲስ ከተፈጠረው አይዲኦሎጂ ጋር ለመቀራረብ ሲፈቅድ ብቻ ይሆናል እንጂ የወደቀው አይዲኦሎጂ ይምራ ወይንም ጎን ለጎን ይሁን ተብሎ እርቅ ብሎ ነገር የለም። 

የወደቀው አይዲኦሎጂ አራማጆችም መሸነፋቸውን መቀበል ግድ ይላቸዋል። ተስማምተን ተካድን ለሚሉት እንሱ አንዲት ድምጽ አልሰጡበትም እኮ። ፍቅርን ለመቀበል እንዴት እንደተገፋ ተመልክተናል፤ አክብሮ ለመቀበል ከመቀመጫ ለመነሳት ምን ያህል ጭንቅ እንደነበር አስተውለናል። ጠ/ሚር አብይ አህመድ ወደፊት ሲመጡ የሳጅን በረከት ዘጭ ዘጭ ብዙ ታግለናዋል። ባልፈቀዱት ባላቀዱት ነገር የሰማይ መብረቅ ነው የወረደባቸው።  

ይህም ብቻ አይደለም ዴሞክራሲን ቢያውቁት የብዙሃን ውሳኔ እንዲገዛቸው ይፈቅዱ ነበር። ምን ማለት ነው የሄ በዴሞክራሲያዊ ማዕካለዊነት በራሱ እንኳን ብዙሃኑ የወሰኑት ውሳኔ በጥቂቱ ዘንድ ተፈፃሚ ይሆናል ስለሚል።

ስለዚህ ህውሃት በዴሞክራሲ ፍልስፍና ራሱ የወደቀ ድርጅት ነው። ለዴሞክራሲም የተፈጠረ አይደለም። በራሳቸው ፍልስፍና ቢሄዱ ብዙው የወሰነው በጥቂቶችም ተፈጻሚ ይሆናል ነው የሚለው። የታሳናቸው ናቸው። 

ብዙው መሪ አድርጎ በመረጣቸው ጠ/ሚር አብይ አህመድ ትእዛዝ አይቀበሉም፤ ህግ የወሰነውን ለመቀበል አልቻሉም፤ ከህግ ውጪ ተፈላጊን ሰብዕ ደሞዝ እየከፈሉ ያሰራሉ። በዬትኛውም መስፈርት በዬሰከንዱ ከመወደቅ ያመለጡበት አንድም መስመር የለም። በዴሞክራሲ አሰራር እንቢኝ አይባልም።

ትሟገታልህ በድምጽ ብልጫ ከተሸነፍክ ትፈጽማለህ ወደህ ፈቅድህ ደስ ብሎህ። ስለዚህ እነሱ ራሳቸው ፍልስፍናው አያውቁትም በደመ ነፍስ ነው ሲመሩ የኖሩት። የኢትዮጵያ ህዝብ ራሳቸው በማያውቁት ንድፈ ሃሳብ፤ ሊፈጽሙትም ባልቻሉት ዱዳ መንገድ ነው ይህን ሁሉ አሳር የተቀበለው። የተቃጠለ የባከነ ዘመን! 

·       ልነትም ዓይነት አለው።

"አድርገንልሃል" የሚባለው የኢትዮጵያ ህዝብ እኮ አድርጎልኛል ሲል ነው እንጂ በድለህኛል ካለ ካሳ መክፈል ነው። ለዛውም በስንት ቢሊዮን ብር እዳ ስንት ዓመት ይፈጃል ያ ብድር፤ ለማይዘልቅ የካብ ድርድር ... ትውልዱ በመንፈስ የደቀቀውስ>  እንደገናም ዛሬም ያሉ ተፎካካሪዎች የህውሃት በሙሉ ያው ተወጣም ተወረደም የሚነግሩን ስለትግራይ ነው። ትግራይን አትንኩ፤ ዘራፊውም ገዳዩም መርማሪውም ዳኛውም ደብዳቢውም ወራሪውም ከትግራይ እትብተኛ ቢሆነም እንዳላያቸሁት እለፉት ነው። 

አሁን እማ የምንሰማው ጎንደርም የእኛ ነውም አለበት። ወይ መታበት?! እንዴት ያለ መንፈስ እና ህሊና እንደሆን ግርም ይለኛል። እና ሽማግሌዎች ከህውሃት ጋር ብቻ ሳይሆን ካበቃለው የእኔን ብቻ አድምጡኝ እድምተኛ ጋርም መግባባት ይኖርባቸዋል። በነፍስ ወከፍ። 

ከ5 ሚሊዮን ያላነስ ህዝብ አዲስ አባባ ላይ አብይ የእኔ ብሎ ሲወጣ እኮ ሰኔ 16 በቃችሁን እናንተን ነው። ይህ ሰልፍ ደግሞ በመላ ኢትዮጵያ ነው የተካሄደው። እና አሁን የዚህ የሽማግሌዎች ድካም ያ ቋንቋ የማይገኝለት የምጥ ዘመን ተመልሰልኝ ብሎም የሚፈርም ይኖራል ብለው ይሆን? አንድም ሰው አይኖርም። ሰቃይ የሚናፍቀው? ፈተና የሚፈልግ? ስደት ሽው የሚለው? በስለላ የሚዋከብ መኖርን የሚመኝ አንድም ነጠላ ዜጋ አይኖርም፤ አይደለም ሌላው በባርነት የኖረው የኢትዮጵያ ህዝብ የትግራይ ህዝብ ራሱ ከወያኔ ሃርነት ትግራይ ተገላግሎ ከወገኑ ጋር መኖርን ነው የሚፈቅደው። ምክንያቱም ለጥቂቶች ወርቅ እና ጨርቅ እና የዘመነ ዘመናይነት እሱ እንደገና ለማገዶነት የሚቀርብበት ምንም የሚዛን ግዴታ ስለሌበት።

ለማደመጥ ራሱ አቅም የለንም እራሱ የተጋሩ መሳፍንታትን አክስንቱን ስንሰማ ያመናል። ርህርህና የላቸውም። የበደለ ዝቅ ማለት ነው የሚገባው፤ የምን መንጠራራት ነው? መጠላት ሲባል ደግሞ የዝም ብሎ አይደለም፤ ሰው ከነመካራው ይቅር ብሎ አሁንም ሞት እና ሰቆቃ ሃዘን እና ዕንባ ደግሶ በጋለ ምጣድ መኖሩን በፈረቃ ግጨጭትን እያመረተ ለሚርሰው ድርጅት ቅንጣቢ ታጋሽነት መጠዬቅ ራሱ ግፍ ነው።

በድላችሁም፤ ሰርቃችሁም፤ ዘርፋችሁም ኑሩም እኮ አልተቻለም። የትኛውም መከራ፤ ዬትኛውም ዕንባ፤ ዬትኛውም ሰቆቃ መሰረታዊ ምክንያቱ የህውሃት ማንፌስቶ ነው። የዚህ ማንፌስቶ ከሥር ከመሠረቱ መነቀል ብቻ ነው የኢትዮጵያ ህዝብ የመድህን መንገድ።

ስለሆነም ከህግ በላይ የሆነን የተባዬን ግን በመንፈስ ላሽቆ ያለቅን  ቡድን አባብሎ፤ አቅላምጦ ወደ ማህል ለማምጣት ካንሰርን ይተላለፍብኝ በሲሪንጅ ይሰጠኝ ብሎ የመፍቀድ ያህል ነው። ማንፌሰቶው የህውሃት ራሱ ኢ- ሰዋዊ የሆነ ባይረስ ነው። 

ጥላቻ አምራች ነው። ቂም አብቃይ ነው፤ ትውልድ ነቃይ ነው፤ ፍቅር አድራቂ ነው፤ ተሰፋን ነጣቂ ነው፤ ሰላም አድራቂ ነው፤ ህግ አልባነትን ሾሚ ሸላሚ ነው፤ ማሸበርን ሰናቂ ነው፤ ባይታዋርነትን አስታጣቂ ነው፤ ፈጣሪን ተዳፋሪ ነው፤ የሰላም የመኖር የራዕይ የተስፋ ጠንቅ ነው። ስለዚህ ይህ ይቀጥልልን ብሎ የሚፈርም አንድም ህሊና ያለው ነፍስ የለም።

ማነው ከእንግዲህ እግሬ ይቆረጥ፤ ጥፍሬ ይነቀል፤ በዘር ማፍሪዬ ሽቦ ይግባበት፤ ከእንሳሳት፤ ከተባይ ጋር ታስሬ ልሰቃይ፤ ተዘቅዝቄ ተገርፌ ልሰቃይ፤ ደም ልና፤ ዘር አልባ ልሁን፤ ልዘረፍ፤ ልሰረቅ፤ አንገቴን ልድፋ፤ በቁሜ ልትላ፤ ከሰው በታች ሆኜ ሎሌ ልሁን፤ ልጆቼ ታፍነው ይሰወሩ፤ ነፃነቴን ለጌቶቼ ሸልሜ በአምስት ለአንድ ልጠርነፍ ብሎ የሚፈርም? እንዲህ ዓይነት አይደለም ሰው እንሳሳትን ኢትዮጵያ ምድር ላይ ፈጣሪ አልፈጠረም።

ቅርሻማ ጉዞ በቃ! ጥቀርሻማ ዘመንም በቃው! የትግራይ ሥርዕዎ የመሳፍንት ዘመንም በቃው!ለወደፊትም የሰው ልጅ ቆሞ እንዲህ ዓይነት ሥርዓት ይመጣል ብሎ ማሰብ ጸሐይ በምስራቅ መውጣቷ ቀርቶ በምዕራብ ትወጣላች ብሎ ማሰብ ማለት ነው። ገዳይ አይናፈቅም! በዳይ አይናፈቅም! ጭካኔም አይናፈቅም! አረመኔነት አይናፈቅም!

ከዚህ መሰረታዊ አመክንዮ ስንነሳ ምን እና ማን ሊያስታርቁ ነው አባቶች አህቶች ወንድሞች መቀሌ የተገኙት። ጭካኔና እና ርህርህናን? አረመኔነትን እና አዘኝነትን? ሩብ ዜግነትን እና ምርጥ ዜግነትን?



 መቀሌ ከናፈቀቻቸው ጥሩ ነው ደጋጎችን። መግዛት መንዳት ቀረብን የሚሉ ገድለውም፤ ዘርፈውም ጨክነውም ያልጠገቡ መታበዮችን ለመጎብኝት ከሆነ መልካም ነው፤ ከዛ በተረፈ ግን የኦሮማራን ኮፒ ራይት ላይ እንወስናለን ከሆነ እነሱ የተከበሩበትን ቦታቸውን ያሳጣቸዋል። ይህ መታሰብ የነበረበት በውነቱ ቀድሞ ነበር። ምክንያቱም ውጤቱ ካለምንም ነጋሪ ወዳቂ ስለሚሆን። በእያንዳንዱ ስንኝ „ገዱ አማራ“ አይቀሬ ነው። የማንፌስቷቸው እንብርት ስለሆነ። 


ከእንግዲህ አማራ ከህውሃት ተንበርክኮ ነፃነት ቅንጥብጣቢ የሚለምነበት ዘመን አቅክትሟል። እንዲከትም ያደረገው ራሱ አማራው በራሱ ተጋድሎ እንጂ ከዬትኛውም አካል በችሮታ ተነጥቦለት አይደለም። 

ይልቅ አማራ ልብ ገዝቶ የራሱን ድል ይጠበቅ አይጃጃል… የመሪውንም የገዱን የመንፈስ ድምጽ ድምጼ ይበለው። ውሃ በቀጠነ አያነቁኑቅ። ልጆቹን ሥርዓት ያስተምር ብአዴንን ህውከት እየፈጠረ ተጨማሪ ሥራ አይፍጠርበት። 

·       ንገትየለሽነት።

የተጋሩ ሰው እኛን መልሰው ይጠይቁናል 27 ዓመት እንዴት ሁሉንም ህውሃት መራ ይባላል፤ በደል ክፍፍል ያድርጉልን ባዮች ናቸው። ሳጅን በረከት ሆኑ ሳጅን አዲሱ አማራ እንዳልሆኑ ራሳቸው አውቁታል። 

በደሉ ባይኖር መቼ እንዲህ አክ እንትፍ ይባል ነበር እና መሪ ድርጅታቸው። 90% በላይ የሆነውን ሁሉን ነገር በአንድ ድርጅት 5% ህዝብ ተይዞ እኛ ተጠያቂ ሆን ብሎ ማልቀስም አይገባም። ትግራይ የመሸጉትም ያ ስለቀረ ነው።

የበለጠውን እጅ ባያገኙማ ኑሮ የሚቀርባቸው የታሰሩበት ካቴን ብቻ ስለነበር የሚያሸፍት ምንም ነገር አልነበረም። እናውቃለን እኮ ሦሱቱ አባል ድርጅቶች የራሳቸውን ጉዳይ ላይ ብቻ ተወያይተው ወስኑ የሚባሉትን ብቻ እንደሚወስኑ ትግራይ ግን የኢትዮጵያንም ጉዳይ ወሳኝ እንደነበረች፤ 

ለዚህ እኮ ነው ሳያስፈቅዱ አማራ ክልልን ሰተት ብለው የአቶ አባይ ወልዱ የታበዬ ጥጋብ አላስችለው ያለው ታጣቂ ጎንደር ከተማን ጥሶ ገብቶ በግለሰብ ቤት ጥቃት ሲፈጽም ተዋርዶ ለዘላለም እንዳይነሳ ሆኖ መቃብሩ ተቆፎሮ ትቢያ ለብሶ እንዲቀር የተደረገው። ጥጋቡ እስኪዘህ ድረስ ነበር፤

ምን በዓለም አደባባይ በመዲና ላይ የስፖርት ዳኛን መደብደብ ጥጋብ፤ ሸንት በኮዳ ሞልቶ ወልድያ ህዝብ ላይ ማርከፍከፍ ጥጋብ ያል አልበቃ ብሎ የተበደለ የተረገጠ ሽንት የተደፋበት ህዝብ  በኢልኮፍተር በተደገፈ ወሎ ላይ ጭፍጨፋ ማካሄድ ጥጋብ አሁን የሄዱት መቀሌ ሽማግሌዎች ይህ ይመለስላችሁ ይሆን? ያን ጊዜ አሰተርዮ ቅዱስ ሚኬኤል ሲደበደብ የት ነበር ይህ ስብስብ አባታችን ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ እራሳቸው? ለመሆኑ አባቶች እዛ ሄደው ምዕመኑን አጽናንተዋልን? ዝም እምለው እኮ የሃይማኖቴ ቅናት ስላለብኝ አንድም ቀን አንዲት ነገር ጽፌ አላውቅም። ቅጥል እያልኩኝ ዋጥ ነበር የማደርገው። 

በምድር የኢትዮጵያ ህዝብን ያህል ቻይ ህዝብ የለም። ዓይን ለማዬት እንኳን አይፈቅድም ግፉ ቢዘረዘር የወልቀይት የጠገዴው 44 ዓመት ሙሉ ነው። ከእነሱ ጋር መጋባት መዋለድ አበልጅነት አሁን አለ። ይህም በመቻል ተይዞ ነው። ከዚህ በላይ ቻይነት የለም።

የሚገረመው ሁልጊዜ የትኛውም የተጋሩ ሊሂቅ እኛ እኛ እኛ ብቻ። ስግብግብነት ግለኝነት … አንዲት ቅንጣት ከሰብ ጉዳይ ጋር የሚያያዝ መንፈስ የላቸውም፤ ለነገሩ ማደመጥም አያስፍልግም። ኤክስፓይርድ ላደረገ የጋራ የመታበይ የታላቋ ትግራይ ህልመኝነት ጊዜ መውሰድም የተጋባ አይደለም። መተው ብቻ ነው የሚሻለው። ፈጣሪ በጥበቡ ገላግሎናል። ተመስገን!

ይልቅ ይህ ባለቀ ሰዓት ያዙኝ ልቀቁኝ የትም አያደርሰም ምክንያቱ የሰማዩ ዳኛ ስላለ፤ ትምክህቱ በመሳሪያ ነው። ያ መሳሪያ እኮ የኢትዮጵያ ህዝብ አንጡራ ሃብት ነው። ከዬትኘው ማዕድን የፈለቀ ነው? ያም ቢሆን የሰማዩ እዮር ማዕቱን አፍስሶ እዬዬ እንዳይሆን ብቻ ነው እኔ እምሰጋው … ለህፃናቱ - ለነፍሰጡር - ለእናቶች እና ለአቅመ ደካሞች ነው … ግፉ ሞልቶ ተርፏል። ደሃ እናት አገር ተዘርፋ ራቁቷን ቀርታለች፤ 100 ሚሊዮን ህዝብ የሥነ - ልቦና ህመምተኛ ነው። አዬሩ ራሱ ህምምተኛ ነው። ስጋት ነው፤ ፍርሃት ነው፤ ራድ ነው።

ለእኔ የሽማግሌዎች ሽምግልና የማያውቁትን ነገር ነው የሚሸምገሉት። አይዲኦሎጂ በሽምግልና መፍትሄ አያገኝም። ይልቅ ህውሃት ለበደለው በደል ካሳ የሚጠዬቅበት ዘመን መምጣቱት ቢያውቁ ጥሩ ነው። 

ራሱ ለጣና የኤልትሪክ ቀጣይ አግልግሎት ማተ ቢስ ስለሆኑ ግብር መክፈል ግድ የሚሆንበት ጊዜ ይኖራል … ምክንያቱም ይሉኝታ ብሎ ነገር አልፈጠረላቸውም እና … ዝብርቅርቆች። 

ሲያምራችሁ ይቅር ከአንግዲህ ሰው ሁሉ አፍር ሲጫነው ብቻ ህውሃት ሥልጣኑ ይመለሳል። ይህ ደግሞ የዱቡሽት ቤት ነው። 

በህልምም የማይታሰብ። ይልቅ የመጨረሻው መሰነባበቻ ቀን በምን ሴሪሞኒ ይሁን መልካም ምልከታ ነው … ለ እሱ ፕሮግራም ቢነደፍለት የተሻለ ነው። ከዚያ የተረፈው የሴራው መረብ ትብትብ መጠላትን ቢያከረው እንጂ የሚፈይደው አንዳችም ነገር የለም።

አብይ ኬኛ!

ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጥር!

ገዳይ አይናፈቅም! 
በዳይ አይናፈቅም! 
ጭካኔም አይናፈቅም! 
አረመኔነት አይናፈቅም!

የኔዎቹ ኑሩልኝ!
መሸቢያ ጊዜ!     




አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።