እሸት ራዕይን ምራቁን በዋጣ ቻይነት ምህንድስና ብቻ አዋጭ ነው።

እንኳን ደህና መጡልኝ።
ጠንቃቃነት ያተርፋል እንጂ አያከስርም።

 „ምንም እንኳን በለስም ባታፈራ፣ በወይን ሐረግ ፍሬ ባይገኝ፣
 የወይራ ሥራ ቢጓል እርሾችም መብልን ባይሰጡ
በጎችም ከበረት ቢጠፉ ላሞችም በጋጥ ውስጥ ባይገኙ
 እኔ ግን እግዚአብሄር ደስ ይለኛል፤
በመዳህኒቴ አምላክ ሐሤት አደርጋለሁ።
ትንቢተ ዕንባቆም ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፲፯ ቁጥር ፲፰

ከሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
26.02.2019
ከእመ ዝምታ - ሲዊዘርላንድ።
                              
ጤና ይስጥልኝ የኔዎቹ እንዴት አላችሁልኝ። ደህና ናችሁ ወይ? በአንድ ጉዳይ ዙሪያ ትንሽ ነገር ልል አሰብኩኝ። አብን ሚሊዮነም አዳራሽ በተከታታይ ጠይቆ እንዳልተፈቀደለት ይልቁንም OMN እንደተፈቀደለት ገልፆል። በዚህ አብን ተከፍቷል። ተገልለኩኝ እያለ ነው። ይህን መጠበቅ ያስፈልጋል።

ስለምን? አሁንም የዞግ ፖለቲካ ነው ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው። አውራው ፓርቲ ደግሞ ኦዴፓ ነው። የምናደምጣቸው ዝበት ያለባቸው ነገሮች ከኦዴፓ የመነጩ ሳይሆኑ ከራሱ ከኢትዮጵያ የዞግ ፖሊሲ ነው የሚመነጨው። አድሎ፤ መገለለ፤ መጫን፤ ጭቆና ዴሞክራሲ በሌለበት አገር ግድ ነው። ተጋድሎው እኮ ሁሉን እኩል የሚያደርግ ቋሚ ሥርዓት ይፈጠር ነው። ለዛ ደግሞ በአንድ ጀንበር የሚሆን አይደለም። 

የለውጥ መሪዎቹ እራሱ እኮ ከዞግ ድርጅት የወጡ ናቸው። ሥነ - ልቦናቸው፤ ልምዳቸው ተመክሯቸው በዛ ዶክተሪን የተቃኜ ነው። ከዚህ ለመፈታት ጊዜ ይጠይቃል። እያንዳንዱ መሪ ከራሱ ጋር እኮ አሁን ፍትጊያ ላይ ነው ያለው። ሬድ ሜድ እንዲሆኑም እንሻለን። 

አሁን እኔ ዶር ለማ መገርሳ እና ዶር አብይ አህመድን እሚያመሳስላቸውን እና እሚለያዩበትን በጥሞና ነው እማስተውለው፤ እነሰኑም ተስማምተው ለመቀጠል የወሰኑበት መንገድ በመቻቻል ውስጥ ስለመሆኑ አስተውላለሁኝ። 

ይህ ደግሞ ለ ኢትዮጵያ ጠቃሚ ነው። ፈንገጠው መስመር አለመከተላቸው። በሌላ በኩል ለውጡ ጥገናዊ ነው። ይህን ብዙ ሰው ይዘነጋዋል። ስለሆነም አብዮት ይመኛል።  

ዋናው ነገር ለመለወጥ በር መከፈቱ ነው። ኮረኮንችም ዳገትም ኮረብታም ቢሆን የተቀዬሰ አዲስ መስመር አለ። ያን መስመር ደግሞ አጠንክሮ አስልቶ አስፓልት ለማድረግ በትልቁም በትንሹም ተስፋ በመቁረጥ አይደለም። ሆድ ሊብሰን አይገባም። 27 ዓመት እኮ ተኑሯል።

እራሱ አማራ መደረጃቱ ትልቅ ድል ነው - ለእኔ። የበይ ተመልካች ሆኖ በእቅሙ የሌላውን ውዳሴ ማህሌት ቁሞ የሚያድርበት ዘመን ማክተሚያ መግቢያ በር መከፈቱ መልካም ዕድል ነው። እንዲያውም የኢህአዴግ ወደ ወጥ ፓርቲነት ለመሸጋጋር ቅዬሳው ስጋትም  የአማራ ብሄርተኝነት መጎልበት ነው ብዬ ነው እማስበው። ሌሎቹ 40 ዓመት አስቆጥረው ከቁብ አልተቆጠሩም ነበር። አማራ ሲነሳ ግን አስቸኳይ ጊዜ አዋጁም ሆነ ሌላው ነገርም ጫን ተደል ነው… ይህ በራሱ መልካም ዕድል ነው ለአላዛሯ ኢትዮጵያ።

አማራ መደራጀቱ ደግሞ ማንም በችሮታ የሰጠው አይደለም፤ በተጋድሎ ያገኘው የደሙ ማህተም ትርፉ ነው። አማራ መደራጀቱን ተረጥቦት አይደለም። በጽናቱ በተቀመመው ቅኔያዊ ተጋድሎ ያገኘው ነው። የአማራ የማንነት የህልውና ተጋድሎ ትርፉ አትራፊ ሊሆን የሚቸለው ደግሞ የፖለቲካ ድርጅቱን የ አብን ማለቴ ነው ራዕይ ወጣት በማድረግ አይደለም። የድርጀቱን ራዕይ እሸት ግን ምራቁን የዋጠ ማድረግን ይጠይቃል

እርግጥ ነው አመራሩ በሙሉ ወጣት ነው የአብን። ወጣት አትሁኑ ማለት ወንጀል ነው እንደ ማህበረሰብ አደራጅነቴ። በግድ በዚህ ዕድሜ ሊመጡ የሚችሉ፤ ሊታዩ የሚችሉ ነገሮች ይኖራሉ ተፈጥሯዊ ነውና። ነገር ግን አማራ ማህበረሰብን ለመምራት አህዱ ሲባል ቻይነትን መርህ ማደረግ ግድ ይላል። አማራ ቻይ ነው። መቻልን አምጦ በመቻል መውለድ ግድ ይላል። አማራ ከብቱን ጥማዱን አያ ሆይ! እያለ አክብሮ ነው የሚይዘውና።

እኔ ለወጣት ፖለቲካኞች እምመክረው ወጣትነትን መሰናበት የሚገባው የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ ለመግባት ሲወሰን ነው። የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ በሙሉ አቅም እና ጊዜ ለመሳተፍ ሲበዬን ከብዙ ነገሮች ላይ ማዕቀብ መጣል ያስፈልጋል። 

ህይወት በጥንቃቄ መመራት አለበት ዓላማ ላለው ወጣት ፖለቲከኛ። ብዙ የተፈጥሮ ፈቃዶች ሁሉ ይቀራሉ። „አያ ሆይ ሳሩን አይተህ ገደሉን“ እንዳይሆን የተቆጠበ የሥነ - ህይወት አያያዝ ይጠይቃል። ጠንቃቃነት።

ተፈጥሮን እራሱ መጫን ግድ ይላል። ከወጣትነት ስሜታዊነት ጋር መተላለፍ። እርግጥ ነው ተሎ ነገሮች ተሳክቶ ማዬት የወጣቶች ፍላጎት ነው። ግን ተሎ ላይሰኩ የሚችሉ ነገሮች እንዳሉም ማሰብ ያስፈልጋል። 

ማሸነፍ እንዳለ ሁሉ መሸነፍም እንዳለ መቀበል ግድ ይላል። በፈቀደው ያህል ሩጫ፤ በፈቀደው ያህል ጥረት ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ውጭ የሚገኝ ተረፈ ዕሴት አለመኖሩን አምኖ መቀበል ያስፈልጋል። ኢትዮጵያ እኮ ዴሞክራሲን በፍሬም ውስጥ ነው የምታውቀው።

የተፈለገ ሁሉ አይገኝም፤ የተወለደ ልጅ ሁሉ እንደማያድገው ሁሉ ወይንም የተዘራ ሁሉ እንደማይበቅል ሁሉ። አሁን ባለው ሁኔታ ሁሉም ቦታ ላይ ፍጹማዊነትን መጠበቅ አይገባም። ከዛሬ 20 ዓመት በሆዋላ እንኳን ፍጽምና በሁሉም መሰክ አይኖርም። ዘመኑ ደግሞ የሚወልደው ሌላ ፈተና ስለሚኖር።  

ሁሉንም ፍላጎት ለማሳካት ቢቻል መልካም ቢሆንም ተጨባጩ ነገር ማሰብ ማጥናት ያስፈልጋል። የኖርንበትን ግራጫማ ዘመን ደግሞ በምልሰት መቃኘት ይገባል። ዛሬን መርቀን ተነስተን፤ ነገን በምርቃቱ ለማስቀጠል ታግሰን ችለን እምናልፋቸው ነገሮች መኖራቸው ግድ ይላል።

የሻሸመኔ፤ የቡራዩ፤ የአዲስ አባበ፤ የለጋጠፎ ወዘተ ችግሮች ከሰባዕዊነት አንጻር ተፎካካሪ/ ተቃዋሚ/ ተቀናቃኝ የሚባሉት ድርጅት መሪዎች ሳይሰማቸው ሳይዝኑ አይቀሩም። ግን አልተነገሩትም። አፍነው ይዘውት ነው የቀሩት። 

ስለምን? ብትሉ አንደኛው ሚዲያው ሥራውን እዬሠራው ነው፤ ሁለተኛ ታግሶ ለማሳለፍ ከራሳቸው ጋር ታግለው ራሳቸውን ስላሸነፉ ይመስለኛል። በስተቀር በአጭር ተቋርጦ መቅረትም ይኖራል ... 

አብን የሆነውን ሁሉ በሚዲያ አውጥቷል። ቀሪውን ሚዲያው ይሰራዋል። ፍርድ እና ዳኝነት ደግሞ የህዝብ ነው። በዚህ እልህ፤ በዚህ ቁጭት ግን ሌላ እርምጃ አብን እወስዳለሁ ቢል መጪውን ነገር ማሰብ ያለበት ይመስለኛል። 

ሰሞኑን የጉራጌ ህዝብ አንድ የፖለቲካ ድርጅት እንደመሰረተ አድምጫለሁኝ። አንድም ሰው፤ አንድም ሚዲያ፤ አንድም ጋዜጠኛ፤ እንደም የፖለቲካ ድርጅት፤ አንድም የፖለቲካ ሊሂቅ አልዘመተባቸውም፤ አልተከሰሱም። አብን ላይ ግን ታይቷል። ቀንበር ሰንሰለት ካቴና ነው የተጫነበት። 

ይህ ምን ለማለት ነው አብን ከፊት ለፊቱ ብዙ ዳገቶች አሉበት። እነዚህ ዳገቶች ለማለፍ ደግሞ መቻልን ምራኝ ማለት ይጠበቅበታል ማለት ነው። አብን ከቅኔው እንቡጥ ከአርቲስት ቴወድሮስ ካሳሁን የህይወት ልምድ መማር አለበት። 

ዜጋ አይደለህም ተብሎ ብቻውን ዕጣ ነፍሱን በተገለበት አገር ታግሶ „አልሄድ አለ እግሬ“ እያለ ታገሰ። አሁን „ሂድ ሂድ እግሩ ያለው“ ሁሉ አገር ሲገባ ሁሉመናው ይከብደዋል። ያ ቅኔ ግን የቻለውን ችሎ፤ የታገሰውን ታግሶ ዛሬን አገኜ። ዛሬም እሱን መሰል ብልህ አስተዋይ ወጣት ፈተናው ቀላል አይደለም። ግን ይኸው ችሎ አለ።

አሁንም አብን መቻልን መርሁ ማድረግ ይኖርበታል። አሁን አብን ሰላማዊ ሰልፍ ለመጥራት አስቧል። እኔ አልደግፈውም። ስለምን?

·       አንደኛ አዳራሽ ተከለከልኩ ብለህ ሰላማዊ ሰልፍ አመክንዮው የድርጅቱን የረጅም ጊዜ ዓላማ ያቀለዋል።

·        ሁለተኛው በመቸኮል የሚመጡ አደጋዎችን ከመፈጠራቸው በፊት ሊፈጠሩ ቢችሉ ማሰብ ይገባል፤

·       ሦስተኛው የሞላ ቀን እና ወራት አለ የዛሬው ፈጣሪ አብን ከተቃጣ ቀስት ሊያድነው አስቦ ከሆነ ብሎ መታሰብ አለበት።

·       አራተኛ ስለምን አዲስ ቅራኔ ውስጥ ይህ ጮርቃ ድርጅት መግባት ይፈቅዳል? ምክንያቱም ነገረ አማራ ግማድ ተሸክሞ መኖር ሆኖ በዛ ላይ ደግሞ አንሶኛልና ጨምርልኝ የተገባ አይመስለኝም። ታግድሎ ይፍራ ማለቴ አይደለም፤ ጥበብ እና ስልትን መርሁ ያድርግ ነው።

·       አምስተኛ  OMN እነሱ ወገኖቻችን ናችሁ ባይሉም እንደ አብን ላለ ብሄራዊ ስሜት ላለው ድርጅት እነሱም የእኔ ናቸው በዛ ላይ እንግዶች ናቸው ስለዚህ ቢቀድሙ ምንም አይደለም ብሎ ቀለል አድርጎ በቅንነት፤ በአዎንታዊነት ማዬት ከሥነ -ምግባር አንጻርም አብን ቢያስከብረው እንጂ የሚየከሰረው ነገር አይኖርም።

·       ስድስተኛው ወጀብ ሲኖር ዝቅ ብሎ ማሳለፍ ይገባል።

·       ሰባተኛው በተጨማሪም አብን የአዲስ አባባን ሰልፍ ለመምራት ለማስተዳደር አሁን አቅም የለውም። ብዙ ነገሮች ሊከሰቱ ይችላሉ። አይደለም አብን የጠ/ሚር ቢሮ በፈቀደው ሰልፍ ላይ ሰኔ 16 የተፈጠረውን ማሰብ ይገባል። አማራ ተሰባስቦ ሲገኝ ምን ሊፈጠር እንደሚችል በጣም በጥንቃቄ ማሰብ፤ ደግሞ ማሰብ ደግሞ ማሰብ ይገባል። አላስፈላጊ ሰልፍ አላስፈለጊ መስዋዕትነት አይገባም። ለብአዴንም ተጨማሪ ጫና መፍጠር አይገባም። ያለበት ቀውስ እና መከራ ይበቃዋል፤ ሁሉም አስልቶ እዬቀጣው ነውና ብአዴንን። 
  
አሁን OMN ሊያደርግ ያሰበው ኢሳት በየከቲት 9 ስላደረገ ነው። የጳጉሜው የግንቦት 7 አቀበባል በመስከረም የኦነግ አቀባባል ያ ሁሉ ጫና እና መከራ እንደመጣው ማለት ነው፤ እንጂ ሚዲያው ከገባ እኮ ቆዬ። በዛ ባለፉ ጊዚያት ማድረግ ይችል ነበር። ፉክክር አለ። ይህ ፉክክር ደግሞ ባለሰከኑ ሌላ ፉክክሮች ከተወራረደ የፋሲካ አውራ ዶሮ መሆን ነው።
በሌላ በኩል እንደ አገርም አገር ያለችበትን ሁኔታም ማሰብ ይገባል። አገር ምጥ ላይ ናት፤ አገር ዕንባ ላይ ናት፤ ለዛውም በታቀደ ሰው ሰራሽ ችግር።  

ስንት ሚሊዮን ህዝብ ነው ሜዳ ላይ የወደቀው? ስንት ሚሊዮን ህዝብ ነው እያለቀሰ ያለው? ስንት እናቶች ናቸው የከፋቸው? ስንት ህጻንት ናቸው ከትምህርት ገበታቸው ተፈናቅለው በሃዘን ውስጥ የሚገኙት፤ ችግሩን መጋራት ይገባል። ችግሩን መጋራት ማለት በተቻለ መጠን የራስንም ፍላጎት ላይ አንጻራዊ ተጽዕኖ ማድረግ ማለት ነው።

ነገ ለሚቻል ነገር ዛሬ በእልህ ሰላማዊ ሰልፍ አደርጋለሁ ብትል አታደርግም ብትባል ምን ይመጣል? ሰልፉ ተፈቅዶም አደጋ ቢፈጠር ማነው ዋስትናውን የሚወሰደው? በጣም የረቀቁ ደባዎች እና አድማዎች ነው ያሉት። ስለሆነም እኔ እንደ ሥርጉተ ሥላሴ አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ነገረ ሰላማዊ ሰልፍ ተግ ማለት አለበት የሚል ጹኑ አቋም ነው ያለኝ።ያረጉ፤ ያቆበቆቡ፤ ያልሰከኑ ጉዳዮች አሉና።

እኔ እንደ ሥርጉተ ሥላሴ አቀባበል እራሱ መንግሥታዊ ከሆነው የእንኳን ደህና መጣችሁልን በስተቀር ሌላው አሁን ላለንበት ችግር ተጨማሪ ችግር ነው ያመረተው። ታሪካችን ነው ያጠቆረው። ብዙ መንፈሳችን ነው የተበጠበጠው፤ ይቅርብኝ ክብር እና ግርማ ማለት ይገባል። ምክንያቱም ማገዶው የድሃ ልጅ ነውና። ለውጥ መደገፍ ሲባል የራሴ ይቅርበኝ የመትለው ነገር መኖር አለበት።

አንድ ነገር ተፈጥሮ መከራ ካለመጣ አይታዬነም ችግሩ፤ አብሶ አሁን ያለው ትዕይንት መከራ አለ እዬተባለ ለመከራው መፍትሄ አፋጣኝ ሳይሰጥ ሺዎች የመከራ ሰላባ ከሆኑ በኋዋላ ነው የማረጋጋት ሥር ተሰራ ሲባል የሚደመጠው ይህ የሳቦታጅ ጉዳይ ነው። አሁን አሁን ነው እኔ የፕ/ መራራ ጉዲና „የቡዳ ፖለቲካ“ የሚሉት ፍልስፍና እዬገባኝ የመጣው። የቡዳ ፖለቲካ ለእኔ የራስ ተሰማ ናደው የሴራ ፖለቲካ ነው።

አብን የተደገሰለትን አያውቅም። አንዳቸውን ብናጣ መልካም አይሆንም። ከዚህም በላይ ለሰከነ የፖለቲካ ጉዞ አብን መሰናዳት ይኖርበታል። ፉክክር የልጆች ጨዋታ ነው ለእኔ። አሁን ይህን የፉክክር የግርግር ፖለቲካ ኢትዮጵያ የተሻገረችው ይመስለኛል። ያልጠገቡት ይሂዱበት፤ የማይሰለቻቸው ይሂዱበት … ሌላው ግን ሃሳብ ያለው፤ ዓላማ ያለው አብሶ ለህልውና እታገላለሁ የሚል የድርጅቱን ህልውና መጠራቅቅ ከሚያስገቡ ነገሮች መታቀብ ግድ ይለዋል። 

አንድ ሰው ቢሰዋ፤ አንድ ሰው ቢደበደብ፤ አንድ ሰው አካሉ ቢጎድል አብን ከተጠያቂነት አይድንም። ስለምን? ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ የተነሳበት ዓላማ አምክንዮ ስስ ነውና። ይህን የሚገፉ ሃይሎች ሊኖሩ ይችላሉ። ነገር ግን ከጠቀሜታው ይልቅ ኪሳራው ነው የሚያመዝነው። አብዝቶ ማስተዋል ይገባል። 

ሌላው ቀርቶ መስዋዕትነት ባይኖር ብለን ብናስበው እንኳን አብን ባሰበው ልክ ሰው ባይወጣለት እራሱ ትልቅ የፖለቲካ ክሰረት ነው። ስለምን? ህዝብ ስጋት ውስጥ ነው ያለው። ህዝብ ተረጋግቶ ለመኖር አይዞህ ርቆታል። 

በሌላ በኩል መንግሥትንም አዳዲስ የቤት ሥራ እዬሰጠን ማጨናነቁም ድርብ አንጀትነት ነው። ይህ አዲስ መንግሥት የ50 ዓመት ችግር እፍ ብለህ ካለጠፋህ ተብሎ ተወጥሮ ተይዟለኝ። አንድ ቤቱን ማደረጃት አቅም የሌለው ሁሉ ነው በላይ በላይ የቤት ሥራ ሲጭንበት ውሎ የሚያድረው … መተዛዘን ያስፈልጋል። የብዕር የብራና የማይክ ሙግቶች ይቅሩ ይነጠፉ ማለቴ ግን አይደለም። እነዛ ይጎልብቱ ግን እንደዚህ ዋስትናው ባልተረጋገጠ ሁኔታ ሰላማዊ ሰልፍን ማሰብ አትራፊ አይደለም። 

ሁለጊዜ አይሞላም፤ ሳይሞላ ሲቀር ማኩረፍ አይገባም። ይህም ይኖራል ብሎ ማሰብ ይገባል። አሁን ግራጫማ ነገር ባናስብም ምርጫ ሲመጣ ብዙ ነገሮች ሊከሰቱ እንሚችሉ አስባለሁኝ እኔ። ፊት ለፊታችን ያለውን የደመና ቅርጭጭት ለማስወገድ ፈተና እያጨን ሳይሆን ፈተናን የሚቀንሱ ነገሮች ላይ ተግቶ መስራት ይገባል።

ወጀቡን ዝቅ ብሎ ማሳለፍ ይገባል። እኔ ፈተና ሲገጥመኝ ጥፍት ነው የምለው። የጸጋዬ ራዲዮ እጅግ የሚናፈቀኝ ለእኔ ብቻ አይደለም ድምጼን የሚወዱት ግን ቋንቋውን የማይሰሙ ታዳሚዎች ሁሉ ነበሩበት፤ ፈተናው ሲያል ትውት ነው ያደረኩት። ድካሜን ቀንሼ ግን በሌላ መንገድ ሥሙ የጋሼ ጸጋዬ እንዲኖር አደረግኩት። የእኔ ድምጽ ለማይፈልጉት፤ ያ ድምጽ ለሚያውካቸው ሰዎች ሐሤትን ቀልቤ፤ እልህ ውስጥ ሳልገባ ድምጼን ሰርዥ ግን አገራዊ ጠቃሚ ነገሮች እንዲተላለፉበት አደረኩት። የስልት ለውጥ አደረኩኝ ማለት ነው።

ይህ ምን ማለት ነው ወዘተረፍ ፈተና ነው ያለብን። አሁን በሩ ተዘግቷል። በመስኮት መሞኮር ነው። መስኮቱ ሲዘጋ ደግሞ በጣሪያ። ጣሪያው ካልተቻለ በመሬታ በታች፤ ስልትን መቀዬር ይገባል። ፊት ለፊት መጋፈጥ ለጉልበታም አመክንዮ ይገባል፤ አዳራሽ ተከለከልን ብሎ ግን የተገባ አይደለም።

አብሶ የአማራ ድርጅ ዙሪያ ገባው በፈተና የታጠረ ነው። እጅግ ውስብስብ ነገር አለበት አማራነት። ስለዚህ ጥንቃቄ፤ ማሰተዋል፤ እርጋታ፤ ስክነት፤ የደረጀ መንፈስ፤ መቻል፤ ማሳለፈ፤ መታገስ፤ በቅንነት ማዬት፤ አሉታዊ መሆነ ይገባል። 

ብዙ ቀናቶች ወደፊት ይመጣሉ ይሄዳሉ እግዚአብሄር የወደደው ቀን ሲመጣ ነው ጠቃሚው ነገር የሚገኘው። ፈጣሪ ያልፈቀደው ነገር አለ፤ ሁሉ የሆነው ለበጎ ነው ብሎ መቀበል ያስፈልጋል። አሁን አብን ያለውን ተቀባይነት ስንቶች በስንት ዘመን ያላገኙትን ነው ያገኘው። ዕድለኛ ነው አብን። ዕድለኝነትን ግን ባግባቡ ካልተያዝ ምርቃቱ ይነሳል።

ብዙ መልካም ነገሮች ናቸው ያሉት። መልካሙን እያደነቁ፤ መልካሙን እያከበሩ፤ ቀሪውን ደግሞ በታገሰ ጥረት በጥሞና መትጋት ይጋባል ባይ ነኝ። ሲጠቃለል የአሁኑ የአብን የሰላማዊ ሰልፍ ፍላጎት አስፈላጊም፤ ወቅታዊም፤ አይደለም። መከራን የሚያጭ፤ የሃይል አሰላለፍን ለውጦ ሌላ የማይጋፉት ጉልበታምን መጠራቅቅን መመኘት ነው። ፖለቲካ ከባድ ነገር ነው። ዘው ተብሎ ተገብቶ ዘው ተብሎ አይወጣበትም። ጠንቃቆች ፍላጎታችን አቅበው ገበረው የሚዘልቁበት ነው።
  
አሁን በዛ ሰላማዊ ሰልፍ ብዙ አይነት መፈክሮች ሊመጡ ይቻላሉ? ያልታሰቡ፤ ያልታቀዱ፤ መቆጣጠር አይቻልም። የሌላ ድርጅቶች ፍላጎት ሁሉ ሊወጡ ይቻላሉ። ሰላማዊ ሰለፍ ገብያ ማለት ነው። ሲያልፍም እንደ ሳሙና አረፋ ወይንም ጤዛ ማለት ነው። 

የችግር ከሆነ ምን አለ ቢደረግ? ለአዳራሽ ግን የተገባ አይደለም። መገለልን በሚመለከት መረጃዎችን በጥሞና ማሰባሰብ፤ በመረጃ በተደገፈ በሚዲያ መሞገት። አንቸኩል ነው እኔ መልዕክቴ። እዮባዊነትን መሰነቀ መልካም ነው። በራሱ ጊዜ የመሰጠው ትሩፋትም ስላለ። ማንም ሰው ይሁን ድርጅት የተሰጠውን ምርቃት ለመልካም ካላዋለው ምርቃቱ ካለ ይግባኝ ሰጪ ያነሳበታል። 

ትእግስት ካሰቡት የምታደርስ በቅሎ ናት!


የኔዎቹ የአብን ኢሜል ያላችሁ ብትተባበሩኝ ድምጼን ብትልኩላቸው፤ ፌስ ቡክ ያላችሁም ብትተበባሩኝ አመሰግናችሁ አለሁኝ። ኑሩልኝ። መሸቢያ ጊዜ።


አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።