ቅዱስ ሲኖዶስ ስንቱን የቅድስና እረኝነቱን አግልሎ ሊዘልቀው ይሆን?

 

 May be an image of 1 person and textMay be an image of 3 peopleMay be an image of 8 people and text
 
ቅዱስ ሲኖዶስ ስንቱን የቅድስና እረኝነቱን አግልሎ ሊዘልቀው ይሆን?
"ከነገር፡ ሁሉ፡ አስቀድሞ፡ ሄኖክ፡ ተሠወረ።
ከሰውም፡ ልጆች፡ በተሠወረበት፡ ቦታ፡ ሳለ፡
የሚያውቀው፡ አልነበረም፡
ይሙት፡ ይዳንም፡ የሚያውቅ፡ የለም።
ሥራው፡ ሁሉ፡ በተሠወረበት፡ ወራት፡
በቅዳሴያቸው፡ ከሚተጉ፡ መላዕክት
ጋርና፤ ከቅዱሳን ጋር ነበር።
(መጽሐፈ ሄኖክ ምዕራፍ ፬ ቁ ከ፩ - ፫)
የፀጋ // የበረከት /// የምርቃት /// የቅብዓ // የትንግርት// የትንቢት// የመሰጠት// የምኞት // የራዕይ// የቅዱሳን// የደናግል፤ የሰማዕታት፦ ባዕት ፍልስፍናዊት ኢትዮጵያ የእኛ!
ቅድስ ሲኖዶስ ዬቅዱስ ላሊበላን ብጽዕና፤ ልዕልና ሞገሥ እና ግርማ አግልሏል።
ቅዱስ ሲኖዶስ የቅኔው ደብረ ኤልያስ ገዳምን ሰማዕትነት አግልሏል።
ቅዱስ ሲኖዶስ የቅዱስ ደብረ ማርቆስን #ካስማነት አግልሏል። እንዲህ በሁለገብ ሸፍት ቅድስናው ሲስተጓጎል??? ዝምታ???
ቅዱስ ሲኖዶስ እያንዳንዱ በዕት የሊቀ - ሊቃውንት መፈጠሪያ የሆኑትን መላ የአማራ ክልል ገጠራም ቅዱስ ባድማወችን አግልሏል።
ቅዱስ ሲኖዶስ የሻሸመኔን ሰማዕታት ገድል እና ታምራትን አግልሏል። ከዕጬጌው ጀምሮ ብፁዓኑ እዛው ሄደው ጉባኤ ሊያካሂዱ ይገባ ነበር። ግን በነበር ተከዘነ።
ይህ ማለት ቅዱስ ሲኖዶስ አስተዳደራዊ ተግባሩን እንጂ የዶግማውን መተግበሪያ ቋቱን በሚመለከት ዝሏል።
ለዚህም ነው ብፁዓንወቅዱሳን አባቶቻችን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚገናኙበትን መሰላል መዘርጋት ግድ የሚላቻው። የወሉ ወይንም የጋራው ሱባኤ ሳይሆን ለእኔ ከሊቅ እስከ ደቂቅ አቨው ብፁዓን ሊቀ ጳጳሳት ገዳምን በሱባኤ የሚያገኙበት ትልም ሊኖራቸው እንደሚገባ ይሰማኛል።
የተከበሩ ፕሬዚዳንት ሳህለ ወርቅ የንስኃ አባት ሊሆኑ አይችሉም! ፈጽሞ! ግን ኃይማኖትስ አላቸውን ፕሬዚዳንቷ??? ወይንም ወ/ሮ ሙፍርያት ካሜል ይሁኑ ወሮ አዳነች አቤቤ #ለሚሊዮን የኦርቶዶክስ ተዋህዶ በጎቻቸው እረኛ ሊሆኑ አይችሉም። መንበሩን በአንስት ሲያስጠቀጥቁት መንፈሴ ቆስሎ - መግሏል። አልደብቀውም።
ወይንም ከወንጌልም ከቁራንም ከዩንቨርስም በላይ #ላዕላይ ነን የሚሉት ሌ/ኮ ጠቅላይ ሚ/ር የዓለሙ ሎሬት፤ የዓለሙ የሰላም አባት¡¿ አብይ አህመድ እጬጌያቸው አይደሉም! ነገርአለሙ ውጥንቅጡ ወጥቶ እንደ ላንቁሶ ውኃ ተዝለግልጎ ቅልቅል እና ግጥግጥ ላይ ነው።
በመፍረስ ውስጥ፤ መደርመስን መፍረስን ቀርቶ #መናድን እንኳን #ዕውቅና አለመስጠት የመንፈስ ቅዱስ ቅርበት ወይንስ ርቀት ይሆን? ጓዘ ቀላል ጥያቄ ነው። ዬ አገር ውስጡ እና የውጬው ሁለቱ ቅዱስ ሲኖዶስ እርቅስ በጋራ ለስለቃ ወይንስ ለድህነት???
አንድ ነገር ትዝ አለኝ ብፁዑ አባት አቡነ ናትናኤል ትግሉ በቋንቋ መማር ከነበረ ስለምን ወደ አሜሪካ ተሰደዱ? እሳቸውም ተገልያለሁ ባይም// ሊሉ ይችላሉ።
ለእኔ ግን አይደለም። የቁጠባን መርህ የ፬ ኪሎ አስተዳደር ሂደት ነው ልክ ኢንጂነር ታከለ ኡማ እንደተላኩት። ቆጥበው ቀን ጠብቀው መዥለጥ ነው። ዕድሉ ለቀጣይ የዶክትሬት ትምህርት፣ ለመማርም፣ በህይወት መትረፍም፣ ዕውቅናም፣ የደህንነት ዋስትናም ይሰጣል። ኢኮኖሚካሊም ያደረጃል።
እኛ ግን ባሉን አበው ቁጠባው ቀርቶ ዘለፋው እና ግለቱ በታቀብንበት። አንድ ብፁዑ አቡነ ኤርምያስን የክፋ ቀን አብርኃምን እንሆ እናሳድዳለን???
ብቻ ማህበረ ኦነግ በለጡን። ትግራይ ገና ከዊዝደሟ ደረጃ ብቅ አላለችም እራሷን እዬተዋጋች ነው። ለመሠረታዊ ንቅለቷ አታሟ አሰናጅ ሁናለች ።
አገር መምራት እንዲህ በዝልኝ አባቶቻችን ቀደምቶች አልነካካቸውም። አገር ከነልዕልዕናው እና ልቅናው የዘለቀው በዊዝደማቸው ጥልቀት ብርቱ ጥንቃቄ እና መሰጠትም ነው። ነው። አንድም ቅንጣት ከሚስጢሩ ጋር የተገናኜ ዬተጋሩ ሊቅ/ ሊሂቅ አላዬሁም። አላዝንም። የመንፈስ ቅዱስ ኃላፊነት ስለሆነ።
ለመሆኑ ብፁዑ ወቅዱስ አባታችን ፓትርያርከ ዘኢትዮጵያ አባ ማትያስ ጎንደር ጥምቀትን አክብረው ያውቃሉን????
የተማሩትም #የፕትርክና !#ትንቢት የተነገረላቸው እኮ ጎንደር ርዕሰ አድባራት ከሊቀ ሊቃውንቱ ቤተ መንክር፤ መዳህኒዓለም ቤተክርስትያን ከተማሩበት ባዕት ነበር።
የፕትርክና ትንቢት ከተነገረበት ቅዱስ ሥፍራ ቅዳሴ መርተው ማስቀደስ ሁሉ ይገባ ነበር። ባዕቱ ሳይሆን ቅድስና የከበረበት ትንቢት በእርግብ አምሳል ተገልጦ የተነገረበት በዕት ነውና። ሚስጢር ሲተረጎምም ሲመሳጠርም ይህ ይመስለኛል። ለመነኩሴ እርሱቱ ሰማይ ብቻ ነውና። ዘመደ አዝማዱም ሁሉም ደግነት እና ቸርነት።
ያከበረን፦ ያስከበረን ባዕት በጎሪጥ ሳይሆን በአካል ተገኝቶ ማመስገን ይገባ ነበር። ምን አልባትም የፈተናው ትብትብ ሊገለጥም ይችል ይሆን ነበር። ሚስጢር መገለጫው የተመረጡ ቦታወች፤ ተራራወች፤ ወንዞች እና ሸንተረሮች፤ ዋርካወች እና ባንባወች፤ ሾላወች እና ……… እንሰሳትም ሊሆኑ ስለመቻላቸው ታቦርም፣ ጎለጎታም፣ እርግብም ቃለ ህይወቱ ተክኖበታል።
የሆነ ሆኖ ቅድስት ቤተክርስትያናችን #ውሉ እና ቃል ኪዳኗ #ልዕልና ልቅናዋ፣ መሪነቷ እና #ክብሯን በልኩ ለልኩ ማድረግ እንዲሳናት #የ፬ ኪሎው የፒኮክ ሊቀ- አለቃ እንደ ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ሚኬኤል የሚታዬው፤ ለአገላለፁ ቃሉ ከማይገናኝ ጋር ስለፃፍኩት ብቻ ይቅርታ በትሁት መንፈስ እጠይቃለሁኝ። ፒፖካዊ አምልኮት ከኢራቅ መጥቶ #የተደነጎረበት ጉዳይም የዶግማዋ ተፃሮ ስለመሆኑ ዕድምታውን የፈራችው ይመስላል።
ይህ በተፈራ ቁጥር ፀጋ በረከት ……:እረድኤት እና ትሩፋትምምርቃትም በጠኔ ይመታል። አናብስት፤ እርግብ እና ሰብ፤ እንዲሁም የወተት እና የአጋይስት ዓለሙ ዙፋን ተሸካሚወች በጠራራ ጠኃይ ሲወገሩስ? ሲነዱ ሲቃጠሉስ?
#እሸታዊት የእኛዋ ልዩ ናት።
የእኛዋ እሸት ናት። የእኛዋ ሁሉን የሰጣት ናት። ያቃታት ዘመንን የማንበብ፤ የመተርጎም እና የማመሳጠር አቅም ይመስለኛል። ነው አላልኩም። አልወጣኝም። ኧረ ምን በወጣኝ??? ይመስለኛል ነው።
ዛሬ አልተኛሁም ቁጭ ብዬ አደርኩኝ። ዓይኔ ቅል ሆኖ አባብጧል። ይገባዋልም። በቃ ፈቃዴን ጥሶ ፍሎ ይዘንባል። ይገባልም። የቅዱስ ላሊበላ ካህናት ጉዳይ ከአንጀቴ ገብቶ ተላወሰ። ለካንስ የቆሎ ተማሪወች በገፍ እስር ቤት ገብተዋል??? አልተኛም። እስካሁንም አልተኛሁም። ፈጽሞ!!!! ተግ ማለቴ ለጥሞና ጊዜ ለመስጠት ነው። እንጂ እኔ የግፍ ዕንባ በምድሬ እስኪቆም ድረስ እራሴን ወክዬ በተከታታይ እና በትጋት እተጋለሁኝ።
#የሆኖ ሆኖ ለዛሬው ………
ምክንያቴ አቨው ዘመኑን የተረዱበት መንገድ እጅግ አሳሳቢ ደረጃ በመድረሱ ነው። ከ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጋር ዘምኖ የመጣን ሊቀ #መንጦላዊትን በዚህ ለዛለዞ፤ አልፎም የማሽሞንሞን እና አራጊ ፈጣሪ ዬማድረግ አያያዝ ውኃ ያዘለውን ጥልማሞታዊ ተራራ ትልሙን መግራት የሚቻል አይሆንም።
ዳር ዳሩም ቢሆን እንዲሁ። #ውጊያው የእናት ቤተክርስትያን #ቅድስናዋን #ክህነትነቷን ነው። ስለዚህ የሚመክት የዊዝደም ጎዳና ያስፈልግ ይመስለኛል።
ይህ ኃይል ለአህጉራችን ለአፍሪካም፤ ለዓለምም አምላክ አለኝ ብሎ ለሚያምነው ክርስትናም እስልምናም የሚመለስ አይሆንም። ለዚህም ነው ጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ ደፍረው የጀመርነውን የመጨረስ አቅም አለን የሚሉት። ውጊያው የጨለማ እና የብርኃን ይሆናል። ትግሉ ትብትብ ነው።
አበው ፀሎታቸው ሱባኤያቸው በምድራዊው ስሌት ሳይሆን ጨለማን ሊመክት በሚችል ገዳማዊ ሱባኤ ሊሆንም ይገባል። የክፋ ቀን ደራሹ ምዕመን ብቻውን መከራን፤ ራህብን ጥማትን መገለልን ብቻውን እዬተቀበለ ነው። ዓውደ ምህረት መንበሩ ባለበት መሃል አዲስ አበባ ላይ ክህነት በባሩድ ሲነድ ቅዱስ ሲኖዶስ የት ላይ ይሆን መነሻው? መድረሻውስ?
#የወጨፈው ሂደቱ ………
1) የትግራዩ ጦርነት መቅድሙ አክሱም #ጽዮን ላይ እናቱ ላይ ተቃጣ???
2) የጎንደሩ ጦርነት ደብርብርኃን ሥላሴ መዋጊያ ዋሻ አዳም ሰገድ እያሱ ታቦት የተሸከሙለት ነበር፤ ነዳያን ፍሪዲ ተጥሎ በክብር በሊቀ ሊቃውንታት ተደግድጎ አብርኃሙ የሚበራበት ቅዱስ በዓት ኦነግ ምሽግ አድርጎት ነበር፣ የዘንድሮ ጥምቀት የቀኑበት፣ የተርመጠመጡበት በምን ሁኔታ ይከበር ይሆን??? ጣና ገዳማትም ዘመን መሰካሪ በአፅዋማት ፍሪዳ ታርዶ አስረሽ ምቺውም አለበት????
በደብረ ብርኃን ስላሴ ዙሪያውን ያሉ እንቁላል አግናባት በእኔ ዕድሜ የእጣን ዓውድ ነበራቸው። ጉሬዛ እሮብ እና አርብ የሚፆም ነበረባቸው። ጠጅ እሳር እና ሪያን ሙሉ በጋ እና ክረምት መለያው ነበር። ወይራ እሸትን ጨምሮ።
3) የጎጃሙ ውጊያ ደብረ ኤልያስ የመነኮሳት የጅምላ ፍጅት እንደ ዘበት ታለፈ። የንዋዬ ቅድሳት አመድነት ተፈቀደ። የጥንታዊነት የቀብር ሥርዓት ጉሮ ወሸባዬ ተባለለት። እርግማኑ ከተቻለ???
ቅዱስ ማርቆስ ላይ የሊቃናት ቅኔ አናትስ እንደ ሰማሁት ቅርስነቱ ከደብርብርኃን ሥላሴ ጋር የትውፊት ውርርስ አለው????
4) ወሎ ቅዱስ ላሊበላ ላይ የሥልጣኔ ጉልላት???? የዓለም ብሌንስ? የላስታ ላሊበላ የደሥታ፤ የሰማያዊ ህላዊ ሐሴቴስ መገፈፍ? ይህ ክብሯ ይሆን ለእናት ቤተክርስትያናችን?።??
ዲያቢሎስ ለአንድ ማዕልት ዕድል ቢሰጠው ከሚያደርገው ውጪ ሙሉ ፭ ዓመት ኢትዮጵያ ምድር ተከናውኗል። ገበርዲን እና ሱፍ የለበሰ #ኢትዮጵያዊ #ፀላዬ #ሰናይ ቅድስት አገር ኢትዮጵያን የመምራት ዕድል ሲገጥመው በአንድ ቀን ጅጅጋ ላይ ፱ አብያተ ቤተ ክርስትያንን አሹጎ፦ አስታርቆ ላስገባቸው አቨው ሥጦታ ሲያቀርብ አመድ እና ተስፋ መንሳት ጎዳናው ረመጥ ነው በዚህ ሜዳ ፍልሚያው ይካሄዳል ነበር ሚስጢሩ።
ለዛ ብቻ ሱባኤ ያስፈልገው ነበር። አይደለም የዝዋይ፤ የሻሸመኔ፤ የአርሲ ነገሌ፤ የሐረር፤ የአጣዬ፤ የጅማ፤ የሽዋ ሮቢት፦ የወይብላ ማርያም፦ የአዲስ አበባ፤ የቡራዩ፤ የለጋጠፎ ለገዳዲ፤ የሆሳዕና፤ የባሌ ታክሎበት። ትግራይ ገብቶ አክሱም ጽዮን ላይ ሰይፍ ሲያነሳስ???
ይህም አልበቃም ሙሉ ሦስት ዓመት አማራ ክልል በመድፍ፤ በድሮን ሲታረስ ሰፊ መባ አቅራቢው፤ ሊቃውንት የሚያፈራው፤ በዓመታዊ ንግሥ ቦታዋች የሚገኜው በረከት እና ምርቃት ሲራቆት፤ የቱሪዝም ፍሰቱ ሲታገት፤ ለአማራ ክልል ባህል እና ቱሪዝም፤ ለኢትዮጵያ ባህል እና ቱሪዝም ምደባ ሴራ እና ሲኦል አና ሲል እናት ቤተ ክርስትያን ጉዳዮዋ አልሆነም። ለምን????
አንድ ጠቅላይ ሚር፤ ሁለት ምክትል ጠቅላይ ሚር፤ ፳ ሚኒስትራት፤ ከ፳ ያላነሱ የጠቅላይ ሚር አማካሪወች ውስጥ ምን ያህሉ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ልጆች ናቸው? ከሥልጣን እንዲነሱ ከተደረጉት ፭ አንባሳደሮች እንኳን የተዋህዶ ልጆች ኢላማ መሆናቸው እናታችን ልብ አላለችውም። እሧ የሚያንገበግባት የዞግ እና የጎጥ የሥራ ድልድል እና ምድራዊ ኮታ?????
በምክትል ሚ/ር እነት ከሁለት አንድ ድርሻ የላትም። ይህ ዕውነት ነው። በሚዋቀሩ ብሄራዊ ሆኑ ክልላዊ መዋቅራት ሁሉ በኮሚቴ እና በኮሚሽን ውክልና ምን ያህሉ ድርሻ ተሰጥቶኛል አጀንዳዋ አይደለም ክብርት እናታችን ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ። ደቡብ እና ኦሮምያ፣ ጉምዝ እና ሱማሌ ክልል አይታሰብም አማራ ክልል እና አዲስ አበባ ሽሚያ ላይ ናቸው ቦታውን ሁሉ በመጠቅለል። ይህንንም ያስተዋለው የለም። የደብረብርሃን፣ የደሴ፣ የባህርዳር የጎንደር ከተማ የከንቲባወች ምደባስ፤ በዬጊዜው ሹም ሽርስ ምንን መሥፈርት ያደረገ ይሆን????
እናት ዓለም ገራገሯ ተዋህዶ የፖለቲካ ሥልጣን ወና ሆኖ እንደምንስ አገርኛ ዜጋ ነኝ፤ ሁኛለሁ እንደምትችል ትመርምረው። ኢትዮጵያዊ ዜግነቷ ከላዮዋ በድፍረታዊ ስልት እና ዝለት መገፈፋንም አላስተዋለችውም። አሳቻ መሪ እና አሳቻ ዘመን ላይ ስለመሆኗም???
ለነገሩ እዮቢዊቱ እናታችን ተዋህዶ ሊቀ - ሊቃውንቷንምየዕውቀት ቀለ ቀንዲሎቿን የምትፈራ፦ የሚያርዳት በመሆኑ የራሷን አካል ሰብስቦ ጉባኤ አንግሶ የመንፈስ ቅዱስም የምርቃት ጥሪ ለማድረግም አልደፈረችውም። ግድፈትም ካለ ለመታረም ከህሊናወቿ መሰናዳት ይገባ የነበረ ይመስለኛል። ውንብድና ሽፍትነት መፍቴሄ ነው ተብሎ ሲቆምስ፤ ሲጰጵስ ሊቀ ሊቃውንታት በአርምሞ እና በተደሞ እዮርም አዘቅዝቆ ይመዝናል።
ይህም ብቻ አይደለም። የተፈናቀሉ ልጆቿን በቋሚነት የምታጽናናበት ተቋምም አልፈጠረችም???? ካንፕ ሁሉ ማደራጀት ይኖርባት ነበር። አወና። ሚሊዮን ልጆቿ ቀን ባህሩር ሌሊት በመርጋማ ተስፋ ማጣት፤ በጋ በሃሩር፤ ክረምት በሰቀቀን ባለቤት አልባ ካለ ባሊህ ባይ ይባዝናሉ።
ዕምነት ሳትለይ የሁሉም መጠለያነቷን ማስከበር ተሰጥቷት ነበር ለዚህ ምፃታዊ ዘመን። ግን አቃታት። አቅም እያላት። አቅመ ቢስነትን ተደፋሪነትን ፈቀደች። ለምን???
በአማራ ሥም እስር ቤቱን የሞላው የራሷ የጉባኤ አባል ስለመሆኑም፣ መባ የሚያስገባ፤ አስራት የሚያስገባ፤ አደግድጎ የሚያገለግል ግርማ እና ሞገሷ፤ ማዕረጓና ጉልላቷ አገልጋዮዋ ስለመሆኑ በኽረ ጉዳዮዋ አይደለም።
የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤዋን ፀሐፋዋን መርጌታ ብርኃኑ ተ/ ያሬድን ከጉያዋ አውጥቶ፣ ተዳፍሮ ለካቴና አስረክባ ተግባሯን በድሎት ከውና መግለጫዬን አዳምጡልኝ ብላለች። ታሥራ ነፃ እንደሆነች ሁሉ? ሎቱ ስብኃት! ማህከነ! እግዚኦ ተሳህለን! አቤቱ ማረን! ማረን!
አገር ያበጀች፤ ዕውቀት የፈጠረች ግን ተንቃ፤ ተቃላ፤ ተገላ መኖርን እንደ ፀጋ አደግድጋ የተቀበለች ምስኪኔታ ብትኖር ኢትዮጵያዊቷ ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ናት። ቀንድነቱ ቀርቶ ጅራትነት እንኳን ያልተፈቀደላት። ሥርዓት አልበኝነትን መዋጋት፤ የቅኖና ጥሰትን መጠዬፍ ዛሬ ዛሬ ብርቅ እዬሆነ፤፦
ግን አዋጄን ብቻ ተቀበሉ ብቻ እና ብቻ ሆኗል መለከቱ። ዘመን እና ምርቃት በአልተግባብቶ እዬተመሙ ነው። ነገስ? አማኑኤል ይወቀው እንዳልል እሱም በመድፍ እዬተቀጠቀጠ ዲያቢሎስ ይድረስለት ካልሆነ በስተቀር እራሱን ለማዳንም???? የላስታ ላሊበላ የካህናት ዕንባ እና ምሬት የነገረን ትርጓሜውን ባልችልም፤ ባይሰጠኝም ንባቡ ያነን ያመለክታል።
የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤ አካላት ነነዌን ምን አለ ገዳማት ውስጥ ቢያሳልፋ? ከዓለም ጋርስ ተፋተው ቢሰነባብቱስ? ይህ ሁሉ ማዕት እዬወረደ ለምህረት አንድም ሊቀ ጳጳስ ገዳማትን አልተለሙም። የበደሉ ስለበደሉ ተሾሙ ተሸለሙ። የክብር ተክሊል ተፈቀደላቸው።
ንጉሥ ላሊበላ ብቻ ሳይሆን ቀደምቶች የኢትዮጵያ መሪወች ነግሥታት መንበረ መንግሥታቸውን ሁሉ ትተው ምናኔ ገብተዋል። በቅዱሱ፤ በድንግሉ በሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ "የይበቃኛል" ዶግማ ተመስጠው፤ ተከርክመው፤ የማይደፈረውን እዬደፈሩ፤ ንግሥናን ፕትርክና ከቅድስና እና ከሰማዕትነት ጋር አዋህደው ጥሞቸውም እዮራዊ ጽዑም ቃናን የተቃኙት። የእነሱ በረከት እና ረድኤትም ነው እኛን ያቆዬን። እኛማ ለእንጥፍጣፊም ያልበቃን #ሙጣጮች ሆነናል። ፈቅደን እና ወደን።
///የተለዬ ዕይታ ///
በዓለም ያሉ አሸባሪ ድርጅቶችን፤ የአገሮች አለመረጋጋትን፤ ፀረ ኃይማኖት ንቅናቄወችን ሁሉ ጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ አሊ በመንፈሳቸው ይደግፋታል። ምክንያቱም የአቅማቸው ምንጭ ያ ስለሆነ። እንደገናም ዓለም ትኩረቱን ወደዚያ ሲያዞር የአፍሪካን አንከር የጥቁሮችን ርህርርህት ኢትዮጵያ የመንቀል ፋታ ያገኛሉ። አማራን የመረሸንም። ተዋህዶን የማሳደድም።
አሁን በዩክሬን እና ራሽያ ጦርነት፣ በእስራኤል እና በሃማስ ጦርነት፤ በደቡብ እና ስሜን ሱዳን ጦርነት እንደሳቸው ሐሴት በልቡ ያገኜ መሪ ይኖራል ብዬ አላስብም።
ኮረና ሲመጣ የትልሜ ማስፈፀሚያ ብለው ጮቤ የረገጡበት ጊዜ ነበር። ታስታውሱ ከሆነ ላስታ እና ጎንደር ሠራዊት ያዘመቱት ያን ጊዜም ነበር። ዕድሜ ለአክቲቢስት ሙሉነህ የኋንስ ሞግቶ ፒትሽን አዘጋጅቶ አስገታቸው። ላስታ እና ጎንደር በኮረና ወረርሽኝ እንዲጠቁ አቅደው ሠርተዋል። ትናንትን ስለምንረሳ ነው።
ብፁዑ አቡነ ኤርምያስ አጽናኝነት እና ሞገስ ሲያስፈራቸውም በሳምንት ሁለት ጊዜ ሰቆጣና ኮንበልቻ ተገኝተው ህይወትም መንገድም እኔ ነኝ ብለውም ነበር። በወቅቱ ጽፌበታለሁኝ።
አባት ብፁዑ ኤርምያስ ቅንነቱ አሸንፎዋቸው ይህን ያስተዋሉበት ጊዜ ያለም አይመስለኝም። ያን የህዝብ ፍቅር ትቢያ ማልበስ የጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ በኽረ ተግባር ነው። ቅድስታችን ፈተና ስትገባ ፈተናው በዊዝደም መያዙ ጎረበጣቸው ከዛ በስል ገብተው ከሠራዊቷ ቅድስታችን እንድትነጥል ሌት እና ቀን እዬተጉ ነው።
የጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ ሐሴታቸው የእኛ መከፋት፤ የእኛ ማዘን፤ የእኛ መጎሳቆል፤ የእኛ መራቆት፤ የእኛ ተስፋ ማጣት፤ የእኛ በጨለማ ስንማቅቅ ማዬት ነው።
ስንት የአማራ ብቅ ያሉ ልጆች ወላጆች በግርዶሽ ዘመቻ እንደፈጁ አንድዬ ያውቀዋል። ወራት ሳይሆን በጥበቡ ለደቂቃም ሊቆዩ የማይገባቸው ቁልቁለት ነው ኢትይጵያ ላይ ያሉት። ከሥልጣን ቢወርዱም ዓለም አይታ የማታውቀውን ፍጅት ፍርሻ ፈጽመው ነው ሥልጣን የሚለቁት። ለዛውም ከፈቀዱ። መርገምት።
እያንዳንዱ የፍርሻ ናዳ አዲስ ተታዳኝ ተሸክሞ አሳዝሎም ነው እዬቀጠለ ያለው። የቅዱስ ላሊበላ ክብር ድፍረት እምዬ ያልኳቸውን ብፁዕ አባት አቡነ ኤርምያስን እና በጎቻቸውን እንዴት በቀዝቃዛ ጦርነት እያረሰው እንደሆን እሰቡት፤ በአስተውሎት አስሉት።
እርቃናችን ዝልኛችን እንሆን ዘንድ ነው ጥሪያቸው። እሳቸውን ደግፈው ለሚንገዳገዱ ማይኮች ወዮላቸው። ቅጣቱ ሰማያዊ ነውና። ኢትዮጵያን #መለሞጥ የጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ አሊ መልዕክት ሰጪ ሳጥናኤል ነው ብዬ ካመንኩም ከፃፍኩም ቆዬሁ። ጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ አሊ= ቤርሙዳ ትርያንግል።
* * * እርገት ይሁን።
በድፍረት አገላለፄ ፈጣሪዬን ይቅርታ እጠይቃላሁኝ። ከአባቶቼ የሚሰጠኝ ተግሳጽ ከኖረም ተንበርክኬ እቀበላለሁኝ።
ውስጣችን እዬራደ ላይ ላዩን በቅብ ማረገድ የተፈጠርኩበት በዓት መለዮ አይደለም። በዕቴ የግንባር ሥጋ ነው። እኔም። ገና 2019 ነበር እኔ ቅድስታችን የድወል አብዮት ታካሂድ ዘንድ በተከታታይ የፃፍኩት። የተናገርኩት። ትንቢት አይደለም። ትንቢተኛም አይደለሁም። በፖለቲካ ህይወት በመኖሬ የዘመኑ የፖለቲካ ባህሪ ከቀደምትነት ጋር ጦርነት እንደሚገባ ስላወቅኩኝ ነበር። ፖለቲከኞችም አልተረዱትም። ብፁዓኑም እንዲሁ። ከአናት ጀምሮ ሥረ መሠረት የሚነቅል ማት እንደታዘዘብን ልብ ያለው እንብዛም ነው። አሁንም።
እግዚአብሄር ይስጥልኝ።
ክብረቶቼ ለዛሬ በዚህው ይከወን። ከዚህ ላይ ምንም አይታከልም። ፲፩ኛው አብይዝምን የመቃብር ሥፍራ እንዲህ ቅኝቱ ይቀጥላል።
ቸር ውለን ቸር ካደርን ነገም በሌላ ዘለግ ያለ አመክንዮ ብቅ እላለሁኝ። አብራችሁኝ ላላችሁ ለዘለቃችሁ ሁሉ ምስጋናዬ ከህሊና ክብርም ከልብ ነው። ከእንግዲህ ቁጥር ስለማያስፈልገኝ የጓደኛ ቁጥር ጊዜ ሳገኝ ሳገኝ እቀንሳለሁ። ተከታዮቼ ብቻ በጓደኝነት እንዲኖሩኝ ምኞቴ ነው። ማለፊያ ጊዜ። መሸቢያ ማዕልት። አሜንወአሜን።
ሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
22/11/2023
ወስብኃት ለእግዚአብሄር።

 

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።