ግን እባክህን አትገንግን? 80 ችግር እንደገና ግን?

ችግር በራሷ ላይ መጫን የለመደባት አላዛሯ ኢትዮጵያ 80 ችግርን ለዘለቄታ ፈቀደች።

„አንተ የዘራኸው ዘር አይበቅልም ትላለህን፤
 አንተ የዘራኸው ዘር ስንኳ ይበቅላል።“

መቃብያ ቀዳማዊ ምዕራፍ ፲ ቁጥር ፭።

ከሥርጉተ ©ሥላሴ 
07.08.2018
ከገዳማዊቷ ሲዊዘርላንድ።


  • ·      ዶቼ …

የኔዎቹ ማንም የዛሬውን ተደሞዬን አስተውሎት አልሰጠውም። ግን ደህና ናችሁን ውዶቼ? በሰሞናቱ  በሌሎች ጉዳዮች ተወጬ ነው እንጂ እጅግ በጥሞና የተከታተልኩት ዜና ነበር ባፈው ሳምንት … ያው ባነሩ ላይ ተለጥፎ ነው ያነብኩት ... 

ውዶቼ ሰምታችኋዋል አይደለም ዛሬ በዚህ „ ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ ዘመን አዲስ ሌላ ፈተናም መደገኑን። "የኦሮሞ ተማሪዎች ማህበር ተሰመረተ" የሚል ዜና አንብቤያለሁኝ። የኖረው የ43 ዓመቱን ዳገት መውጣት ተስኖን ሌላ አዲስ መከራ ደግሞ እዬበቀለ ነው። 

በሌላ ፎርም እና ይዘት። ነገ የአማራ፤ የትግሬ፤ የጉራጌ፤ የወላይታ፤ የኮንሶ፤ የኩናማ፤  ከንባታ፤ የሃድያ፤ የአፈር፤ የሀረሬ ወዘተ 80 የተማሪዎች ማህበር ደግሞ ይመሠረታል። ይህ ለምን ተፈለገ የሚለው ራሱን የቻለ አምክንዮ ነው።

የኦሮሞ ተማሪዎች ማህበር ከመፍጠር ይልቅ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማህበር መፍጠር የተሻለ ነበር። ይህም ቢሆን አስፈላጊ አይደለም። የመማር ዕድል የሌላቸውን ወጣቶች አግላይ ነው። ጨቋኝ ነው። በዚህ መሥመርም ነው የኢህአፓ፤ የሻብያ፤ የወያኔ፤ የመኢሶን፤ የደርግ ሁሉም መከራ የመጣው። ያን ዛሬ ላይ እንድገመው ደግሞ ተብሏል።
  • ·      ርም በግራሞት።

ስለምን ይሆን „የኦሮሞ ተማሪዎች ማህበር“ ምሥረታ ዛሬ አስፈላጊ የሆነው ይሆን? ወደ ኢትዮጵያዊነት ለመምጣት ያቀተው ነገር ምንድ ነው፤ አሁንም ከዞግ ተኮር ለመውጣት የተሳናው ነገር ምን ይሆን ሚስጢሩ? ይሄን አብይ መንፈሱ ኢትዮጵያ አይደለም ለምትሉት ወገኖቼ ማያያዣ ማስትሽ እዬሰጣሁዋችሁ አይደለም። 

መረጃዎችን በበቂ ሳቀርብ ስለባጀሁኝ አብይ ሰውኛ ስለመሆን ለሰከንድ እኔ ጥርጣሬ የለኝም። በተከታታይም አስፈለጊ ከሆነ እሰራበታለሁኝ። ፈተናዎቹ ግን ዳገት እና ዳጥ የሆኑ ይመሰላሉ ኦሮምያ ውስጥ ... የክልል ፌድራዚም ቢፈርስ፤ አራቱ ግንባሮች ህብረ ብሄራዊ ቢሆን? ወይንም አንዱ አሻኝም ብሎ ቢገነጠል፤ የተገነጠለው ሌሎችን አስተባብሮ ደግሞ ዳግም ቢነሳ መጠበባቂያ ክንዳ ይሆን? 

አስገዳጅ ሁኔታዎች እንዳሉ የማስተውለው አለኝ።  አንዱን ለመታገል ሌላ ማስተዛዘኛ ስለምን እንዳሰፈለገ በግል ቢገባኝም ግን መፈተሽ ስለላበት እንሆ ግን እንሆ ነው? በግን የተንቆጠቆጠ። ግንን ሳለገነግን በልስልሱ … ያው ልስሉስ ያደረገኝ የአብዩ ስብዕና  እንጂ ቃሎቼ ቦንቦች ነበሩ። ዛሬ ዛሬ እጅግ ተጠንቅቄ ነው የምጸፈው የአዲሱ የለውጥ መንፈስ ዝንባሌን ስለምሳሳለት።  

እንባ እና ጹሁፍ እንኳን ለመጀመሪያ ጊዜ ነው ከመጋቢት 24 በኋዋላ ትናንት ፎቶውንም አክዬ የጻፍኩት … ምክንያቱም ሽግግር ላይ ከሰናይ ዜናዎች ይልቅ መርዶዎች እንደሚበረከቱ ስለሚታወቅ። … በዛ ላይ መብትና  ግዴታንም አጣምሮ በመጓዝ እረገድ አልመደብንም በፖለቲካ ተሳትፎ ላይ ለባጀነው፤ መብት አለኝ ግን ግዴታ የለብኝ¡ ነው ሞቶው …
  • ·      ፍተሻ።

„ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ ያን ኢትዮጵያዊ ሞገድ አስነስቶ ለዚህ ክብር ያበቃው ድንቅ ጉልልተ ህሊና እንሆ አስተዋሽ አጥቶ የሥርጉተ ሥላሴ ቃለአዋዲ ሆኖ ባጀ። መቼም በ27 ዓመት ውስጥ ህዝባዊ ሞገድ ካስነሱት ጉደኞቹ ሞቶዎች ውስጥ አንዱ ነበር። ለዛውም እጅግ ፈተና በወጠን ወቅት ከሰማይ ዱብ ያለልን የመፍትሄ መንገድ ነበር።

በዛ የመፍትሄ መንገድ ሰፊ የሆነ ተጋድሎ የህሊና ተካሄዶበታል። የወያኔ ትጥቅ እና ስንቅ ታጣቂውን በአንድ ጎራ አብዮታዊ ዴሞክራሲዬ ተናደ በሚል በሌላ ጎራ፤ የዞግ ሥልጣን እጬጌነት ተናደ የሚለው ሌለው፤ የጠ/ ሚር ህልመኛው በሌላው ጎራ፤ የምርኩዞች እንዴት ተብሎም ሌላው የቀውስ ቀጠና፤ አማራ መሬት ላይ ማፈንገጥ እንዴት ይታሰባል የሚለው ሌላው ሽምቅ ውጊያ ነበር። 

እንደ ሥርጉተ እንደ ጋዜጠኛ አለምነህ ያሉ ጅሎች ደግሞ "የጣና ኬኛ፤ የግዮን ኬኛ" ፍቅር ወለድ ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው ነው ከልብ ነው በማለት ይኸው አለን እንዳለን በኪዳናችን ጸንተን። የማተቦቹ ድር። አዲስ ለውጥ አዲስ ተስፋ አዲስ ዘመን እያዬን ነው በማለት አሁንም እንተጋለን።

አንዳንዶቹ ደፋር እርምጃዎች በራሳቸው ወደ ሥር - ነቀል ለውጥም ያደሉ ናቸው፤ ሽግግር መንግሥት አይሰፍለግም የሚልም እድምታ አለን እንደ ጅሎቹ ግንዛቤ ከሆነ። 

የሆነ ሆኖ „የኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ ዕድምታ አዋላጁ ዶር ለማ መገርሳም ከዛች ዕለት በስቀር ሲደግሙት ሙሉውን ሥንኙን ባይደመጡም፤ በኢትዮጵያዊነት ዙሪያ አንድነት አስፈለጊ ስለመሆኑ ሰብከታቸው ላይ ጸንተዋል። አብሶ ስሜን አሜሪካ ላይ ይደግሙታል ብዬ አስቤ ነበር። እንዳለ ከነክበሩ ከእና ግርማ ሞገሱ። ግን አፍንጫሽን ላሺ ሥርጉትሻ ሆኗል። ትልቁን የልዩነት ገደል በህሊና የናደ ነበር "ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው።"ያው ለታሪክ ይቀመጥ። 

አብሶ የስሜን አመሪካኑ ጉዞ የንግግራቸው መድፊያ ይኼው ይሆናል የሚል እሳቤ ነበረኝ፤ "የሞኝ ለቅሶ መልሶ ማላልሶ" ሆኖብኝ። ያው የሞኘቹ ነገር እንዳለው ዓለም አቀፉ ጋዜጠኛ አቶ አለምነህ ዋሴ።

የሆነ ሆኖ እሳቸው ስብከተ አንድነትን መሰስ አድርጎ እጃቸውን እንዳወጣው፤ የዘመኑ እጬጌዎች እንዳደረጋቸው፤ ፍቅርን በገፍ እንደቸራቸው አሳመረው አውቀውታል። በተጨባጭ ሳላዩትም እዬተጉለት ነው አክቲቢስቱም ናቸው። 

ነገር ግን አይዋ ግን የገነገነበት ሁኔታ ደግሞ አለ። በዋናው ማህበረሰባቸው በሚመሩት በኦሮሞ ወገኖቻችን ላይ ግን „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ የአንዲት ዘለላ ያህል ነፍስ ያልዘራ ምኩን ስለመሆኑ የስሜን አሜሪካው የሚኔያ የመንትዮሹ ጉባኤዎች ዕድማታ በአደባባይ አውጆልናል።

 በዛ ጉአባኤ በእኔ ይሁንባችሁ፤ ይህን ማስተካክል እንችላልን በማለት ብልሁ ጠ/ ሚር አብይ አህመድ  የሚችሉትን ያህል ለማስታገስ ያደረጉት ጥረት መልካም ቢሆንም፤ በዓዋጅ ኢትዮጵያዊነትን መቀበልም አለመቀበልም አለመቻሉን ግን አይተናል። እኛ የነበርነበት ነው ምንም አዲስ ነገር የለውም።

የለማ እና የአብይን መንፈስ እኛ የተቀበልነውን ያህል ቀርቶ ስለመፈጣራቸውም የተዘነጉ የሚመስሉ ትዕይንቶች ተስተውለዋል።  እነሱ ንጉሣቸው ኦሮምያ የምትባል አገር እንጂ ከዛ በመለስ ያለው ዕውነት እርማችሁን አውጡ የሚል ግልጽ እና ጽኑ አቋም ተስተውሏል።

 በምራዕቤ ዓለም አብሶ ተጽዕኖ ፈጣሪ አገሮች አገራዊ ራዕይ የላችሁም መባላቸውን በግልጽነት የተናገሩት የዘመኑ ሰብዕዊነት መሪዎች ዶር አብይ አህመድ እና ዶር ለማ መግርሳ ጣምራ ጠ/ ሚሮች ወይንም መንትዮሾቹ ጠ/ ሚኒስተሮች እንደ አብርሃም ወአጽባህ ዘመን ይህን ቁጭታቸውን ለመወጣት ደፋ ቀና ማለታቸው ለዛው ለራሳቸው ማህበረሰብ ከልቡ ጠብ ያለ ነገር አለመኖሩ አዲስ አባባ ሚሊኒዬም አዳራሽ የንጉሥ ጃዋር አሃመድ  የእንኳን ደህና መጣህልን ልዩ ብሄራዊ አንጸባራቂ መስተንግዶ አሳይቷል። በዛ ጉባኤ የታዬው የአምልኮተ ኦነግ ግልጽ ዓዋጅ ተደሞ ነው።

የእኛው ይቀር እና ይህን የሚመለከቱ የውጭ መንግሥታት በፈለገው መልክ ቅናዊ ምልከታ በጠ/ ሚር አብይ አህመድ ካቢኔ ቢኖርም፤ ሽልማቱ ቢቀጥልም፤ ልባቸውን ይጥላሉ ለማለት ግን አያስደፍርም።

 የኢትዮጵያ ህዝብ ለሁለቱ መሪዎች የሚሰጠው ፍቅር ከመጠን የዘለለ ቢሆንም፤ የውጪ መንግሥታት በተፈረሩበት ማህበረሰብ ያለው የማይነቃነቅ አቋም ሚዛን ውስጥ አያስቀምጧቸውም ተብሎ ግን አያታሰብም። ምክንያቱም ያልተነኩ፤ ያለተደፈሩ አመክንዮዎች ስላሉ።

ለዚህም ነው ሊሂቃኑ ከ እኛ ጋር ናቸው ስንላቸው የነበሩት ሁሉ ውስጣቸው ጉልጉል ብሎ በዚህ ዘመን እንድናይ የተገደደነው። መረቡ የተበጠሰ ነው። የተመሸገበት አመክንዮ ሁለቱም ማፈንገጣቸው አልተወደደላቸውም። ይህ እግዲህ ለውጪ አንድ ማስረጃ ሰነድ ይሆናል ማለት ነው። እኛ መሪዎቻችን ስንል እነሱ መሪዎቻችን ለማለት አይደፍሯትም። ከቶ እዬተግባባን ነውን? 

የወጡበት ማህበረስብ ኢትዮጵያዊ ነኝ ሳይል ሚዲያው እና ሊሂቃኑ በተለይም ሁለቱ ብቻ ተነጥለው ነን ቢሉ እጅግ ፈታኝ ፖለቲካዊ ግማድ ፊት ለፊታቸው ይታዬኛል። 

ቀደም ባለው ጊዜ የእኛ ያልናቸው እንኳን በሩብ ልብ ሳያስጠጉን የኖሩትን ጊዜ ሚስጢር ሹክ ያለንን ፈጣሪ ይመስገነው። አሁንም አዲሶችን የኦህዴድ መንትዮሽ አብርሃም ወአጽባህም  የእኛ ናቸው ልንል መቻላችን ተፈጠሯዊ ሲሆን የምዕራቡ ዓለም የቀደመ ምልከታውን አገራዊ ራዕይ የላችሁንም ግን ሙሉ ለሙሉ ይለውጠዋል ለማለት ይቸግራል። ወደል ጥያቄ ምልክት አለበትና። ራሱ አካሉ ኦህዴድ ምክር ቤቱ እልሁ እና ቁጭቱ ከዬትኛው አጀንዳ ላይ እንደ ሰከነ ራሳቸው መንትዮሹቱ ፖለቲካዊ አህትዮሽ በጽሞና እና በአንክሮ መፈተሽ አለባቸው። 

እንግዲህ ፊት ለፊት የወጡት ሁለቱ ብቻ ስለሆኑ እንጂ ኦህዴድ እንደ ድርጅት ልቡ ምን እንደሚያሰብም አይደለም እኛ ዶር ለማ መገርሳ ይሁኑ ዶር አብይ አህመድ በመዳፋችን ነው ለማለት የሚችሉበት ሁኔታ ያላቸው አይመስልም። መሬት ላይ የመነግረን ግብረ ምላሽ ይሄውን ነው።

አሁን እኮ እርሾው ሆምጣጤ ነው የሆነው። የተረጋጋ መንፈስ፤ የሰከነ መንፈስ ሁሉ ጥያቄ ምልክት በጥያቄ ምልክት እዬሁነ ነው። በዚህ ማህል በሦስት ወር ውስጥ ትኩረት ሊሰጠው የሚጋበው አጋር የአማራ የማንነት የህልውና ተጋድሎ ይፋዊ የሚዲያም፤ የአትኩሮትም ሸፋን ማጣት እና የቤንሻጉል ጉምዝ መፈናቀል በራሱ የትኩረት ስስነት ተደራቢ ዋጋ እንዲከፍሉ መንትዮሹን ቅናዊ ጠ/ ሚኒስተሮች ያስገድዳቸዋል። 

ምክንያቱም መሰረታቸው ላይ ያለው መንፈስ ብዙም የሚያወላዳ አይደለም። መቀሌ ላይ ያለው መንግሥትም ለፌድራሉ ይታዘዛል ወይ ለሚለውም ሌላው ጉዳይ ነው … የአንተ አጋር የለውጥ አስገኝ ሃይል ትኩረት ነስተህ፤ ሌላውን ወደ እኔ አመጣለሁ ታጋድሎ አቅምን የሚሻማ ተግዳሮት ነው። ወይንም የቆጡን አውርድ ብላ የብብቷን ጣለች እንዳይሆን ስጋቴ ከፍ ያለ ነው ... ደጋፊ ቅን መንፈሶች ቀስ በቀስ ነው የሚሸረሸሩት። በአንድ ጊዜ አይናዱም። ኢትዮጵውያን ደግሞ ወዲያው ነው ሆድ የሚብሰን። ቡቡ ነን ...

ለምሳሌ የሰሜን አሜሪካኑ ጉዞ ወስጥ ያደረጋቸው መንፈሶች፤ እዳሪ የጣላቸው መንፈሶች፤ ውስጥ የነበሩ ከጨዋታው የወጡ ፈቅደው መንፈሶች ሁሉ አሉ። 

በዚህ ውስጥ ተጨፍልቆ እንዳይቀር ወይንም ተድጦ እንዳይቀር ወይንም ተውጦ እንዳይቀር መትጋት ያለበት አማራ መሆን አለበት። ይህም ማለት በተደራጀ የህሊናዊ ብቃት ሙሉ አቅሙን፤ በተደራጀ አኳኋን በአገራዊ ራዕይ እና ቁጭት አቅሙን አስተባብሮ በመንፈስ ቆቅ ሆኖ መገኘት አለበት። ሁሉንም አቀጣጫ የእኔ ብሎ የመከታተል ታሪካዊ ወቅት ላይ ይገኛል አማራ። 

ስለዚህ አማራ ሁሉንም በልክ አድርጎ ጅግራ ሳይሆን ቆቅ እና እርግብ ሆኖ መጠበቅ ግድ ይለዋል።  
  • ·      የወቅት ስጦታ ሽልማት ነበር … ቢሆን ቢሆን

የዚህ ችግር ዓይነታ ጉዳይ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ በነበረን ውስጥ ላይ ስለነበር እኛ ለመቀበል፤ የስንኞቹ የአራቀረብ ወቅት ካልሆነ በስተቀር በእኛ ውስጥ ኢትዮጵያዊነት አብሮን የተፈጠረ ስለነበር አዲስ ገብ አልነበረም። ወይንም ተደባይም አልነበረም፤ ስለሆነም የአገላለጽ ዘይቤውን የእኛ አድርጎ ለመውሰድ አፍታ አልወሰድብንም። 

ጭንቁ ይህን መሰል ሞገድ እዛው ኦሮምያ በቁቤ ትውልድ ውስጥ ምንም ያልተሠራበት መሆኑ ነው። ዶር ለማ መግርሳ አምጠው የተናገሩትን ወርቅ መንፈስ እንደ መርህ ወስደው ስለልተጉበት ሊሆን ይችላል በሚመሩት ማህበረሰብ ዘንድ ከልብ የገባ ጉዳይ አለመሆኑ እዬታዬ ያለው። 

ሌላው ቀርቶ ዶር ለማ መግርሳ ራሳቸው አዳማ በተገኙበት የኦሮሞ ወጣቶች ስብሳባ ላይ ወጣቶቹ የነባራቸው ገጽ እኛ ለለማ መንፈስ ከሰጠነው ክብር፤ ናፍቆት፤ ስስት ጋር በፍጹም አይገናኝም ነበር። እንዲያውም አስደንጋጭ ጥያቄ ነበር ያነሱት ስለ የምርጫ ተርም ጉዳይ። 

በሌላ በኩል ደግሞ የደንቢ ዶሎውን የጠ/ ሚር አብይ አህመድ ጋር የተደረገው ውይይት ደግሞ የመርዶ ጉባኤ ነበር። ስለምን መጣችሁብን ዓይነት ነው የነበረው። ደንቢ የምትፈልገው የደንቢ ደሎ ነጉሥን እንጂ ሌላ ማዬት አትሻም።

የፈለገው ዓይነት የኦሮሞ ሊሂቅ የደንቢ ደሎ ተወላጅ ካልሆን ለደንቢሻ ከልቧ ጠብ የሚል አይደለም። እኔ በወቅቱ አይደለም ለኦህዴድ  ለኢፌንኮም ለራሱ ለአቶ ጆዋር መሃመድም ፈተና እንደሆን ገልጫለሁ። ስለሆነም „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ ያው ለእኛ ማስተዛዘኛ ሆኖ የቀረ ሞቶ ነው። አልተሰራበትም እንደ ፕሮጀክትም አልተወሰደም። 

እኛን ወደ ኢትዮጵያዊነት ማምጣት ሳይሆን ኢትዮጵያዊ አይደለነም በሚሉት ህሊና ነው ሥራ በትጋት ሊሠራበት የሚጋባው።

ይህ እዬገረመኝ አላዛሯ ኢትዮጵያ ሌላ ፈተና ውስጥ የሚያሰገባት ነገር ደግሞ ጀምራለች „የኦሮሞ ተማሪዎች ማህበር ተመሰረት“ ይላል ዜናው። የት መቼ አይልም? ብቻ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከሥር ባነሩ ላይ በተደጋጋሚ ሲቀርብ እንደ ዋና በኽረ ጉዳዮች ላይ ተጽፎ ነው ያነበብኩት። 

የመርግ ያህል ነበር ዜናውን ሳነብ የተሰማኝ። ኢትዮጵያ 80 ብሄር እና ብሄረሰቦች አሏት። ያ የፖለቲካ ድርጅት ብቻ ሳይሆን 100 ሚሊዮን  የ አሉታዊ የምቀኝነት፤ የቅናት፤ የሴረኝት ኢጎ 100ሚሊዮን ድርጅት በውስጣችን እንደ ዛር ሰፍሮብናል። 

ያ ጥጥቅ ያለ የጨጎጎት ደማና መከራ ሳያበቃ አሁንም ሌላ ሸክም ደግሞ በራሷ ላይ ፈቅዳለች አላዛሯ ኢትዮጵያ። ልፈተን፤ ልትደለቅ፤ ልተሰለቅ፤ ልሾክሾክ፤ ልተርተር፤ ልሸንሸን ይሁነኝ ብላለች እንደ ድንቡልቡሏ መነኒት ኳስ እና መረብ፤ ሜዳና እግር።
  • ·      አንዱ ተደራጅቷል ገና 79 ይቀረናል ማለት ነው። 80 አዲስ የቀንበር እጩኝነት - ተፈቀደለት።

ለምን እንዳስፈለገ እራሱ እጅግ ግራ ይገባል። መንፈሱ እራሱ ጨቋኝ እና አግላይ ነው። አጋጣሚም፤ ሁኔታም፤ ኤኮኖሚያዊ አቅም የሚያንሳቸውን ዜጎች በፍጹም ሁኔታ ያገለለ፤ መማር እዬፈለጉ መማር ያልቻሉትን መንፈስ የሚቀጠቅጥ። የዚህ የዬብሄረሰቦች ተማሬዎች ማህበር ነገ ለእነኝህ መማር ላልቻሉ ድሃዎች የ እኔ ቢጤውች፤ መንገድ ላይ ተወልድው አድገው መንገድ ላይ ለሚያልፉት ምንዱባን ቀጥተኛ የሆነ ጨቋኝ የሥነ - ልቦና ጫና ይፈጥርባቸዋል።

 መደራጀት መብት አይደለም እያልኩ አይደለም።  እኔ እራሴ ሙያዬ ማደራጀት ነው። ነፃነትን በአግባቡ ካልተጠቀምንበት ራሱ ችግር ፈልፋይ ፋፍሪካ ነው የሚሆነው። ዴሞክራሲም እንዲሁ። አሁን የዚህ ድርጅት አባል ለመሆን ከአንደኛ ክፍል ጀምሮ ይሆናል። የአንደኛ ክፍልም ነፍስም ተማሪም ስለሆነ። የግል መኖሪያ ቤትም መከራ ታውጆበታል። እንግዲህ አዲስ አባባ ላይ ስንት የዞግ የተማሪዎች ማህበር ይገነባል? ጦርነት ቀጣይ ነው ...በቤተሰብ ደረጃም። ባል ኦሮሞ ሚስት አማራ ወይ ጉራጌ ልጁ የትኛውን መርጦ ይደራጃል?  

ይህ ጎሳዊ ስሜት በአዲስ አቀራረብ 7ኛ ዕድሜ ላይ እንደ ተቋም በህሊና አንቱ ይሆናል ማለት ነው። አንደኛ ደረጃ ት/ ቤትም አዲስ የዞግ ድርጅት እንደ አሸን ይፈላበታል። ከዛው አልፎ ሜዳውም፤ ጋራ ሸንተረሩም ወንዙም ሁሉም ሰኞ ማክሰኞው፤ ቅልሞሹም መጫዋቻው ዞግ … ወላጆችም ፈረዳባቸው ትዳሩም? 

እኔ ቤት ውስጥ ሚኒ የኢትዮጵያዊነት ፍቅራዊነት ት/ ቤት የውይይት መድረክ ይኑር አላለሁ የአብይ ካቢኔ ደግሞ ት/ ቤት ሌላ የ80 ብሄር ብሄረሰብ ድርጅት ፈቅዷል። አልተገናኝቶም፤ አልተግባብቶም። 

ሌላው ችግር ደግሞ ከሁለት በላይ ከሆነ ብሄር እና ብሄረሰብ የተወለዱት ልጆች ጉዳይ ምን ሊሆን ነው? በኦሮምያ ክልል ያሉ የሚኖሩ የሌሎች ብሄር ብሄረሰብ አባላትስ ምን ሊሆኑ ይሆን? አንዱን ፈተና ሳንሻገር ሌላ ፈተና። ፈተና ለመፈልፈል የተረገምን ምንዱባኖች።  
  • ·      ግን … እባክህን አትገንግን?

ሲሆን ሲሆን አያስፈልግም ነበር። ከሆነም የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማህበር ቢባል ዛሬ ዩንቨርስቲዎች የገጠማቸውን ፈተና በተወሰነ ደረጃ የመገዳደር አቅም ይኖረዋል። አሁን የ4ቱ ድርጅቶች ምልመላ የማቆም መንፈስ ያለ ይመስለኛል በዬንቨርስቲዎች፤ ተቋማቱ የነፍሰ ገዳይ ድርጅቶች ሆነዋል እና። ስለሰዚህ ይህን ለማሳቆም ሲታሰብ ሌላ የጉግስ ዓዋድ ደግሞ ተከፍቶ ነው።

ይህ ህጋዊ ስለሆነ ሌሎች ብሄር እና ብሄረሰቦች ደግሞ ይደራጃሉ። መብታቸው ነዋ። ማን ከልካይ አለባቸው። አብሶ አማራ ከእንግዲህ ተኝተህ በለኝ ማለት የለበትም። በፍጥነት ማቋቋም አለበት።

 እንደማስበው ይህን መንፈስ ያደራጀው ያሰበው ኦህዴድ ይመስለኛል። ለብዙ ነገር ስለሚረዳው። በረጅሙ አስቦ የተሰናዳበት አምክንዮ ነው ብዬ አስባለሁ። ምክንያቱም የኦህዴድ ብልህነት ከሴራ ጋር ተፋቶ ግን ማህበረሰቡን በሁሉም አብቅቶ ከፍ የማድረግ ተልዕኮ ይዞ ነው።
በነበረው መልክ መቀጠል አለመቻሉን ቀድሞታል። 

ስለዚህም ተተኪ አዲስ ስልት በሁሉም ዘርፍ አሳናድቷል። ለዚህ ነው እኔ ኦህዴድ ጭንቅላት ብቻ ሳይሆን ህሊናም አለው የምላችሁ። የፈለገ መሬት ቢገላባበጥ በተረጋጋ መንፈስ ፍንክች ሳይል ሁሉንም  በአቀደው መልክ ይፈጽማል ኦህዴድ።

የዘገዬበት አንድ ነገር ብቻ ነው የሼሁ ጉዳይ ከዛ በተረፈ ግን ኤንም፤ ቢንም፤ ሲንም እንዳይከፋው ሁሉንም አስማምቶ በመቀጣል እና በማስቀጠል እዬሠራ ዋናውን የተደራጀበትን ነገረ ኦሮምያን ደግሞ በአክብሮት ነው የያዘው። ለምሳሌ የኦነግ ክንፍ የአቶ ዳውድ ኢብሳ ጉዳይ ኤርትራ ትጥቁን ካሳፈታችው ምንም ችግር አልነበረም። እዛ ድርስ መሄድ አያስፈልግም።

 ግን እራሱን ያከበረ ድርጅት ስለሆነ እዛው ድርስ ሄዶ አስከብሮ ወደ አገሩ መመለስን እንደ መርህ ይዞታል። ኦሮሞነትን ማስከበር።  አቶ ዳውድ ኢብሳ ከተሰጣቸው ሁለት አማራጭ ውስጥ ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ወስነዋል የሚል ዜና ከሰሞናቱ ዘሃበሻ አስደምጦናል። እኔም ቀደም ብዬ የኤርትራን መንግሥት የጠይቅኩት ስለነበር አንድ ምስጋና ጽፌያለሁኝ።

ባዶ እጃቸውን ትጥቅ ፈተው ከመጡ አቶ ዳውድ ኢብሳ ከዶር መራራ ጉዲና በላይ የሚያሰጋ ነገር አልነበረውም፤ ይህን ኦህዴድ አልፈለገም። ለዚህ ቡድን በብሄራዊ ደረጃ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃም ታላቅ አክብሮት ማሰጠት ስለፈለገ የውጭ ጉዳይ ሚ/ሩ የተገኙበት የመስተዳድሩ ፕሬዚዳን ባሉበት ልዩ ውይይት ለማድረግ ወደ ኤርትራ ልዑኩ ተጓዘ። 

የኦቦ ሌንጮ ለታም ድርጅት ቢሆን ኢትዮጵያ ድረስ ሄዶ መመለሱ እዬታወቀ፤ ልዑኩን እንደተላከለት ሹክሹኩታ ተደምጧል። እመጣለሁ ላለ ድርጅት እስከ አለበት ቦታ ድርስ ሄዶ የፖለቲካ ዕውቅናው ከፍ ማድረግ።

ይሄን ብአዴን ያደርገዋል ወይ? በፍጹም አያደርገውም - አያሰበውም። የአማራ ብሄራዊ ዴሚክራሲዊ ሃይል የሚባል ኤርትራ ነበር፤  በራሱ እግር ነው የሄደው። የንቃተ ህሊና አቅማቸውን የዶር ለማ መገርሳ እና የዶር አብይ አህመድን ልቅና ብቃታዊ አቅም በዚህ መለካት መመዘን ይቻላል። 

የቄሮ አክቲቢስቶችን ሰፊ ክብር ለኦህዴድ ለOBN ሰጥቷል። ብአዴን ለአማራ የህልውና የማንነት ታገድሎ የውጭ አክቲቢስቶች፤ ጋዜጠኞች፤ ተንታኞች ለቅኖቹ ማለቴ ነው አይሰጥም። አዎንታዊ ያልሆትን አይጠቅሙም ለዬትኛውም ማህበረሰብ። 

ቅን መሆን ያስፈልጋል ሰው ነኝ ለማለት። ጥቁርና ነጭን ለይቶ ደፍሮ መናገርም ይገባል። ሰው መሆን ማለት ሚዛን መሆን ማለት ነውና። መልካም በተሰሩት ላይ ድፍርስ እዬለቀቁ መከራ መጥራት ለ እኔ አይመቸኝም። ስለዚህ በጎ የሚያሰቡ፤ ቅኖች፤ በ አማራነት ጉዳይ የምርምር ተግባር የከወኑ፤ ሰቆቃውን ለመጋራት የደፈሩ ጠንካራ ልጆች አማራ አለው። እነዚህን ማለቴ ነው። 

 መሬት ላይ ያሉ መከራውን የተጋሱ ጀግኖች እሰከ አሁን ድረስ የብአዴን  ቢሮውን አያውቁትም። ጀግኖችን ብአዴን ጀግኖቼ አላለም። አማራን ከወከሉት ከጠ/ ሚር ደመቀ አገርብ አብረው የክብር ግንኙነት አልተደረጋላቸውም።  የክብር አቀባባል፤ የክብር ግብዣም አላደረግም ብአዴን እሱ ሳላለከበራቸው የጠ/ ሚር ቢሮም ጉዳዩ አይደለም። እሱ በእሱ ነው የሚገባባዘው ብአዴን። "ባለቤቱ ያቀለለውን አሞሌ ባለ እዳው አይቀበለውም" እንዲሉ … 

ብአዴን እራሱን ማክበር ቀርቶ ራሱን ማወቅ ገና አልጀመረውም። ለዚህም ነው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ይሁን ማዕከላዊ መንግስት የተጋድሎ መናህሬያ ታሪካዊ እውነታዎችን እንደ አልባሌ እያዬ ያለው።

የኢትዮጵያ መንግሥት እና ኦህዴድ ግን ማናቸውም የኦሮሞ ድርጅት፤ አክቲቢስት፤ ተንታኝ፤ ሚዲያ ጀግኖቼ ናቸው፤ እንዲያውም ብአዴን አጀብ ብቻ ሳይሆን አንጥፈህ ጎዝጉዘህ ተቀበል ተብሏል። ሰጥ ለጥ አደርገው እዬገዙ ነው ብልሆቹ፤ በጥበብ እና በስልት። ዋንዳታ!

 ለዚህም ነው የትኛውም የፖለቲካ ድርጅት ኦህዴድ ከደረሰበት የፖለቲካ አቋም አቅም ላይ አይደለም ስል የባጀሁት። አታውቁትም ብያለሁኝ በተደጋጋሚ … ማርከሻ ናቸው። ያስደስቱኛል። ያኮሩኛልም። 

ብልህነታቸው ይመሰጠኛል። ለእነሱ ኢትዮጵያዊነትን ያከበሩትን ያህል  በእኩል ደረጃ ዞጋቸውን ያከብራሉ። የእኞቹ ደግሞ ከዬት መጣ አትበሉን ይሉናል። ኦህዴዶች መነሻቸው ከራሳቸው ከሐረጋቸው ከዳማቸው ነው። ይህም ሆኖ የራሳቸው ማህበረስብ እንኳንስ እርካታ ሊያገኝ ቀርቶ ጠብ ያለ ነገር የለም ነው የሚሏቸው።

ኦህዴዶች የልብ ማህተም አያያዝ ብልህነታቸው ልክ የለውም። የጆዋር አቀበባል፤ የOMN አቀባበል ሂደቱን ስተመለከቱት በፍጹም ሁኔታ የልባቸውን ብቻ ሳይሆን የሙሉ ስብዕናቸውን ብቃት ማዬት ይቻላል። 

ቤተ መንግሥቱን እርክክብ በምልሰት ቃኙት … ታሪካቸውን እዬሠሩ ነው።
እራሱን መምራት የቻለ፤ እራሱን ማከበር የቻለ አቅም ነው ያላቸው። እኛስ? ቢባል የሰሞናቱ ሁኔታ ብቻ በቂ ነው … እነዚህ ሰዎች ጥበብ ናቸው። እያንዳንዷ ደቂቃ ሰከንድ የኦሮሞን ልጅ አክብራ አቅርባ ተንከባክባ ትነሳለች። ለዚህ ነው እምወዳቸው። 

ክብራቸውን ለሌላ መንፈስ ለመሸለም የማይደራደሩ፤ ክብራቸውን በሙሉ ልብ የተቀበሉ፤ የስከበሩ የዘመኑ ምርጥ ልባም ጀግኖች ስለሆኑ ከመንፈሴ ህሊናዬ ይፈቅዳቸዋል።

ሌላው "ህሊና" በሚል እርአስ አቶ ኤርምያስ ለገሰን የሞገትኩበት ነገር ነበር፤ የዶር መራራ ጉዲና እና የኦቦ በቀለ ገርባ እስር መፈታት "ኦህዴድ ይፎካከሩኝል ስለሚል አይፈቅደውም ወይንም ትጋቱ ያንሳል? የሚል ዕድምታውን ሞግቼው ነበር። 

ይሄው አሁን ምንም ምርጫ የሌለው ባዶ እጁን ገብቶ እንደ ማንኛው ሰው ሊሆን የሚገባውን መንፈስ ሙሉ ክብር ለማሰጠት የሄዱበትን እርቀት በማስተዋል ታዳሚዎቹ እዬት። ዛሬ ዶር ለማ መገርሳ እና ዶር ወርቅነህ ገበዬሁ ለአቶ ዳውድ ኢብሳ ክብር ልዕልና ኤርትራ ናቸው።

ይህ መንገዱ የኦሮሞ ትልቅነት በዚህ ይገለጻል ነው ቁምነገሩ። እራሱን አክብሮ ይነሳል ነው ጭንቅላታዊ ተደሞው። "ባለቤቱ ያቀለለውን አሞሌ ባለ ዕዳው አይቀበለውም" የሚለውን የቀደመ ብሂል በ እኛ ዘንድ በዚህ መልኩ ይፈጸማል ነው ዘረ ፍሬው። 

እኛን ስተቀበሉ የኦሮሞ ሊሂቃን የፈለጉትን አቋም ያራምዱ፤ የፈለጉትን ይበሉ መቀበል ግድ አለባችሁ ነው ጉልበታሙ አመክንዮ። ኦህዴድ አቅሙን እያመከለ ነው። እጅግ ብልህ ነው ለዚህ ነው እኔ ለማውያን የሆንኩት። ከልቤ ነው የምዋዳቸው። ዓላማውን ያወቀ ግቡን ያዘልቃልና ...  

መሪነቴ በክብሮቼ መንፈስ ውስጥ እንጂ ተናጠላዊ አይደለም ነው  የተደሞ አመክንዮው። ለዚህም ነው የፖለቲካ አቅሙ ሙሉ ነው ኦህዴድ የምለው። መመጠን በዲቤት ብቻ አይደለም ይህን መሰል ርቁቅ የመንፈስ እዬራዊ ስንቅና ትጥቅን ይጠይቃል። መንፈሳዊ ብቃታቸው ለምዕት ካስማ ነው። ለዚህ ነው እኔ ዶር ለማ መግርሳ የምዕት ቅኔ ያልኳቸው።

ብአዴን - እሳ? ዳሽሽሽሽሽሽሽሽሽሽሽሽሽሽሽ 
እና- ሳሳ
ለሽሽ ሽሽሽሽሽሽሽ
  • ·      ሲባል

የተማሪዎች ማህበር ሲባል የፆታ፤ የሃይማኖት፤ የፖለቲካ አቋም ሁሉ ያጠቃልላል። እና ብሄሩ ግን ኦሮሞ የሆነ ማለት ነው የኦሮሞ ተማሪዎች ማህበር አባል ማለት። አሁንም ዞግ ተኮር በሆነ የፖለቲካ አቅም  ምንም ያልተደራጀ፤ መንፈሱ ብቻ ያለ የአማራ የማንነት የህልውና ተጋድሎ እንጭጭ የብሄር መንፈስ ያሰጋው የአብይ ካቢኔ ሌላ መከራን አስተናግዳለሁ ብሎ ይሄንን ጀምሯል።  

የአማራ ሊሂቃን ጥርሳችሁን ነቅሳችሁ እባካችሁን ይህን አማራ አማራ አማራ የሚል ነገር አስቁምልኝ ብሎ ተማጽህኖ፤ እነሱም ደፋ ቀና እያሉ ባሉበት ሁኔታ፤ ሌላም ፈተና መጥቶበታል፤ ለራሱ ለካቢኒው "ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ቁሞ ማውረድ" ካልቸገረው።

 ይህም ማለት ነገ የዞግ ድርጅት ይቀር የሚል እወጃ ቢኖር እንኳን ሌላ የ66 ዓይነት ተጠባባቂ ዕውቀትን ገብ መሠረት ያደረገ ድርጁ የዞግ ድርጅት ተፈጥሮ ነው ማለት ነው። ሙሉ እገዛ እና ክብካቤውም እንደ ተጠበቀ ሆኖ።  

ወደ ኢትዮጵያዊነት እንሂድ በፍቅር ከሆነ ከዞጋዊ ምልከታዎች የወጡ ተቃሟትን መመስረት ቢያንስ ዛሬ ሲገባ ሌላ አዲስ ፈተና፤ ሌላ አዲስ የተጋድሎ መድርክ፤ ሌላ አዲስ የልዩነት ግድግዳ እያነጹ ከሆነ በልዑል እግዚአብሄር እገዛ ዛሬ አንድ የሆነው የአብዛኛው የኢትዮጵያዊ መንፈስ የቄሮ ትውልድ፤ እና የወያኔ ሃርነት ትግራይ ማንፌስቶ መንፈስ ማህበርተኞችን ሳይጨምር ማለቴ ነው፤ በአንድ ማዕዶት ውስጥ እዬሰበሰቡ ባለበት በአሁን ወቅት ይህ ዜና ሲመጣ አልደነቀኝም፤ አላሳሰበኝም ግን ገርሞኛል።  

እርስ በእርሳቸው የሚጋጩ ጉዳዮች ናቸው። የዳይቤተከር አንድ በሽተኛ ስኳርን በመቀነስ ግን ማር መጨመር ዓይነት ነው የሆነው። ወይንም ቸኮሌት ያቆመ ሰው ውፍርት ለመቀነስ ተምርን ማዘውተር ነው … የዘበጠ መንገድ ነው ለእኔ …

የሆነ ሆኖ እኔ ለአማራ ተማሪዎች እማሳስበው ይህንኑ መስል ድርጅት በመመሥረት ሂደት ውስጥ ማሰብ ያለባቸውን፤ ማድረግ ያለባቸውን፤ መሆን ያለበትን ጉዳይ በእርጋታ አስበው እርምጃ እንዲወስዱ ለማሳሰብ እፈልጋለሁኝ። ይህን የአማራ ተጋድሎ አክቲቢስቶች በተለይ ብዙ ጊዜ ቀናነት እና ጨዋነት እማይበት ወጣት ሙሉቀን ተስፋው አጀንዳው ቢያደርገው መልካም ነው እላለሁኝ።

እኩል መራመድ፤ እኩል መብትን ለማስጠበቅ ይረዳል። ይበጃል ብዬ አይደለም፤ ፍትሃዊ አይደለም ጽንሰ ሃሳቡ እራሱ። ምክንያቱም መማር የማይችሉትን፤ ለመማር ሁኔታው የማይፍቅድላቸውን አግለይ እና ጨቋኝ ስለሆነ። ነገር ግን የኦሮሞ ተማሪዎች ከጀመሩት፤ ፈቃድ ካገኙበት ሌላውም መጀመር ግድ ይላል፤ ዜግነትን ማንም ሰጪ እና ነሺ ስሌለበት። 

እርግጥ ነው የአማራ ተማሪዎች ማህበር ሥራ ለመሥራት ሌላ ክልል እንቀሳቀሳለሁ ቢል፤ በሌሎች ክልሎች ቀርቶ በራሱ በአማራ ክልልም ፈተናው መከራ ነው።

ኦሮሞች ግን ከትግራይ በስተቀር ብዙም ከልካይ የለባቸው። ጠቃሚም አስፈለጊም ያልሆነ የነገ የመከራ ጠሪ እና ፍዳን አሻጋሪ መንፈስ ቢሆንም አማራ ግን ተኝተህ በለኝን አቁሞ በሚችልበት ቦታ ቢያንስ አዲስ አባባ ላይ ይህን ወደ ተግባር ማሸጋገር ይኖርበታል። 

ብአዴንም ይህን በሙሉ ሃይሉ እና አቅሙ ሊያግዘው ይገባል። አንድ ክንፍ ነው። እውቀት ተኮር አቅምን ማማከልን አስቦ፤ ማግሥትን በደረጃ ልክ የማስቀጠል ፍልስፍና ነው። እርግጥ ነው መንፈሱ የቆዬ ነው፤ ለዚህ ሁሉ መከራም የዳረገው የዛን ጊዜው የአዲስ አባባ ተማሪዎች ማህበር ነው በኋዋላ በዞግም በህብራዊነት ቢባልም አንድን ዞግ በአገለለ መንፈስ የመንፈስ ቃልኪዳን የወለደው ነው ወያኔ ሃርነት ትግራይ ሆነ ሌላውም …
  • ·      ንከውነው።

ይህ የተማሪዎች ማህበር በዬብሄረሰቡ ማደራት ወይ መቆም አለበት ወይ ደግሞ ሌላውም በአፋጣኝ ወደ ራሱ ተመልሶ የራሱን አምሳያ ድርጅት ፈጥሮ በእኩልነት መራመድ አለበት። የበይ ተመልካችነቱ በረቀቅ ሁኔታ 27 ዓመት ተኖረ፤ ከእንግዲህ ግን መቀጠል የለበትም በተለይ አማራ።
  
አድነን!
የኔዎቹ ኑሩልኝ!
መሸቢያ ጊዜ።



አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።