ነሐሴ አንድ ቀን ስተራሳት አንተን ገድለኸዋል።

ሰማዕትነት ያፈራው እሸታዊ ማንነት።

„እንደዚሁ ሁሉ እግዚአብሄር የዘራቸው ነፍሳት ፈጥነው ይነሣሉ፤
እሱ ሰውን በውነቱ ካለመኖር ወደ መኖር አምጥቶ ፈጥሮታልና፤
በምታድን ቃሉ ፈጥኖ ያስነሣቸዋል፤ ማስነሣቱን አያዘገይም።““
መቃብያ ቀዳሚዊ ምዕራፍ ፲ ቁጥር ፮

ከሥርጉተ©ሥላሴ
07.08.2018
ከገዳማዊቷ ሲዊዘርላንድ
ገድለ አማራ በባህርዳር ደም የተገበረበት የአማራ የማንነት ታአገድሎ ዕሴት!

አማራ የግፍ ቀንበሩን በበቃኝ ታገድሎውን አህዱ ያለበት የሀምሌ 5ቱ 24ቱ ተጋድሎ ጎጃምን በቅኔያዊ ደሙ አንድ ያደረገበት ዕለት ነው ነሃሴ 1 ቀን። እንሆነ የተጋድሎው የህዝበ ውሳኔ ዕወጃ ሰነድ በደም ማህተም የተዘከረበት የደም ዋጋ ቀን። „እሱ ሰውን በውነቱ ካለመኖር ወደ መኖር አምጥቶ ፈጥሮታልና፤ በምታድን ቃሉ ፈጥኖ ያስነሣቸዋል፤ ማስነሣቱን አያዘገይም።“ የማዳን መለከት ከእዮር የተላከልን ሰሞናት ነበር ከሀምሌ 5 አስከ ነሀሴ አንድ 2008 ድረስ ያለው። 

 ዕሴታዊ የደም ግብር የድንጋጌ ዕለት መስከረም 1 ቀን። ትንግርት በደም ቀልሞ ተጋድሎው ጽናዊታዊ ድልድይ የተዘረጋበት ቀን ነበር ነሃሴ 1 ቀን 2008።

ይህ ቀን ለአማራነት ፍጹም ልዩ ቅዱስ ቀኑ ነው። ሰማዕትነት ፈቅደው ሲቀበሉት ግብሩ በቅሎ - ጸድቆ - አስበሎ እንዲገኝ ቃል ኪዳን የሚታደስበት ስለሆነ "የበሉበት ወጪት ሰባሪ ላለመሆን" የተግባር ቋጠሮን በቆረጠ እና በወሰነ አቋም ለማዝለቅ ውል ከእነዚያ 76 ሰማዕታት ጋር ጎሎጎታን የምናስብበት፤ ቃላቸውን ብንበላ፤ ኪዳናቸውን ብናፈርስ በቁማችን እንፈርስ ዘንድ እምንወሰንበት እለት ነው። 

ሰማዕቱን ማሳብ ብቻ ሳይሆን ዕውን የታገድሎው ዓላማ ገብቶን ከሆን በህይወት ያሉትን ጀግኖቻችን ድምጻቸውን፤ መስዋዕትነታቸውን ሆነን ለማሳዬት ቃልኪዳናችን የምናድስበት ዕለት ነው። የደም ግብራችን ለሽልማት - ለድርድር የማናቀርብ ስለመሆናችን ራሳችን ፈትሽን በፍጹም ጨዋነት አማራነት ማለትን ወደ ተግባር ለማሸጋገር የግል ኢጓችን ገድለን፤ በሱ ላይ እንደ ተፈጥሮችን ውርሳችን ወስጥ በማድረግ በምንገኝበት ቦታ ሁሉ አብነታዊ ክንውን ምሳሌያዊ እይታን አዎንታዊነትን፤ ቅንነት ለእሸቱ አማራነት ልንገብር እራሳችን የምናሽንፍበት መሆን አለበት ሰማዕታትን ስናስብ። 

አማራነት የዳማ ጨዋታ አይደለም። አማራነት እንዲህ ለቅርጫ ሥጋ ማንም ለቀረመት ሲያውለው ሊቆጭን ሊያንገብገብን የሚቸለው ሰሞነ ህማማትን 2008 ከሐምሌ 5 ቀናት ጀምሮ ቆመው ያሰተማሩንን የማንነታችን ሚስጢር የ እኛ ብለን በ እውነት ስለ ዕውነት ስንቆምለት ብቻ ነው። አማራን አታግላለሁ የሚሉት ድርጅቶችም ታታሪዎችም በሆኑ አጀንዳቸው ባልሆኖ የሚያጠፉትን ጊዜ ተግ አድርገው ወደራሳቸው አጀንዳ መግባት ግድ ይላቸዋል።

 ሐምሌ 5 ቀን እና ሀምሌ 24 ቀን የሁለቱ ግማዶች አዕማደ ሚስጢር ማሳረጊያ ዕለት ይህቺ ቅዱስ ቀን ጎጃምን ያነበብ - የተረጎመ እና ያመሰጣረልን ነበር።

ጎጀም ቅኔው ደሙን ገብሮ አማራነቱን ያዋጀበት ታላቅ ቀን ነሃሴ አንድ ቀን 2008። የጎጃም ረቂቅነት የተገለጠበት የገለድል ቀን። የጎጃም ውስጠ ንጽህናውን፤ ቸርንቱን፤ ደግነቱን፤ ቃልኪዳኑ ፍንትው ብሎ በዓለም አደባባይ የበራበት ልዩ ቀን። ነሃሴ አንድ ቀን የመሆናችን አህታዊነት በውን የታየበት ማዕልት ነው። ነሃሴ አንድ የድርብ፤ የንብርብር የሚስጢር ልዩ ሥጦታችን ነው። ለካስ ጎጃም ስለ እኛ ለ እኛ ብለን ወስጣችን እነገብርለት ዘንድ ቃለ ምህዳን ከእዮር የተላከልን ዕለት ነበር። 

በደም የቀለመ ግን ሩቁን ጊዜ አስቦ አማራነት ጎልብቶ በደም ታታሞ በተጋደሎ በርቶ የታዬበት። ያ ገናና ቀን እንሆ ዛሬ ላይ ሆኜ እንደ ግለሰብ እኔ ሳስበው አማራነቴን የሰጠኝ፤ አማራነቴን ያጎናጸፈኝ፤ አማረነቴን በውስጤ ጽላት አድርጎ ያተመልኝ የብጽዕና ቀኔ ነው።

ጎጃም ልዩ ነው። ጎጃም በክፉ ቀን የሚገኝ ድንቅ ህዝብ ያለበት የንጽህና አንባ ነው። ጎጃም ጎንደርን የታደገ ስለ ጎንደር ሲል ራሱን የማገደ የቀራንዮ ተምሳሌት ነው። „ወልቃይት አንቺን ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ“ ብሎ ሞቱን ፈቅዶ የተቀበለ የሰማዕታት አንባ ነው ጎጃም። ዋ! ጎጃም ስላንተስ እኔ ምን ልሁንልህ ከቶ? እንኳን ርዕሰ ሆንክልኝ። እንኳንስ አዕማዴ ሆንክልኝ ይህም ሲያነስህ ነው።

አንተ የጣና የግዮን ሚሰጢር የሁለመና ርትህ፤ አንተ የዕውነት አደባባይ አንተ የውሰጤ ቀለበት ዋ! ጎጃም ከቶ ስለ አነተ እኔስ ምን ልሁነልህ? ጎጃም የመሆን ገበር ነው። ጎጃም ታላቅ የማስተዋል ማማ ነው። ጎጃም ሰው መሆንን የተረጎመ ስለ ሰው ልጆች መብት መረገጥ ራሱን አቅልጦ ፈቅዶ ወደ መከራ የገሰሰ ድንቅዬ ህዝብ መፈጠሪያ ባዕት ነው። ጎጃም የበቃው ራሱን ገብሮ ነው።

ውስጤ መንፈሴ ልቤ ኩላሊቴ ህሊናዬ ስለጎጃም ሳስበው በራሱ የሚሰማኝ የፈውስ መንፈስ፤ የሚሰጠኝ ሐሤት፤ የማገኘው የፍጽምና እርካታ እንደገና የመፈጠር ያህል ነው። ጎጃምን ሳስብ ሁሉ በመዳፌ ያለ እስኪመስለኝ ድርስ ገነት የውስጥ ይሰማኛል። ስለምን? ጎጃም ዕውነት ስለሆነ። ጎጃም በመሆን ውስጥ የሰከነ ሰማዕት ስለሆነ።

ዛሬ እንኳንስ የሰው ቀርቶ የአኖሩት ዕቃ በማይገኝበት ዘመን፤ እንኳንስ  የአክስት የአጎት ልጅ የራስ እህት እና ወንድም በመንፈስ በከዳበት ዘመን አንድ ሙሉ ህዝብ ሙሉ ጎጃም አማራነትን ተቀብሎ ያን ያህል ተጋድሎ ፈጸመ። ያን ያህል ታሪክን በደሙ ጻፈ። የጎንደር በወርቅ የተጻፈ ታላቅ የስጦታ ቀን ቢኖር ነሃሴ አንድ ሁለት ሺህ ሰምት የሰማዕታት ቀን ነበር። 20ሺህ ለካቴናም ተዳርጎበታል። ጎጃም እና ጎንደር ስለ አማራነታቸው የገበሩትን የተጋድሎ ትንግርት ትቶ ይህን ለሌላ ሸልሞ ሰማዕታትን ማሰብ ራሰን መግደል ብቻ ሳይሆን ሬሳንም ማቃጠልም ጭምር ነው። ማግስትንም መክዳት ነው። 

አማራነት እኮ ዝም ብሎ ከመሬት የታፈሰ ጠጠር አይደለም። አማራነት ደም የተገበረበት የማሰዋዕትነት አቤል ነው። ይህን የደም ዋጋ ጥሶ ሌላ ፍላጎት አሳካለሁ ብሎ ቢነሱት ራሱ የአቤል ደም ይጮሐል። አብሶ የጎጃም ህዝብ የአቤል ነውና ደሙ እሰከ መቃብር ይጮኽል። 

ለሰው አይደለም ለሰማዩ እና ለምድሩ ንጉሥ ለልዑል እግዚብሄር ነው መልዕከቱን የሚልከው። አብሶ ጎንደር አማራነቱን ከድቶ ከሌላ መንፈስ ጋር ቢዳብል፤ በውነት የዛ የጅልነት ዘመኑ ወያኔ ሃርነትን አስጠግቶ በራሱ ሜዳ ካመጣው መከራ በላይ ራሱን ለቢላዋ መስጠቱን ይወቀው። ለዘመናት ጎንደር ከጎኑ ተሰልፎ የሚያውቅ የለም። ጎንደር የሚፈለገው ለማገዶነት ብቻ ነበር። 

ጎንደርን ዳግም የወለደው ዕለት አምጡ ድገሙ ቢባል ነሃሴ መባቻ 2008 ነው የባህርዳር ህዝብ ነው። ጎንደሬነት ግማድ ነው። ጎንደሬነት ለዘመናት ተመስጠሮ ተገሎ የኖረ አምክንዮ ነው። ጎንደሬነት ቀንበር ነው። ያን ቀንበር ከላያችን ያወረደልን ደጎ ሙሉ ጎጃም ነው። ዛሬ ልባችን ነፍተን፤ አፋችን ሞልትን አለልን ልንለው ብንችል ጎጃምን ብቻ ነው። አንድ የሰማይ ሚስጢር ተገለጠልን ብንልም ቢኖር አማራነትን አጸደቀልን ብንል የጎጃም ጥልቅ ተደሞ ነው። ጎጃም የቅኔው መንደር ቅኔ ዘጉባኤ ነው።  

ይህን የደም ዋጋ በህብረ ብሄር ፓርቲ ሥም የጠቀጠቅን ዕለት ራሳችን በሁሉም ዘርፍ የምናርድበት ዘመን ይሆናል። ለእኛ ብቻም አይደለም የትንትን ትውልድን ስንወቅስ ነገንም ቀብርን ስለመሆኑ ልብ ልንለው ይገባል።

ታምር ነው ለዛውም በጭንቅ ጊዜ፤ ድንቅ ነው የሰማይ ገድል፤ የገብያ ግርግር በማለት እነ ጸሐፊ አቶ አብርሃም አስራት ሲያጣጥሉት፤ ሚዲያው ሁሉ በእኛ ላይ ዘምቶ በሳቢያ ሲራኮትበት ጎጃም ግን እኔም አማራ ነኝ፤ እኔም ደመቀ ነኝ፤ እኔም ንግሥት ነኝ፤ እኔም አታላይ ነኝ አራብራቱ ነኝ፤ እኔ የፋሲል ነኝ፤ እኔም ስስንዮስ ነኝ፤ እኔም ጎቤ ነኝ፤ እኔም ወልቃይት ጠገዴ ነኝ ደንበሬ ተከዜ ነው፤ እኔም  የመይሳውን ቃልኪዳን  ዕዳ አለብኝ ብሎ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ መድፍ እዬረገጠ ሆ ብሎ ተነሳ።

ቤቱን፤ ትዳሩን፤ ልጆቹን፤ ሥራውን፤ ኑሮውን፤ መንፈሱን፤ ነፈሱን ሳይሰስት ማሃያውን እርግፍ አድርጎ ገብሮ ከጎንደር ጋር ተሰለፈ። „ወልቃይት አንቺን ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ“ አለ። 

ያ ደም የተገበረበት አማራነት ጎጃም ላይ በደም ዳመና ሰማይ ላይ ሲያርግ ጣና ኬኛን ወልዶ ዛሬ ላለለው ቀን አደረሰ። ጎጀም ለቀን አድርሽ ብቻ ሳይሆን የአማራነት ረቂቅ የተጋድሎ ፈርጥም ነው። ጎንደርን ጎጃም እንደገና ወለደው። እንደገና አስነሳው።  

ጎንደርን እንደ ገና አዎን እንደ ገና ፈጠረው ብልሁ ጎጃም፤ ያን የድነቅነት ግርማ ሞገስ እንደገና አደሰው አበቀለው፤ አጸደቀው፤ አደዬው፤ አሰብለው። አምጦ እም ብሎ አምጦ ወለደው ቅኔነቱን። አንስት ብቻ ሳትሆን ተብዕቱም አምጦ ነው አማራነትን የወለደው። አማራነት የህሊና የቃል ኪዳን ጸጋችን ነው። 

አማራነት ክብራችን ነው!ጎጃም ታሪክን ሲጽፍ በእልልታ በኩልልታ በከበሮ በአታሞ በጭብጨባ አልነበር። እንባችን እንባው አድርጎ ራሱን ኑሮውን ይበቃኛል ብሎ ገብሮ ነው። 

ያ የደም ዋጋ፤ ያ የእንባ ዋጋ ጸድቆ ጸንቶ ይኖር ዘንድ በአማራነት መንፈስ ውስጥ መዝለቅ ትውልዳዊ ድርሻችን ነው። የጎጃም ደም በከንቱ ፈሶ እንዳይቀር አማራ ከፈለገ ሽዋም ይሁን ወሎ ወሎም ይሁን በዬትኛውም የኢትጵያ መሬት ይሁን ውጪ አገርም በየደቂቃው እዬተነቀለ፤ እዬተጠቃ ያለው አማራ ጉዳዬ የእኔ ሊለው ይገባል የራሱን ጉዳይ። አማራው የራሱን ትውልዳዊ የቤት ሥራውን እራሱ እንጂ ሌላ እንዲሠራለት መጠበቅ የለበትም።

ዛሬም እንደ ትናንቱ በዛ በለመድነው አቅማችን ሰብሮ፤ ውስጣችን አድምቶ ሲያርሰን በኖረው የራስን ቤት እያፈረሱ የሌላን ቤት የመገንባት፤ የሌላን መንፈስ የማጽደቅ፤ የሌላን መንፈስ ልዕልና የማስከበር ጉዞ ታይቷል። ይህ ከጅልነትም በላይ እብደትም ነው። አንዲት ቅንጣት እራፊ መንፈስ ሌላ ቦታ ማፈስ ቀርቶ አይታሰብም ካለ አማራ በስተቀር።  

ከእንግዲህ በስክነት፤ በእርጋታ፤ በጨዋነት አማራነት ማለት ምን ማለት አንደሆን በአርምሞ ተደመን ወዳ ራሳችን ተምልስን የራሳችን ጉዳይ ራሳችን ባለቤት ሆነን የራሳችን አጀንዳን በስማ በለው ሳይሆን በራሳችን ሠርተን አማራነትን አበጀተን፤ አቅሙን አጠንከረን፤ አጎልብተን፤ አስልተን፤ አስፍተን ወጥ አቋም ይዘን ሳንኩን ሁሉ ተሻግረን ራሳችን በራሳችን በሰራነው አቅም ብቻ ጎልብተን መውጣት ይኖርብናል። የሰው ቤት ማድመቁ መቀርት አለበት።

ከማንም አናንስም፤ ከማንም አንበልጥም። ችግራችን ሆደ ቡቡ ስለሆን  በቅንነት የምናደርጋቸው ነገሮች ተግ ማድረግ ይኖርብናል። ከራስ ላይ ቅንነትን፤ ቸርንትን ደግነትን - የዋህንትነት እንዲነሳ በማደረግ አቅማችን ለአማራነታችን ገብርን እንደ ሰው፤ ሰው ሆን እንታያቸው ዘንድ መትጋት ይጠብቅብናል። እንደ ፍጡር ለመታዬ የራስን ቤት ማደረጀት የተገባ ነው። አማራነት የደም ዋጋ ነው። 

የደም ዋጋ ለሌላም ሸልመን አይተነዋል። የትኛውም ፓርቲ የሰጠን አይደለም የራሳችን ተጋድሎ ያመጣውን ለውጥ ከዳር የማድርስ ግዴታ የምንም ሳይሆን የራሳችን ጉዳይ እና አጀንዳችን ነው። 

ይህ ለውጥ እንደ ባይታዋር ሆነን ለሌላ የምንሸልመው ሳይሆን የደም ዋጋችን ስለመሆኑ ገብቶን በዛ ላይም ተግታን ዘላቂ ፍላጎታችን ይሳካ ዘንድ የለውጡ ተቀናቃኝ ሳንሆን፤ እኩል በሆነ ስሜት እና ብቃት እራሳችን አጎልብተን ተፎካካሪ ሆንን እንወጣ ዘንድ በራሳችን ውስጥ መዝለቅ ዋነኛው አብይ ጉዳያችን ነው። ተደባልቀን፤ ተቀያይጠን ተዋህደን አይተነዋል። የረዳን ያስገኘልን አንዳችም ነገር የለም። 

ቁም ነገር ብልህነት፤ ማስተዋል፤ የራስ ቤትን፤ የራስ ጎጆን አጠናክሮ ጎልብቶ መውጣት ነው። የኢትዮጵያ ፖለቲካ የጎርፍ ሙላት ነው። ጎርፉ ሞልቶ ሲጎደል ተጠቂው ባዶ እጁን ቀሪው አማራ እንጂ ሌላው አይደለም። ስለሆነም ትጥቅ መፍታት የተገባ አይደለም። 

 ሌላው የራሱን ማህበረሰብ ሴብ አድርጎ ነው አማራን አስገብሮ ክብሩን አስጠብቆ የሚኖረው 43 ዓመት ሙሉ። የመጣ ቢመጣ፤ የሆነ ቢሆን፤ የተወጠነ ቢወጠን ከአማራነት አንዲት ስንዝር ንቅንቅ ማለት የደምን ዋጋ እረግጦ ራስን አዋርዶ ሳር ናችሁ፤ እንጨት ናችሁ፤ አልተፈጠራችሁም ላሉን መሳቂያና መሰላቂያ ከመሆን ውጪ ትርፍ የለውም። 

የነፃነት አርበኞችም ቢሆኑ ከአማራ ተጋድሎ ውጪ ያሉት እነሱ ለተገበሩለት ይትጉ፤ አማራነትን ግን ለቀቅ እንዲያደርጉት ይለማናሉ። አማራ ተጋድሎ የራሱ ማንነት ያለው እጅግ ሰፊ መጠነ ሰፊ ጥልቅ ፍልስፍና ነው። አማራነት እንደ ኩርድሾቹ፤ እንደ እስራኤሎችም፤ እንደ አርመኖቹም መሰል ፈተና ያለበት ህዝብ ነው። 

ስለዚህ በራሱ ውስጥ በነጠረ የተልዕኮ መስመር ብቻ ነው ከዚህ መከራ በሃሳብ ገና ያልተጸነሱትን የሚያድን ተግባር መከውን ያለበት ዛሬ ነው። ለዚህ ደግሞ በደሙ ዋጋ ከፍሎ በመጣው ለውጥ አማራ ተጠቃሚነቱን ሠርቶ በሚያገኘው እንጂ ከሰማይ መና መጠበቅ አይኖርበትም።

የጎጀም የደም ግብር አማራነታችን የፊደል ገበታችን እንዲሆን እንጂ አማራነታችን ለሌላ ሸልመን ማከሄጃ፤ ድልድይ፤ መናጆ ወይንም ሎሌ ለመሆን አይደለም። ከማንም የላቀ ነገር አለን ባንልም ግን ለራሳችን በቂ የሆነ አቅም አለን። አማራነት ባያንጠራራም አንገት የሚያስደፋ ማንነት አይደለም። አማራነትን መቀበል ልንዋረድበት፤ ዝቅ ብለን ልንታይበት ወይንም በይሉኝታ ተጠቅልለን የአባት፤ የዘር ጎደሎ እንዳለብን ልንሸማቀቅብት  አንገታችን ልንደፋበት በፍጹም አይገባም።

አማራ ነኝ ማለት ክብር እንጂ ውርዴት ወይንም ውርዴ አይደለም። አማራነት ያሳጠን፤ የነሳን የለም፤ እንዲያውም አማራነት ቀና ብሎ ሲወጣ ነው ምድር ቁና የምትሆነው? ስለምን? እነሱም ያውቁታል እኛም እናውቀዋለን። 

እኛ ምን እንዳለን፤ ምን እንደሌለን፤ ምን እንደምንችል ምን እንደሚፈቀድልን ምን ደግሞ እንደሌለን እናውቃልን። አለን ከምንለው ታላቁ የሰማይ ጸጋችን፤ ጉልሁ መክሊታችን በኢትዮጵያዊነት የማንደራደር፤ በሰንደቅዓላማችን የማንደራደር፤ በአባቶቻችን ልቅና እና አገር የማስረከብ ታሪካዊ ተልዕኮ የማንደራረደር ጽኑ ህዝብ መሆናች ነው። ይሄን ማደረጋችን ነውራችን ወይንም እርማችን አይደለም፤ ይልቁንም ይሄ እኛንም የሰጠን ስለሆነ ክብር ክሩታችን ማዕርግ ሞገሳችን ነው። 

ስለዚህ አማራነት ኢትዮጵያዊነትን አጎልብቶ ቢያወጣው፤ አቅምን መቅኖ ቢሆነው እንጂ ስጋትም ውርዴቱም ሊሆን ከቶም አይችልም። ያለመሰልጠንም ምልክት አይደለም። አለመሰልጠን እራስን ገብሮ የወለሌ ገበታ ማለት ነው። ራስን ሰጥቶ ቁሞ መለምን ነው። ይህ ተኖሮበታል ከእንግዲህ ግን አይደገምም አይሰለስም።

አማራነትን እንውደደው ልክ እንደ ኢትዮጵያዊነት። አማራነትን እናክበረው ልክ እንደ ኢትዮጵያዊነት። አማራነትን የእኔ እንበለው ልክ እንደ ኢትዮጵያዊነት። አማራነትን የአንተ ነኝ አለሁልህ አይዞህ እንበለው ልክ እንደ ኢትዮጵያዊነት። 

አማራነትን እናፍለቅው ልክ እንደ ብሄራዊ ሰንደቅዓላማችን። አንዱ ላንዱ ዘሃ እና ፈትሉ ነው። ሸማው ሸማ የሚሆነው በወጉ ባለሙያ ሲያገኝ ነው። አሁን የአማራ ተጋድሎ ባለሙያው አማራ ነው። ስለዚህ ለሸማው ሌላ ፈታይ ባለሙያ መጠበቅ የለበትም። 

ኢትዮጵያዊነትን እማ አንጥርን አጀንዳ አስደረግን ሙሴ አሰጠን። ይህን መቼም የቁቤ ትውልድ ቄሮ አሰጠ መቼም አይባል ነገር እዬታዬ ነውና። ስለዚህ ለኢትዮጵያዊነት ሙሴው ዶር አብይ አህመድ አሉለት። ሌላ  የአንድነት አታጋይ አያስፈልገውም አማራው። 

ይልቅ አማራው እሸቱን እንቡጡን ያሰብል ዘንድ የራሱን የቤት ሥራ ይሥራ። የአማራ ተጋድሎ አኖሌ ትፍረስ አትፍርስ ብሎ አልተነሳም፤ ይህ አጀንዳው አይደለም። አጀንዳው ጥልቅ እና ሰፊ ነው የእስራኤልን ህዝብ አማራ ይሰበው … ምጽዕተ እስራኤልንም ያንብብ ...

አማራ መሆን አንገት የሚደፉበት ከሥልጣኔ በታች የሚያደርግ አይደለም። ከቶ የአውሮፓን የፍልስፍና ሥልጣኔ ማን አስገኘና ነው አማራነት የመንፈስ ኋላቀርነት ተደርጎ የሚወሰደው? ይምጣ እኔን ይሞግተኝ እና ያሸንፈኝ? ትምክህት ስለማይገባ ብቻ ነው ዝም የሚባለው? ስለምንስ እንፈራለን? ስለምንስ ሁሉ የትግል ሜዳው የኛ መንፈስ እንዲሆን ሁሉ ይመኛል? ወዶን? ናፍቀነው?

እንዲያውም አማራነት ሰው ነው ብሎ መነሳት ሰልሆነ አማራነት የሰዋዊ አምክንዮዎች ታታሪነት አንድ አካል ነው። አማራነት የተፈጥሯዊነት አክቲቢስትነት ነው። ሰው የሚከበረው በቤቱ እንጂ በትውስት አይደለም። ሐረጋችን አማራ ደም ስለመሆኑ ለሰከንድ ሊዘለል ከቶውንም አይገባም። ለድርድርም አይቀርብም።

የአማራን ችግርን በነቂስ ፈልፍሎ፤ አጥንቶ፤ መርምሮ የመፍትሄ አቅም መፍጠር የሚቻለው በነስቢ ሳይሆን አማራ ነኝ ብሎ በሚነሳ አጀንዳ ዙሪያ ብቻ ነው። 

ከዚህ ያለፈው አጀንዳ ህብረ ብሄራዊነት ለአማራ ለዛውም እድለኛ ከተሆነ ከደረሰው 1/80ኛ ድርሻ ነው ያለው። እጅግ ስልታዊ በሆን በግለት እና በጭቆና 43 ዓመት ለገነገነ ችግር በካሊም በተጠቀለለ ድካም የተጓዝንበት ዘመን የተቃጠለ ካርቦን ነው። ዛሬ አማራነት በነጠረ የትግል መስመር ብቻ እና ብቻ ነው ችግራችን በዘለቄታ ሊፈታ የሚችለው። 

ገና ሊወለዱ ላልታሰቡት ህፃናት ጨምሮ አማራነት ዛሬ የተገባውን መሠረት ያለው ልቅም ያለ ተግባር ካልከወነ ነገ እራሱ ከመምጣቱ በፊት ለአማራ ትውልድ ያለቁ ቀናቶች፤ የከሰሉ ወራቶች፤ የዘገጡ ዘመኖቹ ሊሆን ግድ ይላል።  

ምንም ድርድር ምንም ውል አያስፈልገውም አማራ መደራጀትም መታገልም ያለበት በአማራነቱ ብቻ ስለመሆኑ። የተቃጠለው ጊዜ ይበቃል። እድልም ለአማራ ተጋድሎ በደሙ ላመጣው የመደራጀት መብት ተጠቃሚ መሆን መቻሉ የሚያረጋጋጠውም በራሱ ውስጥ በዘለቀው የራስነት ድርጁ መንፈስ ብቻ ይሆናል። የትውስት ድርጅት አማራ ከእንግዲህ አያስፈልገውም። መንፈስን ማባከንም አያስፍልግም።

 ግጭትም፤ እሰጣ ገባም፤ እላፊ መሄድም መቆም አለበት። ከታሪክ ጋር አስጣ ገባም ያን የተለዬ ተልኮ ላላቸው መተው ነው። ያ አማራን አያድነውም "የደንቆሮ ለቅሶ መልሶ መላልሶ ነው" የሆነው። ለውሻ ትንሽ ሥጋ ጣል እንደሚደረግለት ነው እንሱ መንፈስን ሲያባክኑት የኖሩት፤ የቀደሙት ጀግኖች ጉዳይ የአማራ አጀንዳ ብቻ አይደለም … 

አማራ ራሱ ደሙን ገብሮ ባገኘው የመደራጀት መብት የራሱ እንጂ በችሮታ የተሰጠው አይደለም። እንኳንስ ለራሱ የነፃነት አርበኛውን ሁሉ ያስፈታ የጀግንት ውሎ ነበር የአማራ የማንነት የህልውና የተጋድሎ ታሪክ። ስለሚፈሩት ነው ማንሳትም ማውሳትም የማያፈለገው።

ይህ ዘመን አማራ በልመና የተሰጠው አይደለም። ይህ ለውጥ የአማራ የነፍስ ዋጋ ጥሪቱ የራሱ ነው። ዋጋውን ውል ላይ ላማሳረግ ደግሞ አማራ ሆኖ እንደ አማራ በተደራጀ መንፈስ ውስጥ ታግሎ ግቡን፤ ተልዕኮውን ማሳካት ነው። የተጋድሎው ድል ለሌላ በመሸለም በህብረ ብሄር እደራጃለሁ ከሆነ የተጋድሎው መሰረታዊ የኪዳን ውል ይጣሳል፤ አብሶ የጎጃም ደም። የጎጃም ደም የአቤል ነው። ጎጃም የሞተው፤ የደማው፤ በጥርስ የተያዘው ለአማራነቱ ብቻ እና ብቻ ነው።

አማራነት ተፈጥሮው ተናካሽነት አይደለም። አማራነት የግጭት እልፍኝ አይደለም። አማራነት በጎ ነገሮችን በበጎነት የማዬት፤ የማይበጁ ነገሮች ከኖሩም በተገባው መልክ የሚገልጽ ህግ አዋቂነት ብቻ ሳይሆን ፈርሃ እግዚአብሄር ///  ፈርሃ አላህ ያለው ይሉኝታ የሚያጠቃው ህዝብ ስለሆነ በዚህ ዙሪያ ማንነቱን የማይገልጹ ተለጣፊ ባህሪዎችን ማስወገድ ይገባል። ለነገሩ ተጋድሎውን ለማቀጨጭ የተሳቡ ተውሳኮች ናቸው።

አማራነት ተጠራጣሪነትም አይደለም ሰው አማኝ ነው። እርግጥ ነው ተክደናል፤ በተደጋጋሚ ተክደናል ብለን እኛ ተፈጥሯን መካድ ግን አይገባንም። ሁሉንም ነገር በቅንነት በአዎንታዊነት የማዬት ጸጋ ብድር የሚያስኬደን ሊሆን አይገባም። ሳንክ እና ምክንያት እዬፈለጉ ሁሉ ቦታ ጦርነት መክፈት ፈጽሞ ከተፈጥሯችን ውጪ ነው። 

የአብይ መንፈስ  ለእኛ አንጡራ ጠላታችን ሳይሆን መክሊታችን ነው። ልናግዘው ይገባል ግዙፉን የአማራ ተልዕኮ ተሸክሞ የተነሳ ጀግናችን ነው። አማራ በ አገሩ ጉዳይ ተዳርድሮ አያውቅም ይህን የቤት ሥራችን ስለተሸከመልን ልናመሰግነው ይገባል። ጊዜያችን ብክነታችን በእጅጉ ቆጥቦልናል እና። በተተበተበ ቢሮክራሲ እና በግራ ቀኝ ሴራ ነው ፍዳውን እዬከፈለ ሌት ተቀን እዬተጋ ያለው። አብረውት ያሉት ማን ምን እንደሆን እራሱ አይታወቅም። 

ስለሆነም ነገር ጫሪነትን ልንጸዬፈው ይገባል። እኛ ነገርን ፈርተን የምንኖር ማህበረሰቦች ነን። እንሳሳትን አክብሮ በቅኔ እያዜመ የሚይዝ ህዝብ እንዴት ከሰው ልጅ ጋር መቻቻል ያንሰዋል?

እኛነታችን እንዳይወሰድብን ካሻን ከተፈጥሯችን ጋር በውል መገናኝት ግድ ይለናል። የተሰጠንን ካለወቅንበት ምርቃቱ ይነሳል። በ አማራነታችን የተሰጡን መልካም ነገሮች አሉና። እውነት ለመናገር ይሄ ለውጥ የራሳችን ለውጥ ነበር። የማዬው፤ የማነበው፤ የማገናዝበው ነገር ግን ግራ ነው። አማራ መሪውን አክብሮ የማይነሳ ከሆነ አማራነት በዛ ሰብዕና ውስጥ የለም።

አማራ ታገድሎ ይህን ለውጥ እኔ ያመጣሁት ለውጥ ነው ለውጡን ለማስቀጠል ጥያቄዎቼን ለማስመለስ በዛ ወስጥ የራሴን የቤት ሥራ ሥሰራ ብቻ ነው ብሎ ማሰብ ይገባል። ዕውነት ለመናገር የንጉሦች ንጉስ የአጤ ሚኒሊክ ጉዳይ ዋና አጀንዳ አደርገን፤ አስብ እና ምጽዋን የእኛ ብቻ ነው ብለን አጀንዳ አድርገን በዛ ላይ አቅምን መበትን አስፈላጊ ያልሆነ ነገር ነው።

የራሳችን መከራ በላይ በላይ ባለቤት አልባ እየተከመረ ያን ሳንፈታ በራሳችን ላይ ሌላ ጫና በማከል የሚደረገው እርኪ ርኪ የተጋድሎው ተልዕኮ እና እኛ አራባና ቆቦ መሆናችን ያሰጣብናል።

ቀደምት ጀግኖቻችን ቅኝ ተገዢ ሳያስደርጉ አገር ሰጥተውናል፤ አገር አውርሰውናል ያወረሱን አገር ለማስቀጠል መሥራት ነው ዋናው ግባችን ወይንም ጎላችን ሊሆን የሚገባው።

ይልቅ በሳይበር ከሚጣፋው ጊዜ ከፍለን እራስን ወደ አንድ ለማምጣት መስራት ይገባል። ከኢጎ ጋር መፋታት። እራሰን ማሸነፍ። ከቂምን ከሴራ ጋር አለመደመር። አማራነት ማለት ይሄው ነው። ያን ትተቻለህ አንተ የዛ አንባሳደር ከሆንክ ምኑን አማራ ሆንክው/ ምኑንስ አማራ ሆንሽው? ከሁሉ በላይ የምናባክነው የተጋድሎውን ዓላማ ነው። የተጋድሎውን ተልዕኮ ነው።

ዛሬ ትናንት ጀግና ያልናቸውን እንኳን ከተፈቱ ከእስር በኋላ በመንፈሳችን ለመሳጠጋት አቅም የለንም? እነዚህ ጀግኖች ናቸው ሰው ነህ ያሰኙን፤ ሰማዕቱም ከሞት ቢነሱ የምናደርገው ይሄውን ነው። ያሉትን ሳናከብር ዕለቱን ብናከብረው እኛ የውሸት ነን ማለት ነው። የ አውነትም ጣውንቶች ነን። 

ወደ እራሳችን ተፈጥሮ፤ ወዳ ቀደመው ብሂላችን፤ ወደ ተሰጠን ጸጋ እንመለስ። እግዚአብሄር ይርዳን፤ ሰማዕታትን በአርያሙ ያኑርልን፤ ያሉትን ጀግኖቻችን ልዑል እግዚአበሄር ይጠብቅልን፤ ዓለምን እና ኢትዮጵያን ሰላም ያድርግልን። አሜን!

 አማራነትን ለማስከበር ሌላውንም ማከብር ግድ ነው!

አዲሱ ለውጥ የአማራ የደም ዋጋ የራሳችን ነውና ልንጠብቀው፤ ልንከባከበው ይገባል! 

የኔወቹ ኑሩልኝ።
መሸቢያ ጌዜ።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።