ጥሎብን መልካምነትን መጋፋት ነውና።

… ሰው ማበርከት አናውቅበትም፤ አልተሰጠነም፤ ጸጋችንም አይደለም።

„ሰባት ሳምንት ትቆጥራለህ፤ መከሩን ማጨድ
ከምትጀምርበት ቀን ጀምሮ
 ሰባት ሳምንት መቁጠር ትጀምራለህ።“
ኦሪት ዘዳግም ምዕራፍ  ፲፮ ቊጥር ፱
ሥርጉተ ©ሥላሴ 09.08.2018




ውዶቼ ያልተጠናቀቀው ጉዞ በሚመለከት ሊንክ እና አስተያዬታችሁን ለላካችሁልኝ የእኔ ጌጦች እጅግ አድርጌ አመሰግናችሁ አለሁኝ።

 

ወጣ ያለም ሰለሆነ እንደ እናንተ ሌሎቹም ሊኖሩ ስለሚችሉ ትንሽ ልባል።  የበጎ ፈቃደኝነት ወጣቶችን ገለጻ እንዳደረጉ ይህን እማ ሳተናው ላይ አግኝቼው አዳምጫዋለሁኝ።


አገላለጹም ተሳታፊዎችም አዲስ ናቸው። ንግግራቸውም እጅግ ቀስሰተኛ የደከመው ነው። የውስጥ ደስታ በፍጹም ሁኔታ የራቀው ነው።

 

እውን ያ አንበሳ ዶር አብይ አህመድ ናቸውን ያሰኛል? የተለዬ ነገር እኮ አላቸው? ይህ እርግጠኝነታቸው፤ ልበ ሙሉነታቸው፤ ድፍረታቸው፤ በራስ የመተማመን አቅማቸው፤ በመንፈሳቸው ውስጥ ታዳሚውን የማቀፍ የመሳብ ሃይላቸው ማግኔታዊ ነው እኮ።


በእያንዳንዱ ቃል ውስጥ ያሉ ንጥረ ነገሮች እንዲሁ የሚታለፉ አይደሉም። የንግግር ክህሎታቸው እና ጸጋቸው ከተለመደው ውጪ ነው ግርማው። እንዲያውም ካነሳችሁትማ በዚህ ንግግር ውስጥ የሆነ የተቀሙት ነገር እንዳለ ይገልጻል አስተውላችሁ እዩት፤

 

የእኔ ግን ሌላ ነው ጭንቀቴ። አንደኛው ህልሜ ነው። ባዶ ወንበር እና የሌላ ፓርቲ ሊቀመንበር ግማሽ አካል ምን ማለት ነው ይሄ?

 

ሌላው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ሴራ እና የኖርንበት መከራ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ እና የተስፋው ዘላቂነት ሁልጊዜ እክል ይገጥመዋል። ለግለግ ብሎ ወጥቶ እንዲታይ ተስፋ አይፈለግም። ትንሽ ደስታ ሲፈነጥቅ ያን ለማጠልሸት ወዲያው ነው እምንሰማራው።

 

እርግጥ ነው እንዲያውም ዕድለኛ ናቸው ከዚህ አንጻር ጠ/ ሚር አብይ አህመድ። የሆነ ሆኖ እኔ የተረጋጋ መንፈስ ኑሮኝ ደህንነት ሊሰማኝ አልቻለም በብዙ ምክንያቶች። እራሱ የአቶ ዳውድ ኢብሳ ሌጋሲ እና የዶር አብይ አህመድ ሌጋሲ በምን ሁኔታ በምን መሥመር ተገናኝቶ አላዛሯን ኢትዮጵያን ከጭንቅ ሊገላግላት ይችላል? እንቆቅልሹ ይሄው ነው።

 

ደህና ቢሆኑም በጫና የተወጠረ መንፈስ ውስጥ እንዳሉ ነው የሚሰማኝ። በአንድ በኩል አይደለም ለኢትዮጵያ ለአፍሪካ መጠነ ሰፊ ራዕይ አላቸው፤ ያነንም በተለያዬ መልክ ስለገለጹ ሁሉም ይጠብቃቸውል፤ በሌላ በኩል ደግሞ በአቀዱት መልክ እንዳይፈጽሙ ህሊናዊ ድርድር እንዲገቡ ከተገደዱ ለሳቸው ሰብዕና ዕምነትን፤ ታማኝነትን እንደ መካድ ስለሚቆጥሩት ክህደትም መስሎ ስለሚታዬቸው መኖራቸውን አይፈቅዱትም።

 

ብዙ ጊዜ ተከድነው የሚቀመጡ ሚስጢራት ይኖራሉ። እነዛ ተፈቅደው ተወደው ላይሆን ይችላል በዝምታ የሚከደኑት። አንዱ ሲነካ ሌላው ስለሚናድ ሊሆን ይችላል በዝምታ ውስጥ እንዲቀመጥ የሚፈቀደው።

ህዝብ ደግሞ በዚህ አራት ወር ውስጥ የለመደው ነገር አለው መሪውን እንደ ፈለገ ማግኘት፤ ማድመጥ፤ መጠዬቅ ወዘተ … ይህን እንዳያድርጉ ሰፊ ጫና ነበር ታስታውሱ እንደሆን ሽርሽር አበዛ፤ ለምን ቢሮ ተቀምጦ አይሰራም ወዘተ … ወዘተ …




 ያ አቅማቸው እንዲታወቅ አልተፈለገም ነበር። ልክ እንደ ቀደሙት የተሰጣቸውን ብቻ እዬሠሩ እንዲቀመጡ ነበር የተፈለገው።

 

እሳቸው ደግሞ እስከ አለፈው ሳምንት ድረስ በልባቸው በህሊና ሰሌዳቸው ያለሙትን ነው በራሳቸው የጊዜ ሰንጠረዥ ሲከውኑ የቆዩት፤ አሁን ይህን ለማድርግ፤ በራሳቸው ሌጋሲ እንዲጓዙ ለመቻል እክል ከገጠማቸው ውስጣቸው ይጎዳሉ።

 

ምክንያቱም ትልቁ ሰብዕናቸው ታማኝነት፤ መታመን፤ ዕውነተኝነት ነውና። ለህዝብ ያለተመነ ለህዝብ ያለሠራ ሰው ከሥልጣኑ ቢወርድ ይሻለዋል ለመቀጠል ምን ሞራል አለው ነው የሚሉት። ያን ስለምን እንደማያድርጉት ደግሞ ይፋ ለማድረግ ደግሞ የሆነውን ነገር የሚያውቀው አንድዬ ብቻ ነው።

 

እንዳይወርዱ የሳቸውን ካፒታል ለመጠቀም የሚፈልግ ቡድን ከኖረ እና እሳቸውን እንደ ጋሬ ፈረስ ባሻነህ፤ በአዘጋጅልንህ ይህን እና ያነን ሳትነካ ከሆነ ይከብዳል።

 

በግል ህይወታችን እንይ፤ በነፃ ለመኖር የምንፈቀድ ሰዎች እኮ የሚያስረን ነገር አንሻም፤ እንኳንስ ለ100 ሚሊዮን ህዝብ ሌት እና ቀን ለሚታጋ ልዩ ፍጹም ልዩ መሪ።

 

ነፃነት ሙሉው ከሌላ መኖርን አለመደፈር ግድ ይላል።ብዙ ሰዎች ብቻቸውን የሚኖሩት፤ ልጅ ሳይወልዱ የሚኖሩት እኮ ለነፃነታቸው ስስታም ስለሆኑ ነው።

 

ሁሉ ነገር በነበረው ነው ማለት የሚያችል ነገር የለም። በፍጹም። የሆነ ድፍርስ ነገር አለ። ያ ድፍርስ ነገር ይጠራል ለማለት በሰው ሰውኛው እጅግ ከባድ ነው።  ግን እንደዛ ከፍ እና ዝቅ ብለው ከርተት ብለው፤ ፍቅራቸውን የሰጧቸው ብፁዕን አበው በፀሎት ሃይል የሚሆን ነገር ሊኖር እንደሚችል ግን አምናለሁኝ። ጸሎት ጉልበት ነው።


ምንም ይሁን ምንም ደህና ከሆኑም እሰዬው ነው። ብቻ አዕምሯቸውን ባያዩትም፤ ባያነቡትም ግን በመንፈስም ቢሆን ተጽዕኖ ከሚያሳድር ነገር ተቆጥበን በጸሎት እንትጋ ነው እኔ እምለው። ጊዜውም የሱባኤ ነው።

 

የሆነ ነገር ከሆነ፤ ወደፊትም ሊሆን ከታሰብ እምናስቀርበት አቅም የለንም። ያ ወቅቱን ያልጠበቀ እንደ ተጋለበ ታቅዶ አባክኖን የቀረው የአዲስ አባባ የድጋፍ ሰልፉ ባይደረግ ይህ ሁሉ ጭንቅ አይመጣም ነበር። የደቡብ ጭንቅ እያለ ነው ያ የድጋፍ ሰልፍ የተዘጋጀው ውጥረት በውጥርት። ጫና በጫና …

 

ከአሜሪካኑ መልስም ነው ይህ የኢትዮ ሱማሌ መከራ የተደገነው ይህን ያህል ቤተ እግዚአብሄር በአንድ ሰሞናት ብቻ ልክ እንደ ግራኝ አህመድ ዘመን ነው የነደደው። መንገድ ላይ እያሉ ነው የቆሞስ ኢንጂነር ስመኘው፤ የአቶ ተስፋዬ ጌታቸው ህልፈት የተሰማው። ይህ በራሱ እኮ ጫናው ከባድ ነው።

 

እንገዘው የተባለው እኮ አሁን ባለቀ ሰዓት ነው። ለዛውም የማህበረሰባቸው አክቲቢስቶች እገዛ እና የሚያራምዱት ፖለቲካ አይገናኝም የተለያዬ መስመር ነው። ሁል ጊዜ እንኳንም ካልታወቀው አቅጣጫ አዳነን እል ነበር። አሁን ለእኔ ያ ያልታወቀው አቅጣጫ የበለጠ ጠረኑ የቀረበ ይመስለኛል …

 

ውዶቼ --- የወያኔ ሃርነት ትግራይ አቅሙን አንኳሳችሁ ደግሞ አትዩት። ምኑ ተነክቶ? ሌላም ቡድን እንዳለ ማሰብ ይገባል። ያው ወተታችን እኮ ሴራ ነው። ቅን፤ በቅቶ፤ አድጎ፤ ብልጽጎ ማዬት ያመናል። ለማንም አንተኛም። ይህ ሁሉ መልካምነትን እያዬን እንኳን ስንት ነገር ነው እምንጽፈው፤ እምንናገረው … ሰው ማበርከት አናውቅበትም፤ አልተሰጠነም፤ ጸጋችንም አይደለም። ድርሻችን መንቀል ነው። ወይ ማጠውለግ። በዚህ በ አዲሱ ንግግር ያዬሆት የተጠወለገ መንፈስን ነው።

 

ውዶቼ እኔ እንደማስበው ሳይሆን እንደ አፋችሁ ያድርግልኝ። እኔ እንደ እናት ነው እማስበው። ለማንም ሰው እማስበው ከቤቴ እንግዳ መጥቶ ከሄደ ደውሎ ደርሻለሁ ካለልኝ አልተኛም። ጭንቀታም ነኝ። ለዚህ ነው አውሮፕላኑ በሰላም ኢትዮጵያ እስኪገባ አስባለሁ ያልኩት።

 

ሴራ ሲደመርባት በኖረችው አላዛር ይህን የመሰለ መሪ ከሰማይ ዱብ ሲል በዝምታ፤ በችሮ፤ በልግስና ህይወቱ እንዲቀጠል ይፈቀድለታል አይታሰብም። ቢቀጥል እንኳን ቆጥቦ በተሰጠው መንግድ ብቻ መራመድ ካልሆነ ጋዳ ነው …

 አሁን ለባለቅኔው ጠ/ ሚር አብይ አህመድ ብቻ ሳይሆን ብቻ ሳይሆን እሳቸውን በቅንነት ለደገፉ የካቢኔ አባላትም፤ በሩቅም በቅርብም ላሉት ሁሉ አደጋው ቀላል አይደለም።

 

ለሁሉም ግን መጸለይ ነው። በፊትም ቢሆን ቀን ከሌት ተጸልዮ ነው ከዚህ የተደረሰው፤ ወደፊትም ወገባችን ታጥቀን ቢያንስ ለህፃናት ስንል እንጸልይ። መርዶ እና መርዶ ተደምሮ መንፈሳችን መርዶ አድርጎታልና።  

 

የኔዎቹ በተረፈ ላደረጋችሁልኝ መልካም ነገር እጅግ አድርጌ በድጋሜ አመሰግናችሁ አለሁኝ።

 

ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር።

 


ቸር ወሬ ያሰማን። አሜን። 

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።