እልልልልል

የመልካምነት 
ቤተ -ክብረት!
„አግዚአብሄር ጥበብን ይሰጣልና፤ ከአፉም ዕውቀትና ማስተዋል ይወጣሉ፤ 
እርሱ ለቅኖች ደህንነትን ያከማቻል፤ ያለነውር ለሚሄዱት ጋሻ ነው፤ 
የፍርድ ጎዳና ይጠብቃል፤ የቅዱሳኑንም መንገድ ያጸናል።“
 መጽሐፈ ምሳሌ ምዕራፍ ፪ ከቁጥር ፮ እስከ፰
ከሥርጉተ©ሥላሴ
10.09.2018
ከገዳማዊቷ ሲዊዘርላንድ።


             ሃይማኖቴ ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሆይ! ኮራሁብሽ! ተመስገን!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶን ቤተክርስትያን „አገር ናት“ ያሉት ጠ/ ሚር አብይ አህመድ በቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን በ50 ዓመት ታሪኳ ለአንድ የአገር መሪ ጸጋን ስትሸልም፤ ልቅናን ስታከብር የመጀመሪያዋ ነው። 

ይህቺ መከራ ፈተና እና ፍዳ ተልይቷት የማታውቀው ቅድስት ቤተክርስትያን ምን ያህል ከውስጧ የዘለቀ የማስተዋል ጸጋ እንደተሰጣት በዚህ ብቻ ማመሳከር ይቻላል። ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ የሰላም አብነት ተቋሙነቷን የረጋገጠችበት ማዕልት ነው ማለት እችላለሁኝ - እኔ። ይህ የክብር ዕውቅና ምርቃትም ነው። ምርቃቱ ለትወልዱም፤ ለአገርም፤ ለማህበረ - ምዕምኑም፤ ለአገልጋዩም ለመልካ ምድሩም፤ ለተፈጥረዊ ጸጋውም ጭምር ነው።

ይህ ትውልድ ሆነ ማህበረ ምዕመናኑ ለነፃነቱ ተጋድሏል፤ ሙቷል፤ ታሠሯል፤ ተሰዷል፤ አካሉን አጥቷል፤ ክብሩ ተገፏል፤ ባዕቱን ተነጥቋል። ማንነቱን ተቀምቷል። ይህን ሁሉ ችግር ተሸክሞ ደግሞ አገራዊ፤ ብሄራዊ ግዴታውን ሲወጣ በትጋት ቆይቷል።

ሃይማኖታዊ ቀኖናው እና ዶግማው የሚፈቀድለትንም አማኙ ሲከውን ኖሯል። በሃይማኖቱም ተሳዷል፤ ተነግላቷል። ሁሉንም እንደ አዬመጣጡ ታግሶ የኢትዮጵያ ህዝብ ለዛሬዋ እሸት አንበጥ ዘመን ደርሷል።

መልካሙ ነገር ያ የሰቆቃ ዘመን ተወግዶ ሃይማኖት መቀበል፤ ማመን፤ ማክበር እና በዛ ውስጥ ለመኖር መፍቀድ ነፃነት ስለመሆኑ በብሄራዊ ደረጃ በመንግሥት ዕውቅና ማግኘቱ ብቻ ሳይሆን በሃይማኖታቸው ጽናት ምክንያት የተሰደዱ፤ የተንገላቱ ብጹዕን ይቅርታ ተጠይቀው ከፍ ባለ ክብር እና ልዕልና ወደ መደበኛ ተስጥዖቸው፤ ማለትም ለአገርና ለህዝብ የመጸለይ ትጋታቸውን እንዲቀጥሉ የተደረገበት ሁኔታ እዮራዊ ነው።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ፤ በኢትዮጵያ እስልምና እምነት ተካታዮች፤ ጎልቶም ያለዬነው በወንጌላውያኑም አማንያንም የነበረው መከፋፈል ዘመን ሲሰጥ፤ በቃችሁ ሲለን በሙሴው አብይ አማካኝነት ሁሉም መስመር ያዘ። ተመስገን!

የተቀባ ሲገኝ መንገዱ ሁሉ፤ የረገጠው ሁሉ የአሮን በትር ነው። ለምለም ነው። መፍትሄ ነው። ሰናይ ነው። ተስፋ ነው። ሐሤት ነው።

ዛሬ ከኢትዮጵያም አልፎ በአገረ ኤርትራ እና በጎረቤት አገሮች ያለው የአፍሪካዊነት ውህዳዊ መንፈስ እጅግ አበረታች ነው። ስለሆነም ነው ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ይህን የወርቅ ካባ ከውስጥ ከመነጬ ምርቃት ጋር ለጠ/ ሚር አብይ አህመድ እና ለደልዳዋ ቀዳማይ እመቤት ለክብርት ዝናሽ ታያቸው ሙሉ በረከቷን ያለበሰቻቸው።

የተገባ ውሳኔ፤ የተገባ እርምጃ እና እውነት የሆነ ጸጋ እና ረድኤትም ነው። መንፈሱ ሰውነቴን እራሱ ወረረው። ተመስገን!

ባልና ሚስት ከአንድ ወንዝ ይቀዳል እንደሚባለው ቸርነታቸውን ያስቀጥል አማኑኤል አባቴ እያልኩኝ ዛሬ በመንፈስ የቆረቡት፤ እንደ አባት አዳሩ ልዑል እግዚአብሄር በፈቀደው መጠን ትሩፋተ - ቅብዕ ሠርጋቸውም ስለሆነ እንኳን ለዚህ አበቃችሁ ልላቸው እሻለሁኝ ሁሉቱን የቤተ መንግሥት ፈርጦች ጥንዶች።

    በተጨማሪም እንቁጣጣሽም ማለት እሻለሁኝ። 
መጪው ዘመን የፍስሃ የደስታ የታታሪነት የትጋት የቻይነት የታጋሽነት የበለጠ ተቀባይነት እና የስኬት እንዲሆን ከልብ እመኛለሁኝ።

አላዛሯ ኢትዮጵያ ሰቆቋዋ ተወግዶ ተስፋ የበለጠ ስፍቶ እና ፈክቶ የምናይበት ዘመኗ እንዲሆን ከልብ እምኛለሁኝ። ተመስገን!

ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር!

የኔዎቹ ኑሩልኝ መሸቢያ ጊዜ።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።