የዴሞክራሲ ግማዱ እና ገመዱ;

እንኳን ደህና መጡልኝ።
የዴሞክራሲ  
ግማዱ እና ገመዱ

ምንም እንኳን በለስም ባታፈራ፣ በወይን ሐረግ
 ፍሬ ባይገኝ፣ የወይራ ሥራ ቢጓል እርሾችም መብልን
 ባይሰጡ በጎችም ከበረት ቢጠፉ ላሞችም በጋጥ ውስጥ
 ባይገኙ እኔ ግን በእግዚአብሄር ደስ ይለኛል፤
በመዳህኒቴ አምላክ ሐሤት አደርጋለሁ።
ትንቢተ ዕንባቆም ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፲፯ ቁጥር ፲፰

ከሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
28.02.2019
ከእመ ዝምታ - ሲዊዘርላንድ።


·       እፍታ።

ውዶቼ እንዴት ናችሁ ደህና ናችሁ ወይ? አንዳንድ የኢሜል ወዳጆቼ መልዕክት እዬላኩልኝ ነው። እምታምኛቸው መሪዎች „ኢትዮጵያን ከዱ“ እዬተባልኩ ማለት ነው። እኔ እኮ መልካም ሲሰሩ እንደማመሰግናቸው ሁሉ ትክክል አይደለም የምለውን ደግሞ እስሲበቃቸው ድረስ ነው እማከናንባቸው። ቅን መሆን፤ ልብን ከፍቶ መቀበል፤ አወንታዊ መሆን፤ አዲስ እንግዳ ሲመጣ አንጥፎ ጎዝጉዞ መቀበል የአባት አደሩ ነው። ይሄ ሆነ ብዬ ወደፊትም መልካም ነገር ሳይ አልሸሽም። 

በሌላ በኩል በቀደመው ጠ/ሚር ከመሆናቸው በፊት በነበረው የጠ/ሚር አብይ አህመድ ንግግር ውስጥ ሁሉ አንደም ውስልትና በኢትዮጵያ ላይ አላገኘሁም። አሁንም ይህ ጽኑ እምነቴ ነው። የአፍ ወለምታ ግን አያለሁኝ። ይህንም በተለያዬ ጊዜ ሞግቻቸዋለሁኝ።
እራሱ የሰሞኑን የለገጣፎ ጉዳይ የድርጅታቸውን ወስኜ "አላውቀውም የከተማ ከንቲባ ስላልሆንኩ" ያሉትን ጽፌባቸዋለሁኝ። አፋር ላይ „ደርግ የወረደው ህዝብ ስለጨፈጨፈ ነው“ ስላሉም ይህንንም ሞግቻቸዋለሁኝ፤ በቅርቡም እንዲሁ አንድ ከብድ ያለ አምክንዮ እነስቼ ሞግቻለሁኝ።
https://sergute.blogspot.com/2019/02/blog-post_2.html

ያቃታቸውን ነገር "ህሊናው ታስሯል ብለው አቃለው" ያዩትን ጉዳይ ሰፊ ሀተታ ነው የጻፍኩት የህግ ፋክሊቲውንም፤ የጸጥታ አስከባሪውንም መዝጋት ነው እስከማለት የደረሰ … እንዲያውም እንደ እኔ የሞገተ የለም።

የስሜን አሜሪካ ጉዟቸውንም „እኔ አሻግራችሁለሁ“ ያሉትን ሊሂቃኑ በዛ የተገኙትን፤ ጋዜጠኞች፤ የፖለቲካ ሰዎች ሳይሞግቷቸው በመቀረታቸው ወቅሼ ጽፌአለሁኝ።  ይሁን ብዬ አልፌያቸው አላውቅም ግድፈት ነው የምለውን። ስለ ቆመስ ኢንጂነር ስመኛውም ጉዳይ በጣም በድፍረት ገፋ አደርጌ ሁሉ ጽፌያለሁኝ። በኦነግ ጉዳይም እንዲሁ። በራስ ላይ ለመጨከን አለመድፈርን ምን ያህል እምነትን እንደሚሸረሽር ሁሉ ሰፋ አድርጌ ጽፌያለሁኝ።

ሌላው ጥገናዊ ለውጥ መሆኑን አውቃለሁ፤ አሁንም ኢህአዴግ መሆኑን እረዳለሁኝ፤ ሰው ፍጹም አለመሆኑ አውቃለሁኝ፤ ችግርችን ወዘተረፈ እንደሆነም የኖርኩበት ነው። መላክ አልጠብቅም። እኛ እኮ ከሞትም እንኳን የምንዳላ ሰዎች ነን እኮ። ገመናችን እኮ ብዙ ነው።  በዚህ በለውጥ ውስጥ እንኳን ተሁኖ ስንት ሴራ ነው ነው ያለው?

እኔ ለእኔ እውነት ነው ከምለው ጎን መሰለፈ ዘመን አመጣሽ አይደለም። ፍጥረቴ ነገሬ ይኸው ነው። ለዚህ ነው የተፈጠርኩት። ዋሽንግተን ዲስ ያላችሁ አንባሳደር ወንድወሰን ሃይሉን አግኝቶ መጠዬቅ ነው፤ ኢትዮጵያ ያላችሁ ደግሞ ጓድ ገ/መድህን በርጋን አግኝቶ መጠዬቅ ነው። መጥታ ግንባር ግንባራችን ሳትለን ቤታችን እናሰናዳ ነበር የሚሉት። ዋዘ ነገር የለም በ እኔ ቤት። ኮሰትር ያልኩ ወጣት ነው የነበርኩት እንኳንስ አሁን በሙሉ ዕድሜ።

ይኸው ነው እኔ ባህሬዬ ግልጽ፤ ቀጥተኛ፤ ቆራጣ ከቂም ጋር ንክኪ የለለኝ፤ ሰተት ብዬ ችግር ውስጥ ደፍሬ የምገባ፤ ሥለ ሥም እና ከንቱ ውዳሴም ደንታ የማይሰጠኝ በዛ ላይ አዛኝ ፍጥረት ነኝ። ሩሁርህ ነኝ። በዛ ንግግር አሁን ተተርጉሞ በቀረበው በዶር ለማ መገርሳ ውስጥ እንኳን ዕንባዬ ነው የተንዠከዠከው። አዘንኩኝ። ሀዘኔ ለኢትዮጵያ ነው። ለዚህ ነው ኢትዮጵያን አላዛሯ ኢትዮጵያ እምላት።

·       ንሽ ተመክሮዬን ላጋራችሁ …

አንድ ጊዜ ግብዣ ላይ የሰው ደም አልበላም አልጠጣም ብዬ አሻም ብዬ ጓድ ገ/መድህን በርጋን አስደንግጨው ነበር ሻ/ ገብረህይወት ባዘጋጁት ግብዣ ላይ። ይህንም አሁን በህይወት ያለ ብሎጌን የሚከታተል ጓዴ ንስሩ ይታዘበኛል አብሮ ስለነበር። ሌላ ጊዜም ጓድ ፍቅረስላሴ ወግደረስ ጎንደር መጥተው እሳቸው በተገኙበት ሥርዓት ሳንገኝ ከሄዱ በኋዋላ ተገኙ ስንባል ትራፊ ልበላ አልሄድም ብዬ ተልይቼ ቀርቻለሁኝ። 

ያ ጉዳይ ሆኖ ያው የሴራ ፖለቲካ በዛ ተገኝታ ይህም ስህተት ሆኖ ሥርጉትሻ ለወቅቱ የክ/ አገር ጸሐፊ ተከስኩኝ „ደውለው እንደልቡ ስለምን ነው ያልተገኘሸው አሉኝ“ ነገርኳቸው። ሞገደኛ ነኝ።

እዚህ ያለው የፖለቲካ መሪ ነኝ ባዩ ችግር እኮ ይህ ነው ዝልቦ ልቡን ገጥሞ እንደ አሻንጉሊት እጋልባታለሁ ለማለት ድፍረቱ ነው እኮ የዚህ ሁሉ ፈተና ምንጩ። አለመተዋወቅ። እንኳንስ ጎርፍ አምጥቶ ለቆለለው የንፋስ ፖለቲከኛ ነፍስ እነዛ የአገር እጬጌ ለነበሩት ባለቅኔ አለቆቼም ካለምነኩበት በጅ አልልም።

አንድ ጊዜ ሌላ የሆነውን ልንገራችሁ፤ የጤና ጥበቃ ፈተና ይሰጥ ነበር ለነርስነት። የኢሠፓ ተወካይ ኮሜቴው ይፈልግ ስለነበር እኔ ተወከልኩኝ። ከዛ አንዲት የአኢሴማ የክ/ አገር አመራር ነርስ በሙያዋ ልጇ ይወዳደር ነበር። 

እና እንዳሳልፈው የክ/ አገሩ ተቀዳሚ ም/ አስተዳደሪ ደውሎ ይነግረኛል፤ አልችልም አልኩት፤ ለምን ሲለኝ ለብሄራዊ ውትድርና ሲወዳደር የሳንባ በሽታ ከኖረበት ለነርስነትም ስለማያበቃው አልኩት። ደነገጠ። እችላለሁ አለ። ኮሜቴው ከእኔ ውጪ የሚሰራ ከሆነ ጥሩ ነው። አልቀጥልም አለኩኝ በኮሜቴው ውስጥ። ጉዳዩ ከጓድ ገዛህኝ ወርቄ ከክ/ አገሩ የፓርቲ አንደኛ ጸሐፊ ደረሰ። የወከልናት ለዚህ ነው ብለው እኔን ደግፈው ቆሙ አሸንፍኩኝ።

ያለፈውም ደግሞ የሚገርማችሁ ከጠዳ እርቃ የምትኖር አንዲት ገጠር ጉንብሪት ትመስለኛለች ካልረሳሁት እዬተመላለሰ በእግሩ የሚማር ተማሪ ነበር። የሚገርመው ሰዓት አልፎበት ፈታኞች የሚመጡት፤ ፈተናውም የሚመጣውም አዲስ አባባ ነበር እና።
የመፈተኛው ሰዓት ሲያልፍ ለፈተና እንዲቀርብ የወሰንለት ወጣት አልደረሰም እና የቁርጥ ሥራ እንስራ አልኳቸው፤ 30 ደቂቃ እንድንጠብቀው ብዬ ተማጸንኳቸው። ምክንያቱ ማርኩ ከፍ ያለ ነበር። ያ ወጣት የገበሬ ልጅ ነው። እኔና ገበሬ ደም እና ሥጋ ነን። የከተማ ልጅ አልመስልም ለገበሬ ያለኝ ወገናዊነት። እና 30 ደቂቃ ሳንጠብቅ ደረሰልን። ትንሽ ጊዜ ሰጠነው እንዲረጋ። ተፈተነ ደፈነው ፈተናውን እና አለፈለኝ። አንድ ወንድ ሦስት ሴት ነበር የምንወስደው።

ከዛ ህወሃት ሲገባ እናቴ ለህክምና ስትሄድ እናቴን ወቀሳቻት ነርሷ ልጇን ከውድድር ውጭ ስላደረኩት። እናቴ ግን ነገረቻት ራዲዮን ካለሽ አዳምጫት በዚህ ሰዓት የዓለም አቀፍ ራዲዮ ጋዜጠኛ ናት አንበሲት አላቻት፤ እንዳችም አይደለችም እሷ ተሰልፋ እጇን አልሰጠችም፤ ጫካ ወጥታ ታግላ በምህረት ተልምና ገብታ አሁን ደግሞ ከደራጃዋ ላይ አለች አለቻት። እስከዚህ ድረስ ነው እመሄደው። 

አለቃ አለቃዬ የሚሆነው እውነት መንገዱ ከሆነ ብቻ ነው። ወለም ዘለም የለም። ደግሞም ሌት እና ቀን ነው የምሰራው እንደ ብረት። በሥራ ደክሜ አላውቅም። አሞኝ እንኳን ህመሜን አላስታውሰውም።
   
የሆነ ሆኖ አሁንም በለውጡ ውስጥ ባሉ መልካም ነገሮች እምደግፋቸውን እደግፋለሁ፤ እምተቸውን ደግሞ አልምረውም። በሌላ በኩል ዶር ለማ መገርሳን ሚኒያ ላይ ባደረጉት ንግግር ተችቼ ሁሉ ጽፌያለሁኝ። ቶኑ እኛ ያገልለናቸው ያህል ነበር። 

እንኳንም አገኘኋዋችሁ፤ እንኳንም ኖራችሁልኝ አይነት ስለነበረ አየር ላይ በነበረው ሃሳብ የመስጠት ሂደት ብቻ ሳይሆን ያ ሁሉ ትህትና ያ ሁሉ ልስላሴ ምኑ በላው ብዬ ጽፌያለሁኝ፤ እህቴ እራሱ ምን ነካቸው የኔታ ብላኝ አብረን ተወያይተንበታል።

እሷ ፕሮ ፋይሏ ላይ የሳቸው ምስልም ስለነበር። „አራቁን እኮ ነው ያለችኝ።“ በሀምሌው ዝምታ የት ናቸው? አቋማች ምንድን ነው እያልኩ በተለያዬ ሁኔታ ጽፌያለሁኝ። በሻሸመኔው፤ በቡራዩ፤ በአዲስ አባባ ጉዳይ ጽፌያለሁኝ። በጣም ደፋር ጹሁፍ። 

መልካም ሲሰሩ ደግሞ አመሰግናቸዋለሁኝ። አበረታታቸዋለሁኝ። ወደፊትም እንዲሁ እቀጥላለሁኝ። ሰው ናቸው እኮ እነዚህ ፍጥረቶች። ለራሳቸው ወገኖች ማድላታቸው ደግሞ ተፈጥሮኛ ነው። የሚሞገሱት እኮ ወይ ኦርምያ በሚሉት የተፈጠሩ ወይ ደም ያለባቸው ስለመሆናቸው ሁሉ እኔ አስተውላለሁኝ። በሁሉም ያለ ስለሆነ አይደንቀኝም። ሁሉም እኮ የራሱን ነው የሚያስቀድመው። ሲበዛ መጠኑን ሲያልፍ ግን ሲከር ይበጠሳል ሲሞላም ይፈሳል።

በተረፈ ግን ማንም የማያደርገውን ድንቅ ዕንቁ ተግባር ከውነዋል። በዛ በደመቀ ተቀባይነት ውስጥ የኦህዴድ ሊቀምነበርነት ለዶር አብይ አህመድ ሰጥተዋል። ይህ መቼውንም ቢሆን የምዕት ቅኔነታቸውን አይሰብረውም፤ አያበልዘውም በሥርጉትሻ ህሊና ውስጥ ይኖራል እንደ ተከበረ። ደፋር እርምጃ ነበር። ማንም አያደርገውም። 40 ዓመት እኮ ነው ተጎልተውበት ነው ያለቱ። እነ ዶር አረጋይ በርሄ፤ አነ አቶ ሌንጮ ለታ፤ ዶር ዲማ ነግዖ ወዘተ … ። አሁንም አማራ ካልደቆስን ብለው እየታተሩ ነው በወልዮሽ፤ በአማራ ተገድሎ ደም መገበር ለአገር በቅተው።

ወደ ቀደመው ምልሰት ሳደርግ 27 ዓመት በፖለቲካው መስመር የከፋት ነፍሴ ቢያንስ 8 ወር ሰላም አግኝታለች፤ ጤናዬ ተመልሷል። ገንዘቤም አርፏል ፖስታ ቤት ለፖስታ ቤትም እልነከለከልም። ብዙ አላለቅስም። 

ስላለፈ ሊረሳ አይገባም ብዙ እጅግ ብዙ የመንፈስ ትርፍ ተገኝቷል በዚህ ለውጥ። የኢትዮጵያን ብሄራዊ ሰንደቅዓላማ በድምቀት ተወልብልቧል በመላ አገሪቱ። የነገን ባላውቅም። ያ ድል ነው ነፍሴን የማረከው ያፍነሸነሸው ጉዳይ ነው።

እስር ቤት የነበሩ ወገኖቼ ከቤተሰባቸው ጋር ተገናኝተዋል፤ ሞት የተፈረደባቸው ወገኖቼ አገር ቤት ገብተው ወላጆቻቸውን አብሶ ከእናታቸው ጋር ሲገናኙ አማኑኤል ነው የሚያውቀው የተሰማኝን ፍሰሃ። ተፎካካሪ/ ተቀናቃኝ/ ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች አገር ገብተዋል፤ የአማራ ድርጅት ተመስርቷል፤ ሰው መተንፈስ ችሏል።

አብረው ለደቂቃ የማይተያዩ ወገኖች በአንድ መድረክ አብረው ተገናኝተዋል። የተገለሉም ቢኖሩ። ህይወታቸው ያልተፈለጉትም አገር ሲገቡ ቢገደሉም። ለድል ሲባቃ በብክል ቢወገዱም፤ ብዙ ኢትዮጵውያን ቤተሰባቸውን ሄደው አይተዋል፤ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ ታርቀዋል፤ የምንወዳቸው የምናከብራቸው ኤርትራዊ ጎረቤቶቻችን ተመልሰው ኢትዮጵያ መኖር ጀምረዋል፤ ብጽዑን ቅዱሳን አባቶቻችን ለአገራቸው መሬት በቅተዋል፤ እናት እና ልጅ ተገናኝተዋል። አባት እና ልጅ ተገናኝተዋል። የሠራዊቱ አባላትን ቀነ ብለው ማዬት አይኔ ችሏል። ለውጡ ብዙ ትርፍ አለው።

ሰሞኑን የተከሰተው አሁን ነው ለሌላው አዲስ የሆነው እንጂ እኔ ወንበሩ ባዶ ነው ብዬ ሁሉ ተናግሬያለሁኝ። በህልሜ አመላካችነት። ከሀምሌው ዝምታ የቡና ፖለቲካው ወዲህ ስንጥቅ እንዳለ በተደጋጋሚ ጽፌያለሁኝ። መፈንቅለ መንፈስ እንደነበር አስተውላለሁኝ

እሰረኛ ነበሩ እኮ ጠ/ሚር አብይ አህመድ። ያው በሽታውን የማይናገር ሆኖ የራስ ወገን ገመና ሆኖ ሸፋፍነውት ነው እንጂ ብዙ የታመቀ ትዕይንት ነበር በራሳቸው በቅርብ ሰዎች በተጠነሰሰ ሴራ፤ አሁንም አሉ። ውጪ ሲወጡ እኮ ነጻ አይደሉም ጠ/ሚር አብይ አህመድ። ታስረው ነው። እንዳይተነፍሱ።

አሁንም የዛ ግብረ ምላሽ ነው እያዬን ያለነው። በታምር እኮ ዳግሚያ አባ ኮስትር አቶ ንጉሡ ጥላሁን ያን ያህል ጠ/ሚር አብይ አህመድን እዬጠሉ የሳቸው አንደበት ሊሆኑ አይሾሙም ነበር። ዶር አንባቸው መኮነን እኮ የጠ/ሚሩ የልብ የቀደመ ጓደኛ ናቸው፤ እሳቸው ተንሳፋፊ ወይንም ማሟያ ናቸው፤ ለግብር ይውጣ ነው የተቀመጡ … ወይንም በግዞት ያሉ የለውጡ አናት ሚ/ር።

የጠ/ሚሩ የውጭ ጉዞ፤ ጠ/ ሚሩ የሚያደርጉት ከውጭ አገር መንግሥታት ጋር ያለውን ግንኙነት ሁሉ እኮ ኦዴፓ ብቻ ነው እዬመራ ያለው። እነዚህ ሁነቶች ከሀምሌው ዝምታ ወዲህ የተከሰቱ ስለመሆናቸው እኔ አስተውላለሁኝ። ለዚህም ነው ጠ/ሚር አብይ አህመድ በጀመሩት አቅም ልክ አልተንቀሳቀሱም ስል የባጀሁት። ማነቆ አለ። 

ገደብ ያጣው የኦዴፓ የበላይነት አቶ ፍጹም አረጋን የአሜሪካ ባለሙሉ ሥልጣን አንባሳደር አድርጎ ከሾመ በኋዋላ ደግሞ ሳያፍር ይሉኝታ አጥቶ  ያም እንዳይቀርበት ለአለም የኢኮኖሚ ፎረም እሳቸው ሲገኙ የኤኮኖሚ አማካሪ ተብለው የተሰዬሙት ዶር አንባቸው መኮነን ግን ቢሮ ጠባቂ ነበሩ። ይህንን ማንም አላነሳውም።

በሌላ በኩል ሰሞኑን ፕ/ መራራ ጉዲናን አጅበው መከረኛው ግርባ እንዲሆን፤ ጊዜ የማያስተምረው አማራ ሊሂቃን ጋር ባህርዳር ነበሩ ዶር አንባቸው መኮነን፤ በተጨማሪም ሲዳማ ህዝብ ጋር ደግሞ ስለ አማራ ጨኳኝነት አብሮ ለመመከር በዛ ለመቃኘት አቶ ሌንጮ ለታ ወደ አዋሳ ተልከዋል። እንደነዚህ ዓይነት ቅይጥ ደራማዎችን አይቼ ዝም አላልኩም ጽፌያለሁኝ። መዳን ስላለበት ለውጡ ከኦነጋውያን አይዲኦሎጂ

ቀድሞ ነገር የአሜሪካ ባለሙሉ አንባሳደር ሆነው የተሾሙት አቶ ፍጹም አረጋ ቦታው የብአዴን ነበር፤ ያው ያን ጊዜ ትግሬ ስለተገኜ ማለት ነው አንባሳደር ካሳ ተ/ብርሃን ነበረሩበት፤ አሁን አንድ ሰው ከስንቱ ይድረስላቸው ለኦዴፓ ሊንካቸው አቶ ንጉሱ ጥላሁን ስለሆኑ አይሰነጥቋቸው ነገር በፈጠጠ እርምጃ ያው እሳቸው ወደ ጠ/ሚር ቢሮ ሲመደቡ አቶ ፍጹም አረጋ ደግሞ የአሜሪካ ባለሙሉ ስልጣን አንባሳደር ሆነው ተሾመዋል። 
አይዋ ብአዴን እንቅልፉን ይለሸልሻል እንደለመደበት። ዴሞክራሲ እንግዲህ እንዲህ ነው … በራሳቸው ውስጥ እንኳን ያልሞከሩትን ዴሞክራሲ ነገ ዴሞክራሲ ፍንጩ በኢትዮጵያ ያብታል ለማለት ፈተና ነው ገመድም ግማድም።

·       በለግማዱ ባለ መዱ ዴሞክራሲ።

የሆነ ሆኖ ዛሬ መነሻዬ ስለ ባለግማዱ፤ ባለገመዱ  ዴሞክራሲ ነው። መቼም ዴሞክራሲን ቁምጥ ብለን ልናዬው እንሻለን። ናፍቆናል። ከምወደው እና እጅግም ከምሳሳለት ከሳተናው ድህረ ገጽ ትናንት ያዬሁት አንድ መረጃ ደግሞ አለ።

በሃገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ መካተት ለሚፈልጉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በሩ ክፍት ነው ተባለ።

ይህን የገለጹት  የኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሳዳት ነሻ እንደሆኑ ነው ይህን አሉ የተባሉት። ያው ሳተናው ድህረ ገጽ ላይ ገብቶ መረጃውን ማገናዘብ ይቻላል።

·       ሊገደን የሚገባው ጉዳይ።

ይህን ኢህአዴግ ወደ ኢትዮጵያዊ ፓርቲ እሻገራለሁ ማለቱን በሚመለከት ብዙ ሰው አልጨነቀውም። የፖለቲካ ድርጅቶችም ጉዳያቸው አልሆነም። ያው እጮኛ ሆነው የባጁም ስላሉ ይመሰለኛል። አራጊም ፈጣሪ ሆነው የሚያስገልሉትን ሲያስገልሉ፤ በጥርስ የሚያስይዙትን ሲያስዙ ነውና የባጁት። በቅይጥ ድብልቅ ድንብልብል።

ነገር ግን ህዝብ አጀንዳ አደርጎ ሊወያይበት ይገባ ነበር። እኔ ግን ሰፋ ያለ ሀተታ ጽፌበታለሁኝ። አደራጅ ነኝ እና ለስሜቴ ቅርብ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ዕጣ ፈንታ የሚወነሰው በዚህ ስለሆነ ጉዳዬ ብዬ ጽፌዋለሁኝ። እንዲህ ብዬ ነበር …

„ለመሆኑ ኢህአዴግ አሁን ያሉትን 7 ሚሊዮን አባላቱን አብሮ አዋህዶ ነው ወይ ይህም ሌላ መከራ ነው? ስንቱ ከእሱ ጋር ሊቀጥል ይወዳል? እንደገናም ወደ እሱ ወደ አዲሱ ፓርቲ ኢዴፓ እጠቃለላሁ የሚል ተፎካካሪ/ ተቀናቃኝ/ ተቃዋሚ ቢኖር እንዴት ለማስተናገድ ተሰናድቷል። ለምሳሌ ህወሃት ከወጣ ቁምጥ ብለው የሚጠብቁ ድርጅቶች ሊኖሩ እንደሚችሉ ከተፈጥሯቸው መተንበይ ይቻላልና።“

የኢዴፓ እጩነት /አዲስነት ትልሞሽ/

 በ25.02.2019 ሊንኩ ይሕው ያለኩትን የጠዬቅኩትን ነው መልስ ኢህአዴግ የሰጠበት። ኢዴፓ / የኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ፓርቲ/ የሚለውን እኔ ዛሬ ሳይሆን በመስከረም ነበር የጣፍኩት። ሌላ ሥምም ያምጣ ጉደኛው ኢህአዴግ አቶ አስመላሽ ወ/ሥላሴን አማካሪ አድርጎ ጉብ አድርጎ የለ።  ጉድጓድ ተቀብሮ የባጀውን ውሻ ደጁ ላይ አስሮ ነው ወጥ ፓርቲ እመሰርታለሁ የሚለን። ህወሃት ቢራራልኝም ብሎ ... 

ማስፈራሪያ ይሁን አራጣ አይታወቅም የሳቸው እዛ ቦታ መመደብ። ይህን ተሸክመው ነው ተፎካካሪ ፓርቲዎች የሚዳበሉት። ግንቦት 7 መቼም አብሮ እንደሚደመር አስባለሁኝ። ሥራ ቀለለት። ሌለው ቀለብተኛ ግን የለመደበት ነው እና ተራ ይያዝ … ሰባራ ወፍ ሳትቀድመው።

አሁንም ኢህዴግን ሞጥሬ መሞገት እሻለሁኝ። በእሱ በድርጅቱ ውስጥ ዴሞክራሲ እንደለሌ። ምንማለት ነው ይሄ? በመስከረሙ ጉባኤ እኔ ወጥ ፓርቲ እጠብቅ ነበር። ግን ወሰነው ብቻ ነው የተለያዩት። ስለዚህ የወጥ ፓርቲነት ውሳኔው ጉባኤው የወሰነው ስለሆነ ጉባኤው የውክል አካል ድምጽ ስለሆነ ምንም ችግር የለበትም።

አሁን ይህን ለተቃዋሚ/ ለተፎካካሪ/ ለተቀናቃኝ የፖለቲካ ድርጅቶች ኢህአዴግ በሩን ክፍት ማደረጉን ማነው የወሰነው? የኢህአዴግ ፖለቲት ቢሮ? የኢህአዴግ ማዕከላዊ ኮሜት ማን? ትልቅ ውሳኔ እኮ ነው። ከወሳኔም በፍጹም ሁኔታ የተለዬ ውሳኔ? ይህን የሚያክል 27 ዓመት የገዛ የፖለቲካ ግንባር እንዲህ ሚዲያ ላይ ወጥቶ ሲናገር በዬትኛው አካሉ ውሳኔ እና ይሁንታ ነው "ለተፎካካሪዎች በራችን ክፍት ነው" የሚለው?

ለዚህ ውሳኔ እኮ ጉባኤ ያስጠራል አስቸኳይ ጉባኤ። ምክንያቱም የግንባሩ ህልውና ነውና። ግንባሩን የሚያፈርስ እርምጃ ነው። ለዲሞክራሲ ከሆነ ውጥኑ። ራሱ አውራው ፓርቲ ኦዴፓ የኦሮም ዴሞክራሲ ፓርቲ አይደለም ወይ የሚባለው? „ዴሞክራሲ“ የሚለው ሥም ነው? ተወላጠ ሥም ነው? ቅጥል ነው? ቦዝ ሀረግ ነው? ከዬት ይመደብ? ይህችን ብቻ ነጥለን ስናወጠው። በውነቱ ተዘባርቆበታል ኦዴፓ።

7 ሚሊዮን የግንባሩ አባላቱ ሳይመክሩበት፤ ሳይወያዩበት፤ ሳይተቹት፤ ድምጽ ሳይሰጡበት እንደ እኛ ሚዲያ ላይ ነው የሰሙት።  ስለሆነም አሁንም ከላይ ወደታች በዴሞክራሲያዊ ማዕክላዊነት የሚጫንባቸው ማለት ነው።

ቢያንስ አባላቱ በዬደራጃው መወያዬት ባይችሉበት እንኳን ወኪላቸው ብሄራዊ ጉባኤው ተወያይቶ ፈትሾ ማጽደቅ ነበረበት፤ ይህም ቢቀር ጉባኤው እስኪሰበሰብ ድርስ ጉባኤውን ተክቶ የሚሰራው ማዕካላዊ ኮሜቴው አስቸኳይ ስብሰባ ተጥርቶ በዛ መወሰን ይገባው ነበር።  

ዴሞክራሲ የሚጀምረው ከዚህ ነው። በዚህ ስሌት እኔ ሳስበው መጪው ምርጫ የዴሞክራሲ መንፈስ ክው ብሎ ይደርቅብኛል። የቀጣዩም የህዝብ ቆጣራ እንዲሁ። ስለምን? በራሱ ገዢው ግንባር ስላልጀመረው። አቅቶታል። ሌላው ቀርቶ በሠራዊቱ 7ኛ በዓል አስፈላጊም ባይሆን ባላምንበት የቀዩ ጦር ምርጊት አብናተዊ ጉዞ ስለሆነ የሠራዊት ትዕይንት የማስፈራሪያ አባዜ ስለሆነም በዛ ላይ ጠረኑ እራሱ ምረጡን ቅስቃ ነው የነበረው። የበዛ ምስጋና እና ሙገሳ። ያ ሁሉ የጭካኔ መከራ ተዘሎ።
  
እና አሁን እኔ እንደማስበው እራሱን እያፈረሰ ኢህዴግ እንዳለ ነው፤ ልክ እንደ ኢሠፓ። ራሱን እዬናደ ነው ግንባሩ። እና ገብያተኛውን ሁሉ አሰባስቦ እንደ ጽዋ ማህበር ምርጫ ለማሸነፍ ነው እዬተጣደፈ የሚገኘው።

በተለይ እኔ እማልጠብቀው እንዲህ ዓይነት ዝርክክ እና ሙርቅርቅ ሂደት ከጠ/ሚር አብይ አህመድ ነው። የዛ የአዲስ አባባ ጭፍጨፋ ሰሞን መሰሉ ተከስቶ ነበር። እሳቸው መንፈሳቸው የተደራጀ ስንዱ መሆናቸውን ቀደም ባለው ተግባራቸው ስላጠናኋዋቸው እንዲህ መያዣ መገረዣ የሌለው ነገር ሳይ ይገርመኛል፤ መዛኑን ግን ተመስገን ነው አላዝንም ትቸዋለሁኝ። ግን ምንድነው ጥድፊያ? የፖለቲካ ድርጅት እንዲህ በገብያ ግርግር ይመሰረታል ወይ?!

"ኢትዮጵያዊነት ሱሴ ነው" ትልቅ ፍልስፍና ነበር። የፍሬም ጌታ አድርጎ ለጌጥ ከማስቀመጥ እሱን በመሬት ላይ መሥራት በራስ ድርጅት መጀመር። "አዲስ አባባ" ለማለት የሚቃፈቸውን መሪዎች መግራት። ኢትዮጵያዊነት ከዛ ነውና የሚጀምረው።  በኦነግ ዓርማ ላይ ሲገኙ ቅጭጭ አላላቸውም ዶር ለማ መገርሳ ይሁኑ አቶ ንጉሡ ጥላሁን። ትንሽ ቢቀዬጥ ምን ነበረው?!

ሁሉም ንቅናቄ፤ ግንባር፤ ድርጅት ሲመሰረት በዚህ መንፈስ ነው በቃ ምርጫ መጣ ሲባል። ለምርጫ? በቃ! የህዝብ ፈቃድ እና አግልግሎት ተንሳፋፊ ነው። ለዚህ ነው እኔ አገርም ውጭም የነበሩት የፖለቲካ ድርጅቶች ሁለችሁም እኩል ናችሁ ከዜሮ ነው የምትጀምሩት የምለው።

ሌላው "የዴሞግራፊ ለውጥ" የዶር ለማ መገርሳም አዲሱ ፍልስፍና ደግሞ የመደመርን ፍልስፍና ከሥሩ የነቀለ ጉዳይ ከዚህ ጋር ነው እኔ የማዬው። መደመር ወረቱ አለፈ። ወይንም አለቀ። 

በጠ/ሚር አብይ አህመድ ድጋፍ ሰልፍ ላይ ከተሞች በሙሉ በሚያስደነግጥ መልኩ ልሙጡን የኢትዮጵያን ብሄራዊ አርማ ነው ይዘው የወጡት። ኦሮሞ ማህበረሰብ ከተሞችን በመመስረት ባህሉን አህዱ ብሎ መጀመሩን የሚያመሳጥር ትንግርት ነው ከሰሞናቱ ንግግር ያደመጥነው።

የገዳ አባቶቻችን ይህን አላስተዋሉትም እኛ እንጀምረው ነው። ይህም ወደ ሌላ ዕድምታ ይወስደናል። ከተማ የመመሰረት ባህል የማን ስለመሆኑ። በተደራጀ፤ በተገነባ ከተማ ላይ አንድ ነገር መጫን ወይንም በከተማ ማንነት ውህድ ሆኖ መቀጠል የፖለቲካ ብልህነቱም ሆነ የሥልጣኔ ዕድገትን ይጠይቃል። በዚህ ተደመሩ በዚህ ተነጠሉ?

ለነገሩ ደብረዘይት ናዝሬት አዳማ እና ቢሸፍቱ ቢባሉም የሆነው ግን በኢትዮጵያዊነት ውስጥ ስለመሆናቸው ምልክቶች ታዬተዋል በግንቦት 7 ስብሰባ። ስለዚህ ይህ አስግቶታል አውራው ፓርቲ ኦዴፓ፤ እና ሄሮድስ መለስ ዜናዊ ባደረጉት መልክ ነው አሁን ኦዴፓም እዬተጓዘ ያለው። በዚህ ውስጥ ዴሞክራሲን ፍርፋሪውን ማግኘት አይቻልም። 

ወጥ ፓርቲ ቢባልም ያ ወጥ ፓርቲ ኦሮማይ የማድረግ ሂደት ነው እዬተከተለ የሚሄደው። ደንቡንም፤ ፕሮግራሙንም የሚያዘጋጁት እነሱው ስለሆኑ። እዬተጠና የሚባሉ ብዙ ነገሮች ናቸው? እነማን አይታወቅም? ለነገሩ ሁለቱንም ኮሚሽን የደንበር ይሁን የእርቅና የሰላም አባላቶችን እያዬሁኝ የአላዛሯ ኢትዮጵያ መከራ ዘላቂነትን አይቸበታለሁኝ። እርግጥ በዝምታ ነው ያለፍኩት።

አብሶ የፖለቲካ ድርጅት ሊቀመናብርት መደበኛ የድርጅታቸውን ተግባር ትተው ለጥ ብለው ሰግደው ለኢህዴግ ሹመቱን ሲቀበሉ ምን ያህል በላሸቀ ዓላማ ውስጥ ስንት መዋለ ነፍስ እና ጥሪት እንደባከን አስተውያለሁኝ።

ምን አልባት እንጠቃለለን ከሆነ መልካም ነው፤ ትውልድም ያርፋል መቧከሱ እዛው እሱ በእሱ ስለሆነ። የሚገርመው ሁለት አባል ይዞ ሥም ተሸክሞ ወዲህና ወዲያ ሲንከላወስ የከረመው የዶር አረጋይ በርሄ መጠጊያ ያጣ ድርጅት ያን ቢያደርግ አይደንቀኝም፤ ሥራፈት ስለሆነ። ሥራ አልነበረውም። እዬገባ ከማፈረስ እና ከመበተን ውጪ። ግንቦት 7 እና ኦፌኮን ግን ይገርማል። ልባቸውን ጥፍት የሚያደርገው የወንበር ፍርፋሪ ነበር ማለት ነው … ግዙፍ ሥም ይዞ እዛ ኮሜቴ ውስጥ መግባት ትዝብት ነው … ብዙ ወዘተረፍ ሥራ ነበረባቸው ... ብቻ አብሮ የተመከረው አብሮ ለመቀላቀል ካልሆነ ... 

በግራም በቀኝም እንዳለ የማይታወቀው ስርዙ ብአዴን በዚህ ሂደት ውስጥ ብርቱ ጥንቃቄ ማድረግ ያለበት ይመስለኛል። ብአዴን መኖሩን የማይፈቅዱ እንዳሉም መታወቅ አለበት ከመካሪ ዘካሪዎቹ ውስጥ። ብአዴን ባይታዋር ነው። ቅንጥብጣቢ ለቃሚ። ብአዴን አጣብቂኝ መግባቱ አይደለም ቁምነገሩ ኢትዮጵያ መንፈሷ ያለውም በዛው አካባቢ ነው። „አገሪቱ“ ከሚሉት አቶ ንጉሡ ጥላሁን በስተቀር።

ስለዚህ ኦዴፓ ሙሉ አቅሙን ለማጠናከር ብአዴን ከጨዋታ ከፖለቲካ ወሳኝነት ውጪ አድርጎታል፤ ካቤና ላይ ብቻ ሳይሆን ሰሞኑን ብድር መስጠት በሚመለከትም 5 የኦዴፓ ሥ/አ/ ነው የነበሩት አቃቢ ህጉ፤ የገቢዎች ሚ/ር/፤ የጠ/ሚር ጽ/ቤት ሃላፊ/ አንድ የማዕከላዊ ምክር ቤት አባል የአዲስ አባባ ም/ ከንቲባ፤ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ከኦዴፓ ነው ሊቆጠሩ የሚችሉት ለዛውም ከቲም ጃዋር ልክ እንደ አቶ አለምነህ መኮነን ከህወሃት እንደሚቆጠሩት። 

ስለዚህ ራሱ ግንባሩ ዴሞክራሲን እያሳዬን ሳይሆን የኦዴፓ ጠቅላይነት ነው እያዬን ያለነው፤ ቪዲዮውን እዩት … መረጃው ግን እዚህ ሊንክ ይገኛል ...

https://www.youtube.com/watch?v=MeDVgoOCWQc

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ውይይት አዲስ ቴቪ የካቲት 19/2011 ዓ.ም


ለተማሩና ሐሳብ ላላቸው ዜጎች የብድር ሥርዓት ሊዘረጋ ነው

ምደባ ላይም ቢሆን ኦሮሞ መሬት መፈጠር ወይንም የኦሮሞ ደም መኖር መስፈርት ነው። ከውጭም የሚታጨው ይሁን አገር ውስጥ ካለው ይህን አንድ ሁለት ብሎ መዘርዝር ይቻላል። ዕውቅና የሚሰጠው፤ ደምቆ ጎልቶ ሥሙ እንዲወጣ የሚደረገው በዛ ስሌት ነው። ይህ ደግሞ መልካም አይደለም „ኢትዮጵያዊነት ሱሴ“ ነው ብሎ ለተነሳ አንድ የአገር አዳባር። አንገት የተሰራው አዙሮ ለማዬት ነውና።

ወደቀደመው ነገር ምልሰት ሳደረግ ለዶር ለማ መገርሳ ሥርጉተም ዜጋዬ ናት ማለት ይገባ ነበር። ግን አይደለም። ብዙ የታዘብኩት ነገር አለና። አሁንም ቢሆን አልመሸም መምረጥ ነው ኢትዮጵያዊነት ወይንም ኦሮሞነት? ምርጫው የእነሱ ነው። ሂደቱ ግን እጅግ አስጊ ነው።  የኢትዮጵያ ህዝብ ደግሞ ሲወድም እስከ ንፍጥ ልጋጉ ነው፤ ሲጠላም እንዲሁ። እርግፍ ነው የሚያደርገው። ሁሉን አይቷል።

ሁሉን ፈትሿል የኢትዮጵያ ህዝብ ዕዝነ ልቦናው ካልተሰወረ ወይንም ካልተወረረ ወይንም አዚም ካልተደረገበት በስተቀር ዕውነትን ወግኖ መቆም ይኖርበታል በቁርጠኝነት። ወይ አባ ገዳ ጃዋርውያን ወይ ደግሞ ኢትዮጵያውያንን? የትኞችን የኢትዮጵያ አርበኞች የሚለው ሌለው ፈተና ነው። በሥም ስለሆነ ... 

ዴሞክራሲ የስሜት ጉዳይ ነው። ስሜት ልብ የሚነግረውን ነው የሚገልጸው። አዲስ አባባ አሁን ለለውጡ አንጎል ነው። ይህ እንዲሆን ደግሞ በግራ በቀኝ መስከረም ላይ ተሰርቶበታል።  ፍጥጫው ነጥሮ እንዲወጣ። ምርጫ ህዝብ ቆጠራ ካለ ደግሞ ፈጦም መውጣቱ ግድ ነው።

እነሱ ስለዲሞግራፊ እዬነገሩን አይደል? ስለዚህም የለወጡ ተስፋ የሸመኑትን ዘሃ አንድዶ ወደ ሃቅ ነዶ በቃል መሰረት መስምርን መቀዬስ ይገባል - በአስቸኳይ። በመታበይ ግን በተለመደው በተረገጠ ጉዳይ እንቀጥላል ከተባለ ማንም አያተርፍም። ተያይዞ መቃጠል መንደድ መፍረስ ነው … ኦህዴድ በታሪኩ ይህን ሃንደል ማድረግ ተስኖት ከቀረ የዕድሜ ልክ ጸጸትን አዝሎ ይቀራል፤ እንለመደበት ... 

በጥቅሉ አላወቁበትም ዴሞክራሲ እና ተጫኝነትን መተርጎም፤ ቸኩለዋል የኦሮሞ ሊቃናት። በዚህ አጋጣሚ ግን እምገልጸው ግንቦት 7 ማቄን ጨርቄን ሲል፤ አምርሮ ሲያስከፋን፤ ትእግስት አልቆ ፍቅር ሲሰደድ አንድ ጊዜ የጻፍኩት ነበር ወያኔ ዕድለኛ ነው ብዬ ዛሬም ይደገም። ወያኔ ዕድለኛ ነው። ተንቦላ ውጥቶለታል።

ዶር ለማ መገርሳ ቤተክርስትያን ይቀረጽላቸው እሰከማለት የደረሰበትን ንዑድነት የጣሱት ፈቅደው ነው። ፍቅር ከዴሞክራሲም በላይ ነው። የሰው ልጅ የፈለገውን ቦታ መርጦ መኖር አለበት። አስገድዶ አምጥቶ በማያውቁት ቀዬ ማስፈር ራሱ ዲስክርምኔሽ ነው። 

Ethiopia: Reyot - ርዕዮት የአዲስ አበባንና ዙርያዋን የህዝብ ተዋጽኦ Demography ለመለወጥ እየተሰራ መሆኑን አቶ ለማ መገርሳ አምነዋል፡፡ …


ቢያንስ „መቆሚያ መሬት ያግኝ“ ማለት? ምን ማለት ነው? ያ የኢትዮጵያ መሬት አልነበረም ማለት ነውን? ከሁለት ዓመት በኋላስ ምን ታቅዷል? ማፈናቀሉስ ይናፈቅ ነበርን?  

በዚህ ውስጥ ሰውን ማዕከል ያደረገ ተፈጥሯዊ ዴሞክራሲ ለማዬት ያዳግታል? በሌላ በኩል ደግሞ „መጤ“ ነህ የሚሉ የሜጫ ልዕልት ወ/ሮ ሃቢባ ሲራጅን መሰል ደግሞ አሰልፎ ዴሞክራሲ? ፈረደበት!

ውዶቼ አይዞን! የኢትዮጵያ አማላክ ያውቃል። ብዙ ሰው እንቅልፍ አጥቶ አድሯል። ከልቡ ብዙ ሰው ከፍቶታል። ብዙ ሰው ተስፋውን ወደ መቃብር እዬላከ ነው። ብቻ፤ አዎን ብቻ ቸር ወሬ ያሰማን። ተስፋ ማድረግ ጥሩ ነው። በፈጣሪ ተስፋ እናድርግ። የኔዎቹ ኑሩልኝ

ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር ነው።
መሸቢያ ጊዜ።


አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።