ይባረኩ! ጸሐፊ አቶ ግርማ ካሳ።

እንኳን ደህና መጡልኝ።
ይባረኩ ጸሐፊ አቶ ግርማ ካሳ።
„በጎ ነገር ማድረግ ሲቻልህ፤ በወዳጆችህ ላይ ክፉ አትስራ።“
መጽሐፈ ምሳሌ ፫ ቁጥር ፳፰
ከሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
24.02.2019
ከእመ ዝምታ - ሲዊዘርላንድ።

·         መነሻ።
የአቶ ንጉሱ የተለሳለሰ አስተያየት ግፈኞችና ዘረኞችን የሚያበረታታ ነው (ግርማ ካሳ)
 
የኔዎቹ እንዴት ናችሁ? ዘለግ ላለ ጊዜ በአቶ ንጉሡ ጥላሁን ላይ ሰፊ ማብራሪያ ስጽፍ ቆይቻለሁኝ። መጀመሪያ ጠ/ሚር አብይ አህመድ  ወደ ስልጣን እንደመጡ የልብ ስለሆኑ ለኦህዴድ ቃለ ምልልስ OBN አድርገው ነበር። አንዲትም ቦታ „ኢትዮጵያ“ ሲሉ አላዳምጥኳቸው። „በአገሪቱ ተጀምሮ በአገሪቱ ተጠናቀቀ“ እራሱ ቃለ ምልልሱ ደመመን የተጫነው ነበር። አንዳች ምናምን በተጫነው መንፈስ ውስጥ በጭንቅ የሚወጣ ቃል ነበር ያዳመጥኩት። ከዚህ ጊዜ በሆዋላ እሳቸውን መከታተል ጀመርኩኝ። 


በጠ/ሚሩ በመጀመሪያ ጉብኝትም ወደ አማራ ክልል ባደረጉበት ጊዜ የታዘብኩትን ታዘብኩኝ። ለውጡን በመቀበል አይደለም ችግራቸው እኔ እንደማስበው። ዶር ለማ መገርሳ ጠ/ሚር ቢሆኑ እንዲህ ፈተና አይሆኑም ነበር። ውስጣቸው ቁርሾ አለበት። እኔስ እንዴት አንሳለሁ የማለት።

 በለውጡ ውስጥ ገነው የወጡ ሥሞች ረብሸዋቸዋል ብዬ አስባለሁኝ። ከሁሉም የከፋው ግን በሚሊዬነም አዳራሽ ለአባገዳ ጃዋር መሃመድ ያደረጉት ቅጥ ያልተሠራለት የፈጠጠ ገመና ነበር። ያ በውነቱ ክብደታቸውን በ እጅጉ ቀንሶታል።


ከኢትዮጵያዊነት በላይ ክብር የለም። ኢትዮጵያን ያከበረን ማክበር ያዋረደን ፊት መንሳት ይገባ ነበር። እሳቸው ግን ጎሽ ደግ አደረክ ብለው የ አማራን ህዝብ ወክለው ነበር የተገኙት። የኦነግን አርማ በውስጣቸው አዝለው እና ከብክበው አንዲትም ለምልክት የኢትዮጵያ የዜግነት ዓርማ በሌለበት ነበር የተገኙት። ጣውንትነት ነው ይህ ለእኔ።

ከእሱ በፊት የአገር ዋርካ የሆኑ ብጹዕን ንዑዳን አባቶቻችን ከስደት ወደ ኢትዮጵያ ገብተዋል። እሳቸው ለእነሱ ብጣቂ ክብር አልነበራቸውም። እሳቸው ክብር የነበራቸው ለጃዋርውያን ነበር። በሌላ በኩል በተለያዬ ጊዜ ጠ/ሚር አብይ አህመድ በክልሉ ሲገኙ እሳቸው የሉም። ተከስተው አብረው ሆነው ደስ ብሏቸው አይቼ አላውቅም። እኔ ከውስጥ ነው ነገሮችን ሁሉ እመከታተለው።



በቃለ ምልልስ ጊዜም የሚሰጡት መልስ አብሶ ህውሃት መቀሌ ከከተመ በኋዋላ የሚገርሙ ድንብልብል ስንኞችን ነው የሚሰነዝሩት። ስለሆነም በዶር ገዱ አንዳርጋቸው የተመራው ቡድን ወደ ስሜን አሜሪካ ሊጓዝ ነው ሲባል  ቡድኑ ሲመለስ የከፋ ቀውስ ሊገጥመው እንደሚችል ሁሉ ጽፌያለሁኝ። ሳያቸው ለውጡን በባለቤትነት ስሜት ሳይሆን ለውጡን ባገለለ በአንጃዊ መንፈስ ሆነው ነው። ልብ ብላችሁ ተመልከቷቸው።

የተማመኑበት፤ የእኔ የሚሉት ትክሻ እንዳላቸውም አስተውላለሁኝ። ስለሆነም በአንድም በሌላም ጃዋርውያን ስለሆኑ ከዛ መንፈስ የወጣ አቋም ይኖራቸዋል ብዬ መቼውንም አላስብም። እሳቸው የራሳቸውም ናቸው ብዬም ጽፌያለሁኝ። ራሳቸውን ያሰቀመጡበት ቦታ አሁን የተሰጣቸው ቦታ እራሱ አይመጥነኝም ባይም ናቸው።

ኦዴፓ እሳቸውን ከፍ አድርጎ አጉልቶ የሚያወጣው የልቡን ስላገኜ ነው። ኤርትራ እኮ የአማራን ታጣቂ ሃይል ተደራድሮ ለማምጣት ዶር ገዱ አንዳርጋቸው፤ ዶር አንባቸው ተቀምጠው እሳቸው ነበር የተላኩት። ብአዴን ውስጥ መፈንቅለ መደረጉን በዚህ ብቻ ማስተዋል ይቻላል።

የአማራ ህዝብ ተፈርቶ ነው እንጂ አሳቸውን ነው በአቶ ደመቀ መኮነን ቦታ መተካት የሚፈለገው። ህዝቡ ተፈርቶ ነው እንጂ ዶር ገዱ አንዳርጋቸውን ገፋ አድርጎ አቶ ንጉሡን በቦታው ለመተካት ነው የሚታሰበው። 

የእነ አቶ አባዱላ ገመዳ ቡደንኛ ናቸው አርሲኛ። ሁሉ ሰው ሊያስተውለው የማይችለው ለውጡን በሚደግፉት ውስጥ ያለውን ስውር ቀዝቃዛ ጦርነት ነው። ከፍተኛ የሆነ ሳቦታጅ ነው ያለበት። ቤርሙዳ ትረያንግል። አሁን የጎንደር ቀውስ የጀርባ አጥንቱ የዚህ ቡድን ባልደረባዎች ናቸው ህውሃት ብቻ አይደለም። አሁንማ ይባስ ተብሎ የጠ/ሚር ቢሮ አንጎል ሆነው አረፈዋል።

ይህን ሚስጢር ገለጥለጥ እያለ የሚታዬው ነገ ነው። ብዙ ነገር ከጠፋ በኋዋላ። አቶ አዲሱ አረጋ እና አቶ ንጉሡ ጥላሁን በአንድ ልብ ነው የሚተነፍሱት። እውነት ለውጡ በጠ/ሚር አብይ አህመድ ሙሉ ስልጣን ቢመራ ኖሮ የጠ/ሚር ፕሬስ ሰክራትርያት መሆን የነበረባቸው አቶ ካሳሁን ጎፌ ነበሩ። እጅግ በጎ እና ቅን አመለካካት ያላቸው ሰው ናቸው። ኢጎ የለባቸውም። ምቀኝነትም የለባቸውም። የበታችነትም አይሰማቸውም።

አቶ ንጉሡ ጥላሁን ግን በፈለገው አይነት ቁፋሮ እሳቸውን መተርጎም አይቻልም። እሳቸው የራሳቸው ሰው ናቸው። በሳቸው ውስጥ ያለው ትልም በዘልማድ ያለ አይደለም። ዝም ብሎ ዘው የሚባልበትም አይደለም። ብርቱ ጥንቃቄ ይሻል።

ለአማራ ሳጅን በረከት ስምኦን ለቲፒኤልኤፍ እንደተመደበበት ሁሉ እሳቸው ተተኪውን ተልዕኮ ለማስፈጸም የተፈለጉ ምርጥ ናቸው በኦነጋውያን ዘንድ ጌጣችን ነው የሚባሉት። እራሱ ለጠ/ሚር አብይ አህመድ እኔ እሰጋላቸዋለሁኝ። ባሳቻ ቀን የሆነ ነገር እንዳይፈጠር። ቅንነታቸው እና ሰው ማመናቸው የበዛ ስለሆነ።

አሁን ዛሬ ጸሐፊ አቶ ግርማ ካሳ ግርዶሹን መዳህኒዓለም ገለጥ ስላደረገላቸው የተሰማቸውን ጫፉን ሰጥተዋል። ሰሚ ጠፋ እንጂ እኔማ ከሐምሌ 2010 መጨረሻ ጀምሮ ስናገር ነው የባጀሁት። ጥንካሬያቸው፤ ብርታታቸው፤ ድፍረታቸው፤ በራስ የመተማመን ብቃታቸውን ባደንቀውም፤ ብወደውም አገልግሎቱ ግን ለኦነጋውያን ተልዕኮ ነው። የአማራን የህልውና ተጋድሎ እስጠልፈው መና አስደረገውታል።



ኪዳን አላቸው፤ ውል አለባቸው። ለአማራ ድርብ የመከራ ቀን ቀንበርም ናቸው። በሥሙ እንዲህ አማራ ዘመን ይዞ ተዘመን ይነገድበታል። የራሱን ልጀች ጠረኖቹ መገላላቸው ብቻ ሳይሆን ተመርዘው ይገደላሉ፤ ያልቻሉት ደግሞ ይሰደዳሉ።

የሆነ ሆኖ አሁን ያን ድንብልብል ልሙጥ መንፈስ የመረመረ ጹሑፍ ነው አቶ ግርማ ካሳ የጻፉት። ብአዴን ከእንቅልፉ ይነቃል። ቆቁም የአማራ ልጅም ይህም አለ ለካ ይላል። ቅኖቹ አገር አለን ብለው የሄዱትም የቆሙበትን መሬት ይመረምራሉ። በሌላ በኩል ሌላው አንበሳ ደግሞ ይህን የሰብዕዊ መብት የጣሰውን ጭካኔያዊ ተግባር አውግዞ ወጥቷል።

ሕግ የሚከበረው እንዲህ አይደለም፣ ይላሉ የአማራ ክልል መንግስት / ቃል አቀባይ


እኔ እሻው የነበረው ይህን ነበር። ብአዴን ማንዘርዘሪያ እንዲኖረው። ማጣሪያ እንዲኖረው። አንዱን ደራጎን አስውግዶ ሌላ ደራጎን እንዳያነግሥ በጥንቃቄ መራመድ እንዳለበት ነው ብአዴንን እማሳስበው - በትህትና።

እሳቸውን በሚመለከት እኔ ከአቶ አለምነህ መኮነን ለይቼ አላያቸውም። አቶ አለምነህ መኮነን ለህውሃት ያደሩ ነበሩ፤ እኒህ ደግሞ ለኦነጋውያን መንፈስ ያደሩ ናቸው። ማህበርተኛም ናቸው። ከዚህም ያለፉ ነገሮች ይኖራሉ ብዬ ነው እማስበው። 

አንድ ብሄረ መንግሥት ቁልፍ የሆኑ ቦታዎችን ሲሰጥ መጠንቀቅ ይኖርበታል። ሉዕላዊነትም ጉዳይ አለና።

ዛሬ የጠ/ሚር ቢሮ ማናቸውም ነገር ምን ያህሉ እጅ እንደሆነ መተመን ባልችልም በአባ ገዳ ጃዋር መዳፍ ሥር መውደቁ ግን አሊ አይባልም። ማሸነፍም መሸነፍም ሚስጢር ነው። ማሸነፍ ቅድሚያ መረጃ ማግኘት ነው። ጠ/ሚሩ ያላቸው ጉዞ ሁሉ ቀድሞ መሰናክል ሊታቀድልት ይችላል።

ሊያህ፤ ሥምህን ሊጠራ ከሚቀፈው ጋር አብረህ እዬሰራህ በነፃነት ሰው በማምን እንቀሰቃሳለሁ ማለት ዘበት ነው። ምን አልባት እኔ እንደማስበው ድርሻ ያለው በቤተመንግሥቱ ውስጥ ኦነጋውያን ከፍ ባለ ደረጃ ስለሆነ የጠ/ሚር ቢሮ ጫና ሊኖርበት ይችላል በሳቸው ምደባ ላይ። ግን ባለቤትነት እና ሃላፊነት አንዲህ በዘበጠ ኤንም ቢንም እንዳይከፋው ተብሎ ለዛውም በዚህ ቀውጢ ወቅት መወሰን አያገባውም ነበር። ለነገሩ በህልሜ ወንበሩ ባዶ ሆኖ ነው ያዬሁት።

የዶር አንባቸው መኮነን መንሳፈፍ እኮ የሌላ ፍላጎት አይደለም። እኔ እንዲያውም አንድ ጊዜ የጭቃ እሾህ ናቸው ብዬ ሁሉ ደፍሬ ጽፌያለሁኝ። የጠ/ሚር ቢሮ እራሱ አንጃ አለበት። አንጃውን የሚመሩት ደግሞ የስውሩ መንግሥት ተጠሪ ናቸው። ለዛ ነው አሁን ይህ ልብ ቦታ የተሰጣቸው።

በኦነጋውያን ዘንድ ሊቀ ጳጳስ ናቸው አቶ ንጉሡ ጥላሁን። ይህን መላ የኢትዮጵያ ህዝብ ሊያውቀው እና በጥንቃቄ ሊመለከተው የሚገባ ጉዳይ ነው። እሳቸውን እንደ ማንኛውም ባለስልጣን ማዬት እራሱ ግርድፍነት ነው። በጣም ጥልቅ እና በእጅጉ የረቀቀ ተልዕኮ እንዳላቸው እኔ እማስተውለው። የተፍታቱ አይደሉም። ተፈጥሯቸው የታመቀ እና ድፍን ነው። መተርጎም አይቻልም። 

ተርሚናል ምርቃት ሥርዓት ላይ ተገኝተው ነበር። አቤት ጭንቀታቸው ጠ/ሚር አብይ አህመድን ለመጠጋት? ሰው የሚታዘብ አይመስላቸውም። አጋራቸው ናቸው። ወገናቸው ናቸው። ደግሞም በክህሎት አይገናኙም። የጠ/ሚር አብይ አህመድ ዕውቅና እና ተቀባይነት ለሳቸው የጭንቅላት ሪህ ነው። ስለዚህም ነው ቆርጠው እና ደፍረው ለጃዋርውያን ከፍና ዝቅ ሲሉ የምንመለከተው።



ዛሬ እውነት ለመናገር የበራ ቀን ነው። አቶ ግርማ ካሳ ይህን አስተውሎታቸውን መጻፋቸው። ለውጡን የሚገዘግዙት በስልት እና በጥበብ ለማስተዋል መፍቀድ ግድ ይላል። ብቻ የቆዬ ሰው ይዬው … አንድ ቀን ይፈነዳል።

እጅግ የሚያበረታታው ግን እዛው ብአዴን ውስጥ ደግሞ ለህይወታቸው ብርቱ ጥንቃቄ ከተደረገ እውነትም የእኛ የሚያሰኙ ጠንካራ፤ ትሁት እና ሰው አክባሪ መንፈሶችም እንዳሉ እኔ አስተውላለሁኝ። ዶር ገዱ አንዳርጋቸው እና ዶር አንባቸው መኮነን እንደለመደባቸው በልዝነት ካላስጠቋቸው በስተቀር የተሸለ አቅም እና የተሻለ የረጋ ክህሎት እያዬሁኝ ነው።

በስተመጨረሻ … ጸሐፊ አቶ ግርማ ካሳን እጅግ አድርጌ አመሰግናቸዋለሁኝ። ይህን በአትኩሮት ማዬታቸው ፈጣሪ ሚስጢር እንደገለጠላቸው ነው እማስበው። ጥልቅ በሆነ ብልሃት ውስጥ ያለ ድንብልብልን መንፈስ መርምሮ አቅጣጫውን መለካት ብልህነት ብቻ ሳይሆን ልዩ እዮራዊ መክሊትም ነውና።

ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር።

የኔዎቹ ኑሩልኝ።
መሸቢያ ጊዜ።  


አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።