የዕብለት ዕምነት ቃልቻ ።


እንኳን ደህና መጡልኝ።
የዕብለት ዕምነት ቃልቻ።

„የሰው ልብ መንገድን ያዘጋጃል
እግዚአብሔር ግን አካሄዱን ያቃናለታል።“
መጽሐፈ ምሳሌ ፲፮ ቁጥር ፱

ከሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
14.05.2019
ከእመ ዝምታ ሲዊዘርላንድ።

                                           ተስፋችን በዬዘመኑ።
·       ር።

የአስተሳሰብ ግድፈት ወይስ ጥፋትን ለመሸፈን የጠ/ አብይ ትዕግስት እና የሕግ የበላይነት

(በጸሐፊ አቶ ያሬድ ኃይለማርያም )በድምጽ የተሠራ።)

የዕብለት ዕምነት ቃልቻ። (የወግ ገበታ በድምጽ - 15.05.2019)

·       ፍታ።

ካለ ነጭ እሪያን አይሆንለትም፤ ካለ ዝንቅንቅም እእካለ ጠጅሳርም በጅ አይልም፤ ካለ ድልቂያም አሻም ባይ ነው፤ ስልቱ ቅብጥርሶ ነው፤ ነፍሱም ምንትሶ፤ አውሊያው ጨንገሬ ጋሼ ዕብለት ይባላል … ታቦቱ ቃልቻ ይባላል። ሸፍጠኛ ነው። ሸፍጡ  ቢደረደር አንድ ፈራሽ አገር ይሰራል … የትውልድ ምድረበዳ ቀያሽ።

ግን ክብረቶቼ እንዴት ናችሁ የኔዎቹ? ደህና ናችሁ ወይ?እኔ አምላኬ ክብሩ ይስፍ ደህና ነኝ። ውዶቼ ሰላምታውን አዘገዬሁት አይደል? ይቅርታ ይደረግልኝ። ዛሬ ህም! ስለትናንቱ ህምታ ሂሳቡ ሳይወራረድ ሰነዱም ሰሌዳ ላይ በሰርተቴ ጠመኔ በሀተታ ጀንዴ ላይ ዘርጋ እንዳለ ነው። …

·       የወግ ገበታ።

ዕለቱን ስለጊዜበሉ ስለ ዕብለት ዕምነት ቃልቻ ትንሽ ነገርን ማለትን ወደድኩኝ።

·       ግን የሰው ልጅ ስንት ጊዜ ይሆን የሚፈጠረው?
·       በመፈጠር እና በመኖር መሃልስ ምንድነው እትብቱ?
·       በትንፋሽ እና በእትብትስ ማህል ምንድን ይሆን መስመሩ?
·       ግን የሰው ልጅ ስንት ቆዳ ይሆን ያለው?
·       ስንትስ ዓይነት ገጸ ባህሬ አለው የሰው ልጅ?
ግን የሰው ልጅ ምን ያህል ጊዜ ይሆን የሚፈጠረው? አንድ ጊዜ ብቻ እንዳትሉኝ እሱ  የዕብለ ትዕምነት ቃልቻው ላልሆነው ሲፈርስ ውሎ ለማያድረው፤ ሲሰራ እና ሲፈረስ ለማይባጀው ምራቁን ለወጣ ነፍስ ነው … እሺ … ውዶቼ?

ግን የሰው ልጅ ስንት ጊዜ ይሆን የሚረገዘው? አሁን በማዬው ሁኔታ አብሶ በኢትዮጵያ ፖለቲካ የሰው ልጅ ዕድሜውን ሙሉ ጽንስ ላይ አለ ብዬ እንዳምን ተገደድኩኝ። ይህ እንዲሆን የሚያደርገው ደግሞ እንደ ሥርጉተ ሥላሴ  የዕብለት ዕምነት ቃልቻ ነው ብዬ አሰብኩኝ።

ባላንባራስ ዕብለት ፈጣሪው ጣዖቱ ለሆነ ነፍስ ሁልጊዜም ጽንስ ላይ ነው። ይህ ማለት ምን ማለት ነው? ተወልዶ አያበቃም ማለት ነው።

ተወልዶ ካለበቃ ሁልጊዜም ይወለዳል ማለት ነው። ጉዳዩ ሁልጊዜ መወለድ ብቻ ሳይሆን ለአቅመ አዳምም ለአቅመ ህይዋንም አይደርስም ማለትም ነው። ባጉም ባጉም ሲል ከራርሞ መልሶ ደግሞ ያልረጋ ደም ሆኖ ይከረቸማል። የሚገርመው እሱ ብቻ ሳይሆን ለአቅመ አዳም እና ለአቅመ ህይዋን የደረሱትንም ተጣሮ እንደፍጥርጥራቸው የማድረግም ልዩ ባለሙያ ነው።

የኢንፓዬር እንፓይርነቱ ሰነድ ድርሳኑ በማፈረስ እና በመፍረስ ውስጥ መለመጥ ነው። መላመጥ አላልኩም፤ መለመጥ ነው የሾጤው ቆሌ ክፍሉ … ሾካክ ነው የእሱ ነገር። የሚገርመው እፍረት ማተብ የሚባል አልፈጠረለትም። እቴ እሱ …
    
ሁልጊዜ መወለድ ሲባልም ብቻ አዟሪት ሽክርክሪት አለበት ማለት ይሆናል፤ ያ አዟሪት መልሶ ከነበረበት ቦታ ስለሚወስደው ተመልሶ ይጸነሳል ማለት ነው። ተዜሮ ላይ።
ባጉም ባጉም ማለት ሲጀርም፤ እንደ ገናም ወፌ ቆመች ሲባል ለፊደል ገበታ ሲጠበቅ መልሶ ደግሞ ወደ ጽንሰት ይሄዳል። ስለዚህ ዕድሜውን ሙሉ ጽንሰት ላይ በሂደት ኮቢ ይቀለማል ማለት ነው። ታዲያ ቀለሙ ወጥ አይደለም። ዥንጉርጉር ነው። ቅይጥ ነው ዝንቅቅንቅ፤ ዝርዝር ነው ዝልብልብ።

የቀለሙ ዥንጉርጉር አስገዳጅ ሁኔታ ኢትዮጵያዊው የአራት እግር ቀለም አምራች ፋፍሪካ እንዲከፍት እጬጌው ሂደት ስለሚያስገድደው ማለት ነው።

ችግሩ ከእኔ ካልደረስ እንዳትሉ ክብረቶቼ፤ መንፈሰህን ሳትፈልገው፤ መንፈስሽን ሳትፈልጊው መገበር ግድ ይለሃል፤ ግድ ይልሻል። የትውልዱ ቤተኛ ነህ/ የትውልዱ ቤተኛ ነሽና።

አንተም የሂደት አባ፤ አንቺም የሂደት እማ ነሽና። ችግሩ አውራና ግልገል ተብሎ ከሁለት ሲከፈል አባ እና እማ የችግሩን ግልገል  መንፈስ መታደም ግድ ይላቸዋል ወደዱም ጠሉም።

አውራውን ችግር የምትጋፈጠው ግን ያው እናት ናት። ውዴቼ እንዲህ አይነት ሳይጎለምስም ጨርሶም ዕንቡጥ ሆኖ ሳይኖር ቅይጥ አፈጣጠርን ነፍስን የምትሸከመው ምድር ናት።
እሷ መከረኛ ናት። ፍደኛ። የፍዳዋን ግማድ ተሸካሚው ደግሞ የዬዘመኑ ትውልድ ነው። እሱም አሳረኛ ነው። እሸት ቅምስ የሚባለው በግብር ነው። ግብሩ ደግሞ መኖርን ገብሮ መባከን ይባላል።

አሳሩ ሁልጊዜም የዕብለት ጣዖት አማኙ የሚያዝላት ብርጌድ ምጥ ስለሆነ።  አዬር ሃይሉ ደግሞ ምን ያዝላት ይመስላችሁዋል? ዳጥጥጥ አላልኩም አልወጣኝ ዳጥ ነው ያልኩት። ዳጥ ሲባዛ በምጥ። መከራ ሲባዛ በአሳር ሲባዛ በፍዳ።

ተዚህ ላይ የቁጥር ተማሪ መሆን ይገባል። በመንፈስ፤ በሥነ - ልቦና፤ በጥሪት፤ በሥልጣኔ፤ በእርሾ መንዝሩት …. 60 ዓመት ሙሉ ዛሬም ያላባራው ነገም ቀጣይነቱ በአዲስ ሿሿቴ እና ኳኳቴ … እውነትን በመቀንጠቢያ እንኳን የማይገኝበት ድሪቶ።

መቼም መከራን ተስፋ ማድረግ አይቻልም። ላድርግ ቢባልም ፊታውራሪ መከራ ራሱ ይልፍ አይሰጥም። ስለምን? ከተፈጥሮው ውጭ ስለሚያደርገው።

 ስለዚህ የምጥዳጥ መከራ ስለምትሸከመው ምድር ቢያንስ የእኔ ቢጤ ብቸኛ ባተሌ በአርምሞ የሚኖር ሰው ድንኳኑ ባዶውን እንዳይሆን ልዝ ቢጤ ማዘጋጀት ደግሞ ግድ ይሆናል።

ያው የብክነት ሊኳንዳ ቤት በመክፈት በቃኝን ለማያውቀው፤ በዬአፍላው ኒሻን ተሸላሚው የምንትሶ ግራር¡ የዚህ ቀጥተኛ ሰለባዎች ደግሞ የድምጽ አላባዎቹ የኢትዮጵያ እናቶች ማህጸን ይሆናል ተቀባዩ ማሳ። የማይመሰገነው፤ ይቅርታ የማይጠዬቀው፤ ዞር ተብሎ የማይታዬው።

ዕድሜ ልካቸውን ጽንስ ውስጥ የሚኖሩ ነፍሶች ሲረገዙም፤ ሲወለዱም ሂደት ነው ገላጋያቸውም። መልሶም ወደ ጽንስነት የሚቀይራቸው ያው እጬጌው ሂደት።

ስለዚህ ዋና አባጃቸው፤ የስንበት ሰነድ ሰጩም እጬጌው ሂደት ነው። ህ! የዋዛ!
ትእዛዙ ደግሞ አያዳግሜ ነው። እንደ እኛ ባኒግ ትውር አይልበትም። ሲያገላብጣቸው፤ አክሮባት ሲያሰራቸው፤ ባለፈም ካሜራውን ገጥሞ ኪኖው ሲያስቀድሳቸው፣ ሲያስወርባቸው ሲያሰኘው አሽቀንጥሮ ሲወረውራቸው እጬጌው ሂደት አዛዥ ለምኔ ያሰኛል …

ስለዚህ ቅኖቹ፤ ልባሞቹ፤ በተደሞ በአርምሞ ሆነው ከእጬጌው ሂደት ጋር ከፍና ዝቅ ሳይሉ በነበራቸው አቅም ልክ፤ በተስተካከለ የሙቀት መጠን፣ ሳይሞቃቸውም ሳይቀዘቅዝቸውም ደርበብ ብለው፤ ደልደል ብለው፤ ጨዋነት ውጠው መቀመጥ ይገባቸዋል። ለምንጊዜም። „የረጋ ወተት“ እንዲሉ  ወጀቡ ተግ ሲል ደግሞ ሌላ ወጀብ ስለሚላክ አቅምን መቆጠብም አንድ ነገር ነው። ለክፉ ቀን።

እንደ አፍለኛ እለታዊ ጥንስስ ከቸረቸራ ወደ ምቸት፤ ከምቸት ወደ በርሚል፤ ከዋና በርሚል ወደ ጉርድ በርሚል ሽርሽሩ በተነካካ ወይንም ባሽካካ ቁጥር አደብ ከተገዛ ጤናው ይገኛል።

መሬት እንኳን ስለለመደችው እልልታዋ ቀርቷል። በተንኳኳ ቁጥር አትባትትም፤ አትባንንም። በተጸነሰ ጊዜ ራዲዮሎጂስት፤ በተወለደ ጊዜ ደግሞ የነርስ አቅርቦቱ አገር ስለፈታ።  

ስሊዚህ ቢያንስ እንደ ሰው የሚያስብ ባለአርምሞ ለጊዜበል እርግዝና ግልገል እጬጌ ሂደት እልል አንድ፣ እልል ሁለት፣ እልል ሦስት፣ እልል አራት እያለ 12ኛ ጊዜው ሲደርስ እልልልልልልል ብሎ በቀውስ የባጀወን ባዕት በተጨማሪነት በጩኸት ናዳ ማወክ አይገባም። ጫታ ያስፈልጋል -ስክነት።

እናቴ ያች አሳረኛ ምድር የሜጫው ሱናሜ ይበቃታልና … እም ሌላም ሱናሜ አለ ለካንስ እቴ ምድን ነው የሚበላው አያ

በዬትኛው ፊደል ነው የሚጀምረው? በእንግሊዘኛው ዴ ነው የሚጀምረው አዎን ዴሞግራፊም የምህንድስና ሱናሜም ማህበርተኛ ነኝ ለሜንጫው ብሎ አንድ ሱቅ በደረቴ ከፍቷል አሉ … ተዐብ ነው መቼስ ዘንድሮ …

ሌላው ልብ ሊባል የሚገባው ጉዳይ ደግሞ እግረተከሉ ደቦል ተመልሶ ወደ ጽንስነት መቀዬሩ ደግሞ ግድ ስለሚል ዘመን አመጣሹን የጽንስ ማረጋገጫ መሳሪያንም ገዝቶ ማስቀመጥ ይገባል። ያው ቅልሽልሽታውን አስቀድሞ ለመመከት።

… ያው ሰብሎ ለመታዬት፤ ወግ ደርሶት ስለማያውቅ የነበረውን ቤተኛ ሁሉ አላውቅህም ብሎ እንደ አሮጌ አካፋ እና ዶሞ እያሸቀነጠረ … አፍለኛ፤ አፍለኛውን ስለሚያሰኘው የቦካውን ለልባሞች ማስቀመጥ ይገባል እንደማለት። አዲሱ ሚዜ ለወረት ስለመሆኑ ልብብሎ ነግ ለእኔም ማለት ይገባዋል … ሁሉም ተራውን ነው የሚጠብቀው።  

የቦካ ማለት አውሊያው ጋር አብሮ አለመባከን፤ አቅምም አለማፈሰስ። እሰጣ ገባ አለመግባት። ግጭቱን እንዳላዩ ሆኖ „ሙያ በልብ“ እንደ ጎንደሮች ሆኖ የራስን ተግባር መከወን ይገባል። እጬጌው ሂደት አዲስ ሁኔታ ሲያመጣ ደግሞ ያው እንደ ሽንብራ ቂጣ መገላበጥ ነው … የባላንባራስ የዕብለት ቁራኛ ነገር።

ተወልዶም፣ አድጎም፣ ለወግ በቅቶም ሳይሆን ጽንስነት ብርቅነት ስለሆነ እሱ እሱውን ስለሚያሰኘው ጣዖቱ አያ ጨንገሬ የእብለት ቃልቻም ጠቅልሎ አሰናብቶ መለመላ እንዳያስቀር በልክ መያዝ ይገባል … ነው የእለቱ ጭብጤ አመክንዮ።

እልልታውን ደግሞ ዕድሜወን ለሰጠው ተ5 ዓመት ሳይደርስም ተመልሶ ጽንስ ሊሆን ስለሚችል በደርበቡ ገርበብ አድርጎ መተው ይበጃል እንላለን …
አፍንጫህን ላስአቶ ሂደት።
March 21, 2014

እጬጌው ሂደት።

08.04.2018

ለዚህም ነው ሥርጉትሻ እንዚህን ሁለት ጡሑፎች አስቀድማ የጣፈችው …
ከፍ እና ዝቅ፤ አዋላጅ እና መቆናጠጫ፤ አራሽና አበልጅ በመሆን እና ባለመሆን ፍጠረተ ነገሩን በርጋታ ብቻ፤ በማስተዋል ብቻ ማዬት የሚገባ ስለሆነ። የጤፍ ጠላ መሆንም አይገባም።

ርጋታ ስክነት ይፈልጋል ኢትዮጵያዊው ደርባቤ አዬር። ችግሩ እኮ እኛና ኢትዮጵያዊ አዬር ጋር መመጣጠን ስላልቻልን ነው ዬዘመኑ ፍላታችን፤ እና ብርደታችን ቴርሞሜትር አልቦሽ 

የሆነው። ፈልቶ ለሚቀዘቅዝ፤ ቀዝቅዞ ለሚፈላ አብሮ ንታ አይገባም እንደማለት …
በፈለገው ቀመር ዕድሜውን ሙሉ በጽንስ ለሚኖር መንፈስ የእልልታ አድርሽኝ ብቻም ሳይሆን ሳንጃም አያስፈልግም፤ ገጭ ገው ነገር። ያው ተመልሶ ደግሞ ጽንሰትም ውልደትም ስለሚኖር … 

ያው ኢትዮጵያዊው ፊደልም፤ ቃላትም፤ ሥያሜም፤ ቀለምም አያልቅም። … ቁጥር መቼስ አያልቅም … እንደዛ ነው ነገሩ …

ምን አለ …? ጭቃም፤ ድንጋይም፤ አይቀርብበት፤ ወጭ የለበት በዬዘመኑ ወላጆች ባሰናዱት በተሰናዳ ሰብዕን እዬገቡ ማረስ፤ ሲያሻ ደግሞ መበተን፣ መተርትር ወይ ደግሞ መናድ፤ ደግሞ በአዲስ ሚዚዎች እንደገና መሞሸር በጽንሰት።

አዬ ፊታውራሪ የ ዕብለት እምነት ቃላቻ….  አቤት! የጋብቻ ብዛት፧ ስንት ጊዜ ተጋብቶ ተፋታ፤ ስንት ጊዜስ ተጸንሶ ተወለደ፤ ተወልዶስ ተጸነሰ? !

ለቀን አድራሽ ዞር ብሎ ማዬት የለም ከአዲሶቹ ጋር ደግሞ አሸሼ ገዳሜ ነው። እነሱ ድግሞ ተራ ሲደርሳቸው ለባለተራ በፎርፌ መልቀቅ ምን ሲቸግር፤ ዕድሜ ለድምጽ አልባዎቹ የኢትዮጵያ እናቶች … ወልደው፤ አሳድገው፤ ለቁምነገር አብቅተው ይሸኛሉ ለማቅ አውጫጭኝ።

የሚገረመው የሰው ግብር የዶሮ ያህል ክብር የለውም ኢትዮጵያ ውስጥ። ትናንትም ዘፍን ዛሬም ዘፈን … በዘመን ሰጥ ዕብለት ጭፈራ፤ ድልቂያ፤ ኳኳቴ … ቻቻቴ፤
የዕብለት እምነት ቃልቻ ፋፍሪካውም አያልቅም ካርቦንዳይ ኦክሳይድ አልቆ እንደማያውቀው ሁሉ ….

ስለዚህ ለማያልቅ ነገር አቅም ማፍሰስ አይገባም፤ ከቆጧ ላይ ሆኖ አሻግረው እዬተመለከቱ እሚሆነውን ማዬት ብቻ ሊሆን ይገባል ለልባሞች። ይኸው ነው ለዛሬው።

ትእግስት ሲያልቅ ፍቅር ይሰደዳል፤
ፍቅርም ሲያልቅ ትእግስት ይሰደዳል።

·       ምትናፍቁኝ የአገሬ የኢትዮጵያ ልጆች - እንደ መከወኛ።

ከቶ ዘንካታ ወይንስ ሞንሟና ወይንስ ጀርጋዳ ምስጋና ላቅርብ ውዴቼ? ሁሉም ይገባችኋዋል እና ዝንክትክት ባለ፤ ሙንሙን ባለ ጀርጋዳ ትህትና የዕውነት ከመቀመጫዬ ብድግ ብዬ አክብሮቴንም ገልጬ ልሰናበታችሁ።

ኑሩልኝ እናንተን አንድዬ አያሳጣኝ። አሜን!
ድንግልዬም ትጠብቅልኝ። አሜን!
መሸቢያ ጊዜ።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።