#የአማራ #እናት #ስትፈጠርም፦ #ስትፈጥርም ዕጣ ፈንታዋ በኢትዮጵያ ፖለቲካ #ቀራኒዮ!

 

#የአማራ #እናት #ስትፈጠርም#ስትፈጥርም ዕጣ ፈንታዋ በኢትዮጵያ ፖለቲካ #ቀራኒዮ!
"የቤትህ ቅናት በላኝ።'
 
የአማራ እናት አሳረኛ ናት።
የአማራ እናት መከረኛ ናት።
የአማራ እናት ፍደኛ ናት።
የአማራ እናት ስቃዬኛ ናት።
የአማራ እናት ስትፈጠር ለቀራኒዮ ነው።
የአማራ እናት ስትፈጥርም ለቀራኒዮ ነው።
 
የአማራ እናት ተስፋዋን ነጣቂው ተስፋዋን ሲፀነስ ነው የሚነጥቀው። የአማራ እናት ተስፋዋ ገና በቀንበጡ ለፖለቲካ ማገዶ ነው። የአማራ እናት በብዙ መከራ ያሳደገችው ቡቃያ ለኢትዮጵያ የሴራ ፖለቲካ ማገዶ ነው። አንድ ፔና ያልገዛ ፖለቲካውን አህዱ ሲለው ሁለመናውን የሚበጅተው በአማራ እናት ቡቃያ ነው። 
 
ይህ ለ50 ዓመት የዘለቀ የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ትልም ነው። አሳካነም፦ ወደቅንም፤ አተረፍንም ከሰርንም የሚሉ ፖለቲከኞች መነሻ መድረሻቸው ጥሬ ምርቱ የአማራ እናት ቀንበጥ እና ሸበላ ፍሬ ዘር ናቸው። 
 
የአማራ እናት ተፀንሳ፤ ተወልዳ ስታድግ መንፈሷ እዬተዘረፈ፤ ሐሤቷን እዬተነጠቀች ነው። ሳቋን በግፍ ተቀምታም ነው። ልጆቿ በህይወት ቢኖሩ እንኳን በአሻት ሰዓት አታገኛቸውም። መኖሯ በስጋት የተጥለፈለፈ ነውና። የኢትዮጵያ ፖለቲካ ለአማራ እናት ቀራኒዮ ነው።
 
በኢትዮጵያ ፖለቲካ የአማራ እናት የሳቀችበት፤ ወህ ያለችበት፤ የተመሰገነችበት፤ የተሞገሰችበት የታሪክ አጋጣሚ አላውቅም። ይህን ህመም የሚጋሩ የኢትዮጵያ እናቶች መኖራቸውንም እረዳለሁ። ተግቼላቸውምአለሁ።
 
በዚህ በስድስት ዓመት በአዬሁት፤ በታዘብኩት ልክ በአማራ እናት ተስፋ ላይ ምሳሩ ጠንቷል። ከዛም በፊት ቢሆን ያው ነው። የአማራ እናት ተሰፋ የተገኜ "ለውጥ" ለእሷ ምጣቷ እንሆ ሆነ። የጠሚር አብይ አህመድ መንግሥት መደበኛ ተግባሩ የአማራን እናት ማሰቃዬት ለምን ሆነ? እንዴትስ ሆነ? መቼስ ይሆን አደብ ኖሮት እራሱን አርሞ ሊፀፀት የሚችለው?
 
ከ10-20 ሺህ በአፋር የታሠሩ የፋኖ፤ የልዩ ኃይል፤ የሚሊሻ ኃይሎች ምን ያህሉ በህይወት ይኖራሉ? በትግራይ እና በፌድራሉ ጦርነት ከአማራ መኮንኖች ጀምሮ በጦርነቱ ምን ያህሉ ተረፋ? አሁን ከዓመት በላይ በዘለቀው የፌድራሉ እና የአማራ ፋኖ ጦርነት ምን ያህል ሰቆቃ የአማራ እናት አስተናገደች?
 
የአማራ እናት በዬተገኘችበት ቀዬ ምን ያህል ችግር አስተናገደች? ምን ያህል ጽንስ ተጨናገፈ? ምን ያህል ጋብቻ ተነቀለ? ምን ያህል ህዝብ ከመኖሪያው ቀዬ ተነቀለ? ምን ያህሉ እንደወጣ ቀረ? ምን ያህሉ ተሰደደ? ምን ያህሉ ታገተ? ምን ያህሉ ከዩንቨርስቲ ተባረረ?? ምን ያህሉ ከመደበኛ ትምህርት ተስተጓጎለ?
 
ምን ያህል ተቋማት፤ ከተሞች ነደዱ? ምን ያህሉ አገልግሎት ከመስጠት ተቋረጡ? ምን ያህል የአማራ ልጆች በማንነታቸው? በእምነታቸው? በዕውቀታቸው ታደኑ? ታሰሩ? ተወገዱ? የመከራው ሽግግር ከዬት ላይ ይቁም? 
 
መስቃው እንዴት ይወገድ? ስጋቱ ከዕለት ኑሮ እንደምን ይሰናበት? የአማራ እናት እስከ ልጆቿ፦ እስከ ልጅ ልጆቿ ፦ እስከ የአማራ ሥልጣኔ አድናቂ ወዳጆቿ ድረስ ስለምን በባዕታቸው እንዲህ ሰርክ ይንገላታሉ? ለምን?
 
ለምን የአማራ ሕዝብ ይገፋል? ስለምን የአማራ ሕዝብ በእግዚአብሄር// በአላህ ፈቃድ ወደምድር መምጣቱ ይጠቀጠቃል? ለምን አባ እመ ቅንዬ የአማራ ሕዝብ እጁ #አመድ #አፋሽ ሆነ??? አማራ ከሌሎች ወገኖቹ ጋር ሆኖ በቅንነት ባቀናት ባድማው ስለምን ተሳዳጅ ሆነ? ለምን?
 
የአማራ እናት በዬክልሉ፤ በዬባዕቱ፤ በየጣቢያው፤ በዬቦታው ለምን ደመከልብ ሆነ? ክፋ ሃሳብ ቅናት፤ ምቀኝነት፤ በቀል፤ የትውስት ፖለቲካ የፈጠረው ረመጥ የአማራን እናት እያገላበጠ ቀጣት፤ ቀጠቀጣት። ሰው የሆነ፤ እንደ ሰው የሚያስብ የዓለም ፍጥረታት ሁሉ፤ ፈጣሪን ጨምሮ ከውስጣቸው ሆነው ሊያስቡት ይገባል። የሰሞኑ #የመሬት #ርደት ምንጩ የፈጣሪ፤ የአላህ #ቁጣ #ምልክት ነው ለእኔ።
 
ሁሉም ተችሎ። ሁሉም ተሁኖ። እጅ አውጥቶ ያነገሰን ህዝብ እንዲህ አልይህ፤ አልስማህ ብሎ ሙሉ ስድስት ዓመት #በበቀል #መምተር ልጅ፦ ትውልድ ያተርፍ ይሆን?
መከራ ሲጠና፤ መኖር ፈተና ሲበዛበት #ከፋኝ ማለትን ተከትሎ ዱር ቤቴ ባለው #ፋኖ #ሰበብ፤ ለምን ከቤታቸው የተቀመጡ ንፁኃን በወል ይገደላሉ? ለምን በገፍ ይታሠራሉ? ለምን ይንገላታሉ? ለምን በስጋት #እንዲንገረገቡ ይደረጋል? ለምን #መኖራቸው ይዘረፋል? ግፋ በዛ ተትረፈረፈም። 
 
በእርጋታ፤ በስክነት በበዛ ጥሞና ሁሉንም በምንከታተል ነፍሶች ላይም #ዝምታችን ሊያስተምር ለምን አልቻለም? እኔ በጦርነት ቀጠና ተወልጄ ማደጌ ሁሉን መራራ ሕይወት መጋፈጤ ጦርነትን ደጋፊም አበረታችም አይደለሁም። ብዙ ዕንቁ ዕድሎቼን ገፍቼ በምናኔ ገድሜ እምኖረውም በእምዬ ሲዊዝ የጥይት ድምጽ ባለመስማቴ ነው። ይህም ሆኖ የአማራ ሕዝብ ስቃይ፤ ፈተና፤ ስጋት እኔንም ይመለከታል። ቤተሰቦቼ በእኔ ምክንያት እንደምን እንደ ተቀጡ ሕይወቱን ኑሬበታለሁኝ።
 
ፈተናው በስደትም ሰቅዞ አሳር ያሳያል። እና በውነቱ የአማራ እናት #ስትፈጠርም#ስትፈጥርም በስማ በለው ሳይሆን በመገበርም፤ በመግበርም ሕይወቱ ተኖር። የፖለቲካ ድርጅት፤ የቡድን አባል ሳይኮን በስደት ይህን ያህል አሳር ካለ በፖለቲካ ለሚሳተፍ፤ አገር ለሚኖር #ቋያ ነው። 
 
ወላፈኑ ሳይሆን #በላርባው የምትቀቀለው #የአማራ #እናት - የአማራ #ሚስት - የአማራእናት ወዳጅ - የአማራ #አክስት- የአማራ #እህት፦ የአማራ #ምራት፦ የአማራ #አማት ናት። በአማራ ፖለቲካ ጉዳይ #ማህበራዊ መሠረቱን ያጣው ሁሉ ስለሚተምበት በርም የለሽ ስለሆነ ሌላኛው የዝምታው ምንጭ ሲሆን፤ በተጨማሪም "ላም እረኛ ምን አለም" አይደመጥም። 
 
ገና ከእስር ቤት ሲወጣ በቀጥታ ለአቶ እስክንድር የፃፍኩት ፋኖን እመራለሁ ብለህ እንዳትነሳ ብዬ ጽፌያለሁኝ። ዘኔ እስክንድር መርዬ ነው ሲልም ይቅርታ ጠይቅ ወይንም ኃላፊነትህን አስረክብ ብዬ ጽፌያለሁኝ። የባልደራስ የሥልጣን ወሰኑ አዲስ አበባ እንጂ አማራ ክልል ስላልሆነ፤ የአደረጃጀት መርኽ ጥሰትም የአቅም አወቃቀር፤ አደረጃጀት ስኬት እና ፈተናን አስቀድሜ ስለተረዳሁኝ። 
 
የብዙ የአማራ የማንነት እና የህልውና መከራ ከጅምሩ ደራሽ ተደራቢነት ነው። በዚህ ውስጥ የአማራ እናት ተስፋዋ በላርባ ተቀቀለ።
 
የሆኖ ሆኖ ፋታ የለሹ የአማራ ተስፋ ግድያ፤ የአማራ ሕዝብ ወላዊ እስር እና እንግልት በአስቸኳይ ሊቆም ይገባል። ለዛ ከተበቃ ያ ምርጫ እና ፍጥጫም ይመጣል - ካልተራዘመ። ጠቅላይ ሚር አብይ እንደ ልቡ ስለሆኑ። እና ምን ሊኮን ይሆን? ኃይል እና እርግጫ በቅጡ ለተደራጀው ሙሉ ተመክሮ ለነበረው ለህውሃትም አልሆነም። እንኳንስ በኢህአዴግ የትውስት ውራጅ አባል የተደራጀው ብልጽግና። መርኽም የአደረጃጀት ስልትም ላልተከተለው ብልጽግና ቀርቶ።
 
አሁንም ድምጼ ንፁኃንን አትግደሉ!
ንፁኃንን በስጋት አትቁሉ!
#ንፁኃንን #በቀያቸው #በገፍ እና #በግፍ #አታሳድዱ!
ንፁኃንን በገፍ #አትሰሩ! የታሰሩትን #ንፁኃን ካለምንም ቅድመ ሁኔታ ፍቱ! ይህ እኮ ነው የህዝብን ልብ ሙሉለሙሉ የሚያሸፍተው። ስንቱስ ይሰደድ? ሰው አልባ ምድሩ ምን ያደርጋል??? 
 
ለፋኖ ቃለ አቀባዮችም የምለው እባካችሁ ለህዝባችሁ ጥንቃቄ አድርጉ። ህዝባችሁን አሳልፋችሁ ምስክር ሆናችሁ ለካቴና አትስጡ? እባካችሁ ተለመኑን? እባካችሁ? ከዚህ ቀደምም አሳስቤ ነበር። ስንት ቤት ይዘጋ? ለአማራ እናት ልታስቡ፤ ልታዝኑ፤ ልትሳሱላት፤ ልትጠነቀቁላት ይገባል። ትግሉ ለአማራ ሕዝብ ከሆነ። ጥበብ።
 
#የአማራ #እናት #ሙሉ #ስድስት #ዓመት #ለምን #ትታሰራለች?
የአማራ እህት ሙሉ ስድስት ዓመት ለምን በጭንቀት ታምጣለች?
#የአማራ እናት ዘመኗን ሙሉ ስለምን #ማቅ ትለብሳለች?
 
ክብሮቼ እንዴት አደራችሁልኝ? ደህና ናችሁ ወይ? በነገረ አማራ ጉዳይ ደራሽ ባለቤቶች በርከትከት ስላሉ ጥሞናው የተገባ ነበር። አሁንም በባዕቱ፤ በቀዬው እንደ በግ ያገኜ ክብሩን የሚገፈፈው የአማራ ሕዝብ አሳዝኖኝ ነው። 
 
ድንገቴ ባለቤት ነን ባዮች ፈቀዱም አልፈቀዱም መከራ ላይ የተጣደው ቤተሰብ እረፈት ይነሳል። እስቲ ይሁኑበት በሚል በሰፋ ትዕግስት ተቆዬ። ፋኖም የአማራን ጥበብን ይማር። "ሁሉ ተፈቅዶልኛል፤ ሁሉ ግን አይጠቅምም።"
 
የአማራ እናት ዘመኗን ሙሉ ስለምን ማቅ ትለብሳለች? ክብሮቼ እንዴት አደራችሁልኝ? ደህና ናችሁ ወይ ? አሁንም በባዕቱ፤ በቀዬው ህዝባችን ተንገረገበ። #ድንገቴወች እስቲ ይሁኑበት በሚል በሰፋ ትዕግስት ተቆዬ። ችግሩ ከመወሳሰቡ ውጪ ትርፋ እንብዛም ነው። ፋኖም የአማራን የማንነ ት ጉዳዮች ስለተረከበ በሌሎች የጎዳደሉ ጉዳዮች ላይ ነበር አትኩሮቴ። 
 
የሆነ ሆኖ የግፋ እስር ይቁም! የኑሮ ውድነቱ ዛቻውና ግልምጫው አይበቃንም???
የወሉ ካቴናስ መቼ ይገታ!
እግዚአብሄር ይስጥልኝ። አሜን።
 
ሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
08/10/2024
#አማራነትን #አትሰሩ!
ጊዜ ራዲዮሎጂ ነው።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።