ሽኝት በቅኔ እትብታዊነት ነባቢታዊነት!

የእናት እና የልጅ መለያዬትን ያህል
የነበረው ተመስጧዊ ሽኝት በጥሞና!
ሃሌ ሉያ። "ነፍሴ ሆይ እግዚአብሄርን አመስግኚ።"
(መዝሙር ምዕራፍ ፩፵፭ ቊጥር ፩)
ከሥርጉተ ሥላሴ
09.07.2018
(ከገዳማዊቷ ሲዊዘርላንድ)


  • ·       መነሻ።

„Ethiopia:የጠ/ አብይ የደመቀ የሽኝት ፕሮግራም ከአስመራ“

ድመቀቱ አይደለም እኔን የመሰጠኝ፤ መለዬት እንዲህ መፈራቱ። ሽብርቅ ለሆኑ ዲኳዊ ጉዳዮች እንብዛም ነኝ። አብሶ ይህ የሚሊዮኖች የነፍስ ጉዳይ ነው። ስለዚህ ጥሞናም፤ ተመሰጦም ያስፈልገዋል። እንዲያውም አቅም ያላቸው ይህን ስመጥር ቅኒያዊ ትልም በጸሎት ቢደግፉት ጥሩ ነው።

እንዲያውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እና የኤርትራው የወል የ7 ቀን የሱባኤ ሁኔታ ቢኖራቸው፤ እስልምናም፤ ካቶሊክም፤ ፕሮቴስታንም በወል ይህን የሰላም ጥረት በጸሎት፤ በሰጊድ፤ በሱባኤ፤ በድዋ አጥር ቅጥር ቢሆኑለት ምኞቴ ነው። ቢያንስ በግል ሁላችንም ማድረግ እንችላልን። የባከነው የትውልድ ዘመን ማክተም አለበት። ይበቃናል።

ለእኔ የመንፈሴ ጉዳይ መለያየቱ እንዲህ ጭንቅ መሆኑ ነው። እያንዳንዷ ሰከንድ የፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ መንፈስ ዕዝነ ህሊናቸው ከኢትዮጵያ አዬር መንገድ ላይ ተተክሎ ነበር በተመስጦ እና በጥሞና። ያ ነው እኔን መንፈሴን ሁለመናዬን የገዛው። ቅንነት ነጥሮ የወጣበት፤ ንጽህና እና አሳቢነት ፈልቆ የታዬበት ድንቅ ገጠመኝ። ያዝልቀው እንጂ አያያዙ የእናት እና የልጅ ያህል የጠራ የፍቅር ጥሪኝ አለበት። ተመስገን!
  • ·       ስጢረ አሸኛኘት። 
ይገርመኛል። ይደንቀኛል፤ ይፈትሻኛል፤ ይመረምረኛል፤ ያወያዬኛል፤ ያነጋግረኛል። አሁንም ይገርመኛል። ግራሞቴ አላበቃም። የተናገርኩት ነው የሆነው። ባለቅኔው ጠ/ ሚር አብይ አህመድ በኤርትራ ህዝብ ውስጥ ይጎዘጎዛሉ ብዬ ነበር። የልብ የልባቸውን ያወጋሉ ብዬም ነበር። አስተርጓሚ ስለማያስፈልጋቸው ከፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ ጋርም የልብ የቤተዘመዱን ይጨወታሉ ብዬ ነበር። የከፋው መለዬቱ ሆነ እንጂ …

እኔ እንዲህ ዓይነት አሸኛኘት አይቼ አላውቅም። ሳሳሁለት! ሴሪሞኒው አይደለም። በቅርጽ ጉዳይ እኔ እንብዛም ነኝ። በቁሳዊ ጉዳይም እንዲሁ። መንፈሳዊ ጉዳዮች ናቸው ህሊናዬን የሚገዙት። ይህ ነው ንጽህና። ይህ ነው ቅድስና። ይህ ነው መሆን መቻል። ይህ ነው ለቃል ታማኝነት።

ፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ የልባቸውን ሰው አግኝተዋል ብዬ አስባለሁኝ። ደግሞ ሹመዋቸዋል የውጭ ጉዳይ አስፈጻሚ አድርገው። በዬሄዱበት ኤርትራንም የልቤ ብለው እንዲያዘክሩ። „ሦስት ማዕዘን“ እኮ ይሄው ነው ዓላማው። ይህም ይሁን ሽኘታው ግን ልብን ይነካል።

ለካንስ ለዚህ ነበር ያ የማላውቀው ስሜት የመጣብኝ፤ የኤርትራ ልዑክ ቦሌን መሬቷን ሲረግጧት አብሮኝ ስለመኖሩ እማላውቀው ስሜት ነበር የተፈጠረው። እኔ በውስጤ እንዳለው ፍጹም አዲስ ስሜት እንሱንም ተሰምቷቸዋል። መለዬትን ወዶ በመለዬት፤ መለዬትን ስቆ በመለዬት፤ መለዬትን ደስ ብሎት በመለዬት ቢሆንም መለዬት የአኃቲነት መለዬት ከሆነ እንዲህ ያደርጋል።

እጅግ በተመስጦ በቅኔ ነበር ሽኘታው። ሽኝታው ራሱን የቻለ የታሪክ መጸሐፍ ነው። ሰላም ዋጋዋ ዕሴቷ ዲካ የለውም። እናቶች አረፉ። እፎይታን አገኙልኝ። እኔም ሐሤት አደረኩኝ። ባለድርብ አዕምሮው ባለቅኔው ጠ/ ሚር የአሮን በትር ለምለም ነው። ቅንነቱ ለቅኖች እንዲህ የውስጥ ነው። ቅኖች የሚፈተኑት ይህን በመሰለ የታሪክ አጋጣሚ ነው። ቅንነት በኢትዮጵያ ነጥሮ የወጣበት ዘመን ይህ ዘመን ነው …  
ዛሬና ትናንት ያዬሁት ቅንነት የበለጠ ፈልቆ የጸደይ አበባ ሆኗል። አድዮ አታዳላም ኤርትራም እኮ ትበቅላለች። ፊቷ አይዞርም፤ መስከረም ላይ ብቅ ብላ እንዴት ባጃችሁ ወገኖቼ የኔዎቹ ትላለች አገረ ኤርትራንም። ዛሬ ቀኑ የአድዮ ነበር … እንቁጣጣሽ … በየዓመቱ ያምጣሽ … አትሂዱብን እኮ ነበር ዕድማታው፤ ከሄዳችሁም በፍጥነት ልናያችሁ እንፈቀዳለን ነበር …

እንደ ወፊቱ አገላለጽ የእረፍት ጊዜ ሲቻል ቤተሰባቸውን ባቅኔው ጠ/ ሚር ይዞ መሄድ ህልማቸው ኤርትራ ነው፤ ዱባይን አይደለም የሚመኙት እእ … የናፈቃቸው እትብታዊነት ነው።

እሺ እነ አላጋጦ ኢትዮጵያዊነት አጀንዳውን ከእኛ ወሰደ ትርክት እንዲ ውሃ የበለው ቅል ሲሆን ምን ትሆኑ? … አይደለም ኢትዮጵያ ኤርትራ ተመስጥራ በአብይ መንፈስ ውስጥ ባለችው ንጹህ ሙዳይ መቀመጧን ይህ  ዕንቋዊ ወቅት ገለጠው … እረፍትም ከቤተሰቦቻችን ጋር ነው ያሉት በቅኔኛ …  
  • ·       መለዬት ሲፈራ …

እያንዳንዱ  በሽኘታው ላይ የተገኘው ሁሉ መለዬቱን ፈራው። የእውነት ፈራው። ፈጣሪ ይቅር ሲል እንዲህ ነው። ያለፈው ጊዜ አስተምህሮት እንዲህ ከውስጥ እንዳይደገም፤ እንዳትመጣብን ውግዘ ተአርዮስ ሲባል፤ ጥላቻ ዝር እንዳትል ተብሎ ሲባረር ማዬት መኖር እንዴት ደግ ነው ያሰኛል። ለመለያዬት የነበረው መከራው ከባድ ነበር። ማመን ግን እንዴት በምን ይገለጥ …

አውሮፕላኑ ረጅም ጊዜ ሲያኮብኩብ ቆዬ። ምን ሆኖ ነው? ምን ገጥሞት ነው ብዬ ጭንቅ ይዞኝ ነበር? እነሱም የተጨነቁ ይመስለኛል። የሆነ ሆኖ ከሽኝታው በኋዋላ ጉሙን እዬሰነጠቀ ባለክንፉ ከአድማስ ባሻገር እዬራቀ እዬራቀ ሄዶ የኤርትራን ወስን ዳርቻ እስኪያልፍ ድረስ፤ ከዓይን አስኪሰወር ድረስ ፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ እዛው ቀጥ ብለው ቁመው ከሙሉ ካቢኔያቸው ጋር ሆነው ሰማይ ላይ አንጋጠው ነበር። እንዴት ሰው ናፍቋቸው ነበር? ውብ ነገር። 

ውበቱ በምንም ዕሴታዊ ሚዛን ሊለካ አይችልም። ሸበላ ወራት … ዘንጣፋ የተስፋ ዘመን … ዘንካታ ወቅት … 

ትናንት የኤርትራው ጋዜጠኛ „ወርቃማ ታሪክ“ ሲለው ነበር። ከወርቅም በላይ ነው የሆነው። ህዝቡ ያን ያህል መንገዱን ሁሉ ቄጤማ እዬነሰነሰ፤ መንገዱን ሞልቶ አብሮ ከመኪና ጋር እዬሮጠ፤ በዛውም ሰላም እዬተባባለ …. እናቶች ያን ያህል እዬዘፈኑ፤ ወጣቶች አብይ የእኛ እያሉ፤ የሃይማኖት ሰዎች እዬወረቡ ...

የነበረው እልልታ …. አብይ አብይ እልልል አብይ አብይ እልልል ተደምረናል እልልል ተደምረናል እልል በድምጽ ማጉያ እኮ ነው በእያንዳንዱ መፈክር ልክ እልልታውን ሲያቀልጡት የነበረው። ወንዶች እልልታ ሲያሰሙ የመጀመሪዬ ነው፤ ደስታ አያደርገው የለ … ታድለን!
  • ·       ትንግርት በጥሞና።

ዛሬ ደግሞ የዛሬው ደግሞ እኔ እራሴ እዬመለስኩ እያመላለስኩ ደግሜ ደግሜ ፊታቸውን አዬሁት የፕ/ አሲሳያስ አፈወርቂን። እጅግ ይመስጣል። እጅግ ይመረምራል። ይመራልም! እውነት ጠቅላላ ሁኔታው ሰውኛ ነበር። 

ጠቅላላ ሁኔታው እትብተኛ ነበር። ጠቅላላ ክህሎቱ ተቋም ነበር። ምጡብኝ፤ ኑብኝ፤ አትልቀቁኝ ይላል። ሁሉም ሳቀ። ሁሉም ደስ አለው። ሁሉም ፍንድቅድቅ አለ። መለዬት እንዳይመጣብን አደራህን ኤልሻዳይ አምላክ።

ሁላችንም ፈራነው መለዬትን እጅግ ፈራነው። ተመስገን። ሁለም የናፍቆትን፤ የፍቅርን፤ የአብሮነትን፤ የመከባበርን፤ የመተሳሰብን፤ የመረዳዳትን፤ የመተቃቀፍን ስንቅ ቋጠረ … የታደለ ዘመን …

ሰላም ወስጥን ይፈጥራል!
ሰላምን ህሊናን ያበራል!
ሰላም የዕውነት ቃል ኪዳን ነው!


ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር!

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።