የህውሃት ለቅሶ ... ግፍ አይሆንም? ጡር ፍሩ!

የስሞታ ክምር አይሆንም እን
ተለመደው የልዕልና ብርንዶ!
እንኳን ደህና መጡልኝ።
„እጆቼን ሰልፍ ያስተምራል፤ 
በክንዴም የናስ ቀስት እገትራለሁ።“
 መዝሙረ ዳዊት ፲፯ ቁጥር ፲፬“

ከሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
19.01.2019
ከእመ ዝምታ ሲዊዘርላንድ።



·       ርምታ!

እንዴት ሰነበታችሁልኝ የእኔ ቅኖቹ? እኔ አምላኬ ክብሩ ይስፋ ደህና ነኝ። በዬአቅጣጫው የሚሰማ አቤቱታ አንድ አይነት ነው - እንግሊዞች ሬድሜድ እንደሚሉት። የህውሃት ማንፌስቶ ማህበረተኞች የስሞታ ክምር በተለመደው የጭካኔ ብርንዶ የሰብዕ ቁርጥ አለመቀጠል የሁሉም የወል የለቅሶ ቤት ሆኗል።

ሁሉም በአንድም በሌላም ተገፋን፤ ጥፋቱ ሁሉ ተጠቃሎ በአንድ ድርጅት ላይ ሆነ፤ የ27 ዐመቱ ዕዳ በእኛ ላይ ብቻ ተጣለብን፤ እምናመለከው የህውሃት ታቦት ሰሚ  አጣ እያሉ እያጣወሩ ነው። ከ2008 ዓመተ ምህረት በፊት ወደ ነበረው መመለስ አለበት እያሉን ነው፤ ወንዝ ወደ ላይ ወይንስ ወደ ታች ይሆን የሚፈሰው?!ለመሆኑ 2010 እራሱን መልሰን ማምጣት እንችል ይሆን? 

·       ቻ እኛ እንዲህ እንላለን…

27 ዓመት ሙሉ የኢትዮጵያ ህዝብ የተሸከመውን በደል ብራናውም ብዕሩም አይችለውም እና ጡሩ ፍሩ እያልን ነው። እነሱ ለ9ወራት ከጨቋኝነት፤ ከገዢነት፤ ከበላይነት መወገዳቸው የከበዳቸው 27 ዓመት ሙሉ በባይተዋርነት አሳሩን እዬበላ መወለደኑ የጠላውን 100ሚሊዮን ምንዱብ ህዝብስ ምን ይል ይሆን? ብግፍ የፈሰሰው ደም እና ዕናባስ ከቶ ተገኝቶ ቢጠዬቅ ምን ይል ይሆን? 

የሚገርመው ይህ የአብይ ዘመን ባይመጣ፤ ባይሳካ ሊመጣ የሚችለውን በፍጹም ሁኔታ ያሰቡት አይመስለኝም። ያልከፋው ጥርሱን ያልነከሰ የለም መገለል እኮ በመኖር ውስጥ ያለ አፍ ያለው መቃብር ቤት ነው።

ይህ የአብይ ዘመን ባይመጣ እኮ ዓይን ለዓይን ለመተያየት ራሱ እጅግ ከባድ ነበር። የተበሳጨ አዬር ነው የነበረው። ያ ብስጩ አዬር ደግሞ ብስል ከቀሊል፤ ዲታ እና የእኔ ቢጤን የሚለይ አይሆንም ነበር። የበላውም፤ ያስበላውም ምንም ያላገኘውም ደሃ ባተሌ ለፍቶ አዳሪ እኩል ነበር ፍዳን በደቦ እንዲከፍሉ የሚገደዱት። 

ሁሉንም ተጋሩ በአንድ ዓይነት፤ በክፉ ዓይን የሚታይበት ማንዘርዘሪያ የሌለው ሁኔታ ነበር የሚገጥመው። ከተጋሩ የተፈጠሩ ህፃናቱ እራሱ ምንም በማያውቁቱ ነገር ይቀጡ ነበር። ጦርነት ህግ የለውምና። አብሶ የርስ በርስ ከሆነ ሰቅጣጭ ነው ...

ይህ ስላልደረሰ ህመሙ፤ ቁስለቱ፤ መግሉ አይታይም። ስለምን? ዕድሜ ለችሎተኛው የአብዩ ዘመን እንጂ ይህችን ስልጣን ሌላው ይዞት ቢሆን ኑሮ ተገፍቶም አያልቅም ነበር ረግረጉ …

ራሱ የሥነ - ልቦናው ዘመቻ ማንም ከሚሸከመው በላይ ይሆን ነበር። ይህን ያልተገፋው ወርቅ ዘር አያውቀውም - ዛሬ፤ በጋብቻም፤ በዝምድናም፤ በአብልጅነትም በልማታዊ ማህበርተኝነት ያለው አብሮ የነበረው ሁሉ አያውቀውም፤ መከረኛው ብዙኃኑ ግን መኖሩን በስጋት ውጋት በትርፍ ዜግነት ተወቅቶበታል። ስለዚህ አሰተርጓሚ አመሳጣሪም አይሻም እና ያን የጭራቅ ዘመን እንዲመለሰብት አይሻም። በውነቱ ስደት ላይ  ያለነውም ዕንባችን ደርቋል።   

27 ዓመት ሙሉ የብዙኃን ስቃይ፤ መከራ፤ ስደት፤ ሰላም ማጣት፤ በአደባባይ መረሸን፤ መገለል፤ በክፉ ዓይን መታዬት፤ ከእድገት ዝቅ መደረግ፤ ከኑሮ መፈናቀል፤ ከሥራ መፈናቀል፤ መገፋት፤ መታሰር፤ መገደል፤ መወረር፤ መዘረፍ፤ መጨቆን፤ መደብደብ፤ መተልተል፤ በመስቃ መጨቅጨቅ፤ መስጋት፤ መፍራት፤ መጨነቅ የሥርዓቱ - ዝበት ያመጣው ስለመሆኑ ችግሩ ውስጥ ላልነበሩ እነ ቀምጣሌ አቦቶ ዘመናዮች በእነሱ ቤት ምንም አልሆነም፤ ምንም አልተፈጸመም፤ ማንም ማንንም አልበደለም። ስለምን? ረኃብን የሚያውቀው የተራበው ብቻ ስለሆነ።

የጨርቅና የወርቅ መታያ፤ የወርቅ ውድድር፤ የቢላ ቤት ታይታ፤ እና የፉክክር የኃብት ጣሪያ ድርድር ከመጠን ያለፈ መወጠር እና መቀናጣት፤ የመኖር ደረጃ ከፍታ ተነጥሎ ተለይቶ ከእነ አጋፋሪዎች ጋር በበዛ ልዩነት በልዕልና መታዬት እነሱ አይታያቸውም የወያኔ ሃርነት ትግራይ የማንፌስቶ ማህበረተኞች፤ ህወሃትን ተቀናቅነናል የሚሉትም ቤተ ተጋሩ ሊሂቃን አይታያቸውም። ህሊናው ራሱ የት ላይ እንደበቀለ ችሎት የሚያስኬድ ነው።

እንኳንስ 27 ዓመት ሙሉ 27 ቀን ራሱ የመከራ ሌሊት አይነጋምና እጅግ ብዙ ነው። ኢትዮጵያ ትውልዷ ዕዳ ሲከፍል እንዲኖር የተገደደበት ዘመን፤ ከድህነት ጋር ተዋዶ እንደገናም ተገድሎ፤ እንደገናም ታስሮ፤ እንደገናም አካሉ ጎሎ፤ እንደገናም ማፍሪያ ዘሩ ተንኮላሽቶ በአገሩ ተገልምጦ፤ በብቸኝነት ተንገላቶ በ2ኛ ዜግነት ለመኖር ባለመቻል ተሰቅዞ ግን ተችሎ ተኖረ።

ዛሬ ደግሞ የያዙትን እንደያዙ ሲለቀቁ በጽልመተ ተስፋ ብዙኃኑ መማቀቅ ያ ሐሤት ነበር ለህውሃት ማንፌስቶ ማህበርተኞች፤ ያ ዕድገት ብሥራት ነበር ለዛ ኢ ሰብ ለወረቀት አምላኪዎች።

ይህም ሆኖ ሊዬቅ፤ ሊወስ የሚገባው ዛሬ ያለው የለውጥ ሃይል ሊሆን ባልተገባ ነበር። አድኗቸዋል እኮ። ዘር ማንዘር የጋብቻ ዝምድናው አክሎ ምን ያልተነካካ ነገር ኖሮነውና። ከመሬት ተነስቶ ዲታነት እኮ ሌላ መስፈርት አልነበረውም ተጋሩነት ብቻ ነው። ወይንም ለተጋሩ ባርነት ማደር።

የሰው ልጅ ለበደለው መጸጸት እንዴት ያቅተዋል? ተው የሚል ባለግራጫስ እንዴትስ ይጠፋል? በድለናል ማለትስ እንዴት ይከብዳል? ሊጠዬቅ፤ ሊፈረድበት የሚጋባው ትዕቢት መሆን ይገባው ነበር። 

አይዋ ትዕቢት ከልክ በላይ ተቀናጥቶ ጎንደር መሬት ድረስ ሄዶ የአቶ አባይ ወልዱ የጥጋብ ውንብድና በውርዴት የወደቀ ዕለት ህወሃት እና ማህበርተኞች ከመንበራቸው ወርደው እንጦርጦስ የተላኩበት ቀን ነበር ሐምሌ 5። ያ ቀን መንጠራራየተነፈሰበት ቅዱስ ዕለት ነበር ለንዑዳኑ። ተደፈረ የትግራይ ሥርዕወ መንግሥት። 

የችግሩ መንስኤ የችግሩ ሥር ህግ ጣሽነት ነበርመታበይ። የጎንደር ምሥረታ እኮ ከገብያ ዕድምታ ጋር የተዋህደ ነው። ያን የዘመናት ቅርስ እና ውርስ ወንበዴዎችን ቤንዜንና ክብሪት አስታጥቆ ልኮ በሳት ሲያነድ አንድ የትግራይ ሊሂቅ ህሊና ያለው ወጥቶ አላዋገዘም። አልኮነነም። እኔ ራሴ እንደዛ ቀን አልቅሼ አላውቅም። ጎንደር በትገራይ ልጆች ሲቃጠል ከመስማት ከማዬት በላይ ምን የሚያስለቅስ ነገር ይምጣ? እኛን?!

እንደ ሰው ቢታሰብ ስለምን ገብያ ይቃጠላል? ገብያ እኮ መገናኛ ነውገብያ እኮ የሰላም አውራ ነው። ገብያ እኮ ጉሮሮ ነው። ገብያ እኮ ህልውና ነው። ገብያ እኮ የሰው ልጅ እስትንፋስ ነው። ቢያንስ ጎንደር ላሉ ህፃናት እንዴት አይታዘንም? አንጀተ ገመዶች። አሁን ማነቁነቅን ድንኳን ጥሎ ከማባበል ከመንበር የነጠለው የአቶ አባይ ወልዱ መታበይ ስለመሆኑ ልብ ቢሉት ይገባል። በማንም ማለከክ አይችሉም። የራሳቸው ትዕቢት ነው የደፋቸው። 

 መወቀስም፤ መታሰርም መቀጣትም የነበረበት ግን አንባሳደር ሹመት ነው ያዬነው፤ እግዚአብሄር እንደዴት ይታዘብ? ያም ይሆን ለውጡ ለሰፊው የተጋሩ ቤተሰብ አዳነ ብለው ነው ሥም አውጥተው ሊጠሩት የሚገባ እንጂ ማይክ ያገኘ ሁሉ በተሟጠጠ ተስፋ መንጠራራት ሌላም የሰማይ ቁጣ እንዳያመጣ … እሰጋለሁኝ እኔ እንደ ሰው … አሁንም ዘመናይነቱ ስለበዛ…

ይህ መታበይ እንሆ መንፈስን አቃጥሎ በመቀሌ ምሽግ ቀኑም አልቃናም ብሎ ሌሊቱም አልነጋም ብሎ ስሞታ ተዘርቶ፤ ስሞታ በቅሎ፤ ስሞታ ሲያሰብል ተውሎ ይታደራል።

ትግራይ ቴቪ፡ አማርኛ ዜና ምሽት 200 ስዓት ጥር 09/2011/


ማዋል እና በማደር ህክምና የማያገኘው መታበይ ለትግራይ ህዝብ ህወሃት ሽንፉቱ መልስ ስላጣ ብቻ በዚህና በዚያ እያወገረገረ የበላይነቱን እንዳላጣ አድርጎ ነጥብ ቁጠሩልኝ ሲል ማድመጥ የመሸነፍ፤ የተስፋ ማጣት፤ የውስጥ መራቆት፤ የራዕይ እከክ በእከክ መወረር መሆኑን ማንም አያጣውም።

በዚህ ማህል ህፃናቱ ዛሬ ያሉት፤ ነገም ገና በሃሳብ የሚጸነሱት ይህን የጎ መታበይ ምን ሊያመጣባቸው እንደሚችል እና ቀንበሩን ሳስሰበው እኔ  ይጨንቀኛል። በዚህ ዘመን አንድ ተጋሩ በሚኖርበት በዬትኛውም የአትዮጵያ ቀዬ ውሎ - ሰርቶ - ጥሮ ግሮ አንገቱን ቀና አድርጎ መኖር መቻሉ በራሱ ለእኔ የታምር ያህል ነው እማዬው። እነ አትንኩን ዛሬ በሁሉም አቅጣጫ ሌላው እዬተነጠለ ከሳት እዬተማገደ ነው፤ ይህ የተገለበጠ ቀን መከራው ጫን ተደል ነው …


ምክንያቱም የቁርጥ ቀን ህግም ጠበንጃም ሥራ ፈት ነው የሚሆኑትና። የበገነው ሁሉ ቁጭቱን ለመወጣት ቢነሳ የሚተርፍ ነፍስ ይኖር ነበር ወይ? እታን፤ እታን፤ እህን! ጸንሰው ያሉ ተባዕታን በአብራካቸው አንስታት በማህፀናቸው ስለማይታይ፤ ስለማይደሰስ ነው እንጂ አጥንት ጸንሰዋል። ይህ ተችሎ ደግሞ ከቶ ይህ የምህረት ዘመን የሚወቀሰው የሚነቀሰው ስለምን ይሆን?

ግፈኞቹ የሰሩት መከራ ዛሬም ባለማባራቱ ነገን ማጥቆሩ ሳስበው እኔ ሁልጊዜም የሚጨንቀኝ ለተጋሩ ህፃናት ስለሆነ እንደ ቸርነቱ በወያኔ ሃርነት ትግራይ ግፍ እና ተዘርዝሮ - ተፍታቶ - ተተትርትሮ - በማያልቀው ግፍ መጠን የእዮር የመጨረሻ ቁጣ የመጣ ዕለት ማን እንደሚያስቆመው አንድዬ ይወቀው።

ሰው እንዴት አጥፍተዋል ልጆቻችን የኢትዮጵያ ህዝብ ተበድሏል በዛ መርዛማ ማንፌስቶ መከራ ተቆልቷል ፍዳውን አይቷል፤ ተንገርግቧል፤ ተወግሯል አቤቱ! ይቅር በለን ፈጣሪያችን፤ እናንተም ወገኖቻችን ይቅር በሉን እንዴት አይልም?

ሰማይ እና ምድር ቢገናኝ የዘመነ የትግራይ ሥርዕዎ መሳፍንታት ከእንግዲህ በቀደመው መልክ መግዛትም -  መንዳትም የሚችሉበት እንጥፍጣፊ ዕድል የላቸውም። መፎከር ይችላሉ፤ መመኘትም እንዲሁ …  

ማመስ እንደለመደባቸውም ይችላሉ - ይህም ጎሽቶ እስኪጠራ ድረስ ነው። የተቻለውን ያህል ቢቻልም እንዲህ ሆኖ ግን ዘመኑ መቀጠል አይቻልም። ሲከር ይበጠሳል ሲሞላም ይፈሳል ይሆነና ከዛም ቤት እሳት ስላለ እንደ አለፈው ጊዜ በወታደር ማስጠበቅ በማይችሉበት ቦታ ሁሉ ያለው የተጋሩ ነፍስ ምን ሊሆን ይችላል ብዬ ሳስብ እኔ አሁንም ጭንቀታም ስለሆንኩኝ ጭንቅ ይለኛል። 

በመፈናቀሉ የሉም፤ በመቃጠሉ የሉም፤ በመሳደዱ የሉም ትግራይም ሰላም ነው ሌላ ቦታ ነዋሪዎችም ቀውሱ ሳይነካቸው እነሱን አልፎ ሌላውን ያጭዳል ይህ ግን አይቀጥልም ... የታመቀ ነገር ከፈነዳ ማቆሚያ የለውም ... 

በነፍስ ወከፍ በግል፤ በወል እና በጋራ የሚደመጠው የ27 ዓመቱ መከራ በተጋሩ ዘንድ አልተመከረበትም፤ ዕውቅናም አልተሰጠውም። እንዲያውም የተሳሰተ መንገድ ላይ ነው የአብይ ሌጋሲ ነው ሲባል ነው የሚደመጥው? ግን ማተብ የት ላይ ይሆን ያለው?


ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሽነፎ የተፈጠረ ሚስጢር።


                                           የኔዎቹ ኑሩልኝ።

                                           መሸቢያ ጊዜ። 

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።