አለማፈር እስቲ ይጠራ ...


   ወይ አለማፈር …
                             ከሥርጉተ © ሥላሴ 25.08.2018 (ከጭምቷ ሲዊዘርላንድ።)
                           „መንገዳችን እንመርምርና እንፈትን፣ ወደ እግዚአብሄርም እንመለስ።“
                                           (ሰቆቃው ኤርምያስ ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፵)

  • ·         ኢትዮጵያ ወግ ደረሳት።

ኢትዮጵያ ወጉ ደርሷት የሰማዕታት ቤተሰቦችን ደውሎ የሚያጽናና መሪ ፈጠራለት። ተመስገን! የተጎዱትን ደግሞ በአካል ሄዶ የሚያይ በማጽናኛ መንፈሱ ድብስብስ የሚያደርግ ብሩክ ቅዱስ የሆነ የአሮን በትር ተሰጣት። ተመስገን! ተጎጂዎችን ለመርዳትም በመንግሥት ደረጃ እርዳታ የሚያሰባሰብ በብሄራዊ ድርጅት እስከ መፍጠር ደረሰች አላዛሯ ኢትዮጵያ። ይገርማል። በተጨማሪም አንድ ጠ/ ሚር ደም ለወገኖቹ የሚለግሥ ኢትዮጵያ ፈጠረላት። አሁንም ተመስገን። የሊቢያ ሰማዕታት ብትን የአፈር እና ዕንባ አልተፈቀደላቸውም ነበር። 

ለዚህ ሰውኛ ቀን ነበር ሌት ተቀን ተግተን እኔ በብዕሬ ሳተናውም ደከመኝ ሳይል በብራናው የተጋነው። ተመስገን ቃሉ አነሰብኝ። ምን ልበለው? እንደ ገና ተፈጠርኩኝ ልበል ይሆን። ዕድሜዬም ከመጋቢት 24 ቀን ጀምሮ ይሁንልኝ ብያለሁኝ። አዎና! በእኔ ዕድሜ እንዲህ ዓይነት ህልም የሚመስል በትረ ፍቅር … መሪ ማዬት ስለታዕምር ነው። ፍቅር እንዲህ አገር ምድሩ የእኔ ሲለው … ገድል። የጸሐይ ዘመን።
  • ·         የሙርቅርቁ ብዛት የውልቅልቅ ጥገት።

አሁን ወደ በኽረ ጉዳዬ ኮተት ልበል፤ እንደ እነ እንቶኔ … በስንት ግራሞት ስንት ድብልቅልቅ መሬት ትሸከም ይሆን? በስንት ዝብርቅርቅ ምድር እሾኾችን ተሸከሚ ተብሎ ይፈረድባት ይሆን? በስንት ቅልቅል ፕላኔታችን አፍንጫዋ ተሰንጎ ጨለማ ልበሽ ብሎ ይፈረድባት ይሆን? አሁንም ይገረማል … ይደገም።

ምቀኞች፤ ተንኮለኞች፤ ሸረኞች እባቦች፤ ጊንጦች መልካም ነገርን ይሸሻሉ ይፈራሉ። ደግነት ራድ ያስይዛቸዋል። የመልካም ነገር ሐዋርያትንም ያሳድዳሉ፤ ይዋጋሉ፤ ቢሞቱላቸው ይሻሉ። ቢታሙሙላቸው ይፈልጋሉ። ሰላማቸው ታውኮ ከጉዟቸው ቢደናቀፉ ይመኛሉ። የክፉ ነገር በሽተኞች ጊዜም፤ ዘመንም አያስተምራቸውም። የሚማሩት ነገር ቢኖር እንደ እባብ ቆዳቸውን እዬቀያየሩ በመሰሪ ዓላማቸው መልካምነትን መዋጋት ብቻ እና ብቻ ነው። ደግነት ስለምን ይፈሩታል? ርህርህና ስለምን ያርዳቸዋል? የጃርት ጉባኤ ርደት …

መልካም መሆን የተሳናቸው የመልካም ነገር እንጥፍጣፊ የሌላቸው መሆኑን የሚታወቀው መልካም ሰዎች ላይ በረድ ሲለቁ በዘመቻ መሆኑ ነው፤ ክፉዎችን የሚያስማማው ይሄው ነው። አንድ ጊዜ ይሁን ሁለት ጊዜ ይሆን በተከታታይ ሰው በተነፈሰ ቁጥር ፋታ መንሳት - መበደል ነው።

በዘመናችን የመልካምነት ታላቅ ሐዋርያ ሆነው የወጡ መልካሞች ተጠልፈው፤ ቀጭጨው፤ ጎብጠው፤ ተሰውረው፤ አቧራ ለብሰው እንዲያም ሲል ሞት ተፈርዶባቸው አይሆኑ ሆነው በዬዘመኑ ቀርተዋል።

አሁን የለማ የገዱ የአብይ እና የአንባቸው የመልካምነት ጉዞ ውጪ አገር ተጀምሮ ኖሮ ቢሆን እስከ አሁን ድረስ ደብዛቸው ጠፍቶ በነበረ። ወይንም የለማ እና የገዱ መንፈስ የውጭ አገር የድጋፍ ሰጪ ኮሜቴ ተጠማኝ ቢሆኑ ኖሮም አይቀሬ ነበር። አንድ ጊዜ ይህን ጉዳይ አብራርቼ ጽፌዋለሁኝ።

መልካሞች ብቅ ብለው እሸት ቅመሱ ማለት ሲጀምሩ ተረባርቦ ማድቀቅ የተኖረበት ነው በልግመኛው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ዶግማ። ለዚህም ነው የአማራ የህልውና ተገድሎ ብቄተ ቢስ ሆኖ፤ የብድር ዱቄት ሆኖ አንዲቀር እውቅና ተነፍጎት በዝንጥል አቅም የኦሮሞ ንቅናቄ ብቻውን የማህበረ ፈርዖን ሴራ እንዲጋፈጥ፤ ተሰብሮ፤ ደጋፊ አጥቶ እንዲቀር የታደመበት።

የኦሮሞ ንቅናቄን ነጥሎ ዕውቅና መስጠ የሳጅን በረከንት ጋንታ አቅም እግኝቶ የገዱን መንፈስ ለማስዋጥ የተሴረ ሴራ ነበር። ስለሆነም ብቻውን የኦሮሞ ፕሮቴስት የተደራጀ እና የተሰባሰበ አቅም አንሶት ወዳድቆ፤ አቧራ ለብሶ እንዲቀር ተበይኖበት ነበር። የሁለቱን ህዝቦች የተጋድሎ መንፈስ የጥምረት ጉዞ የተፈራ እና አቅም ሆኖ እንዳይወጣ በሚገባ ተሰርቶበታል በተከታታይ።

የአማራ ተጋድሎ የህውልውና ተጋድሎ ዕውቅና መነሳት ማለት ቅን ፖለቲከኛው ፈጽሞ ያልገባው የሚስጢር አስኳል ነበረው። የኦሮሞ ንቅናቄ ከግቡ እንዳይደርስ የታሰበ የተሰላ እና የተሰወረ ሴራ ነበረበት። ስለምን? ይታወቃል አማራ ከተነሳ ምን ሊመጣ እንዲሚችል። አማራ በጥገኛ ሥነ - ልቦና ሳይሆን በውስጡ በበቀል በራሱ አቅም ከተነሳ ገድቦ የሚያስቀረው ማንም እና ምንም ሃይል አይኖርም። ለዚህም ነው የአማራ መደራጀት እንደ ጦር የሚፈራው።  

አማራ ከኦሮሞ ጋር መንፈሱን ካጋባ ኢትዮጵያ ከታቀደውም፤ ከታሰበውም ከሚታለመውም በላይ የፈውስ መዲና እንደምትሆን ይታዋቃል። አይደለም ለራሷ የአፍሪካ መድህን መሆን መቻሏ ልብ ልክ ነው። ስለዚህ የኢትዮጵያ ራዕይ በተሰናከለ ድውይ መንፈስ ልፈስስፍ ብሎ፤ ወለም ዘለም በሚል የፖለቲካ እሳቤ  የኢትዮጵያ ታላቅነት በሰዎች ሥም ተጠልሎ ብቻ የጥገኛ ፖለቲካ ጥወራ ነበር ምኞቱ።

ለዚህም ነው „ከመለሰውያን ወደ ለምውያን“ የሚል ታቅዶ በኢሳት ፕሮግራም የተሠራው። የጣና ኬኛ፤ የአባይ ኬኛ፤ የኦሮሞ እና የአማራ ሙሁራን ህብረት የተፈረራ ገናና የ21ኛው ዓመት የተስፋ ጋብቻ የግንኙነት ብር አንባር ነበር። ስለሆነም በተገኘው መስክ ሁሉ ውጊያው ቀጠለ። ውጊያው ከአድዋ፤ ከማይጨው፤ ከጅጅጋው፤ ከመተማው፤ ከወልወሉ፤ ከአንባሌው በላይ ነበር። ምክንያቱም ዘመኑ 21ኛው ምዕተ ዓመት ነው። ዘመኑ ሉላዊነት ነው።

መገንባት የዘመናት ጥረት ውጤት ነው። ማፍረስ፤ መናድ ግን የደቂቃዎች ተግባር ነው። ዛሬ ዓለም በአንድ የመረጃ ማዕክል የምትመራ ናትና። ውጊያው በግራቀኝ በተጠናከረ የወልዮሽ ሚዲያ ሲካሄድ በወቅቱ ይህ የለውጥ ማዕበልን በአንዲት ዝቅ ባለች የሳተናው ብራና፤ አንዲት ትቢያ ላይ ያለች ሴት ማህከል ነበር።
ከጅምሩ ዘመቻው ኦህዴድ ላይ ያተኮረ ቢሆንም ቀስ እያለ ወደ ገዱ መንፈስም የዞረ ነበር።  የውስጥ ዝርዝር መረጃ አዋቂነት እና የሳጅን በረከት ስምዖንን አግኖ የማውጣት ሂደትም ታይቶበታል። ስንኩልነት።

ምክንያቱም የለማ መንፈስ የጀርባ አጥንት የገዱ መንፈስ፤ የኦሮሞ ንቅናቄ ክንድ የአማራ የህልውና ተጋድሎ መሆኑ በሚገባ ታውቆ ስለነበር ዘመቻው ጠነከረ። ከምስጋና አቅም እንኳን ተበላልጦ ነበር የተላከው። ብዕር የያዘ፤ ማይክ የጨበጠ ሁሉ በማቃለል፤ በማጣጣል፤ በማላገጥ የለውጥ ሂደቱን በተቀናቃኝነት ቆሞ ወጋው።

በመሃል አውሬው የደራጎን ማህበር ደግሞ አጋጠመኝ፤ ሳልከፍለው ፕሮፖጋንዲስት ሰጠኝ ብሎ ተፍነከነከ። የሚችለውን ሁሉ መሰናዶ በማድረግ በቻለው ሁሉ ለውጡን ተዋጋው። የተፎካካሪ ፓርቲ መሪዎች ነን የሚሉትም ለዴሞክራሲ እንታገለላን እያሉ „ጉልቻ ቢለዋወጥ ወጥ አይጣፍጥም“ በማለት ዘመቱበት። ይሄነን ታዋቂ ሚዲያዎች በቂ ሽፋን በመስጠት የኢትዮጵያን ተስፋ ለመቀማት ላሰፈሰፈው ሳንክ መንፈስ ሁሉ አግልግሎቱን ተግተው አሟሉ።

አገር ውስጥ በሳጅን በረከት ስምዖን መሪነት ውጪ አገር ደግሞ አክብረነው በኖርነው በኢሳቱ ፖለቲካ ተንታኙ በጸሐፊ ኤርምያስ ለገሰ መንፈስ ማዕከልነት ታወከን። ትንሹ ሳይሆን ግርዝዙ ሳጅን በረከት ስምዖን ሆኖ አረፈው አቶ ኤርመያስ ለገሰ። ተበሳጨ ከምል አበደ ብል ይቀለኛል። ጨርቁን ጥሎ አበደ። ኢሳትን እፍታን እርግፍ አድርጌ ተውኩት። ኢሳትን እራሱ ክብሩ ነው ያስደፈረው። ማለት ሰው ቅንነትን፤ በጎነትን፤ መታሳሰብን፤ መቀራረብን፤ መደማምጥን፤ ማስተዋልን፤ በዕወቅት መመራትን፤ ኢትዮጵያን ከፍ ማድረግን እንዴት ተጻሮ ይወጣል። እርግጥ ነው የፓርቲ አባል መሆን መቼም ጋዳ ነው። ይሁንና ምህርትን፤ ቸር መሆን እዬያህ እንዴት ዓይነህን መጋረድ ይቻላል፤ ለዛውም ከወያኔ ሃርነት ትግራይ ካድሬነት ወጥተህ የግንቦት 7 ካድሬነት ይጎምዝዛል። ይህን ከፈቀድክ ስለምን ትሰደዳለህ። 

አንተ ዓይነህ ያዬውን የአማራ ተጋድሎ አላዬሁም በል ተብለህ „የነፃነት ሃይል“ ስትል ያን የተቀበልክ ሰው እንዴት እና እንዴት ከነበረው የካድሬነት ህይወት ወጣሁ ማለት ያስችላል። ጉራማይሌ። ሌሎችም ታክለው በዚህ ዙሪያ ታከቱ … ግን ሆነ? አልሆነም። በዜሮ ተባዛ። ውጤቱም ዜሮ ሆነ። ያለፈ አንድም አመክንዮ የለም። አመክንዮ ቀርቶ ተመሳሳይ ቃል እንኳን አልተደመጠም። እዛው መክኖ ነው የቀረው። 

አሁን የገረመኝ ነገር እሱ አቶ ኤርመያስ ለገሰ አቅማቸው ሲያንደፈድፈው ከርሞ፤ ጥበባቸው ሲጎመዝዘው ከራርሞ ለዶር አብይ አህመድ ነፍስ ተጨንቆ፤ ለደህንነታቸው መረጃ አለኝ እያለን ነው። የእሳቸው ህይወት ጠባቂ፤ ስለሳቸው ካቢኔ ተቆርቋሪ ሆኖ፤ ለዛውም  የኢትዮጵያን የደህንነት ማዕከል መሥራች እና መሪ የሆኑትን የአገር ጠ/ ሚር ነው አሁን ደግሞ እመራለሁ ብሎ ነው የተነሳው። በዛ ላይ ኦቦ ለማ መግርሳ አሉበት በዚህ የሙያ ዘርፍ። ዘርፉን ደግሞ እኔ አውቃለሁ ብሎ አካኪ ዘራፍ እያለን ነው። ግን አያፍርም? ትንሽ አይሰቀጥጠውም፤?

"አለቃህ እንደቀደደው ቀደህ አሳኝ ያለ፤ በአፍ መፍቻ ቋንቋህ ስለምን ተናገርክ" ብሎ አንተ እና አንቺ ሲል የነበረ ፍጥረት አዛኝ ሲሆን? ሚስጢር አዋቂ ሆንኩኝ ሲል። ለዛውም እጬጌዎች የሙያው ባላባቶች ተቀምጠው። እኔ እንደሚታዬኝ የሚታመሱበት መሠረታዊ ምክንያት በሽታው የጋራ ነው ባይ ነኝ። በሽታው ደግሞ ይሄ ነው። attention seeker ስለነሱ ማሰብ ያቅለሸልሸኛል። ጥሩ ጥሩ ሰዎች እያሉበት ግን በግለኝነት፤ በምቀኝነት፤ በሸር እና በተንኮል አጨቀዩት ሚደያቸውን። 

ያ ሁሉ ታልፎ አሁንም ከዛው ላይ መዳከር አሁን ምን ይሉታል? … ለዛውም የተቋሙን መሥራች ሊመራ … ልክን አለማወቅ … ይልቅ የሚያምርበት በሌብነት ዙሪያ ያለውን የኢፈርትን ገመና ቢተክዝበት ይገባል። ለዛም የዘረፋትን በውጪ አገር ያለው መረጃ ስለምን በግልጽ ቀረበ ብሎ ሲያጣጥል ነበር።

እኔን ብዕሬን ፈርተው ያስቆሙኝ እኮ በትክክለኛ ቋንቋ ያው ቁልጭ ያለ Discrimination ነው። እነሱ በሚመሯቸው ድህረ ገፆች እኮ ለማንበብም ትውር አንልም። አልፈው ተርፈው በሞፈር ዘመት ነው ደግሞ ይገባናል የሚሉት። እኛን ብቻ አስተናግዱን። አገር ምድሩ የእነሱ ርሰት ጉልት ነው። ነገም እንኳንም አለደረገብን እንጂ ተሳክቶ ቢሆን ኖሮ  የአውራው ፓርቲ ህልም  የኢትዮጵያ የሚዲያ ዕጣ ፈንታ ይሄው ነበር። 

ብቻ የለመድኩት ነው በዬጊዜው ሲያስቆሙኝ፤ ትንሽ አታልዬ እና አዘናግቼ ብቅ እል ነበር። የእኔን ብዕር እንኳን ነፃነት የማይሰጥ የፖለቲካ ድርጅት የሚሊዮን ድምጽ ለመሆን ምንም ነው። እደግመዋለሁኝ። ምንም ነው። አቅም የለሽ ነው።
አዬው እኮ የቁም ሰማዕቱ አቶ ፈንታሁን ደስአለኝ አንድ እግሩን አጥቶ ምን ያህል "ለዚህ ታላቅ መሪ ምንም ዋጋ አልከፈልኩለትም እባካችሁ እርዱልኝ ይላል" አንድ ታዳሚ የኦሮሞ ሚዲያ ሲያናገረው ዕንባው መጣ እና አቋረጠው፤ ሌላው ከዚህች ቀን በላይ ሌላ ድል አልጠብቅም አለ። ምን ያልተባለ ነገር አለ። ቃላት መሸከም አልተቻላቸውም። ለዛውም ይህ ሀዘን ባይጨመርበት ኖሮ ትንግርት ነበር፤ የወያኔ ሃርነት የለመደበት ነው የቴዲን ኮንሰርት ለማጨለም ነበር ወሎ ላይ ጦርነት የከፈተው፤ ወሎ ላይ ያ የሃዘን ድባብ ባይደቀን ከዚያም በላይ ህዝብ፤ ከዚያም በላይ ድምቀት በኖረው ነበር የባህርዳሩ ኮንሰርት። አሁን የሆነው ይሄው ነው። ከታሰበው በታች ነው እንጂ የእነሱ ዕቅድማ ከዚያም በላይ ጉዳት ለማድረስ እንደነበር ነው የሚደመጠው። የተረገሙ። ታዲያ እንዴት ተብሎ ለእነዚህ እሾኾዎች ገመና ከዳኝ ይኮናል?


ቢያንስ ጋዜጠኛ፤ አክቲቢስት፤ ተንታኝ፤ የፖለቲካ ሊሂቅ እንዴት የሚሊዮን የወል ድምጽ ማድመጥ ይሳነዋል። ቢያንስ እንዴት እራስን ወቅሶ ከህዝብ ድምጽ ጎን ለመቆም ስለምን አይቻለውም? ህዝብ በአንድ ድምጽ እደመራለሁ ሲል እኮ እኔ ለማውያን፤ ገዱውያን፤ አብያውያውያን፤ አንባቸውያን ነኝ ማለቱ ነው። በቃ። አሁን ይህን መንፈስ ህዝብ አልመረጠውም ማለት ይቻላልን? ደግሞ ይሄስ „ከመለስውያን ወደ ለማውያን“ ያሰኝ ይሆን? „ከመለስውያን ቀስተዳምነውያን፤ ቅንጅታውያን፤ ግንቦትውያን፤ ጥምረታውያን፤ አገራዊ አድን ንቅናቄውያን“ እንደ ሽንብራ ቂጣ ስንገለበባጥ ለእኛ ከሳሽ ወቃሽ የለብንም። 

ነገ ደግሞ ሰማያውያን እንሆናለን … የነጭ ተደራዳሪ አማላኪው አሁን በድንጋጤው ብርክ ይዞት ሰማያዊ ፓርቲ አማራ ክልል ላይ ነው ያለው … አማራም በተጠቀለለ ሃሞት እንደገና ለዳግም ስለት አማቅቃለሁ ብሎ እንደማይንጨባረቅ ተስፋ አለኝ …
  • ውጪ እዳሪ መሆን ኪሳራ ነው
ከዚህ ውጪ መሆን አይቻለውም። ሊሆን የሚገባው የፖለቲካ ድርጅቶች ሆኖ ሚዲያዎች ይሄንን የፍቅር፤ የአብሮነት፤ የመተሳሰብ፤ ሸር እና ተንኮል የሞተበትን ደግ ቅዱስ ሩህሩህ ሰማዕት መንፈስ የሚደግፍ የሚያበረታታ ሥራ ለምሥራት መቁረጥ ነው። በቃ። ሚሊዮኖች አብይ ኬኛ! አሉ። ምን ትሆኑ … ውድቅድቅ ስብርብር፤ እንኩትኩት … ፖለቲካ እኮ ሂደትን ማድመጥ ያስፍለገዋል። ቀድሞም መተንበይ፤ ጉዳዩንም ማጥናት፤ ጉዳዩን አስጠግቶ ማድመጥ … ዛሬ ላይ ሆነህ የቅንጅት መንፈስ መጠበቅ ቁልጭ ያለ ማሙ ቂልነት ነው።
  
መደገፉ ደግሞ ንጹህ መሆን አለበት። ስርክራኪ፤ ወጋ ጠቀም ያለ የለበጣ ጉዞ መቅረት አለበት። አጥርቶ መደገፍ ወይንም አጥርቶ መቃወም።

አሁን ማን ይሙት አቶ ኤርምያስ ለገሰ ለዶር አብይ ነፍስ ጨንቆት? ፊታውራሪ አለማፈር እስቲ ተጠራ? ቀድሞ ነገር እኮ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነውን“ 1% ነው እኮ ነበር የሰጠው። ይህም ብቻ አይደለም „ገዱ ለማ ገዳይ“ ናቸው ነበር ያለው። ይህም ብቻ አይደለም የኦፌኮን መሪዎች እንዲፈቱ አይፈልግም ኦህዴድ፤ ይወዳደሩናል የሚል ስጋት ስለሚኖርበት ሲል የአቦ ሌንጮ ለታን ፓርቲ በቀይ ምንጣፍ ተቀበለ። 

በዬዕለቱ የአቶ ኤርምያስ ሟርት ከፎቅ እዬወረደ ተፈጠፈጠ። …  ይህም ብቻ አይደለም "እናንተ ልጆቻችሁን ስለ ኢትዮጵያዊነት አስተምሩ፤ ኦሮምያ ላይ ሆናችሁ፤ ለእኛ ግን የፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሁኔታ አመቻቹልን፤ ማዕካላዊ መንግሥቱን ለመምራት አትመጥኑም፤ ልካችሁን አውቃችሁ ተቀመጡ፤ ቀዩ ምንጣፍ እኛ ከብራስልስ ይዘን እንመጣለን" ያለ ጉደኛ ፍጥረት እኮ ነው። ሳያፍር ሳይቸር። እሱ እኮ እንደተሙረቀረቀ ጥሎት የመጣውን ታግለው ላሸነፉ ጀግኖች ቤት ጠባቂነት ነው የተመኛላቸው። ይህም አልበቃውም በዛ ዓለምን ድንቅ ያሰኘ ንግግር ማግስት ወጥቶ አብይ ተንሳፏል፤ ኢትዮጵያ „በነበረከት ኮሜቴ“ እዬተመራች ነው ብሎ የወጣ እኮ ነው።

ብትታገሱትም፤ ብትነግሩትም አይሰማም። ወስጡ ምን እንዳለ የሚያውቀው እሱ ብቻ ነው። አሁን ማድረግ ያለበት ሲበትነው፤ ሲያውከው፤ ድርጅቱን ባልሆነ የምክር አገልግሎት ሲመራ የቆዬበትን የከሰረ አቅሙን ይዞ ሰብሰብ ብሎ ቢቀምጥ እና ቢያንስ ሊያደምጥ ቢፈቅድ ምንኛ ዕድለኛ በሆነ ነበር። ከሁሉ አለሁ እያለ ከሚጣድ። ምን የእነ ማህበር ... ምን እነሱ እኮ ጎንደር አቶ መላኩ ፈንታ የሚባሉ ከእስር ሲፈቱ ህዝብ አከበራቸው ብለው እርምጥምጥ የሚሉ ጉዶች እኮ ናቸው። ምን አገባችሁ ቢባሉ ምን ሊሉ ነው?

ግን ምንድነው ፍጥረታቸው? ከቻሉ ማን ይከለክላቸዋል አቅምን ያምጡ፤ ይውለዱ፤ ተወዳድረው ያሸነፉ በቃ … ስሜን ኢትዮጵያን ያገለለ መንግሥታቸውን ይመሥርቱ እና ይታዩ። አንድ ቀን አውሎ የሚያሳደር አቅም፤ ይህን ዝክንትሉ የወጣ መከራ መሸከም ከቻሉ። እዚህ ያለውን መሰብሰብ እንኳን አልቻሉም … ሃሳብ የለሽ ቁጥር ብቻ … የራሳቸውን ባድማ ጤንነት እና ሰላም አስጠብቀው በበትረ ሥልጣነ መንግሥታቸው ያላጠቃለሉትን ማህበረሰብ እና ቀዬ ሲያስቀጠጥቅጡ የኖሩ ጉዶች …

ከቻሉ ያ ሲያብጠልጥሉት የባጁት የአብይ መንፈስ ዓይናቸውን ፈቶላቸዋል እና ቁጭ ብለው እንደ ድርጅት ይሄ በዬጊዜው ወጥ አመራር አጥቶ ሲያቦክስ፤ አቅም ብቅ ባለ ቁጥር በተጻጸራሪነት ቁመው ጦርነት የሚከፍቱበትን እኛን ብቻ ተቀበሉን ተባደግ ፍልስፍናቸውን ቀጥተው እንደሚሆን ቢሆኑ ይሻላቸዋል። አሁን ምን ያስፍልጋል ለአብይ ካቢኔ የደህንነት መረጃ ሠራተኛ ለመሆን ደግሞ መቋመጥ። ቤትህን ሳተጸዳ ጎረቤት።

  • አቅም። 
ከተጀመረ ጀምሮ ተናግሬያለሁኝ ኦህዴድን በውድድር ማሸነፍ ከባድ ነው። አቅሙ የሚደፈር አይደለም። አንድ ሁለት ሰው አይደለም ብዙ ናቸው። ብዙ። ለእያንድንዱ ሃላፊትን እስከ ሦስት የሚደርሱ ተተኪዎች አላቸው። ለፌድራል ሰውን ሪኮምንድ ሲያደርጉ የሚመጥን ተተኪ ሰው ኦህዴድ የሚያዘጋጀው አስቀድሞ ነው። እኔ እንደ አንድ የትምህርት ክፍለ ጊዜ ነው የማጠናቸው። እያንዳንዱ እንቅስቃሴ ወግ አለው፤ ለዛ አለው፤ ማዕዛ አለው፤ ሳቢ ነው። አጓጊ ነው። ድርጁ ነው። ሥልጡን ነው። ሰውኛ ነው። ተፈጥሮኛ ነው። አትገናኙም። ማወዳደር የሚቻለውው ከረባት እና ገበርዲን ሳይሆን ፍሬ ባለው የድርጅት አቅም፤ ብቃት፤ የመምራት ጥበብ፤ ብልህነት፤ ሆደ ሰፊነት እና የድርጅት ጽናታዊ አቋም ነው። 

የድርጅት አቅም እና ብቃት ለመገምገም ደግሞ የትውስት ቤት አንቆጥርም። ቂጥ ያስፍልጋል። ንግድ አይደለም ማደራጀት። ቢያንስ መሸነፍን፤ መውደቅን፤ መውላለቅን ተቀብሎ፤ ግደፈትን፤ ስህትትን ለመመርመር ሥር ነቅል እርምጃ መውሰድ ሲጋባ ዛሬ ገብተን እናነኩራለን ማለት የማይደፈረውን የሰለም መንፈስ በእጅ ለማስገባት መጣር ጅልነት ነው። ቀሪውን መንፈስ ለመሰብሰብ እኮ አቅልም፤ አደበም ያስፈልጋል። 

ስትከስር ድርጅቱን ዘግተህ በአዲስ አወቃቀር እና መንፈስ አዲስ የሆነ ዘመኑን የተቀበለ ብቃት ይዘህ መውጣት ግድ ይላል። ይሄው አቤቱ ሰማያዊ ፓርቲ የነጭ አደራዳሪ ብሎ ከተኮፈሰበት ወረድ ብሎ ለመናጆነት ካሰበው አማራ መሬት ላይ ይገኛል። አንድም ቀን ስለ አማራ ተጋድሎ ትንፍሽ ብሎ የማያወቀው ሰማያዊ … ለድምጽ ለቀማ ወረድ ብሏል ከተራራው … ዲያስፖራውም እያመለጠው መሆኑን ተገንዝቧል … ግን አምክንዮውን መድፈር አይችልም።

አማራ መሪ አለው። አማራ አጀንዳ አለው። አማራ ጀግና አለው። ቀልድ የለም  ከእንግዲህ ከፋኝ ለጫካ ሲቀር፤ ደግሞ በሰላሙ መንደር ወክ እንዲህ የለም … አማራ ድልድይነቱ አክትሟል። ለአማራ ከኦህዴድ የተሻለ ብሩህ መንፈስ የለውም። ኦህዴድ ብቻ ነው አማራን አክብሮ የተነሳው። ለአማራ ከዶር አብይ አህመድ በላይ ሁለመና፤ ክብር፤ ጌጥ ህይወት የለውም።

በኢትጵያ የስልጡን አድማ መስራች የራስ ተሰማ ናደው ሌጋሲ ለአማራ ግጥሙ አይደለም። ሰማያዊ ማለት ይሄው ነው ፍሬ ነገሩ። ራስ ተሰማ ናደው ዘብርሃነ ኢትዮጵያን የድንግል ማርያም ወዳጅ የሆኑትን እቴጌ ጣይቱ ብጡልን በግዞት ያስቀመጡ ከቤተሶቦቻቸው ጋር የለዩ፤ ወደ ትውልድ መንደራቸው ሄደው እንዳይቀመጡ ያደረጉ ሲሆኑ እሳቸውም ላሰቡት ቦታ ሳይበቁ ህይወታቸው አልፏል። ነገ ደግሞ ውህደቱ ብቻ ሳይሆን ቢሳካ ድምጹ ከማን ጋር እንደሚዳበል ይታወቃል አቤቶ ሰማያዊ።

ይልቅ ዛሬ ሳተናው ላይ አብን በኤርትራ ጉዳይ አቋሙን አልወሰነም የሚል አንብቤያለሁኝ። እንዲህ ነው እኔ የምወደው። መርጋት፤ መስከን፤ ማድመጥ፤ አጋርን ተጋፊን ጠንቅቆ ማወቅ። ጥልቅ ጥልቅ አለማለት። ዕዮባዊነትን መሸመት። መንግሥት የራሱን ተግባር ሲከውን ከሱ የተሻለ አለኝ እበልጣለሁኝ፤ እሻላለሁኝ የሚለው ተፎካካሪ ፓርቲ ደግሞ አደብ ገዝቶ በራሱ ተግባር ላይ መታተር ያስፈልጋል። እሰው ቤት እየገቡ ከማነኮር ይልቅ ዝርክርኩን የራሱን ባሊህ ማለት አለበት …
  • ዜና።
ዛሬ ሌላ ደስ የሚለው ዜና ለሥርጉተ ሥላሴ ተገኝቷል። የሰብዕዊ መብት ተሟጋቹ ፕ/ አለማዬሁ ገ/ ማርያም ለዩ ሚናችሁን የሚል ጥሪ አቅርበዋል። ፊት ለፊትም ወጥተው እንደሚታገሉ ዓውጀዋል። እንግዲህ ከአንዲት መሃይም ትቢያ ላይ ከወደቀች ሴት ሙግት አልፎ ጉዳዩ የሊቀ ሊቃውንታት ሆኗለኝ። ይሄ ማለት እሳቸውን ደፍሮ የሚያስቆም፤ ብዕራቸውንም ማዕቀብ እንዲጣልበት ማደረግ ስለማይቻል እነ አቶ ኤርምያስ ለገሰ ለሚያማስሉት የመርዝ ብጥበጣ ደጉ የአብይ መንፈስ ተጠቂ አይሆንም ማለት ነው። 

ስለዚህም ሥርጉትሻ እልልልል ብላለች … ምክንያቱም የጹሁፎቹ መርዝ በፈረቃ ይለቀለቁ የነበሩት ቀላል አልነበረም። ለበስ ብለው ይቀርባሉ፤ ግን ውስጣቸው ፈንጅ እና ቦንብ ያጠመዱ ናቸውና። አሁን የጋዜጠኛ መሳይ መኮነን ጹሑፎች በለብታ የሚጋለብበት አይደለም። ፍልፍ አድርጎ አጋለብጦ መፈተሽ ያስፈልገዋል። እሱን ተዳፈርሽ ተብዬ ነው ማዕቀቡ የተጣለብኝ። ይገባልም ብለናል። የቤተመንግሥት ጋዜጠኛ ባለፈም ዓለም አቀፍ ጋዜጠኛን መጋፋት ደረጃን አለማወቅ ነበር። ግን የቀደሙት እረኛንም፤ ደሃንም ያዳምጣሉ።

 የሆነ ሆኖ ስለባድም ጉዳይ እኔ ያልኩትን ኢትዮጵያ ያሉ ሙሁራንም፤ ጠ/ ሚር አብይ አህመድም ደግመውታል፤ ኤርትራም ቅናዊ ምላሽ ሰጥተባታለች፤ ግንቦት 7 ትቅማጥ እንደያዘው የሳለእንግሊዝ ቤተኛ ተጣድፎ ወጥቶ ነበር መዝግቡኝ ያለው …

እርግጥ ነው ፓርቲ አባልነት የሚወደድ እና ወደ ራስ ማድላት ሊኖር የሚጋባ ቢሆንም ግን ሁልጊዜ መልካም ነገሮችን ጠቅጥቆ የማይታይ የማይጨበጥን ተስፋ እምኑልኝ ማለት ግን ግብዝነት ነው። አቅም የለም። አገር ለመምራት የሚያስችል አቅም እኮ ፍቅርን፤ ደግነትን፤ ርህርህናን፤ ሰዋዊነትን፤ ሃቅኝነትን፤ ቃልን መጠበቅን፤ በቃል ውስጥ መብቀልን፤ ዜግነትን፤ ተፈጥሯዊነትን፤ ምህረትን፤ ይቅርታን፤ ግልጽነትን አይፈራም በፍጹም። 

በዛ ላይ ፖሊሲ የሌለህ እንዴት እና እንዴት ተብሎ? የማይሆነው ነው እንደ ጣዖት ተመልኮ የተኖረው። ወያኔ ሃርነት ትግራይም የማይፈራውን ነበር ሲፈራ እና ሲርድ የከረመው። በሌላ የፖለቲካ አቅም ማንነት። ማስታወቂያ ላይ ተገኙልኝ በዚህ ቀን እና ቦታ የተባለ ፖስተር ሰላማዊ ሰልፍ ላይም ተይዞ ይወጣል። ሰዉ ተግኝቶ እኮ ነው። መሥራት መፍጠር መብቃት ከዬት ይመጣል። የፖለቲካ ተመክሮ የአሻቦ ግዥ እና ሽያጭ አይደለም። ይህን ገመናህን ተሸክመህ ተወዳድሮ ለማሸነፍ ዳገት ነው። በሃሳብ ደረጃ፤ በመንፈስ ደረጃ እንኳን የገዘፈ ፈተና ፊት ለፊት አለው። 

ቢያንስ መንገዶች ቀና እዬሆኑ መምጣቸው እራሱ ማድመጥ ተስኖህ ይሄው በሚሊዮን ድምጽ ተዋጥክ። አደብ ይስጣችሁ። የራሳችሁን ሥራ ለመሥራ ያብቃችሁ። ሰው እያደናችሁ አባል አንድ አባል ሁለት እያላችሁ ተጽዕኖ ፈጣሪ ከመልቀም ይልቅ ግልጽ ባለ የፖለቲካ አቋም እና ብቃት ተፈጠሩ። እንጠብቃለን ዶር አብይ አህምድ የኢሳት የዓመቱ ምርጥ እንደሚባሉ ወይ ደግሞ አንድ ሌላ ተጽዖኖ ፈጣሪ የሚባል ሰው ይሄው ነው አቅሙ፤ 

ግን እንዴት ነው ዘንድሮ የአውሮፓ ህብረቱ ምክክር ተስተጓጎለን? አዲስ የትንሳኤ የምሥራች እኮ እየጠበቅን ነው … ከቶ ቃል ቁሞ ሲሄድ ስለታዬን ይሆን? አልገብቶም ወይንም አልተረድቶም። 
  • ልዋጭ።
ሰማያዊ ፓርቲም ሞቅ ደምቅ ብሎ ይጠብቃል … መሬት ላይ … የኢትዮጵያ መንግሥትም ትንሽ ላቅ ባለ ሁኔታ ተራራውን ሥም እና ዝና ይቀበላል። ግን ከኤርትራ መንግሥት ዝቅ ባለ ሁኔታ። አቤት እስታሁን ስንት ሰው ቤት ተሂዶ ይሆናል። ማን አዲሱን መንፈስ ይቀርባል እዬተባለ ምሻምሾው አይቀሬ ነው።
አቅም እና አቅል ለዚህ ዛሬ ላለው ዝብርቅርቅ የኢትዮጵያ ፖለቲካ የሚመጥን ብቃት የለውም ግንቦት 7። ዕውነቱ ይሄው ነው። 

ዘመን የሚሰጠውም የሚነሳው የምሥራች አለ። አሁን ለግንቦት 7 የአውራ ፓርቲ ህልመኝነት የመርዶ ዘመኑ ነው። ስለዚህ እንደ ገና ተጸንሶ እንደ ገና መወለድ አለበት። ከሌላ ጋር ቢጣበቅም ያው በሽታውን ይዞ ኮተት ስለሚል አይበጀውም። ስለዚህ የበሰለ ተግባር ለመከወን ራሱን ከመንበሩ አውርዶ „ሀ“ ብሎ መጀመር ያለበት ብዙ ተግባራት አሉበት። 

የቦታ ለውጥም፤ የሃላፊነት ለውጥም ቢኖር መልካም ነው። ዕድል ያለው ሰውን ወደ ፊት የማምጣት ወሳኝ እርምጃ ያስፈልገዋል። አንዱን የገዳን ቤተኛ ከውስጡ አውጥቶ ኦህዴድን እከሌ ተቀላቀለ ደግሞ ይለንም ይሆናል። ልክ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ ቀልድ አብን ላይ እንደዛ የሰማያዊ የነበረ ቁልፍ አመራር ተሰጥቶታል፤ ልክ አንድነት ለአዲስ ገቦች ቁልፍ ቦታን ይሸልመው እንደነበር። የማያተርፍ መንገድ ስለምን እንደሚደገም አይገባኝም... ለነገሩ ዘመን አመጣሹ ፖለቲካ ...ሽልንግ ወይ ድግሪ ይኑርህ በቃ ምርጥ ሰው ...   
  • ነገረ ኤርትራ፤
ይልቅ ጉድ የሚፈላው ዶር አብይ አህመድ እና ፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ በጤነኛ መንፈስ ተግባብተው በንጽህና ህዝብን ማገናኘት ችለው የአኩል ተጠቃሚነት መርህ ከነደፉ ያን ጊዜ ጨርቅ ጥሎ እንደሚያሳብድም ይጠበቃል። … ተቁቶ የኖረ የመከራ ጉቶ ተናዳ ተብሎ እንደ ኤርትራ ፕሬዚዳንት ጽ/ ቤት የደህንነት ሰው ለመሆን መቃጣት ብቻ እርግጠኛም ተሁኖም ነበር፤ አታደርገውም ኤርትራ ተብሎ። ለእኛ ፍላጎት በሚመች መልኩ ፖለቲካውን ስናጠጋጋ እዬወላለቁ መቅረትም እንደ አለ ልብ አልተባለም … በሁሉም መስክ ያሉ መልካምነት „በግን“ የጨቀዩ ናቸው። ውስጣችን የሚታወክበት ያልጠራ በሽታ ይዞናል።

አቅም ከኖረ እኮ ፕሮፖጋንዲስትም ቀስቃሽም አያስፈልግም። አቅሙ ራሱ አደራጅም መሪም ደጋፊም ተሟጋችም ነው የሚሆነው። ሚዲያ የፖለቲካ ድርጅቶችን ተግባር ተክቶ መሥራት አይችልም። ኤትክሱም አያስኬድም። የልምድ ድርቀት ካልኖረ በስተቀር። ሌላው አቅምን ቢፈሩት ይህም የሚሆን አይሆንም አቅም ጥሶ የሚወጣው በአቅሙ ነው። ብልህ አቅም የፖሮፖጋንዳ ስልባቦትን በጽኑ ይጸዬፋል።

ቅኔቹ ዛሬ የተለጠፈ ነው። በፍቅራዊነት የቃላት የፖስተር ቻናሌ። ከፈቀዳችሁ ማዬት ከልፈቀዳችሁ ደግሞ መብቱ የእናንተው ነው። 

Love Nature’s Relationship Part Three (Chapter Three)


  • በጣም ጥቂት ሙግቶች 
ይህን ይመስሉ ነበር። ከእኔ ብሎግ ፖስት የተደረጉት ብሎጉን የጀመርኩት ግንቦት 1፣ 2018 ስለሆነ ነው እንጂ የተሠሩበትን ቀን ግን የቀደሙ ናቸው ቀኖቹ። ሥርጉት ከመሸ አይደለም ደጋፊ ሆና የድል አጥቢያ ማህበርተኛ ለመሆን የፈቀደችው። ይሄ ግን እጅግ ጥቁቱ ነው ... ጊዜው ሲኖር ሁሉንም መፈተሽ ትችአላለችሁ። ለኦህዴድም መልካም እድል የተመኘሁት ዕጣ ነፍሴን እኔ ብቻ ነበርኩኝ። እርግጥ የሳተነው ብራና በቅንነት ረድቶኛል። 

ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር።
ዓለሞቼ ኑሩልኝ።

መሸቢያ ጊዜ።






















https://www.youtube.com/watch?v=3XasnG3Ena8&t=3400s
https://www.youtube.com/watch?v=76IFoT-5yrg

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።