አብይ ኬኛ! ክፍል አንድ።

አብይ ኬኛ - ለቅኖች ብቻ!
ከሥርጉተ ሥላሴ (Sergute©Sselassie)
 18.12.2017 ዙሪክ ሲዊዘርላንድ
„እግዚአብሄር በአንድ መንገድ በሌላም ይናገራል።
 ሰው ግን አያስተውለውም።“
 (መጸሐፈ እዮብ ምዕራፍ፴፫ ቁጥር ፲፬ 33)
  • ክፍል አንድ።

የት እንጀምር ብዬ እሜቴ ጠበቃዬን ጠየቅኋዋት። ሳታቅማማ ከፈለግሽው ስትል ይሁንታዋን በቅንድቧ ቀደሰችው፤ አንገቷንም ቀና አድርጋ ገጼን እያስተዋለችም በብሌኗ ፈረመችበት። ቅቤው ይውጣ እንደማለት። ፈገግታዋን ስትመርቀኝ ደግሞ ጉልበቴ በአቅም- መንፈሴ በህብር ቀለመ። 

ይህ ሥም የታናሽ ወንድሜ ሥም በመሆኑ አይደለም አብይ ኬኛ! ብዬ ከች ያልኩት። የኔው ታናሽ ወንድሜማ ያው የእኔው ነው። ጎንደር ልዩ የአብይ ገጸ በረከት ስለተሰጣት ነው ዛሬ ሙሉወርዴን በማለፊያ መቀነት ሸብ አድርጌ የብዕር እንጉርጉሮ ያሰኘኝ።

ወደ ዋና አምደ ጭንቅላት ወደ ሆነው አትኩሮቴ፤ ግራሞቴ፤ ተመስጥዬ እና ተደሞዬ አብረን ከማለቴ አስቀድሜ ግን ጠፋ ባልኩበት ሰሞናት ምነው የሊሂቃን ዝምታው፤ ኧረ አንድ በሉ እንጂ የሚል አንድ ጹሑፍ ያው ከተለመደው ማዕዴ ከሳተናው አነበብኩኝ። „የህዝቃኤል ጋቢሳ መንገድ (ሰለሞን ይመኑ)“ እኔ ባነበብኩበት ሰዓት ወደ 832 አንባቢ ሸር አድርጎታል። ይህ የሚያሳዬው ጉዳዩ አትኩሮት እንዳገኘ ነው። በአንባቢው ልቦና ውስጥ የከተመ አህታዊ ውስጥነት አለው ማለት ነው የጹሑፉ ጭብጥ።

እኔ ደግሞ እማስበው ከዚህ ውጪ ነው። መቼም እኔ በዬትኛውም የአኗኗር ዘይቤዬ ፈንገጥ ያለ ተፈጥሮ ነው ያለኝ። ስለሆነም  መደከም ያለብን ትላለች ፈንገጥ ያለችው የሥርጉተ ነፍስ በእኛ በሆኑ፤ እኛን እኛን የሚል ጠረን ባላቸው አመክንዮ ላይ መሆን አለበት ነው ንጥሩ - የእድምታዬ። የእኛ ያልሆነው የእኛ ሊሆን አለመቻሉ ብቻ ሳይሆን፣ መንፈሳችንም እዬሰረቀ ሰላማችን ስለሚያውከው ቢያንስ ለውስጥ ሰላማችን ብለን እንኳን ለራሳችን መንፈስ ቀናይ ታታሪዎች /Activist/ እንሁን ነው የምለው። ይህ እሰጣ ገባ እያመረቀዘ ውስጣችን የመግል ቤተኛ ነው የሚያደርገው። 

አቅማችንም ከለ አግባብ ቧጥጧ የጥል ግድግዳን ገነብቷል።  በታፈነ የቅራኔ ነውጥ ኑረንበታልም። አቅማችን፤ መዋለ ጊዜያችን፤ መዋለ መንፈሳችን የእኛ ባልሆኑት ላይ መድከም፤ መዛል የለበትም። ኪሳራ ነው። ብልህነት አትራፊ በሆነው ጉዳይ ላይ የጎደለውን እዬሞሉ፤ ያነከሰውን እዬጠገኑ ወይንም ወጌሻ እዬሆኑ፤ የተዛባውን በድፈረት እዬገሰጹ፤ መልካሙን ደግሞ ሁነኛ እዬሆኑ በማድመቅ - በማፋፋት - በማጎልመስ ላይ መትጋት ነው የሚያስፈልገው። የማይድነው ነገር አይድንም። ከዚህ ከማሌ ርዕዮት ጋር የከተሙ ፍልስፍናዎች የሴራ ድንኳኖች ናቸው። 

ካናሰር ድህነቱ የሚወራረደው ድንጋይ ሲንተራስ ብቻ ነው። ስለሆነም ከሞት ጋር ግብግብ ገጥሞ ነጭ የደም ሴልን ከማራቆት ከቀዩ የደም ሴል እና ተምጥኖ ከተሰራው የነጭ ደም ሴል ጋር ህብረቱን ሆነ አጋራነቱን ማበልጸግ መንገዳችን ሊሆን ይገባል ባይ ነኝ። ከአዬር ላይ ጉጉስም ወጥቶ ፍቱኑ የአምክንዮ አስፓልት በሆነው አንዳችም የማሌ ርዕዮት ልቅላቂና እንጥብጣቤ በሌለው፤ መሠረት ከያዘው፤ መሬት ላይ ከሚገኘው ቅናዊ ጎዳና ጋር መጣመሩ ነገን ያሳድራል፤ ዛሬንም ያበራል። ማግስታዊነትንም በቅንነቱ ጸንሶ ይወልዳል። ለምለማዊ ፍች አለ መሬት ላይ። 

አሁን እንደ ቀደመው አቨው … ውስጤን እንዲህ ብገልጸውስ …?
አሃ! ናፍቆቱ ሲያባትለኝ፤ ህሊናዬን አስቶ ሊያሳብደኝ ሲነስተኝ ከዓለሙ የሁለመና አውድ ዓፄ ጉግል ገባ እልና ምስሏን እጎበኛታለሁ። እሳለማታለሁ። አሳሳታለሁ እና። የእዮባዊ ቅንነትና የመከራ ጽናትም ለሆነችው ባዕቴ፤ እማደርግላት ባይኖረኝም ቀኑንንም ሌሊቱንም ድርሳን አደርስላታለሁ። አንድዬ በቃሽ እንዲላት እምጸነዋለሁ። 

ከአጋም የተጠጋች ናት እና። በተጨማሪም በዛ ለዛ ባለው ማጠንቱ አጥብቶ ያሳደገኝን የጎንደሩን ደብረብርሃና ሥላሴን እንዴት ባጀህ እንዴት ከረመክ የእኔ ማህባ እለዋለሁ። እንነጋገራለን፣ እንምካከራለን፤ ስለናፍቆታችን ብትክትክ እንላለን። „መቼ ትመጫለሽ?“ ሲለኝም መልሴ …  „ያላለቀ ቀንን ፈልጌ ካገኘሁት እለዋለሁ።“ እድምታችን በንጽህና የዳጎሰ ሰለሆነ አያዋለሁ - እያዬኝ፤ እያዬሁት - መሳሳሙን በፍቅር እነስነካዋለን፤ በናፈቀኝ እቀፉ ውስጥም አድርጎ ሙቀቱን - አይዞሽ ባይነቱን - ይለግስልኛል። 

እኔ ፎቶ እማዬው በተለምዶ ውጩን አይደለም፤ ውስጡን እንጂ። ጸሎቱም ከውስጥ ተነስቶ ነው። ማህሌቱም ሆነ አቋቋሙም እንዲሁም ሰዓታቱም ከውስጥ ጋር በመታደም። ውስጥን ማዬት፣ ውስጥን ማናገር፣ ውስጥን ማጥናት፣ ወደ ውስጥ ማቅናት አውራ የመፈቃቀድ ደጀ ሰላም ነው። እንግዲህ በዚህ መሃል ነው እንዲህና እንዲህ የሆነው … „እንዴት በሉ?“ እህ! እንዴት ማለት በትሃ ነው።

ግን ተዚች ላይ አንዲት ነገር ልበል የዛያ ሰሞናት የተጋሩ የጠበንጃ ጉባኤ በሳቅ ሲሽሞነሞን በሙታን መንደር በከተመችው እትዬዋ ጎንደር ላይ በቁስሉ ላይ ረምጦ አንሶል ይታከልበት ብሎ ሚጢሚጣ ሲነሰንስበት በዚህ ማሐል ነው እንዲህም የሆነው …. 
  • በዚህ መሐል፤


በዚህ መሐል ነው አንድ ድንቅ ሥልጡን ሐዋርያዊ ሐመራዊ ቅንነት ከፊቴ የተደቀነው። ግርም እያለኝ አፍጥጬ አዬሁት። እሱም በጥልቀት አዬኝ። እስቲ ተጠዬቅ ብዬ ቀጥል ስለው የሰማይ ታዕምር እስኪመስለኝ ድረስ ሳልነቀሳቀስ ቀጥ ብዬ እመለከተው ጀመር። ከመቀመጫዬ አፈፍ ስል አልታወቀኝም። የዕውነት የፊልም ቅጽበት ነበር የሚመስለው። ጸሎት ነው የሆነልኝ። ቤተ - እግዚአብሄር ያለሁም መሰለኝ። እንደ ገዳም ሆና በተሠራችው በቤቴ/ በቤተ መቅደሴ ነው የውስጥነት ቀረጻው የተከናወነው። ቤቴ ጸጥ ያለች ናት። በምድር የምወደው ነገር ዝምታን ነው። 

አባቴም የሚታወቀው በዝምታው ነበር። እናቴ ደግሞ በሳቃ። እንዲያውም የእናቴ እናት ጽግሽ እናቴን „ስትወለጂ አፍሽ ጠባብ ነበር፤ በሳቅሽ ብዛት ሰፋ ትላት ነበር።“  ቁሜ አዳምጬ ስጨርስ እንደለመደብኝ በጸጥታ ተዋጥኩኝ። ቤተ መቅደሴም ጸጥ እረጭ አለች። ኮሽታ ተነፈጋት። መቼም በዛች ቅጽበት ወፍ ለቅማ ትውጣለች። ታዲያንላችሁ ድጋሜ እባክህን እናትአለም ዩቱብዬ የእኔ ፍቅር ድገምልኝ ስለው ደገመው። „ኧረ አንቺ ከፈለግሽ ስለምን ሺ ጊዜ አይሆንም“ አለኝ እና የይለፉን ትኬት በነጣ ሰጠኝ፤ መቼስ ዩቱብዬን ከቅንነት በስተቀር ኢጎ አይጎበኘውም። ሲያጋጥም አልኩኝ እና እኔ እህታችሁ ሰለስኩት። አልጠገብኩትም።

 ውስጤ ሆነ። ጌጤ ሆነ፤ ማርዳዬ - አልቦዬ - ድኮቴ - መስቀሌ - ድሪዬ። የእውነት አለኝታዬ ሆነ። የምር መተማማኛዬ ሆነ። „አለሁሽ አይዞሽ አትፍሪ“ አለኝ። አበረታታኝ። አጽናናኝ። አጸናኝም ብርቱ ክናድ ሆነኝ። ተስፋን ዘንበል አድርጎ አጠጣኝ። ጥማቴም ትጉስ ሆነ። ነገረ ጎንደር እንዲህ የራስ አጀንዳ ሲሆን ከማዬት በላይ፤ እንዲህ የውስጥ ማተብ ሲሆን ከማዬትና ከመስማት በላይ ምን ሐሤት አለና።

በቃ እኔና ጭምቷ ቤቴ - ቤተ መቅደሴ ሻማችን አብርተን ውዳሴ ማርያም ደገምን። ጎንደር አንድ ልጅ ወለደች። ከምጥ ተገላገለች። በሃሳቡ ውስጥ ጎንደር መኖር አራሱ በራሱ ዕጹብ ድንቅ ነው። እንኳንስ ውስጥን በፍጹም ሁኔታ የገበረ ተቆርቋሪነት። አረፍኩ። የእውነት አረፍኩ። ዛሬ ይህን ጹሑፍ ለመጻፍ ያአነሳሳኝም እንደ እኔ እርፍ እንድትሉ ነው። በተጨማሪም በሁለቱ አውራ አምንቶች የምትገኙ አቨው ለእኒህ የቅንነት ወተት ለዶር አብይ አህመድ የጸሎት ጥበቃ ታደርጉላቸው ዘንድ ልለምናችሁ፤ ልማጸናችሁም ነው። ዓለማችን ደግ ሰው አይበረክትባትም። 

በዓለማችንም አሉታዊ ነገሮች ካለድንብር እንዳሻቸው ጅረታቸው ይለቀቃል፤ አዎንታዊ ነገሮች ደግሞ በእስር ይማቅቃሉ። ደንበር - ክትር - አጥር ይሰራላቸዋል። በዛ ላይ ሰውዬው ደግሞ ህውሃት ነው። መልቀሙን ያውቅበታል ቀንበጥ ደግነትን፤ ቅንነትን፤ አብሮነትን። ሲያሻው በመኪና ግጭት፤ ሲያሻው በአውሊያው፤ ሲያሻው በምግብ ብክለት፤ ሲያሻው ደግሞ በካቴና፤ ሲያሰኘው ደግሞ በቢላዋ …

ኢትዮጵያ ልጆች አሏት። ለዛውም ጎንደርን ውስጡ ያደረገ …. ጎንደር ከዘመን ዘመን በጥቁር ዓይን የምትታይ የግለት ፋብሪካ ናት። የመገፋት ማሳ ናት። የብቸኝነት አንባ ናት። ጎንደር የሚሿት ለሥልጣን የሹም ሽር አቅርቦት ለጥሬ ዕቃ ብቻ ነው። ጎንደር መፈጠርም ግማድ ተሸክሞ መኖር ነው። እዛ መወለዴን ባልመካበትም ግን ስፍስፍ ያለ ፍቅር አለብኝ። መከራው ግን ያጎብጣል። የሚቻል አይደለም። ይህም ሆኖ ጎንደርዬን እወዳታለሁ፤ ከራሴም በላይ ከአርያሙ ሥላሴ በታች። ትበልጥብኛለች። እኩል እማያት እምዬዋን ኢትዮጵያን ብቻ ነው።

  • የዶር. አብይ አህመድ ፍልስፍናዊ መክሊት።


እርዕሰ ጉዳዩ … ተቋም ብቻ ሳይሆን አቧራ ያልነካው፤ ነፋስም ሽው ያላለበት፤ ያልነፈሰበት ሰማያዊ ፍልስፍና የአዲስ መክሊት ፈር ቀዳጅ ነው። እያንዳንዱ ሥንኝ ቃለ ምህዳን ነው። ቃለ ህይወት ያሰማልኝ ብዬማለሁ። ስለሆነም እነሆ ቃል በቃል ላቅርበው። መቼስ ወግ አይቀርም ወያኔ ሃርነት ትግራይ ሞቷዋን አውጆ ቁም ስቅሏን እያሳያት እኒያ ጠ/ሚር አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝም እረግጠዋት አላይሽም! ሃራም! ብለው የሄዱት ጎንደር „የከተሞች ቀን አክባሪ¡“ መባሏ - ይገርም ነው። ተዘውትሮ ማላጋጥ ነው ከነግጦሽ ሠፈር መቼም የሚደመጠው።

ጥረት መልካም ነው እና ውስጥ እንዳለን፤ የእኛ አብይ እንዳለን፤ የእኛ ጠበቃ እንዳለን፤ የእኛ ዋቢ እንዳለን፤ የ እኛ ንጹህ ተቆርቋሪ እንዳለን ነው በዚህ ቃለ ምህዳን ያዳመጥኩኝ። ልጅ ወልዳ በማይበርክትላት ጥቁር ለባሿ ጎንደር የላይኛው ሊያመሳጥርልን ይሆናል እንጂ አሁን ጎንደር ምኗ ይታያል? እንደ ማበሻ ጨርቅ ከተወረዎርች የተወረረች ምስኪን ምን ውበት? ምንስ ጠረን ኖሮ? „እግዚአብሄር በአንድ መንገድ በሌላም ይናገራል። ሰው ግን አያስተውለውም።“ ፈጣሪ ይህን ቃል ኪዳኑን ሊፈጽም ይሆናል። ይህን ምክንያት የፈጠረው

„ዶሩ በ2009 ዓ.ም ጎንደር በተከበረው „የከተሞች ቀን“ ላይ ያቀረቡት ክፍል ሦስት „ ይላል ርዕሱ።
ሐዋርያው ሐመራዊ ዶር. ጎንደሬ እንዲህ ይላሉ
  • ፍልስፍና አንድ፤


„የዛሬ 23 /24 ዓመት ገደማ አጋጣሚ እዚህ ጎንደር ነበርኩኝ። ይሄ ቦታ አዳራሽ አልነበረም። በጣም የሚገርማችሁ ጎንደር ኢትዮጵያ ሆቴል፣ ፎገራ ሆቴል፣ ጎሃና ቋራ የሚባሉ ትላልቅ ሆቴሎች ነበሩት። ገብያ ማዕከሉም በጊዜው ትንሽ ሞደርን የሚባል ነበር። በጊዜው ከዚህ ወደ ርዋንዳ ዘመትኩኝ። 

ያኔ ሩዋንዳ 1994 ግጭት ነበርና ስዘምት ኪጋሊ ገጠር ነበረች። ከጎንደር አንጻር። አይወዳደሩም። ኪጋሊና ጎንደር በፍጹም አይወዳደሩም። ግን ኪጋሊ ባለፉት 20 ዓመታት ፕሬዚዳንቷ ማህበረሰባዊ እንቅስቃሴ ያደርግ ነበር። ካጋሜ በወሩ መጨረሻ ቀን አካባቢ እንቅስቃሴ ያደርግ ነበር። በዬወሩ ህዝብ ጋር ወጥቶ ከተማ ያጸዳል። እሚገነባ ላይብራሪ ካለ አብሮ ይገነባል። እሚሠራ ሥራ ካለ ይሳተፋል። መሪው ይሄ ስለሆነ አሁን ኪጋሊና ጎንደር ሳይሆን ኪጋሊና አዲስ አበባን ልናወዳደር አንችልም።“

አዬ ዶር. ቅንዬ … የጎንደር መሪዎች ደግሞ አፈራቸውን እዬደለቁ ለባላ ጊዜዎች ይሸልማሉ። ህዝቡም ብስጭት እና ትካዜ ህይወቱ እንዲሆን ፈርደውበታል። አፈር ለጎንደር ማተቡ ነው ሃይማኖቱ። ኤርትራዊው አቶ በረከት ስምዖን ምጽዋን ሄዶ ማልማት ሲጋባቸው፤ ስደት ላይ የሚኳትነውን የኤርትራ ወጣቶችን ሊታደጉት ሲገባ ካልሥራቸው ገብተው ጎንደርን በበቀል ቀንበር እነሆ ያርሷታል። ጎንደርን ከሥሯ በትጋት ይነቅላሉ። መነጠሯት። 

ትውልዱንም ለእስር አቅርቦት በጨረታ ይገበያዩበታል። እንሆ ጎንደርን የጸረ ኢትዮጵያ የቁርሾ ማወራረጃ ጽዋ አድርገዋታል - አቶ በረከት። የጎንደርን ትውልዱን ባልተወለደ አንጀታቸው 26 ዓመት ሙሉ በትዕቢት ማጭድ ያሳጭዳሉ። በጢሱ ውስጥ እሳቸው አራሳቸው አቶ በረከት ስምዖን ይፈርሻሉ - በሐሴት ከነ ተጋሩ ጋራ። ሱሪውን ያወለቁት አቶ ገዱ በመኖር ውስጥ የከሰሙ፤ ልም ከንቱ ናቸው።

 ህሊናቸውም ኮረኮንች የበቀለበት - ጠፍ ነው። ለፈጠራ የተዘጋ የአሽዋ የግብይት ማዕከል። በዚህ ውስጥ የእርስዎ ይህ የቀደመ ሥልጡን ንጡህ አምክንዮ እንዴት ተብሎ? የመስቀያ ገመድ ለተሰናዳለት ጎንደር … እህ … አያፍሩምና አቶ በረከት የኢትዮጵያ ህዝብ በልጆቹ እዬተማራ ነው ይላሉ። ጎንደር የምትመራው በሳቸው በኤርትራዊው መሆኑ፤ አማራም የሚማቅቀው በሳቸው በኤርትራዊው ስለመሆኑ ዓይናቸውን በጥሬጨው አሽተው ይደናበራሉ። በጋለ በሞፈርና ቀንበር ቀፍድደው በማረሻ በጥንድ አስጠምደው ሰውን እንደ ከብት እያረሱ ….
  • ፍልስፍና ሁለት፤


„ለምሳሌ ይህን ፕሮግራም ያዘጋጃችሁ ሰዎች የፕሮግራሙ መጨረሻ አንድ ቀን ሲቀረው ሁሉም ታዳሚ ዶር. አንባቸውን ጨምሮ ጥዋት 12.00 ሰዓት ተንስቶ ጎንደርን ሳያጸዳ ከሄደ መጥቶ ገንዘብ አፍስሶ ሊሆን ይቻላል፤ ድግስ ደግሶ ሊሆን ይችላል፤ ግን አንድ ነገር አስተምሮ አልሄደም ማለት ነው።“

ይህም ቢሆን የማከብረዎት በምን የመንፈስ አቅም። በምን ጉልበት። ማን ኑሯት ጎንደር። ጎንደር እኮ መጠጊያ አልቦሽ ናት።ማመዛዘን የሚችል ህሊና ሲኖር፤ ኩርኩሙ ተግ ሲል። ከባርነቱ ነፃ ሲወጣ …. ቁልጭ ያለ የአፓርታይድ ሥርዓት እኮ ነው ጎንደር ላይ ያለው። ስቃይም አለው አይነት። መጨቆንም አለው አይነት፤ መተርተርም አለው ዓይነት፤ ምን ደንበር አለውና የመከራው ዳጥ እና ጭቃ … ሞቷን እንኳን የሚዘግብ፤ ተጋድሎዋን ደፍሮ የሚናገር ሁነኛ ጎንደር የላትም። ስለምን? በዬትኛውም ወገን የጎንደር ገድል ተቀብሮ ግን የሌላ አቅም ሆኖ እንዲታይ ነው የሚፈለገው። ይህ ከሃቅ በላይ ሌላ ሃቅን ሊገልጽ የሚችል ቃል ቢገኝለት መልካም በሆነ። ግን መዝገበ ቃላት የጎንደርን የዙር ህማማት መግለጥ የሚችል ተርጓሚ ሥነ - ቃል አልፈጠረም። 
  • ፍልስፍና ሦስት


„የጎንደር ዩንበርስቲ 50,000/45,000 ሺህ ማህበረሰብ አለው። በወር አንድ ቀን አንድ እሁድ ጥዋት ለአንድ ሰዓት ለሁለት ሰዓት ተከፋፍሎ ጎንደርን ማጽዳት“
ይህማ እናትዬ ንጹህ ፍልስፍና ነው። እንዲህ ለማሰብ የውስጥ ሰላም፤ መረጋጋት፤ እራስን በራስ ለማስተዳደር ከላይ የእኔ የሚሉት ሰው ሲኖር ነው። ፊቱም - ጎኑም - ኋላውም - በዓራቱ ማዕዘን በውጋት በጥድፊያ፤ በስጋት ተሰቅዞ ያለ አዕምሮ የመፍጠር አቅሙ ከውስጡ የተበላ ነው የሚሆነው። … 

ትውልዱ ጎብጦ ተሰቅዞ ነው ያለው። … ቢጀምሩትም እንጃ … ግራ ቀኝ ማሰጠንቀቂያው ያጣድፋቸዋል። ዳኞቹ ደግሞ ጎንደር የሚኖረው ተጋሩ እራሱ ነው። ዘመቻው ጎንደር ከነበረች ወደ አልነበረችም ለመደምሰስ ነው። ጥፍት እንድትል። ኢትዮጵያ ከመፍረሷ በፊት የጀርባ አጥንቷ ጎንደር ትቢያ መልበሰ አለባት። ድንጋይ መንተራስ አለባት። የነፃነት ታጋይ የሚባለው ያአልገባውም ቅኔ ይሄው ነው። ቢያንስ ህዝቡ ማህበራዊ ንቃተ ህሊናው ቀድሞ ለሚያደርገው የነፃነት ተጋድሎ እንኳን ክብሩ ቀርቶበት የታሪክ ቅሜያው እና ሽሚያው ቢቀርለት በማን ዕድሉ። ውስጡን የሸለማት ከእርሶዎ በስተቀር አንድስም እንኳን የፖለቲካ ሊሂቅ የለም።  
  • ፍልስፍና አራት 


 „ሃምሳ ሺው ሁለት ሁለት/ ሦስት ሦስት ዛፍ መትከል ቢለምድ“ ብዙ ገንዘብ የማይመለስው ሥራ ይሠራል። ሥራም ብቻም አይደለም፤ ሰው ጎንደርን ይወዳል፤ ጎንደርም ዩንቨርስቲውን ይወዳል፤ ተቋሙ ትርፍ ይሆናል ማለት ነው“
ቢሆንማ ነበር። አሁን እኮ ኢትዮጵያዊ የሆነ በቡድን ወደ ጎንደር ለመዝናናት የህዝቡን የመከፋት ዓይን ለማዬት እኮ በፍጹም ሁኔታ ሄዶ አያውቅም። 

ለጎንደር ሁሉም ዕድል ድንቡልቡል ነው። ቅርሶቿም ተዘርፈዋል። የቀረው እኮ የፋሲል ህንፃው ብቻ ነው። ያም የማይጫን ሆኖ። በረጅም ጊዜም የታቀደው ለመጠቅለል ነው። በዛ ላይ ጭንቅ ላይ ናት፤ ሰላሟ በእጅጉ ታውኳል። ምን ሊይ? ምን ሐሤት ሊሸምት ኢትዮጵያዊው ቱሪስት ወደ ጎንደር ይሄዳል? የመስቀል ደመራ ሁሉ ቦታ ሲዘገብ ጎንደር ላይ ግን ያዩት ነው። መሽቶ እስኪነጋ በባሩድ የምትቀጠቀጥ ሶሪያ እኮ ናት ጎንደር። ሚዲያም የማይዞርባት። በመረሳት ውስጥ ትቢያ ለብሳ፤ አፈር ጎዝጉዛ ክስመትን ጠባቂ … የኤሎሄ ቤተኛ። በረከት የሚባል መጋኛ አራጅ የበቀለባት።
  • ፍልስፍና አምስት


„በዛ መንገድ የተመረቀ (graduated) ያደረገው ሰው ደግሞ ITW ብቻ ሳይሆን ስሜታዊ የማሰብ ችሎታ (Emotional Intelligence) ያለው ይሆናል። ማገልገል የገባው ይሆናል።“
ትክክል ነው። ግን ጎንደር መወለድ በራሱ ውሃ ያዘለ ተራራ ተሸክሞ መኖር ነው … የትም ቦታ ታዳኙ የጎንደር ልጅ ነው። ግለቱ ከ - እስከ የለውም። ቦታ ያላቸው ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት እዛው ጎንደር ውስጥ እነ ተጋሩ ናቸው - ባለጊዜዎች። አራጊም ፈጣሪም። አዛዥም ናዛዥም። ፈጻሚም አስፈጻሚም። በጋብቻ የታሠረው የተሻለ ዕድል ሊኖረው ይችል ይሆናል። ይህም ? ሥር ነው። በሚቻልበት ሐገር መገፋቱን እና መገለሉን ችለን መኖር አልቻልንም። ኑሮ ለጎንደሮች የትም ቦታ፤ በዬትም ሁኔታ ጋዳ ነው። የፈተና ክምር በዝቀሽ መንሹ አልቦሽ በፍግመት የደራበት።
  • ፍልስፍና ስድስት።


„ለምሳሌ የዚህ ከተማ ከንቲባ (Mayor) በዚህ ዓመት ሥራ ሲቀጥር አንዱ ክራይተሪያ መሆን የሚገባው ሳትቀጠር በነጻ ስንት ጊዜ ከተማን  አጽድተሃል የሚል ሰርትፊኬት ያስፈልግዋል።“

መቼም ይህን ሃሳብ ሲያፈልቁት እንዴት ውስጠዎት ቁስል እንዳለ ነው የሚሰማኝ። ጎንደርን ከ22/23 ዓመት በኋዋላ ሲያዮዋት ጉስቁልናዋ ውስጠዎትን ዘልቆታል። መከፋቷ አንጀተዎትን በልቶታል። እንኳንም አዮዋት። ይህም በመሆኑ ከጎንደር በላይ ቆስለዋል። አዎን ጎንደር የተጠቀጠቀች ከተማ ብትሆንም ቢያንስ በእጅ ባለ አቅም ቢሞከር … መልካም በሆነ። ግን ያው እሱ በእሱ ነው። አቶ በረከት ከዛ የአጋዚ ጉባኤ ጎንደር ላይ በተካሄደው „ሰለ ከዬት መጣህ መባል ሹመኛ“ ደስኩረዋል። 

አዎን የአማራ ግማዱም ይህ ነው። ሽመኞቹ ያልተወለዱት በመሆናቸው ነው እያሳረዱት ያለው። ማን አድርሷቸው … ባለ ርስቶችን … ተወላጆችን። አማራ „ክልል{ ተለይቶ ህብረ ብሄራዊ መልክ ይኑረው፤ አማራው እንደ አማራ ከሁሉም መንፈስ ተገሎ እዬሞተ በውስጡ ሬሳውን ይተቀፍ ነው ብሂሉ። የአንተ ነው ተብሎ በተከለለው የእኔ የሚለው የሥልጣን ተዋረድ ሊኖረው አይገባም። ልጆቹ ሥጋጃ አንጣፊነት ብቻ ሊሆን ይገባቸዋል። መወከል ያለበት ሃሳቡ እንጂ የአማራ ልጅ መሆን የለበትም። በሌላውም „ክልል“ ደግሞ ቀንበር ከመሸከም ውጪ የክልል ውክልና አይገባውም። አድማጭም ፍትህም ርትህም ሰማይ ቤት ይጠብቅ። ይሄ ነው የ26 ዓመቱ የ አማራ ልጅ ዕጣ ፈንታ። 
  • ፍልስፍና ሰባት።


„በነፃ ያለገለገል ሰው ብትከፍለውም አያገለግልህም። ይህ ሰው  (this guy's) ሥራ ፈት/አጥ ዓይነት (Unemployed) ነው የሚሆነው። የተቀጠረ ግን የማይስራ ነው የሚሆነው። የማከብረዎት ዶር. አብይ ይህ ነባቢት የሆነ ፍልስፍና ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ ተወልዶ የማያውቅ ልዩ ፈጠራ። መንፈሱ እራሱ አዲስ የሥራ አብዮትን አቀንቃኝ የለውጥ ነብይ ነው። እራሱ ይህ በነፃ የማገልገል መንፈስ „ ©የአብይ መንፈስ“ ተብሎም ሊሰዬም ይገባል። 

እነ አጅሪ እነ ተጋሩ ይህን ፍልስፍና ቀብ አድርገው እንደራሳቸው የፈጠራ ሀብት አድርገው ካለ © ይሄኔ ጀምረውበት ይሆናል። ለዚህ ያበቃቸው እኮ ተዝቆ የማያልቀው የቅን ኢትዮጵያዊ ጭማቂ የእውቀት ግብዐት ነው። እንሱንማ እናውቃቸዋለን …  በዓይነ ምድራቸው „ማሌሊት ያሸንፋል“ ብለው ይጽፉ የነበሩ ናቸው። እኔ ራሴ በዓይኔ በብሌኗ ያዬሁት ነው ደባርቅ አካባቢ እና በዳባት ዙሪያ ላይ። ልብስ አይሸፍነው የለ ሆኖ በገበርዲን ተለብጠው ነው እንጂ ጫካና ግንዛቤው … 26 ዓመት እንዲህ ተኮፈሰ … ሰው አጥታ ኢትዮጵያ - ሁነኛ።
  • ፍልስፍና ስምንት።


 „ሰው በነፃ ማገልገል ሲማር ነው ሲከፈለው የበለጠ የሚያገለግለው። እኛ ጋ ስተወስዱ እብዛኛው ሰው ቢሮ ይገባል። ጃኬት ያንጠለጥላል እንዳለ ይታሰባል። አቶ እከሌ ስትሉት „አሁን ወጣ“ ይባላል። 11.00 ሰዓት ላይ ጃኬት የለም። ይህ ሰው (this guy's) የአገር ኢኮኖሚ የሚገድል ነው።“

ዶር. አብይ አህመድ ይህ ታላቅ የሥራና እና የሠራተኛ ዓዋጅ ነው። የሥራ ባህል የቅድመ መሰናዶ ተቋም ነው። ብሩህ ፖሊሲም ነው። አዲስ መንገድም ነው። የሚናፈቅ። አቅም ካለተዕቅቦ ሊለገሰው የሚገባ። ሙሉ ፍቅር እና እቅፍ ከምስጋና ጋር የሚገበው። ይገርማል። መሪ እንዲህ ይገለጻል። አዲስ መንገድ ጠራጊ ሃሳብ ይዞ የሚነሳ … ሊደመጥ፤ ውስጥ ሊሆን የሚችል እጅግ ጉልበታም የአምክንዮ አቅም። አመሰግነዎታለሁ እጅግም አድርጌ።

ይህን የመሰለ የቀደመና የሚመስጥ ምልከታ ሳደምጥ የመጀሪዬ ነው ማለት እችላለሁ እኔ በግሌ። እምሰማው ያው የተለመደው „ዴሞክራሲ ሥርዓት፤ ለሁሉም እኩል የሆነች ኢትዮጵያ“ እንዴት? ለሚለው አምክንዮ ግን ፍሬ አልቦሽ አሰልቺ ትርክት ብቻ። ችግሮችን ከመሠረቱ አጥንቶ ለመፍትሄዎች የቀደመ ከውስጥ የሚገባ ፍሬ ጋዳ ነበር። አሁን ተመስገን ነው። ለናሙና በተወሰደችው ጎንደር እጅግ አትኩሮት ለተነፈጋቸው ከትግረይ ውጪ ላሉት ከተሞች እንደ ድሬድዋ፤ እንደ ጅማ፤ ደብረታቦር፤ አንቦ፤ ሮቤ ላሉት ሁሉ የመንፈስ ማረፊያ አግኝቷል። 

ይህ  እያንዳንዷ ፍሬ ቃል ለቅኖች፤ ህሊናቸው በሴራ ፖለቲካ ደጅ ለማይጠና ዜጋ ልዩ ተቋም ነው። የምርምር ማዕከል ነው። የአዲስ የፈጠራ የአመራር ጥበብ ልቅና ነው። ውስጥን ከውስጥ አድርጎ የነተነሳ ብሩኽ መንገድ ነው። ቅኔ ነው። ስዋሰውም ነው። መንገዳችን በዚህ መልክ እንዲቀዬስ የምንፈቅድ ቅን ዜጎች በሌሎች ነገሮች የምናጠፋውን መስተጓጎል ገታ አድርጎ ይህ ንድፍ ወደ ተግባር ይሸጋገር ዘንድ አቅሙን ለአቅም ብቻ በመለገስ አቅማችን እንደ አባይ ወንዝ በከንቱ እንዳይፈስ በአቅም አስተዳደር ጥበብን ልንቃኝበት ይገባል

አቅምን ማስተዳደር የሚቻልብት አዲስ ነፃ የሆነ፤ በማንፌስቶ በሽታ ያልጋ ቁራኛ ያልሆነ መርሃግብር መንደፍ ያስፈልጋል። አቅምን አክብሮ፤ አቻችሎ የሚተለም ፓሊሲ። ልብ ያለው ከልባችን ቦታ ነው። ህሊናችንም ያለው ከህሊናችን ቦታ ነው። ዓይናችንም ከተሰጠው ርስተ ጉልት ላይ ነው ያለው። 

ይህን ጸጋችን ቀና በሆኑ፤ ትውልድን ሊገነቡ፤ ነገን ሊያስቀጥሉ በሚችሉት ጉዳዮች ላይ አትኩሮታቸው እንዲከትም መፍቀድ ያስፈልጋል። የአቅም ሲናርዮ፤ የመንፈስ አቅም ንድፍም ያስፈልጋል። ይህን ቅናዊ መንገድ የእኛ ስለእኛ ልንለው ይገባል። 

ትውልዱ እውር ድንብሱን ሲሄድ የኖረበትን ግርዶሽ የገፈፈ ነው። ይህ ሁለአቀፍ አዳኝ ፍልስፍና 2 ደቂቃ ከ54 ሰከንድ ነበር ቆይታው። ሶስት ደቂቃም አልሞላውም። ድረሰት ስናዳምጥ ለቆዬን ሁሉ የብሥራት ቀን ነው። ትውልዱ እንዲህ ሉ መሳጭ፤ ልቅም ባሉ ብቃቶች እና ተስፋን አቀንቃኝ ራዕዮች፤ ፍልስፍናዎች ላይ ነው አቅሙን ማፈሰስ የሚገባው። በማዳህኒቱ ላይ፤ በመፍቻው ላይ፤ በፍቱኑ ላይ ነው አትኩሮቱን በቅንነት መለገስ የሚኖርበት።
  • ፍቱኑ።


እነኝህን ስንኞች የውስጣችን፤ የእኛ ፍላጎት፤ የእኛ ራዕይ፤ የእኛ የማህለኛው ስሜታችን ማይክሮስኮፕ አድርገን ልንቀበላቸው ይገባል። ይህን የማሳስበው አሁንም ለቅኖች ብቻ ነው። ቅንነት መንገድ ነው። መንገዱ ወጣ ገብ ቢሆንም ከቅናዊ ዕሳቤዎች ጋር በተክሊል ለመቁረብ ግን በእጅ ያለ የመወሰን የአቅም ፍቱን ክህሎት ስለሆነ ማድረግ ይቻላል። መሆን በመሆን ውስጥ ነው በፍቱንነት እሚተረጎመው። መሆን በመቀበል ውስጥ ይኖራል። መሆን በመፍቀድ ውስጥ ይጸድቃል። መሆን በቅንነት ውስጥ ይበቅላል። ኑሮን ለማኖር ቅንነትን በመኖር ውስጥ መፍቀድ ያስፈልጋል። 

እርግጥ ነው አፍ ባለው መቃብር ውስጥ ባለችው ጎንደር ውስጥ መተንፈስም ሲደላ ነው። የተቻለው ያህል መሬት በተጋሩ ተወሯል ልታድግበት - ልትለማበት - እንደ ሌላው እኩል ልትሆንበት የምትችላው አንጡራ የገንዘብ ሰብሎች (Cash Crops) ለም መሬቷን ጎንደር በግፍ እና በሃይል ተቀምታለች። የቀረው ኩርማንም በሶስት ተሸንሽኖ ለግዳጅ ዝግጁ ሆኗል ምጥ ላይ ነው ያለው፤ የተያዘ የተረዘዘው ሁሉ ቀን ከሌት እዬተጫነ ህዝቡ በድህነት ተወሯል፤ ኑሮ ጎንደር ላይ ከማህል በከፋ ሁኔታ ውድ ነው። አፈር ሳይቀር ሌሊት ጉዞ ወደ ታላቋ ተንዳላቃቂ በርሃናማዋ ትግራይ ሆኗል። 

ይህም አንሶ እሳት በቤንዚን ለታዘዘላት ጎንደር ይህ ዝልቅ ብቁል ቅንነት የማይሠራ ነው የሚሆነው። ልጅ የላትም። ተቆርቋሪ የላትም። ጥቃቷን የሚያወጣ አንድስም እንኳን የላትም። ኢትዮጵያን የጠላት ሁሉ ክንዱ የሚያርፈው ጎንደር ላይ ነውና። ኮሶ ተጥታ መሻር አልቻለችም ጎንደር። 40 ዓመት አርግዛ መገላገል ያልቻለች ናት ጎንደር። ጽንሱ በሆዷ ውስጥ አጥንት ሆኖ ይነስታታል። ያሰቃያታል። ይጠዘጥዛታል። በዕንባ አውሎ የምትገረፍ … መከረኛ ናት ጎንደር።   
  • ጎንደር እና ጥቁር ዕጣዋ።


የጎንደር ኑሮ መከራ የተከዘነበት ነው። ስለምን? ለሚለው አቀማመጧ ምሽግ ስለሆነ። ህዝቧ ደግሞ ዜግነቱ ደግንት ስለሆነ። ማንነቱ ደግሞ ፈርሃ እግዚአብሄር በመሆኑ። ይኸው ጸጋው ጠቅሟታል ወይ ቢባል ጎንደር እንደ እኛ ሰውነት ኩነኔና ጽድቅ ስላልተሠራላት የምትጠብቀው የገነት ህልም የላትም - ጎንደር። 

ኑሯዋ ምድራዊ ብቻ ስለሆነ ንጹህ ተፈጥሯዋ ጎድሏታል። እንደ ሰው ሰማያዊውን ሐገር የምትናፍቅ ቢሆን ግን ጎንደር በእዮር አደባባይ የጎንደር ጽላት ይቀረጽላት በነበረ። የተግባር እምቤት ናትና።

የመጣው ገዢ ሁሉ በዙር የሚቀጠቅጣት መከረኛዋ፤ የዕንባ ጓደኛዋ ጎንደር ከዛሬ 22/23/24/ አመት ጋር እንኳን ሊነጻጻር የሚችል ምንም የሌላት ምንም ሆናለች። የእኛ ዶር. አብይ አህመድ ውስጣቸው የጤሰበትን አምክንዮ ሲገልጡ ጢሱ ሲትጎለጎል የሚታዬውም ከዚህ ዕውነት ነው። 

የእኛ ዶር. አብይ አህመድ በዕውነት ውስጥ የበለጸገው የዕእምሮ ልቅናቸው ነፍሳቸውን እናይ ዘንድ ይለፍ አስገኝቷል። እሳቸው ያዩት በዛ ዘመን ዘመናዊ የነበረው ገብያ ዛሬ አመድ ለብሷል። በግፍ የእሳት እራት ሆኗል። በቤንዚን ነዷል። ከተማዋ በድቀት መክኗል። ተስፋዋ በተስፋአልባነት ተገንዟል - ዝጓልም። ልጆቿ 40 ዓመት ሙሉ በስጋት፤ በጭንቅ፤ በመረሸን፤ በአካል ጉዳተኝነት የታደሉ ናቸው። ሽልማታቸው ይሄው ነው። 

ኢትዮጵያን በማዳኑ በኩልም እንደ ሌላው ወገናቸው የደም ግብር ከፍለዋል በሁሉም የጦር ግንባር የተመሰከረላቸው ጀግኖች ናቸው። ግን ጎንደር ዛሬም ጨለማ፤ ነገም ጨለማ፤ ተነገወዲያም። ጎንደር ላይ በህብረት አሳሮች የዕንባ ኦርኬስተር አቋቁመው በዋይታ እዬተራጩ ይዘምራሉ፤ ጨለማዎቹ በወልዮሽ ይዳንሳሉ ግጥግጡንም ያስነኩታል በጭጋግ ተውጠው።

  • እኔን ይብላኝ ቅዳሜ ገብያ፤


ዶር. አብይ አህመድ እንዳሉት ዘመናዊነት ይታይበት በነበረው የገብያ ማዕከልም /ቅዳሜ ገብያ/ ያን ተጥልለው ኑሯቸውን ይገፉ የነበሩት ነፍሳትም መንገድ አዳሪ ሆነዋል። ለዛውም ጎዳና ማደሩም ከተፈቀደላቸው። ይህም ለግዞተኛው ጎንደሬ የቅንጦት ነው። ከውስጥ የመገለውን ህዝብ ብሶት ባሻጋሪ ደልቶት ከሚኖር አንድ ተወልጄ ጋር አጣምሮ ለችግርህ መድህንህ እኛ ጉና ላይ አብረንህ ተቀብረናል ማለት በውነቱ ዘመናይነት ነው። ቅልጣንም ነው። ያ ተጠቃሹ እና ተወቃሹ ተወላጅም በነፍስወከፍ ለደረሰው ሰቆቃ የህዝብን የመከራ ተጋድሎ ለማቀጣጠል ሆነ ለመመራት የጭብጡ አናት አይመጣጠንም። ጎንደር እራሱ መከራውን እዬኖረበት ነው። 

በሞቱ ውስጥ አፈር ያልቀመሰ ሬሳ ተሸክሞ እዬኖረ ነው። ሥጋው ሲቆረስ በተቆረሰው ሰቀቀን ውስጥ እሱ መሬት ላይ አለ። ለስቃዩ ባለቤት እሱ ራሱ ነው። ለመከራው፤ ለፍዳው ቀስቃሽ ፕሮፖጋንዲስት ወይንም የዬትኛውም ድርጅት ማንፌስቶ ይሁን ሚዲያ አያሻውም። ፓርቲው ዕንባው ነው። ማንፌስቶውም ዕንባው ነው። 

መከፋት ከውስጥ እንጂ ከውጪ በአዋጅ አይሆንም። ሊሆንም አይችልም። ይልቅ መከራው በማያበራበት ሁኔታ ላይ ለከዘነው ህዝብ የእነ ማህበረ ሳዖል ማላገጡ ቢቆም እሱ ነው የሚሻለው። „ጽድቁ ቀርቶበት በወጉ በኮነነኝ።“ አንዲት የትግራይ ሴት የወርቁ የጨርቁ ጥጋቡ በማን ላይ እንደሆነ ማስተዋል ጎድሎባቸው ሲነደቀደቁ ተመልክቻለሁ በጠመንጃው ጉባኤ ላይ። እግዚአብሄር ይታዘባል ብሎ ማሰብ ይገባ ነበር። እንደዛ በመስቃ የተንቆጠቆጠ ዲስኩር ከማነብነብ … 

የሆነ ሆኖ የጎንደር ምንዱባን ሌሊት ሌሊት መታረዱ፤ መታፈኑ፤ መደፈሩ፤ ከቀረላቸውም መልካም ነው። ግን ጎዳና ሲወጡ ሌላ ጉራንጉር የህይወት ገጠመኝ ደግሞ ስላለ ወደ ገደል የተወረወሩ ፍጡራን ናቸው። ባሊህ ባይ ያጡ። ገብያ የህዝብ የመረጃ ማዕከል ነው። ገብያ የኑሮ ማዕከል ነው። 

ገብያ የባህል ማዕከል ነው። ገብያ ጉሮሮም ነው እህል ውሃ። ገብያ ጋዜጣም ነው። የሚነበብ የሚጻፍም። ዓለም እራሷ ገብያ ናት። አያድርገውና ዓለም ብትቃጣል የዓለም ዜጋ ምን ይሆናል? በጎንደር ቅዳሜ ገብያ በመቃጠል ውስጥ ትዕቢተኛው ተጋሩ እስከ ልቡ በረከት ስሞዖን ድረስ አትረፈውበታል። የበቀል ጽዋቸውን ለጤናችን ተባብለውበታል። ተጋሩ በሚቆጣጠረው ሚዲያም ደምቆላቸዋል። 

ሥነ - ልቦናም እንኩት እንዲል የተመከረበት ስለነበር። እግዚአብሄር ግን ከአመድ ትርፍ እንደሌላው ስለሚያውቅ ከሰው በላይ ያዝናል። በአምሳሉ የፈጠራቸው የፈረሃ እግዚአብሄር ባለሟሎች ደግሞ እንዲህ ከውስጣቸው ዕንባውን ያደርጉታል። መቼስ ዶር. አብይ አህምድ ለእርሰዎ ምስጋና ሲያንስ ነው። የደጋጎች አምላክ ይጠብቅዎት። 

ቤተሰበዎትን ፈጣሪ አማላክ ይባርክ - ይቀድስ። ከጥቃቱ ሁሉ ድንግል ትጠብቀዎት። እንደ ጎጃም የአማራ ህዝብ ለጎንደር በመከራዋ፤ በሀዘኗ ውስጥ ፈቅደው ስለከተሙ ፈጣሪም ውለታዎትን ይከፍለዎታል ብዬ አስባለሁ። ይህም እኮ መመረቅ ነው። ከርጉማን ያልቀላቀለዎት አምላክም የተመሰገነ ይሁን። አሜን! ችግሯን አዬት … ውስጠዎት አደረጉት። ጥቃቷነን የእኔ የእኛ አሉት። አዎን አብይ ኬኛ!

ቅዳሜ ገብያ በአቶ አባይ ወልዱ በተደራጁ ወሮበላዎች የታሪክ ቅስም ሰባሪዎች፤ የትውልድ እርግማኖች፤ በአቶ በርከት ስምኦን ትብብር በቤንዚን ሲነድ ያለቀስኩትን ዕንባ ያህል መቼም አልቅሼ አላውቅም ነበር። የዕንባዬ ገደብ አልነበረውም። መከፋቴም መጠን አልነበረውም። ቅርስ ነበር። ፋሲል ግንብ የተቃጠለ ያህል ነበር የተሰማኝ።

 አሁንም እኔ ስጋት አለኝ። የበታችነት የሚሰማው ፍጡር እንደ እንሰሳ ነው የሚያስብው። ከሰብዕና የወጣ አውሬ ነው የሚሆነው። ማናቸውም ነገር ፈልሶ፤ ወድሞ ማዬት ነው ህልሙ። ምክንያቱም የሥነ - ልቦና አቅሙ ስልብ ስለሆነ። በሌላ በኩል የጎንደር ሞት አቶ በረከት ስሞዖን ሲፈጥርባት ነው። በረከት እያለ አንድስም እንኳን የጎንደር ልጅ፤ አንድስም እንኳን የጎንደር አዲስ ቀን በፍጹም ሁኔታ አይመጣም። ለሞቷ ነው ጎንደር እሱን እሹኽ ያበቀለችው። በትውስት ማንነት ታመሰች ጎንደር ….

  • ስለምን ጎንደር የቁርሾ መጋገሪያ ሆነች በእንቡጢጣ


1.      የመጀመሪያው የኢትዮጵያ የመንግሥት ቅርጽ መሠረትነት በንጉሦች ንጉሥ በዓጤ ቴወድሮስ የቀደመ፤ ሥልጡን አቮል ዕሳቤ ጎንደር ስለተባረከች። ከጥበብ በላይ ልቅና ነበርው ይህ „ኢትዮጵያን አንድ የማድረግ ህልም“ መንፈስ … ዛሬም ኢትዮጵያን ሊያጠፉ የሚንደፋደፉ ሁሉ የበቀሉን በትር የሚያሳርፉት ጎንደር ላይ በደቦ ነው።

2.       የመጀመሪያው ባለ ራዕይ መሪ ድንቁ የጥበብ ፍልቅ ሩህሩሁ ዓጼ ፋሲል በዬጊዜው ሲባክን የነበረውን፤ ማዕከል ያልነበረውን መንግሥታዊ አስተዳደር ማዕከላዊ የንጉሦች ሥርዓተ - ህግጋት መሥራችነት በብልጹግ ቤተ መንግሥታዊ ጥበብ ጎንደር ላይ ስላዋቀሩት ነው። ይህ የጥቁሮች የመጀመሪያው ቤተ መንግሥት ቋሚ ቦታ ሳይኖረው ከታች ከላይ ይል የነበረውን መንፈስ ከሰለጠነው ዓለም ጋር የተስተካከለ፤ ተወዳዳሪ የሆነ ቤተ መንግሥት መሠረት መሆኑ ጎንደርን ለጥቃት ዓይነ ገብ እንድትሆን አድርጓታል። ቅርሱ የዓለም ሀበት መሆኑ፤ እንዲሁም የመጀመሪያው ጥራቱን፤ ደረጃውን የጠበቀ የመጀመሪያው አፍሪካዊ የጥቁሮች ቤተ መንግሥት መሆኑ፤ አፍሪካም በዚህ ውስጥ ጥቁሮችም በዚህ ውስጥ በጥበብ ተስተጋብረዋል።

3.       የነገሥታቱ፤ የልዑላኑ መሠረት መሆን። ህብራዊነት በተለይም ከኦሮሞ ማህበረስብ ጋር ያለው ጥልቅ ሥነ - ጥበባዊ የእትብት ደማማዊ ስህን ልቅና። ከስንት ዘመን ጠገብ የፍትጊያ ጉዞ በኋላ አሁን ላይ ያለው የመተሳሰር „የኦሮሞ ደም ደሜ ነው። በቀለ ገርባ መሪዬ ነው።“ ዳግም ልደቱ የነበረውን የዝምታ ወይንም የድምጽ ተዕቅቦውን ጥሶ መውጣቱ ልዩ ብሥራት መሆኑ። ጎንደርን ለሌላ የሳላ እጥፍ ድርብ ጥቃት አጋልጧታል። የቅማንት ጉዳይ/ እንደገና እንድተሸነሸን ሊኳንዳ ቤት መከፈቱ፤ ጎጃምና ጎንደር ላይ የፈሰሰው የነጹሓን ደም እና ሃያ ሺህ ወጣቶች በአንድ ወር ውስጥ መታሰር ብቻ ሳይሆን ሌሊት ሌሊት በገፍ የነበረው ቀበር ሁሉ ምንጩ 16/17ኛው መቶ ክ/ዘመን ታሪካዊ ትውፊት የሁለቱ  የዓጸፄዎች ህዝቦች በፍቀራዊነት መስህብ ትንሳዔው በመታወጁ ነው።
4.     የጎንደር ቅርስ ዲታነት ከመሬት በላይ ብቻ ሳይሆን በታችም አንቱነቱ።

5.     ከዚህ መሠረታዊ የሆነ የሥልጣኔ አርክቦት ጋር የህዝቡ ህሊና ወይንም ሥነ - ልቦና በብቃትና በብልህነት የመገንባቱ ውርርስ ትውፊታዊ ዕሴት መሳጭነቱ፤ መሬት ያዬዘ አቅም የመሆን ብልሃቱ፤ ይህን በዚህ ዘመን እንኳን የአማራ ተጋድሎ ወላዱ የጎንደር የማንነት አብዮት ሀገራዊ ምልከታው ልቅናውን በውል ፏ ብሎ እንዲታይ አድርጎታል - በ ዓለም አደባባይ። ለዚህ ነው ባልተለመደ ሁኔታ የተጋሩ ቱባዎች ጎንደር ላይ ከነ አጋዚያቸው ሰሞኑን የከተሙት።

6.     ለምሽግ የሆነ ቦታ ብቻ ሳይሆን ምሽጉን ምሽግ ሊያአደርግ የሚችል የመንፈስ ሃብታትም ጥሪት ባለቤትነት ብልጹግ መሆኑ። የግንባር ሥጋነት ባለሟልነትን አክሎ።

7.       የማህበረሰቡ አፈጣጠር ህብራዊነት፤ የቀለሙ ጥልቀትና መስተዋድዳዊ መስተጋብሩ ጽናታዊ ህላዊነት ቅቡል መሆኑ።
8.       የአብሮነት መንፈሱ ትውልድ አሻጋሪነቱ ልዩ አንጸባራቂ ዘመን ጠገብ መሆኑ።
ከነዚህ መሠራተዊ፣ ማራኪና ሳቢ፤ አልፋና ኦሜጋ ዕውነታዎች ስንነሳ ጎንደር የውስጥ ሰላሟ ብቻ ሳይሆን ዳር ድንበሯም ጥሰት እንዲኖረው ተደርጋለች። ቀና ብለው የሚወጡ ልጆቿም እዬተነጠሉ፤ እዬተለቀሙ የቁርሾ ሰለባ በገፍ ሆነዋል - እዬሆኑም ነው።
ጎንደር እና ቅንነቷ፤ ኪሳራዋ እና ጨለማዋ።
ቀደም ብዬ እንደ ገለጽኩት ምሽግነቷ፤ ብልህነቷ በዬጊዜው ሰዎች ገዢዎች አልተመቹንም ሲሉ የሚመጡት ወደ ጎንደር ነው። ሽዌው በሽዋ አይመሽግም፤ ወይንም የጋሞ ሰው ጋሞ ጫካ ላይ አይመሽግም። 

የሚተመው ሁሉም ወደ ጎንደር ነው። ጎንደር የከፋቸውን ሁሉ በቅንነት ባሰጠጋችው ልክ ተቀናቃኙ ሥልጣን ላይ የሚኖረው ዬዬወቅቱ ገዢ መደብ ደግሞ ባልወለደ አንጀቱ በፋስ አናት አናቷን ይቀጠቅጣታል። ጎንደሬ የተባለው ሁሉ በጥርጣሬ መታዬት ብቻ ሳይሆን፤ በተለያዬ ሁኔታ እንዲሰዋ ይደረጋል። ይህን ጥሶ የወጣ ነፃነት ያገኘ ባለሙሉ ዜግነት የተሰጠው፤ በክፉ ዓይን በጥርጣሬ የማይታይ የህሊና አቅም ለማግኘት ይቸግራል። ከሥሩ ነው ጎንደሬ በዬደረሰበት የሚነቀለው።

አሁን ኢህአፓ፤ ኢዲዩ፤ ወያኔ ሃርነት ትግራይ፤ ሻብያ ከተማ ውስጥ ብዙ አባሎች ነበሩት፤ የከተሙት ጎንደር ላይ ነበር። የትውልድ እልቀቱን ያወራረደው የጎንደር ማህጸንና አብራክ ነበር። ቀይ ሽብሩ ሆነ ነጭ ሽብሩ የሞት ግጥግጣቸው ጎንደር ላይ ነበር። የጎንደር ሰው ኢዲዩን ለማጥቃት የሚመጣውን ድርጅት ተቋቁሞ ያን ሰው ደብቆ አደራ ያወጣል። ኢህአፓም ቢሆን እንዲሁ። ወያኔ ሃርነት ትግራይም ቢሆን እንዲሁ። የደርግ ሠራዊትም ቢሆን እንዲሁ አደራ በማውጣት ቃልኪዳኑን ጎንደር ይጠብቃል። በፍጹም ሁኔታ ጎንደር ብልህ ማተበኛ ነው። 

አንዱ ድርጅት ሌላውን ለመበቀል በሚያደርገው ሂደት የሚጨፈጨፈው ደግሞ የጎንደር ህዝብ ነው። መሬቱ - ጥሪቱ - ትውፊቱ - የሚወረሰው ደግሞ ያው ጎንደር ነው። በጦርነትም የሚደቀው ያው እሱ ነው። በደርግ ዘመን ወያኔ ሃርነት ትግራይ ለሰሞናት በሚቆጣጠራቸው ቦታዎች የመጀመሪያ ተግባሩ ት/ቤቶችን ማቃጠል፤ ክሊኒኮችን ማንደድ ነበር። ዙሮ የሚመሽጋው ደግሞ ጎነደር ላይ ነው። ስንቁን የሚዘርፈውም ከጎንደር ገበሬ ነው። የጠፉት ቦታዎች ከወያኔ ወረራ በኋዋላም ቦታዎች ጠፍ ሆነው ይቀራሉ። ት/ቤት ሆነ ክሊኒክ አይኖራቸውም።  በግራ በቀኝ የሁሉም መከራ ቡፌ ጎንደር ላይ …. አና ይላል።

በዚህ ውስጥ የዕእምሮ ሰላም ማጣት ህሊና ተረጋጋቶ ማሰብ፣ መመራመር መፍጠር አይችልም ማለት ነው። ተማሪዎች ተረጋግተው መማርም አይቻላቸውም። ስለሆነም ጎንደር ውስጥ የሚያድግ ልጅ በምን ያህል ሰቆቃ ውስጥ እንደሚያድግ ዶር. አብይ አህመድ በዕዕምሮ ፈጠራ ላይ የተለዬ የምርምር ተግባር እዬከወኑ ስለሆነ ሚዛኑን ማስላት ይሳነዎታል ብዬ አላስብም። ስንት ሳይንቲስት፤ ስንት ፈላስፋ፤ ስንት ተማራማሪ ሊሆኑ የሚችሉ እትብቶቿን ከ40 ዓመት በላይ በዘለቀው የእርስ በርስ ጦርነት፤ ዛሬም ባላባራው ጦርነት ጎንደር ልጆቿን፤ ተስፋዎቿን አጥታለች። 

አይደለም ትናንት ዛሬም? ይህም ሆኖ አሁንም የውስጥ ሰላሟ ታውኮ የሁሉንም የመከራ ዓይነት በማስተናገድ ላይ ትገኛለች። ኑዛዜ ላይ ናት። ሰኔል ተዘጋጅቶ ቹቻ የረጠበላት። ግፍ ነው ገዳይሽን አንጥፈሽ - ጎዝጉዘሽ አስተናግጂ፤ ስለመገደልሽ እልል በይ፤ ሐሤትም አድርጊ ማለት - በራሱ። ከበደሉ ሁሉ የከፋ የግፎች ሁሉ አውራ ነው እንዲህ ዓይነት ትርኢት። እግዚአብሄር ይማርሽ የአባት። ባይረሶችሽ እኛ ነን የአባት። ይቅርታ አድርጊልን መከፋትሽን እንክሳላን የአባት። ለነገሩ ሃይማኖቱ ቀርቶ ሰውነቱ የለ።

እንዴት በሞት ላይ ያለች እናት ከበሮ ተስጥቷት ዳንሺ ትብላለች? ሰቀቀኗን ልታስታግስብት የምትችልበት የእረፍት ጊዜ መሰጠት ሲገባ፤ በቁስሏ ላይ ሌላ ምርቅዛት ሚጥሚጣ ይታዘዛል። ከዘመናይነት በላይ ቅንጥም፤ ጥጋብም ነው። …. ጎንደር ላይ „የእርቅና የሰላም ጉባኤ“ ተብሎ በጠበንጃ ታጥሮ የሞላላቸው ሲፏልሉ ማዬት እና መስማት … በራሱ ትውልድን ያመክንል። እርግማንም ነው ዘር የማያወጣ።

የማከብረዎት ዶር አብይ አህመድ አንድ ምሳሌ ልንገረዎት ከልበዎት አንደሚያዳምጡኝ ተስፋ በማድረግ እናቴ ባለቤቷ የሁመራ አራሽ ስለነበሩ አበባ ሲሸፍቱ የኢዲዩ ቤተሰብ ተብላ የገዛቸው ቦታ ሁሉ ተወረሰባት። ባይገርመዎት በዛ ዘመን የባህርዛፍ ተክል ፍል ተፈልቶ የሚለማበት በገንዘባቸው የገዙት ቦታ ሁሉ ነበራቸው እዛው ጎንደር ውስጥ። ሁሉም ተወረሰ። ልጆቿን ለማሳደግ ከፍ ያለ ችግር ገጠማት። ሁላችንም ትናንሾች ነበርን። ከእህቶቼና ከወንድሞቼ ታላቅ እኔ ነበርኩኝ። ስለሆነም ገና በውል ወደ ታዳጊ ወጣት ሳልሸጋገር ነው ጎብጬ በሃላፊነት ብዛት ያደኩት። 

አሁን እኔ የታዳጊ ወጣትነት፤ የወጣትነት ታሪክ ልምድም ሆነ ተመክሮ የለኝም። ምንም እማውቀው ነገር የለኝም። እኔ እና ታዳጊ ወጣትነት ሆነ ወጣትነት ተላልፈናል። ደግማን ላንገናኝም ተማምለናል። ሳያውቀኝ ሳላውቀው። ለሥራ ስደርስ ትምህርት መቀጠሉን ትቼ ለእህቶቼ መድረስ ነበረብኝ። 

ጎበዝ የደረጃ ተማሪ ነበርኩኝ። የባይወሎጂና የኬሚስትሪ። በዛን ጊዜ ኢንሳይኮሎፖዲያን በአማርኛ መተርጎም ጀምሬው ነበር። ሥራ ስይዝ ከነበረኝ ንቃት፤ ቅልጥፍና፤ ሥልጡንነት፤ ሥራ - መውደድ ጋር ተያይዞ እድገቴ ባልተጠበቀ ሁኔታ እጅግ ፈጣን ነበር። የኢሰፓ ቋሚ ሠራተኛ ሆንኩኝ። ኢሠፓ ሲወድቅ አሁንም እናቴ ተጠቂ ሆነች። ቤት አልነበራትም ሜዳ ላይ ነበር የተወረወረችው። እህቶቼ ታሰሩ። 10 ዓመት ሙሉ እህቶቼ ትምህርታቸውን ትተው ፍርድቤት ለፍርድቤት ይባክኑ ነበር። ዜሮ አምስት ሳንቲም አልነበራቸውም። ኑሯቸውን ለማሸነፍ እንኳን ጊዜ አጡ። 

ከጫካ ስመለስ ምህረት ጠይቄ ስገባ ደግሞ ሌላ ዲል ያለ ፈተና ደግሞ ጠበቃቸው። ምህረት ተጠይቆ ከገባሁ በኋዋላ ነበር እኔ የታሰርኩት። ይህ በዓለም የሌለ ጥቁር ታሪክ ነው። ምህረት ምህረት ነው። የሆነ ሆኖ ተጨማሪ ዕዳ ሆንኩባቸው። የእህቶቼ ጮርቃ ጭንቅላት በሰቀቀን ተወልዶ - አደገ። መጀመሪያ በወላጅ አባታቸው በኋላም በእህታቸው። አሁን ደግሞ እናቴ ትኑር አትኑር አላውቅም። እሷም እኔ ልኑር አልኑር አታወቅም። ሃሳብ መግለጽ በኢትዮጵያ የወንጀሎች ቁንጮ በመሆኑ ምክንያት።

እኔ ደግሞ ደፍሬ ወጥቼ ለመናገር ግልጽና ቀጥተኛ የሆነው ተፈጥሮዬ ያስገድደኛል። አሁን ይህቺ ምስኪን እናት መቼ ነው ሰላሟ የሚመጣላት? በህይወት ካለች። ከእኔ ጋር የምትሰቀውስ መቼ ነው? እህቶቼስ የውስጣቸው ሰላም የሚሰፍንላቸው መቼ ነው? ባባታቸው፤ በእህታቸው የቅድሚያ ተጠቂዎች ናቸው። የትውልዱም አካል ናቸው። እንዲህ ናት የጎንደር እናት። በማያባራ የዕንባ ዶፍ የምትማቅቅ። የጭንቅ ረግረግ ነጠላ የለበሰች። የስጋት ሙሉወርድ በድርብ ገመድ የታጠቀች።

 የሚገርመዎችት ስደተኛ ካንፕ ውስጥ ስኖር 20 መጽሐፍትን ጉልበቴ ላይ አስደግፌ በእጄ ጻፍኩኝ። ችዬ 7ቱን አሳተምኩኝ። የትውልዱ ነገር ስለሚጨንቀኝ በዛ ዙሪያ የተሠሩ እጅግ ጠቃሚ መጸሐፍት ናቸው። የልጆችም የአዋቂዎችም። እነሱን እንኳን የመሸጥ ነፃነት እዚህ በነፃ ሐገር የለኝም። 

ጎንደሬነቴ በፈጠረው ቀውስ ምክንያት እንዲሁም የፖለቲካ ማንፌስቶ ቤተኛ ባለመሆኔ። የመንፈስ ሃብቶቼ ተዘግቶባቸዋል። ይህ ለእኔ ዐውደ-ጽሑፋዊ መድልዎ ነው (contextual Discrimination)። እኔ ለእማማ ጎንደር ብርቋ ልጇዋ መሆኔን አሳምሬ አውቃለሁ። የሆነ ሆኖ የትም ቦታ በዬትኛውም ሁኔታ የጎንደር ልጅ በዛ ሰቀቀን ውስጥ አልፎም፤ ያን ሁሉ መከራ ተሸክሞ አድጎም፤ ስደት እዬገረፈውም አቅሙ እስረኛ ነው። ዕወቀቱ እስረኛ ነው። የማድረግ ችሎታው በእሾኽ የታጠረ ነው። 
  
ጎንደሬዋ እናት የወለደችው ልጅ በስደት ይህን መሰል ተደራቢ ግለትና አድሎ ስትሰማ ምን ትላላች? ውስጧ አንዴት በሃዘን ይርመጠመጥ? እንዴትስ ከእሳት እንደገባ ብላስቲክ ማህጸኗ ኩምትር ይል? ጎንደር እራሷ የመጀመሪያዋ ሴት ጸሐፊ ልጇዋ ስታዝን እንዴትስ ከምር ይከፋት? እንዴትስ ሰቅሰቅ ብላ ታለቀስ? በፍጹም ሁኔታ ግብረ ምላሹ ረቂቅ ነው። ጎንደርም እሰከ እትብቶቿ እስረኛ ናት። በዬትኛው ዘመን ፍቺ ሊያገኝ እንደሚችል መገመት ይቸግራል። 

ስለዚህ ይህን መሰል ከመሰረቱ መጠጊያ ያጣ የወገን ሰቆቃ፤ የሚመስጥ የትውልድ ፍዳ፤ አብሶ የጎንደርን ከሦስት ትውልድ በላይ ያሸማቀቀ የእንባ ዋናተኛ እናትን የሀዘን ስሜት የእኔ ብሎ፤ ከውስጡ ሆኖ ባለቤት ሊሆን የሚችል አይደለም ሰው ህልም እንኳን በሌለኝ ሰዓት ነው የእርስዎን ንግግር ያገኘሁት። ደስታ ቀላል ነው። 

ሙሉ ዕድሜዬን በውስጤ አምቄ የኖርኩት የፈውስ ቀን ነበር ብለዎት ይሻለኛል። ተቆርቋሪነት ቃሉ ቀላል ይመስላል። ትውልድን ግን ከሥነ - ልቦና ጥቃት ታድጎ ተስፋ አምራች የመንፈስ መስኖ ነው። ገነት። ኤዶም። ንግግርዎት ፈውስ ነበር። ተስፋ ነበር። ነገ ነበር። ውስጥወት የውስጥን ቁስለት እንዲሽር በፈቀደኝነትና በፍጹም የመቆርቆር ህሊና ሸለሙት። ውስጠዎትን በስውር የተሰበረውን መንፈስ ወጌሻ እንዲሆን በልግስና ሰጡን። ወጌሻነቱ ለዛውም የነባቢት። ነፍሴ እነሆ ተመለሰች - ሐሤትም አዋዋለች። 

እውነት ለመናገር ከጎጃም የአማራ ወጣቶች ያገኘሁትን ብርታት እና ጥንካሬ ያህል ንግግርዎት በልግስና ተስፋን በገፍ መግቦኛል። ዶር. አብይ እርስዎም እንደሚያውቁት የሰው ልጅ በመጠጥና በውሃ አይኖርም። ለመንፈሱ ልማት የቅንነት መስኖ ያስፈልገዋል። አይዟህ/ አይዞሽ መዳህኒት - መድህንም ነው። ረቂቅ ነው ትርፉ። ይባረኩ። 
 
  • የታቀደ ዕዳ።


ወያኔ ጎንደርን ሲቆጣጠረው የ12ኛ ክፍል መልቀቅያ ፈተና ይሰጥ በነበረበት ጊዜ ነበር። ታቅዶ ተሰልቶ። ታናሽ ወንድሜ የሳይንስ ተማሪ ነበር። ከሙሉ ሥነ- ምግባር ጋር ለከፍተኛ ውጤት የታጨ ተወዳጅ ተማሪ ነበር። ግን ጎንደር ጦርነት ላይ ስለነበረች የጎንደር ክ/ሐገር ልጆች መፈትን አልቻሉም። የእኔ በትምህርት አለመቀጠልን በእሱ ይሳካልኛል ብዬ ራሴን ከሁሉም ነገር ቆጥቤ በትጋት የምጠብቀው ልዩ ዕድል ነበር። 

በዛ ላይ እናቴ ሳቅን ታዬዋለች ብዬ አስቤ ነበር። ግን አልሆነም። እናቴን በዚህ ውስጥ በመንፈሰዎት እባክዎት ይዮዋት  … በእኔ ያልተሳካላትን በወንድሜ ማዬት እንኳን አልቻለችም። ቁስሏ ሳይሽር እኔ ጫካ ገባሁ። ሌላ መከራ አሸከምኳት። እናቴ ለናሙና ያቀርብኳት ዕውነቱን ለማንጠር ነው እንጂ የጎንደር እናቶች ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ጥላሸት ያደራበት ህልማቸው ይሄው ነው። የጎንደር እናቶች የልጆቻቸው ህልም እንዲህ ባክኖ፤ መቅኖ አጥቶ ነው የሚቀረው። 

አሁን ደግሞ ባለፈው ዓመት ሆን ተብሎ የጎንደር ልጆች ማትሪክ ይወስዱ በነበረበት ዕለት ነበር የትግራይ ተራራዎች ደንበር ጥሰው ገብተው ህጻናትን ጎንደር ላይ በባሩድ ያነደዱት። ለዛውም ለህውሃት ሥረዎ መንግሥት ላቡን ጠብ ባደረገ ጓዳቸው በኮ/ደመቀ ዘውዱ ምክንያት። ቀጥሎም አንባ ጊዮርጊስ በምትባል ከተማ ላይ አጨዳው ቀጠለ። አንዲት ቤት ከማረተ ቆርቆሮ ውጪ የሆነች የላትም በዛች የገጠር ከተማ። በዛች ከተማ ላይ የአጋዚ የጭካኔ ባሩድ አልበቃ ብሎ የሱዳን ወታደሮችም ወንድ ህጻናት ሲያአርዱ እናቶች ጫካ ነበር የበላቸው። 

… በዬዕለቱ በሱዳን ወታደር እና በኢትዮጵያ ወታደር በፈረቃ የሚያልቀውን የጎንደር ደንበር ላይ የሚገኙ የህጻናትን ዕጣ ፈንታም፤ እናትንም በዚህ ህሊና ውስጥ ይዩት … ጎንደር የጠዬቀው ማንነታችን ይከበር። ደንበራችን ይከበር። ባርነት በቅቶናል። ጭቆና በቅቶናል። መሬታችን ይመለስ ነበር ያለው በሰላማዊ መንገድ። ጉዳቱ አለበቃ ብሎ የደረሰውን ፍዳ ከእኔ በቅርበት እርሰዎ ስለሚዩት ያውቁታል … እንኳንስ ሥልጣኔ ጎንደር ላይ ሊታሰብ ቀርቶ። እንኳንስ ቀና ብላ ትንፋሽ ልትተነፍስ ቀርቶ … የባርነትም አለው ዓይነት … ይህ ዕውነት ሰው መሆንን ብቻ የሚጠይቅ አምክንዮ ነው፤ ሳይንቲስትንትን አይጠይቅም። በዚህ ሰበብ የታሠሩት ከተፈጥሮ ውጪ ሆነዋል። የንግሥት ይርጋ ጥፍር ሲነቀል በዛ መንፈስ ውስጥ የሚሊዮን እናቶች ጥፍርም ተነቅሏል። ንግሥትን ጎንደር በ50 ዓመት አታገኛትም። የጎንደር ሴት ወደ ፖለቲካው ዓለም ለመቀላለቅል ወጉ፤ ልማዱ፤ ሃይማኖቱ እጅግ ጥብቅ ነው ከራራ። የቤተሰብ ጫናም ጫን ተደል ነው። ቤተሰብ ፊት ነው የሚነሳው። ይህን ጥሳ የወጣች አንዲት ዕጣ የሴት ነፍስ ደግሞ ፍዳዋ የዕድሜ ሙሉ ነው። ያለሁበት የኖርኩበት ንጥር ሃቅ ነው። ለመሆኑ ሴቶችን ያላሰተፈ ዴሞክራሲ ምን ይሉታል? ሥም አለውን?
  • ህመም።     


አሁንም „ከፋኝ“ የሚለው ሁሉ ምኞቱ፤ የህልሙን ስንቁን፤ ቀለቡን፤ የሰው ጥሬ ዕቃውን የሚያልመው ጎንደር ላይ ነው። የትናንትናው ሻብያ ሳይቅር። ዛሬም በጎንደር ጭድነት ህልም አለው። በሌላ በኩል ጎንደር ላይ ታፍኖ የሚታሠር ሁሉ „ግንቦት ሳባት“ ነው የሚባለው። ይህ በሁለት ጣምራ ስለት የጎንደርን ትውልድ የሚያጭድ የሴራ ግማድ ነው። ጎንደሬዎች እራሳቸው ወደ ራሳቸው ተመልሰው እንደ እርስዎ ቀርቶ፤ እንደ ሰው ሊያስቡላት ለጎንደር ትውልድ አልቻሉም። ትናንት በደርግ ጊዜ አመድ ለብሰው፤ ከሞት ያመለጡ ህጻናት ዛሬ ደግሞ በግራ ቀኝ ማገዶ ናቸው። ዛሬ ደግሞ ስንቅና ትጥቅ ብቻ ሳይሆን ባሩድም ስንቁ እንዲሆን ይፈለጋል። „ከፋኝ“ የሚለውም ገደልኩ ብሎ የሚፎክረው ጎንደሬውን ነው - ተጠቂውን። አጥቂው ላይ አይታሰብም። አጥቂው አይደፈሬ ክንድ አለው። ሙከራው ፉከራው ጎንደሬን ገድሎ ነው። ቤት ትዳር ሲፈርስ በማህል ህጻናትም አሉ የፈረደባቸው የጎንደር መከራ ተረኞች። ካለወላጅ አባት ያድጋሉ። ለሌላ ጊዜ ደግሞ ለ እርድ ይሰናዳሉ። ሌላው ይማራል፤ ይመረቃል፤ ይዳራል ይኳላል። ጎንደር ላይ ደግሞ በምሾ ደምቆ የነገ ተስፋ ይቀበራል። 

በዚህ ሁኔታ በሞት ጭንቅ የሚያድጉትም ህጻናት ህውሃት ቢወገድ ነገም „ከፋኝ“ ለሚለው ጎንደር ለማገዶነት ይታጫል። ዛሬ በትግራይ የአፓርታይድ ሥርዓት በማገዶነት ያደጉት ደግሞ ለነገም ተረኞች ናቸው። ዛሬ ለተጋሩ ባርነት ሥር የወደቁት ደግሞ ለነገ የጦርነት ብርንዶ ናቸው። ማህበራዊ ህይወቱም፤ ሃይማኖቱም፤ ዕውቀቱም፤ ፈጣራውም ሥነ - ጥበቡም በዚህ ማቅ ውስጥ ናቸው። መቼ ነው የሚቆመው?  መቼ ነው የሚቆመው?  ሌላው ቀርቶ የጎንደር እትብተኞ አስበውት አያውቅም። ስለምን? በዬጊዜው ልብን የሚሸልሙት እያሰገረ በተለያዬ ሥያሜ ለሚመጣ የማንፌስቶ ልቅልቅ ሰለባና የቁም እስረኛ ስለሆኑ። አንድ ጊዜ መሳሳት የአባት ግን ሁልጊዜ ትውልድን ለእርድ ሰንጋ አቅራቢነት ማጨት ዕብንነት ብቻ ሳይሆን ራስን መቀበር ነው። ነገ ደግሞ ጎንደር ባደረገው ልክ የፍሬ ተቋዳሽ ሳይሆን ባደረገው መልካም ነገር ልክ የፊት ተጠቂነት ረድፈኛ ነው። የአቶ በረከት ስሞኦን የታወቀ ነው። ህልማቸው የኢትዮጵያን አከርካሪ መስበር ስለሆነ ባወቁት መንገድ ገብተው ይሉታል፤ ያውቁታል የጎንደርን የሥነ - ልቦና አቅም። ጎንደርን ማክሰል ነው የታጠቁበት፤ የሰለጠኑበት። የወያኔ ህልም ኩላሊት በመሆናቸው አይደንቅም። በዛ ላይ የማንነት ችግራቸውን ቁንጣን የሚያስተነፍስላቸው፤ ቁጭታቸውን ካሳ የሚያገኙበት ስለሚመስላቸው እርዱን ጎንደር ላይ ይቀጥላሉ። አሁንም በአዲስ ካባ ሹም ሆነው ብቅ ሊሉ ይቻላሉ። ጎንደርን ከተማዋን በአውሮፕላን እሰኪያሰወድሙ ድረስ አሉታዊ ተጋድሏቸው ይቀጥላል። ህልማቸው የጎንደር ምድረበዳነት ነው።

የሚያሳዝነው ልጆቿ እንኳን አያስቡላትም። ተዚህ ላይ ሻለቃ መላኩን ለአብነት ማንሳት ይቻላል። … ከውስጣቸው ጎንደር አልነበረችም። ኑራም አታውቅም። ለትግራዩ ሻ/ ገ/ብርህይወት አሳልፈው በመስጠት የጭፍጫፋ በሩን ቧ አድርገው ከፍተው ዳኛ አልባ አሳጨዱት። ሻ/ ገ/ህይወት የስሜን አውራጃ አስተዳደሪ ሆነው ጭልጋና የወገራ አውራጃ በተጨማሪነት አስተዳዳሪ እንዲሆኑ ሾሟቸው። የሁለቱም አውራጃ አስተዳዳሪዎች ጎንደሮች እያሉ። የትም ቦታ ሆኖ አያውቅም ይህ ጉዳይ። ምን አለ ጎንደር መሞከሪያ ጣቢያ ናት። ዛሬ ደግሞ ኤርትራዊ  … የጎንደር ተወካይ ናቸው። ጎንደር ምኔ ብሎ እሳቸውን ይወክላል? አቶ በረከት በዬትኛው አንጀታቸው ስለ ጎንደር ሀዘኔታ ሊኖራቸውስ ይችላል? አደጉበት እንጂ አልተወለዱበት … ብጣቂ የደም ጥሪት ልቅላቂ የላቸው … „ኦሮሞው በኦሮሞው፤ ትግሬው በትግሬው ነው የሚመራ“ ይሉናል። ታዲያ አሳቸው ምን ባይስ ምንድንስ ናቸው? አማራ አይደሉም። ምን ይሠራሉ። ስለምን የአማራ መሪ ለዛውም የጎንደር ተዋካይ ሊሆኑ ቻሉ? ቢያልሙትም አማራነትን አይችሉም። ደም ነው። ተወልጄነት ነው አማራነት።
  • የውስጥ ቀለበት ፍቅር ልቅና።


እጅግ አድርጌ የማከብረዎት ዶር. አብይ አህመድ ጎንደርን እንዳዮዋት ውስጠዎት አስቀመጧት። ነፍሰዎትን ሰጧት። የእኔ አሏት። ስለሆነም ኪንጋሊ ሲሄዱ ጎንደርን በመንፈሰዎት መስጥረው፤ ጸነሰው ሄዱ። ሌላው ይህን አያደርገውም በፍጹም።   የእርስዎ ግን ታእምር ነው፤ ትንግርት፤ የሰማዬ ሰማይት አብሪ ኮከብ። መስጥረዋት የሄዱትን እናት ጎንደርን ከ22 ዓመት በኋዋላ ሲያዮት ታማ አልጋ ላይ ሆና፤ ለኑዛዜ ጸሐፍተ ሄኖክን ስታፈላልግ ጣር ላይ አገኟት። ይህ ሚስጢር ለእርስዎ ብቻ የተገለጠ ነው። ከአውሮፓና ከአሜሪካ ልጆቿ ወደ እሷ በዬአውዳመቱ ይጎርፋሉ። አንድም ቀን በዚህ ሚዛን ውስጥ ጎንደርን ውስጥ ያደረገ፤ የመንፈስ ተጋድሎ ሲያደርጉ የታዬ አልተስተዋለም። እዛው ያሉትም ቢሆኑ በሞተችው ጎንደር ላይ ሆነው ከሞላላቸው ጋር ይደልቃሉ። ጎንደር እኮ የአንድ ገበሬ ማህበር ያህል አቅም የላትም። ከወረዳም በታች ናት። ያቺ የታሪክ ማህደር - ያቺ የልጅ አደራ አውጪ አንባ ሁለመናዋ አልቋል። ሁለመናዋ ተበልቷል። ሁለመናዋ ተናውጧል። 

ዛሬ ጎንደር ጥጋበኞች የሚያቀረሹባት፤ በትዕቢት ተወጥረው የሚታዩባት፤ መድቀቋ አታሞ የሚደለቅባት፤ የሙት መንደር ናት ጎንደር። እርግጥ ነው ከዛ ያሉ ጎንደሬዎች በአፓርታይድ ሥር የወደቁ ናቸው፤ በተለይ አማራዎች። የበላይ ተቆጣጠሪዎቻቸው የትግራይ ደም ያላቸው ብቻ ናቸው። ወይ በጋብቻ የተሳሰሩ። የጎንደር ነፍሶች ትንፋሻቸው እራሱ በቁጥጥር ሥር የወደቀ ነው። ተፈጥሮዋ ሳይቀር ከላይ እሳት፤ ከጎን እሳተ ጎመራ፤ ከፊት ለፊት ቃጠሎ፤ ከታች ረመጣዊ ነበልባል የታዘዘባት ሆድ የባሳት ናት ጎንደር፤ ነዲድ የነገሰባት።

የሚገርመዎት የእኛው ዶር አብይ አህመድ ኢህአፓ እዛው መሽጎ ቀን ያሳለፈባት፤ ወያኔ ሃርነት ትግራይም ስንቁም ትጥቁም ጎንደር ነበረች። ወያኔ ሃርነት ሥልጣን ሲይዝ ማንፌስቶውን የተቀበሉ ወደ ዛው አቀኑ። አብረው ከወያኔ ሃርነት ትግራይ ጋር ለመሥራት። ያቺን የጥንት የጥዋቷን የመከራቸው ለታን ጎንደርን ግን ለደቂቃ አስተውሰዎት አያውቁም። ትዝ አትላቸውም። አንዲት ብጣቂ የምስጋና ቃል ከአንደበታቸው አትወጣም። ስለሆነም ጎንደር ልጅ ያላዋጣች ብቻ ሳይሆን፤ ያበላችበት ክንድ ብድር መለሽ ያላገኘች ያልታደለች ዕድል የራቃት፤ ነገ የጠመመባት፤ ማግስት የከሰለባት ናት። በስቲያም የለገመባት ናት።የሚገርመው ለድጋሚ ምሽግ መታጨቷ ነው። ገደልን ሲባልም ጎንደሬው ታድኖ መሆኑ ነው። እንቆቅልሽ - በእንካ ስላንትያ።

እውነት ለመናገር ጎንደር ሲታሰብ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የእናትነት የፊደል ገበታ መሆን ነበረበት። መከራዋ የእኔ ሊባል በተገባ። ከፍቶን ስንናገርም ዕውነታቸው ነው ይጋበልም አይባልም። እንዲያውም ለሌላ በቀል ስልት ይቀዬሳል። ሌላ ግልት ይዶለታል። መሆን የነበረበት ግን ለትውልዷም ሰፊ ጥንቃቄ ሊደረግላት በተገባ። ግን ለግብር አቅራቢነት ብቻ ነው ጎንደር በሽፍት የምትታለመው። በተከታታይ የምትታጨው …. ወይ ደግሞ ለፕሮፖጋንዳ ሸቀጣ ሸቀጥ የጀምላና የችርቻሮ ግብይት። ጎንደር የሺህ እናቶችን ዕንባ ያበሰች፤ ልጆቻቸውን በእቅፏ ያሞቀች የእናትም እናት የአደራ ቤተ መቅደስ ነበረች። ግንስ አንድስም እንኳን ማተበኛ አላገኘችም። ባለጊዜዎቹ የትግራይ እናቶች እንኳን የእናትነትን ሰማያዊ መክሊት ጠቀጠቁት፤ ቦጫጭቀው ቀዳደዱት። የመከራ ቀናቸውን የጎንደርን እናት በጠራራ ጸሐይ ሰቀሏት። በጨለማት ቀኖችም እዬተነደቀደቁ „ጉና አብረን ተቀበርን“ በማለትም ተሳለቁ። እርግማን።
  
  • ውስጤ።


ውድ ወንድሜ ዶር. አብይ አህመድ ይህን ጹሑፍ ስጽፍለዎት እንደ ሌሎቹ ጹሑፎቼ በተረጋጋ ስሜት ሆኜ በፍጹም አይደለም። በዚህን ያህል ምሬት የጻፍኳቸው ስንኞች ሞትን እያዬሁ እያዳመጥኩ ብቻ ነበሩ። ለመደበኛ የምስጋና ደብዳቤ እንዲህ በሀዘን ኩርምት ብዬ ስጽፍ ይህ የመጀመሪያ ነው። ስለምን?
·         ንድ ብቻ መሆነዎት።
·         ሊያደርጉ የሚችሉት ነገር ውስን በመሆኑ።
·         እንዲህ ያለ ቅንነት ብቻ ሳይሆን፤ ችግርን የመፍታት አቅሙ ልዑቅ የሆነ ወንድምን ይህ የሶሻሊዝም የሴራ ፖለቲካ የሚፈጥረው ጥቃት ብቻ ሳይሆን፤ የመጠፋፋት ጥቁር ደመናም ስለሚታዬኝ፤ ፈራሁኝ። እጅግም ሰጋሁለዎት።
·         ቅንነትን የሚያስተናግድ ልቦናዎች ዝግነት ብቻ ሳይሆን ዝገቱም ዲካ የለሽ መሆን አሳቀቀኝ። ጥንቃቄ ያተርፋል እንጂ ስለማያከስር አደራ ጠንቃቃ ይሁኑ። አደራ! ሊፈጽሙት ቃል ይግቡ እሺ?
·         ቅኖች እጅግ ጥቂቶች መሆናቸው ብቻ ሳይሆን፤ የቅኖች ጋላሪ ስሌለን፤ ቅኖች እንኳ የራሳቸው ቋንቋ ቢኖራቸውም የመከላከል - የመረዳዳት መስመሩ ግን አልተዘረጋም። የትም ቢኖሩ፤ የዬትኛውም ሀገር ዜጎች ቢሆኑ አንዱ ቅን የሚያስበውን ሌላውም በዛች ቅጽበት ያስባታል፤ ግን ግሎባል ሥርዐቱ አልተዘረጋም። ተቋም የለንም። ማህበር የለንም። ቢያንስ የቅኖች ማህበር ቢኖር አንዱ ለሌላው ጥበቃ የሚያድርግበት፤ ጥላ ከለለ የሚሆንበት መረብ ይኖረን ነበር። „አይዞህ/አይዞሽ“ መባባሉ፤ በጸሎት መረዳዳቱ ራሱ የመንፈስ ስንቅ በሆነ ነበር። አሁን ባለው ሁኔታ ግን ቅኖች ለብዙ ጥቃት ይጋለጣሉ። ሳይደመጡ እንዲቆራረጡ ይደረጋል። ብሎኪንግ ይፈጣራል። ይህም ስጋቴን በእጅጉ አጎላው። እግዚአብሄር አምላክ ነገን በቅንነት ጥገት ናፋቂ ነዎት እና ለዚያ ያብቃዎት። አሜን።
·         ቅንነትን የማድመጥ አቅም ውስኑነት ይረታል። ቅኖች ልቦናቸውም ሆነ ህሊናቸው ክፍት ነው። መንፈሳቸው ዘብ አልቦሽ ነው። ነባቢታቸው ሲናርዮ አልቦሽ ነው። ቅንነት ቢደመጥ ከሴራ፤ ከሸር፤ ከተንኮል፤ ከቅናት ጋር ተፋቶ ሥርዬትም ይሰፍናል፤ ምህረት ይጎላል። ትውልድ በሞራል ይተርፋል። ግን ገና መሆናችን የዕዬለቱ እስትንፋሳችን ሆኖ ይታያል … እንዳዩት „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ የሚለው ዓራትዓይንማ መንገድ ለቅኖች እንደ ብርሃን መታዬቱ አልተማቻቸውም - አብሶ ለሴረኞች። ከዚህ በላይ ፍቅር ሰባኪ ሐዋርያ፤ ዓራት ዓይናማ መንገድ አልነበረም። ከፍቅር በላይ ምን ተፈጥሮ ምንስ አምክንዮ ነበረ። ፍቅር እኮ የመኖር ጭንቅላት ነው። ስለሆነም የቅንነት ድርቀት በጽኑ አለብን። ሎሬቱ ጌታ ብላቴ ጸጋዬ ገ/መድህን እንዳለው ፍቅርን በጽኑ ስለምንፈራው። ይህ ደግሞ እንዲህ ዘለግ ብሎ ለሚወጣው ቅንነት የሌላ ወጥመድ ሰለባ እንዳይሆን አሁንም ቅኖችን እረፍት ያሳጣል። ምን ይፈጠር ይሆን ያሰኛል። እኒህ ደግ -ቅን -ሩቅ - አሳቢ፤ ሃዘንን ከውስጥ ታገሪ፤ ውስጥን አሳቢና ሰብሳቢ ይሰነብቱልን ይሆን በማለት ስጋት አደረብኝ።

ስለሆነም በእነዚህ ምክንያቶች ነገስ በዚህ ቅንነት እንዲቀጥሉ እገዛው፣ ትብብሩ፣ አድማጭነቱ ምን ይገጥመው ይሆን? በሚል ውጥር ባለ ስሜት ውስጥ ሆኜ ነው የፃፍኩት። ጥቃት እንዳይደርስበዎት ሰጋሁኝ። ግን ወሰንኩ። ቢያንስ እግዚአብሄር ይስጥልኝ ማለት ስለሚኖርብኝ። ምስጋናዬ ግን ለእርስዎ ብቻ አይደለም። ወልደው ላሳደጉዎት መልካም ወላጆችዎትም ጭምር ነው። ከታረመ ቤተሰብ ማደገዎት ምርቃት ስለሆነ ይመስለኛል እንዲህ የኢትዮጵያን ችግር ውስጠዎት ለማድረግ ያስቻለዎት። የኪጋሊ ጉዞዎት ጋር ጎንደር አብራ ተጉዛ የኪጋሊ ታዳሚ ነበረች። ይደንቃል። ይመስጣል። ይሰብካል። ሐዋርያነትን። ሴቶች ጥበቦች ናቸው፤ እና ለተፈጥሮዎት የበለጠ የብቃት ጥራት የትዳር አጋርዎትም የጥበብ አዝመራ እገዛም፤ ውለታም አለ ብዬ ስለማምን እሳቸውንም ከፍ ያለ ምስጋና ላቀርብላቸው ወደድኩኝ - ጥልቅ በሆነ ትሁት መንፈስ እግዚአብሄር ይስጥልኝ።
  • ክውና ስለዛሬ።


የሰው ጥሩነት መለኬያው ለሌላው በሚያደርገው የተመሰጠ ውስጣዊ በሆነ የቅንነት ተግባር ይለካል። ጥሩነት ድንበር የለውም። መልካምነት የፍቅር ተፈጥሮ መግባቢያ ቋንቋ ነው። ደግነትን አምራቹ መልካምነት ሲሆን አምክንዮው የውስጥ ሰላምም ጠባቂ - ልዩ ዘብ ነው። ይህ መንፈስ ጠበቂው ህዝብ እንጂ ወታደር አይሆንም። ከህዝብ ብሶት የተነሳ ተነሳሽነት፤ የህዝብን ችግር ለመጋራት የፈቀደ መንፈስ የፈጣሪውን ተልዕኮ ፈጻሚ ሐዋርያ ነው። ጻድቅም ነው። ዶር አብይ አህመድ እርስዎ ለእኔ አጽናኝ ሐዋርያ ነዎት። ለዛውም በንጽህና - በቅድስና። ስለዚህም በቅናዊ መንፈስ ከሙሉ አክብሮት ጋር አምስግነዎታለሁ። ተከታይ  ጹሁፍ ይኖረኛል … የተመሰጥኩበት …. አብነተዎት ምርኮኛ እና ተከታይዎት እንድሆን አድርጎኛል እና … ሌሎች ቅኖችም በተለይ መከራ በከተመበት የሥነ ጥበብ ቤተኛም የመንፈስ ጥግ ያለው ስለመሆኑ አበክሬ ማስገንዘብ ስለምሻ። በተጨማሪም ሰሜቶች ከግብታዊነት ወጥተው በስክነት የተጨባጩን ዕውነት ትራስና ፍራሽ ያደርጉ ዘንድ ማሳሰብ ትውልዳዊ ድርሻዬ ነውና። 
+ የኔዎቹ ስታዳምጡት ደግሞ የመንፈስ ፍሬዘሩ፤ ንዑድ ተቆርቋሪነትን ከፍቅራዊነት ህላዊነት ጋር ይለግሳችኋል በ++++ እንሆ …

Gonder Vs Kigali, Dr Abey explains why Gonder remained poor. / አቢያ ኪጋሊንና ጎንደርን ያወዳደሩበት ... 


ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር።
ዓራት ዓይናማው መንገዳችን „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“
የኔዎቹ አብራችሁኝ በትእግስት ስለቆያችሁ እግዚአብሄር ይስጥልኝ። ኑሩልኝ። መሸቢያ ጊዜ።





አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።