የባልደራሱ ባላደራው የፖለቲካ ድርጅት ምሥረታ ጉዞ ጥንቃቄ ስለማስፈለጉ።


እንኳን ወደ ቀንበጥ ብሎግ በሰላም መጡልኝ።

የባልደራሱ ባላደራው የፖለቲካ ድርጅት
ምሥረታው ላይ ሆነ ጉዞው ጥንቃቄ
ማድረግ ይኖርበታል። የትውልድ
አድዮ ለመሆን ከተለመ።

„የሰው ልብ መንገድን ያዘጋጃል፤
 እግዚአብሄር ግን አካሄዱን ያቃናለታል።“
{መጽሐፈ ምሳሌ ምዕራፍ 16 ቁጥር 9}

ሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
11.01.2020

ከጭምቷ ሲዊዘርላንድ።
ይድረስ ለባልደራስ የባለ አደራው ምክር ቤት
አዲስ አበባ።
ግልባጭ ለሁሉም የባልደራስ የባለ አደራው የድጋፍ ሰጪ ትጉኃን አካላት፤
በያሉበት።
11.01.2020

·       ትህትናዊ መሳሰቢያ። 

ክብረቶቼ በስብሰባ ሥርዓት ከአስተያዬት ማሳሰቢያ ይቀድማል እና  ሦስት ማሳሰቢያዎቼን እንሆ።
1.ባለ አደራ ወይንም ባልደራስ እያልኩ ስለምጽፍ ግር እንዳይላችሁ። ሁለቱም ሥያሜዎቹ ቢሆኑ ዕይታዬን የመሸከም አቅማቸው እኩል ነው። በቀለለኝ መንገድ ነው የምጸፈው። በሌላ በኩል ግን የባልደራስ ባለ አደራው ወይንም ባልደራስ በአደራው ጥሩም አማራጭ ይመስለኛል።
2.አብን በተደጋጋሚ ለምሳሌነት አነሳዋለሁኝ። ያው ልጅ ድርጅት ስለሆነ ቀለል ይለኛል። እንዲጠነክርም ስለምሻ።
3.            ሌላው ጋዜጠኛ፤ የሰብዕዊ መብት ተሟጋች፤ የዴሞክራሲ ታጋይ እና የባለ አደራው ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ እስክንድር ነጋ እያልኩ መጻፍም በጥበብ ውስጥ እንዳለ ሰው እሱንም ስለማስበው በአጭሩ አቶ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ብለው „አንተም“ ብለው አቶ እስክንድር ነጋንም እንዲሁም አድናቂዎችም እንዳትከፉቡኝ በትህትና አሳስባለሁኝ። አሁን ጠቅላይ ሚኒሰተር አብይ አህመድን አንድም ቀን ጠቅላይ ሚኒስተር ዶር አብይ አህመድ ብዬ ጽፌ አላውቅም። ወይ ዶር አብይ አህመድ ወይ ጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድ ነው የምለው። ለነገሩ እሳቸውም የጥበብ ቤተኛም ናቸው። ዛሬ ዛሬ ነጠፈባቸው እና በሰጨኝ ከተመባቸው እንጂ። አሁን ወደ ቀደመው። 
·        እፍታ።
እንዴት ናችሁ የአገሬ ቅኔዎች? ደህና ናችሁ ወይ? ዘንድሮ ክረምት አይመስልም። እቴጌ ልዕልት ጠሐይም ኮፈስ ብላ ብቅታን ታዘወትራለች። ሻሾም ብቅ ሳይል ዓውደ ዓመታቱ አለፉ። ምን አልባት የሚያዚያ ነገር እንደልቡ ስለሆነ ያን ጊዜ ወይንም በቀጣዮቹ ወራት እንዴት ናችሁ ይለን ይሆናል። በጋውም በጣም ረጅም ነበር። ይህ ሉላዊ የአዬር ለውጥ ጉዳይ ነገንስ እንዴት ሊያስተናግደው ይሆን? ወደ ኤክስፐርቶቹ እንሸኜው አይደል?

·        መቅድም።
ብዙም አይደንቀኝም አዲስ የፖለቲካ ድርጅት ሲፈጠር። እንብዛም አልጽፍበትም። ተዋሃዱ፤ ተቀናጁ፤ ተጣመሩ፤ ግንባር ሆኑ ሲባልም አልፈነጥዝም እንደ ዕለታዊ ነገር ነው እማዬው። እንዲያውም በዚህ ጉዳይ ላይ ግራሞቴን „ አፍንጫህን ላስ አቶ ሂደት“ መጋቢት 21 ቀን 2014 አ.አ.አ ብዬ የጻፍኩትን ደጉ ዘሃበሻ አውጥቶት ነበር። ምክንያቱም የኢትዮጵያ ፓለቲካ የውስጥነት ችግር ስላለበት ሁልጊዜ ሲናድ ነውና እማውቀው። ትርፉ ማህበረሰቡን ተርትሮ፣ ማህበራዊ ኑሮውን ቀውስ ውስጥ ማስገባት ነው። ይሄው ዕድሜ ልካችን አጋ ላይተን መቧከስ።

ወደ ተነሳሁበት ስመጣ አብን ሲፈጠር ከእነስጋቴ መፈጠሩ መልካም ነው ብዬ ጽፌ ነበር። ያም በአማራ ብሄርተኝነት ላይ ይወርድ የነበረው፣ ዛሬም ያላባራው ወጀብ ውስጥ ተጋድሎውን የሚረከብ ተቋማዊ መንፈስ ያስፈልግ ስለነበረ ነው። እራሱ ተጋድሎውን የሚያነብ፤ የሚተረጉም የሚያመሳጥር ሚዲያም ተንታኝም አልነበር ዛሬም እምብዛም ነው። የሆነ ሆኖ የባልደራሱ ባለ አደራ ግን አግኝቷል ብዬ አስባለሁኝ። ዕድለኛም ነው። የባልደራሱ ባለ አደራው የህልውና ታጋይ ነው። የተጋድሎውን መንፈስ እና ዲስፕሊን የሚቀበል ፖለቲካዊ ተቋም ግድ ነው። በስተቀር ማህራዊ ንቅናቄው ባክኖ ይቀራል። የትውልድ ጥያቄም ባለቤት ያጣል። 
 
ስለሆነም በአማራ የማንነት እና የህልውና ተጋድሎ የማህበራዊ ንቃተ ህሊና ውጤት በመሆን በራሱ ጊዜ ሲፈነዳ ከነበረው የኮፒ ራይት ግብግብ ድኗል። ራሱ ጀመረው ራሱ ህይወቱን - ኑሮውን - ተስፋውን ራዕዩን ቀጠለው። ብዙ አቅም አላበከነም። ለዛም ነው የአማራው ተጋድሎ የኢትዮጵያ መንግሥትም ዕውቅና ስለነሳው፤ እንደ ድርጀት ተጋድሎውን የሚወክል አብን ሲመጣ ጥሩ የህሊና እረፍት ስለሰጠኝ የጻፍኩበት። አመሰራረቱ ላይ የነበረውን ግድፈትም በወቅቱ ጽፌ ነበር። 

ቀላሉን እንኳን ባነሳ ሰማያዊ ቀለም የሰማያዊ ፓርቲ መለያ ነበር። ተሳታፊዎች ያን ቀለም ነበር ምርጫቸው ያደረጉት። እኔ እራሴ ጥርጣሬ ነበረኝ። ያ አግባብ አልነበረም። አሁን እራሱ በሰሞናቱ የኢህዴግ ይባል የብልጽግና የሥ/አሰ/ ስብሰባም በቄንጠኛ ሰማያዊ ቀለምን ተጠቅሞበታል። ሰማያዊ ስለከሰመ ነው እንጂ ይህን ቀለም የመረጠው አገራዊ ፓርቲ ስለነበረ አግባብ አይሆንም ነበር ለሙሽራው ኢህዴግ። ብልጽግናን ሙሽራው ኢህዴግ ብለውስ? የምርኮኛ ባለሚዜም በሸበሽ ሆኖለታል፤ ዕድለኛ። እም! „ምርጫችን ብልጽግና“ ይልኃል የትናንት የነፃነት ታጋዩ ቀንዱ ጋዜጠኛ ሳይቀር። ህም!
  
ቀደም ብዬም ባለ አደራው ወደ ፖለቲካ ድርጅት የመቀዬር ሃሳብን እና ጠቀሜታውን ጽፌ ነበር ፌስቡኬ ላይ፤ ሲወጠንም ተቋም እንደሚያሰፈልገው ቀንበጥ ብሎጌ ላይ ጽፌያለሁኝ። ሊንኩን ከሥር እለጥፋለሁኝ። አሁን ከመቋጫ የተደረሰ ይመስለኛል። እግዚአብሄር ከፈቀደለት ጥሩ ተፎካካሪም ሆኖ ይወጣል ብዬም አስባለሁኝ። ከሁሉ በላይ ዕምነቴ በእግዚአብሄር በአላህ ፈቃድ የተፈጠረ ነው ከሚለው የሚነሳ ነው። በዚህ በፍጹም አልጠራጠርም። የባልደራሱ ባለ አደራው ኢትዮጵያ ከቀስት ትድን ዘንድ ክስተት ነው ብዬ በጽናት አምናለሁኝ። የዕንባም ጥሪ አለበት የሚል አቋምም አለኝ። መገናኛም ነው። ድልድይ። የዘመኑ የመከራ ሚስጢር የተገለጠለት መንፈስ ነው የባልደራሱ ባለ አደራው። ስክነቱን እወድለታለሁኝ። ብስለቱንም እመሰጥበታለሁኝ። ብቻ ይጨርስለት። በህይወቴ ጥድፊያ አልወድም።

·       የባልደራሱ አደራው እና ባለ አደራው እንዴት ተገናኙ? 
1.ዘመን ማንበብ፣
2.ዘመን መተርጎም፣
3.  ዘመን ማመሳጠር የቻለ የበሳል መንፈስ ባለቤት ከመሆን ይመስለኛል። አደራው የሚመነጨው ከዚህው ጥልቅ መክሊቱ ነው። የጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድ „የጦርነት እንገባለን“ በሰጨኝ ዓዋጅም የባልደራሱ ባለ አደራው የዘመን ንባቡን፤ የዘመን ትርጉሙን፤ የዘመን የማመሳጠር አቅሙ ስለ አሰጋቸው ነው ብዬ አስባለሁኝ። በመስመር ተዋውቀዋል። እሳቸውም በቄንጠኛ አዲስ አበባን ለኦሮሞያ ክልላቸው አስረከበዋል። ለዚህ አንድ ሁለት ብሎ ምልክቶችን መስጠት ይቻላል። ያሻው ይምጣ እና ይሞግተኝ። ጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድ ሲሾሙ በመንፈስ ነበር ፍላጎቱ። 
     አቶ ለማ መገርሳ የኦነግ ሽርፍራፊዎችን፤ የኦሮሞ አክቲቢስቶችን በማሰባሰብ የሠሩት ሥራ በኢህዴግ ላይ ሞጋች ቢገጥም ሌሎቹ ኦነጋውያን ጫና እንዲፈጥሩ ነበር። ኦህዴዶች ከደሙ ንጹህ ነን አይነት ጨዋታ ነበር ያሰሉት። ኢህዴግ ለሽ አለላቸው እነሱም የልባቸውን ሠሩ። የፈሩት አልደረሰም። ዛሬ አዲስ አበባን በቀጥታ የሚያስተዳድራት የኦሮሞያ ክልል ነው። ይህ ንጥር ወርቅ ሃቅ ነው። የቀረው የዶሴ ፍርርም ብቻ ነው። 
    የአፍሪካ ህብረት ሆነ ሌሎች ዓለም አቀፈ ድርጅቶች በኦሮምያ ክልል ሥር ናቸው። ግን ተከድኖ። ለዚህም ነው አቶ ሽመልስ አብዲሳ አላስችላቸው ብሎ በዬጊዜው ጫን ጫን የሚያሰተነፍሳቸው። አልቻላቸው አለ። አቅልም ነሳቸው። አቶ ለማ መገርሳም „እኔ ሥልጣን የለኝም ወይ“ ሲሉም አዳምጠናል በነገረ ዴሞግራፊ በመጣው መዘዘ። ቀስ ያሉ ስለሆነ እንጂ ነገረውናል። ጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድም በግልጽ ነግረውናል።
  
ወደ ቀደመው ምልሰት ሲሆን እወነተኛ ተፎካካሪዎች ለመሆን ሁለቱም አቅሙ አላቸው ብዬ አስባለሁኝ ሙሽራው በአዳማ ሥርዕዎ መንግሥት የሚመራው ኢህዴግ እና የባልደራሱ ባለ አደራ። የልብ የመገናኜት መስመር አለው የሁለቱ ጉዳይ። „ስንተዋወቅ እንተናነቅ እንዲሉ“ የባልደራሱ ባለ አደራ መፈጠር ዱብ ዕዳም ነው ለጠቅላይ ሚኒሰተር አብይ አህመድ። 

ምክንያቱም ምርኮኛን በወረፋ ለመቀበል ጊዜ ባጡበት ወቅት ሌላ ፈታኝ ሞጋች አካል ብቅ አለባቸው። ያላሰቡት፤ ያልጠረጠሩት። እናም ሚዛን ላይ ተቀመጡ። ለእኛም እጬጌው ቀን መጋቢት 1 ቀን 2011 ዓ.ም መስታውት ገዛልን። ባገኜው እኔ እህታችሁ ምን የመሰለ የኢትዮ አፍሪካ ምስል ያለበት ሃብል አስርለት ነበር። 

ለዚህም ነው ዶር አብይ አህመድ የሌላው የግልብ ጉዞን „ጦርነት እንገባለን“ ሲሉት ያልተደመጡት፤ እንዲያውም እቅፍ አድርጌ አስረክብኃለሁም አለበት። የሁለቱ ፍላጎት ግን መናበብ ችሏል። ጠሚር አብይ አህመድን ፈተና ላይ ያስቀመጠ ጉልበታም ክስተታዊ ንቅናቄ ነው የባልደራስ ባለ አደራው። ስለ ባልደራስ ሞጋችነት የጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድን ያህል የገባው የፖለቲካ ሊሂቅ የለም። ለዚህ ነው በመንግሥት ደረጃ ታቅዶበት መግለጫዎቹ፤ ስብባዎች ማዕቀብ በይፋ የተጠለባቸው፤ ከዛም አልፎ የሰኔው 15 ቀን 2011 እና የጥቅምት 2 ቀን 2012 የተመሰጠረ ደባ የተወሰነው - የተከወነውም። በትክክል ገብቷቸዋል። ሚስጢራቸው እንደ ተበላ።

ስለዚህም አቅማቸውን አቅም አብቅሎ አንጥሮ ለማውጣት ልካቸው የባልደራስ ባለ አደራው ነው ብዬ አስባለሁኝ። አቅም አለኝ ካሉ ቢያውቁበት ታድለዋል። ጠበንጃውን፤ ሳንጃውንም፤ ሸፍጡንም፤ ጠልፎ መጣሉንም፤ ካቴናውንም፤ ሴራውንም ወደ ተፈጠረበት መልሰው በጨዋ ደንብ ወደ እውነተኛው መስመር መጥተው አቅማቸውን አንጥረው ቢያወጡት የሁሉም ምኞት ነው። ያው ሌላ ሰው የለም በሙሽራው ኢህዴግ አንድ እሳቸው ብቻ ናቸው ሞጋች ሆነው የሚቀርቡት። 

ማን አለ ለመሆኑ? ካድሬም፤ አክቲቢስትም፤ ፕሮፖጋንዲስትም፤ ሞጋችም፤ የደህንነት ሰውም ዕጣ ነፍሳቸውን እሳቸው ነው ያሉት። አሁን ደግሞ ወደ የሚያወግዙት ማህበራዊ ሚዲያ ብቅ ብለዋል። ወጣቶችን ፌስቡክ አትሳተፉ እያሉ። 

ሌላው ብልህ ጉዳይ እኔ ግንቦት ሰባትን ስሞግት በነበረበት ጊዜ ተቀራርባችሁ ስትተያዩ ትተዋወቃላችሁ ብዬ ነበር። አሁን አጋጣሚው አግዞ ለሚስጢረኝነት ስለተበቃ ከሌሎች ጋር አቅም ለአቅም ፊት ለፊት ተገናኝተው ሲፈታተሹ ስለባጁ እኔ እሞግታቸው የነበሩ የተቃዋሚ ድርጅቶች አንቱዎች የአሁን ምርኮኞች የፖለቲካ ድርጅቶችን አቅም ከመጤፍ አይቆጥሩትም ዶር አብይ አህመድ። ንቀዋቸዋል። ለዚህም ነው ልባቸውን ነፍተው 50በ60 ፖለቲካ የጀመሩት።

ለዚህም ነው አቶ ክርስትያን ታደለን ምክንያት ፈልገው ከምርጫው ቀድመው ብለው ሳያስጠጡ ያሰሩት። አቅምን፤ ችሎታን፤ ሞጋች ሃሳብን ፈሪም ናቸው። በሌለው ላይ ሲሆን ነው እሳቸው ማን ችሎኝ የሚሉ፣ በተለይ አማራ ላይ ሲሆን ያዙኝ ልቀቁኝ ያበዛሉ። የኦሮሞ ሊሂቃንማ ከአንድ ቀንጣ ሰው ከአቶ ለማ መገርሳ በስተቀር ማን አለና እሳቸውን ሊመክት የሚችል? አሁን በአንድ መድረክ ሰብሰብ ብለው ስታዮዋቸው ኦነጋውያን ከሊቅ እስከ ደቂቅ የፈረደባት ኢትዮጵያ ያሰኛል። የዕውነት አገር ስንቱን ትሸከም? ቃርሚያ የሆነ ነገር።

·        የባልደራሱ ባላ አደራው የተቋምነቱ ባህሬው።  

እንደ ሥርጉተ ዕይታ የባልደራስ ባለ አደራው የህልውና ተጋድሎ ተቋም ነው። እንደ ገናም የትግልም ድርጅት ነው። የህልውና ተጋድሎው ትግል ያስፈልገዋል፤ የትግል ድርጅትም ትግል ያስፈልገዋል። ለምሳሌ የትግል ድርጅት ኢኃን። አብን የህልውና ተጋድሎ ድርጅት ነው። ሁለቱም ትግል ያስፈልጋቸዋል። የባልደራሱ ባለደራው ግን መንፈሱን ሳዬው የህልውና ተጋድሎውንም፤ የትግልም ድርጅትነትንም አጣምሮ እንደያዘ ነው የሚሰማኝ። በጣምራ ህዝባዊ ህሊናዊ አደራ ውስጥ ወደፊት ጠንክሮ እንደሚቀጥልም አስባለሁኝ። ሁለቱን የትግል ባህሪ ተቀብሎ ከተነሳ ለሁለቱ የትግል ባህሪያት ያለውን የማንነት እና የዲስፕሊን ደረጃ አስጠብቆ መጓዝ ግድ ይለዋል። ስለዚህ ጥምር ጥንካሬን በጥበብ ይጠይቃዋል ብዬ አስባለሁኝ።

ኢትዮጵያን አንድ የማድረግ መንፈስ አምጦ የማስወልድ። ይህ ይመስለኛል የባልደራሱ ባለ አደራ ብሄራዊ ምዕታዊ ጥሪ። ፍርሰት ውስጣችን እያረሰው ነው - ከገባን። ይህን ጠሚር አብይ አህመድም ኢትዮጵያ በውስጣቸው ካለች ልብ ብለው ሊያዳምጡት የሚገባ ጉዳይ ነው። „እግዚአብሄር በአንድም በሌላም ይናገራል፤ ሰው ግን አያስተውልም“ ይላል አካል የሌለው የእግዚአብሄር አገልጋይ ቃለ ወንጌል። አማኝነቱ ለሰብዕና ግንባታ ስሚንቶ አቀባይነት ብቻ ካልተቀጠረ የፈጣሪን ቃል ዕውቅና ቢሰጡት መልካም ነው። መሠረትኩት ባሉት ፓርቲ ብዙ የመርኽ ፍልሰት ስላዬሁ ስለሞገትኩትም፤ ይህ ዕይታዬ ለሳቸው ለሙሽራው ኢህዴግም ይጠቅመዋል። ምንም እንኳን ለባልደራስ ብጽፈውም።
·        የባልደራስ ባለ አደራው ጥንካሬ ምንጩ።

ምንጩ እኔ እንደማስበው …
·        በእግዚአብሄር ፈቃድ መፈጠሩ፤
·       ቅንነት እና ትህትና የበዛበት መሆኑ፤
·       ፈርኃ እግዚአብሄር ፈርኃ አላህን ማስቀደሙ፤
·       ኃላፊነትን ለመውሰድ የሚደፍርባቸው መንገዶች ሰባዕዊነት ወይንም ሰዋዊ ጠረን ያላቸው መሆኑ፤
·       አቅሙ ውራጅ አለመሆኑ። ያልተሞከረ አዲስ አቅም መሆኑ። ስብጥሩም በርህርህና ላይ የሰከነ መሆኑ።
·       ቀለሙ አዲስ መሆኑ። ለእኔ ውኃማ ይመስለኛል። ብሩኽነትም አይበታለሁኝ ለትውልዱ - አድዮ ነገር - ቢጫ። 
·       ማህበራዊ ንቅናቄው እራሱ የፈጠረው ህዝባዊ መሆኑ፤
·       ከመነሻው ቀድሞ ፈተና ውስጥ የነበረ ከተፈጠረም በፈተና ወተት ነጥሮ የወጣም መሆኑ።
·       የተከፋ፤ ባለቤት ያጣ ህዝብ ተሰብስቦ የመረጠው ብቸኛ ተቋም መሆኑ፤

ላቂያነት።

በህልውና ተጋድሎው ትግል እና በትግል ውስጥም ተወጥኖ የመጣው መንፈስ በጀመረው መንፈስ ስለሚቀጥል የባልደራሱን አደራውን የአደራ ማንነት የመሸከም አቅም እንዲኖረው ያደርገዋል። ተለጣፊ የለበትም። በዚህ የህልውና የትግል ተጋድሎ ራሱን የቻለ ዲስፕሊን ስለአለም ዲስፕሊኑን የመሸከም አቅም ይኖረዋል። በተለይ አሁን ወደ ባልደራሱ ባለ አደራ አመራር በሚመጡት ላይ ጥንቃቄ ማድረግ ከቻለ ተስፋ ይኖረዋል። ተስፋው ደግሞ የትውልድ ፓርቲ የመሆን ነው።

አብሶ ከ60ዎቹ የፖለቲካ ሊሂቃን ማህል ካልቀላቀለ ዕድለኛ ይሆናል። ማርክሲዝም ሌኒኒዝም አቅም የሚበላ ዋጮ ፍልስፍና ነው። ወፍጮ። ዕድገቱም የቅንድብ ጸጉር ነው። ትውልድ አማካኝም ነው። ቂመኛም ነው። መንፈሱም እርግጫ ያበዛል። ግጭት ይወዳል። ትዕቢትም መለያው ነው። ስለዚህ ከዚህ መሰል ዲሪቶ መከራ ጋር ፈጣሪ በጥበቡ እንዲታደገው መበርታት ይኖርበታል የባልደራሱ ባለ አደራ።
 
ሌላው ከላይ እንደገለጽኩት በታሪክ በህዝባዊ ስብሰባ የተጸነሰም መሆኑ አንድ ሌላ የተጋድሎ ምዕራፍ ነው፤ በስሌት፤ በቀመር፤ በተለዬ ታክቲክ እና ስትራቴጅ የተፈጠረ አይደለም። ለቀኑ ቀን የሰጠው ዕለት የችግር ቋጠሮ ይፈታል እላለሁኝ እኔ። የሆነው ይኽ ነው። ይህ በራሱ አዲስ ቀለም ነው። ከመጋቢት 1 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮም በእስር፤ በአፈና፤ በመታገት፤ በመገፋት፤ በባይተዋርነት ብቻ ሳይሆን የግራ ቀኝ የሴራ ድርን እዬጣሰ የመጣ ስለሆነ በበሰለ የተጋድሎ መስመር ነጥሮ እንዲጠነክር ሁኔታው አግዞታል ብዬ አስባለሁኝ።

እስከ አሁን እንደተከታተልኩት ተለጣፊ፤ ተዋሽ መንፈስ የለውም። እራሱን እያሳደገ፤ በራሱ ውስጥ እዬተፈተነ የመጣ መንፈስ እራሱን አስብሎ ነው የሚቀጥለው። እራሱ የኮፒ ራይት ችግር አለመኖር ትልቅ እፎይታ ነው። የአማራ የማንነት እና የህልውና ተጋድሎ የገጠመውን ያህል የገዘፈ የፈተና ዳገት የለበትም። ኃብቱ የራሱ ነው። በጽንሰቱም፤ በምጡም፤ በውልደቱም፤ በእድገቱም ውስጥ እሱ እራሱን ያገኘዋል። የእኔ የሚለው የራሱ ታሪክ ያለው ነው። አልተዳበልም። ለኢትዮጵያ የፖለቲካ ህይወትም እንደ አንድ ፈርጣዊ ክስተት ልናዬው የሚገባ ይመስለኛል። ተፈጥሯዊውም ነው። በዚህ አመክንዮ ከኢትዮጵያዊነት አፈጣጠር ጋር በጣም ይመሳሰልብኛል። 
 
·        የባልደራሱ ባለ አደራው ወደ ፖለቲካ ድርጅት የማደግ አስፈላጊነት ሊቀጠር አይገባውም።

እኔ በተደጋጋሚ በአጫጭር ጹሑፎች ስጽፍበት ነበር ፌስቡኬ ላይ። እንጨት ተለቅሞ ሜዳ ላይ የመቅረት፤ የውርንጫ ድካም እዬደከመ ነው የባልደራስ ባለ አደራ እል ነበር። ደክማችሁ ለማን ልታስረክቡት ነው እያልኩ ነበር እምጽፈው። ፈተናው ሌላ ጭልፊት አካል ሲሳዩን መውሰዱ አይደለም፤ መሰረታዊ ጭንቀቴ የነበረው፤ ጠላፊው የባልደራሱን ባለ አደራ ንቅናቄ ማንነት እና ዲስፕሊኑን የመሸከም አቅም አይኖረውም ነበር ስጋቴ። አሁን በእኔ ህይወት ውስጥ እኔን ተክቶ መኖር የሚችል የለም። የአንድ ሰው አሻራ እራሱ ያ ሰው ብቻ ነው። የሰው ኮፒ የለውምና። የተቋም የአፈጣጠር መንፈስም እንዲሁ ነው። 

የብአዴን ችግር ይሄ ነው። ብአዴን አይደለም የአማራ የማንነት እና የህልውና ተጋድሎን ሚስጢራት፤ የአማራነትን ማንነት እና ዲስፕሊን ሥነ - ልቦና እንኳን የመሸከም አቅም የለውም። የሚገርመው ትናንትም ዛሬም አማራነትን እዬተጫነ፤ እየመነጠረ፤ እያስመነጠረ የአማራ የማንነት እና የየህልውና ተጋድሎን መንፈሱን የራሱ ለማድረግ ይጥራል። 

ለራሱ ማድረግ ብቻ አይደለም የሌላ ቅርስ እና ውርስ እንዲሆንም ታግሎታል ተጋድሎውን። ገልጃጃ ድርጅት። ያልቸለው መንፈሱን መጠቅለል ነው። መቼውንም አይችልም። ስለምን? እራሱን ተጻሮ መንፈሱን መሸከም አይቻለውምና። አማራ ጨቋኝ ብሎ የሚያምን ድርጅት ጋር አብሮ ተዋህዶ እዬሠራ እንዴት ብሎ? የአማራ የማንነት እና የህልውና ችግር ፈጣሪው ግንባሩ እራሰ ኢህዴግ እስከ ህገ - መንግሥቱ ነውና።

ስለዚህ በምን አቅሙ ሊሸከመው ይችላል የተጋድሎውን መንፈስ ዲስፕሊን፤ ጥሪ እና ተልዕኮ? አይደለም ለብአዴን ለአብን አመራሮችም ፈተናው አለባቸው። በተጋድሎው ዲስፕሊን፤ ባህሪ፤ ተፈጥሮ ውስጥ ራሳቸውን ቀርጸው ለመውጣት ዕውቅናም እራሳቸው በመስጠት፤ ጊዜም፤ ስልጠናም ያስፈልጋቸዋል። ህይወቱን መኖር። እርግጥ ነው በተጋድሎው አፍላ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ተሳታፊ መሆናቸውን እንደ አንድ ግብዕት ማዬት ይቻላል። ግን ሚስጢሩን በመሆን መቻል ማብሰል፤ ማስበል ይኖርባቸዋል - ሳይሰለቹ። የህልውና ተጋድሎ የወረት ጉዳይ አይደለም። ጽናት እና ዝልቀትን ይጠይቃል።   

ትልቁ ትርፍ የባልደራሱ ባለ አደራ ይህ ችግር የለበትም። ስለዚህ ይህን አቅሙን በውስጡ ላልተወለደው አሳልፎ ሰጥቶ ቢሆን ኖሮ የትውልድ ኪሳራ ነበር። አሁን ወደ ፖለቲካ ድርጅትን ሲቀዬር በጣም የተገባ፣ ብልህ፣ ሥልጡን፣ የዘመን ውሳኔም ነው። ለእኔ እንዲያውም ዘግይቷል ባይ ነኝ - በሰውኛ። እርግጥ መዘግዬቱም የፈቃደ እግዚአብሄር ጉዳይ ነው። እግዚአብሄር ሥራውን የሚሰራበት ቀን አለው እና።

 በሌላ በኩል እንደ ዜጋ የማይታዬው ውጭ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ዜጋ ተሳትፎ መንፈሰም ታክሎም መፈጠሩ ሌላው የሚስጢር ማዕዶተ -  ስጦታ ነው ለዘመናችን። ቅልቅል ሳይሆን ውህድ ወጥ ሆነ። ይህ መታደል ነው። ለዚህ አቶ ኤርምያስ ለገሰን አለማመስገን ንፉግነት ነው። ጉልህ ተግባር ከውኖ ትጋቱን በሙሉ ስኬት ተልዕኮውን አጠናቋል። በፖለቲካ ድርጅት አካልነት አብሮ ለመቀጠል አለመፍቀዱም ቆራጥ ውሳኔ ነው። ልዩ አብነት!

·        የወሰኑትን ማድመጥ አደብ በማፍራት።     
አብን ያሉ አካሎቹ በተጋድሎ ውስጡ በባለቤትነት ሲወጠን በጥንስሱ በተጋድሎው ትዕይንት ህዝባዊ ንቅናቄ መቅድሙ መሬት ላይ ባይገኙም በተቆርቋሪነት ፈቅደው ነው ኃላፊነቱን የተቀበሉት። እንደገናም የተጋድሎው መነሻ ድንገቴ ስለነበረ እንመራለን እያሉ ለተደራጁት ሁሉ ለምሳሌ ዳግማዊ መአህድ፤ አንድ አማራ ወዘተ አቅሙን መሸከም አልተቻላቸውም። ትግሉን እንመራለን ብለው የተሳተፉት አክቲቢስቶችም ቢሆኑ ዲስፕሊኑን ፈቅደው መኖር፤ በህይወቱ መዝለቅ አልተቻላቸውም። በጥቃቅን ሳንክ ተቋረጡ። የተጋድሎ ትግል ፈተናው እንዲህ ይገለጣል። ትግሉ እንደ ተንጠለጠለ ግቡ ሳይታይ ብዙም ገፍተውበት አላዬሁም።

ይህ ለሙሽራው ኢህዴግ የምሥራቹ ነበር። ለዚህም ነው አሁን የተጋድሎውን ተፈጥሮ ዲስፕሊን ፈቅደው በተቀበሉ፤ ለተጋድሎው ታማኝ በሆኑ የአብን አመራሮች ላይ ካቴና የታዘዘው። አቶ ክርስትያን ታደለ ለተከታተለው በዲስፕሊኑም ሆነ በተጋድሎው ተፈጥሯዊ መንፈስ ውስጥ በጥልቀት በግንዛቤ አቅሙ አለበት። ብዙ አጥንቼዋለሁኝ። ለዚህም ነው ከምርጫ በፊት ሰበብ ተፈልጎ የታሠረው። 

በባልደራሱ ባለአደራ የነበረው የአዳማ ሥርዕዎ መንግሥት ተጫኝነትም ይኸው ነበር። ለመበተን ብዙ ተሠርቶበታል። ካቴናውም አልቀረለትም። መንፈሱን ለሌላ ለማስተላለፍም ተደክሞበታል። ወደፊትም ፈተናው ቀላል አይሆንም። መሰናክሉ እስከ ህይወት ሊደርስ ይችላል። የምግብ ብክለቱን፤ የመኪና አደጋውን አክሎ። ስለዚህ ጥንቃቄ ያተርፋል እንጂ ስለማያከስር መጠንቀቅ ይገባል ከፈጣሪ በታች።  ጠሚር አብይ አህመድ ቡፌ ናቸው

በዚህ በተጋድሎ መፈጠር ሂደት ውስጥ አብሮ መዝለቅ ወሳኙ ዲስፕሊን ነው። ከብረት ቁርጥራጭ መሰራትን ይጠይቃል። የሚሳተፉበት ብዙ ነጥረው የሚቀጥሉት ግን ጥቂቶች ናቸው።

·        የህልውና ተጋድሎ በገብያ ህግ አይገዛም። 
  
የህልውና ተጋድሎ ትግል ዲስፕሊኑ በገብያ ህግ አይመራም። ፈጽሞ። የህልውና ተጋድሎም የዝና ኮሮጆም አይደለም። በፍጹም። የህልውና ተጋድሎም የኢጎ ጆንያ አይደለም። በፍጹም። የህልውና ተጋድሎ የጫጉላ ሽርሽር አይደለም። ለገባው የህልውና ተጋድሎ ሰማዕትነት ነው። በድንግልና፤ በንጽህና፤ በፆም - በጸሎት፤ በድዋኣ ታግዞ ትውልድን የማትረፍ ጥልቅ ዓላማ ያለው።

በባልደራሱ ባለ አደራው አስፈላጊነት ላይ ብዙ ተቺ ጹሑፎች አነባለሁኝ። እጅግ አስፈላጊ እና ወቅት የጠዬቀው፤ ተጨባጭ ሁኔታም ያተመለት፤ እግዚአብሄርም የፈቀደለት እንደሆነ በጽኑ አምናለሁኝ። የጋዜጠኛ አቶ እስክንድር ነጋን ወደ ፖለቲካ መስመር ማተኮር የረበሻቸው ወገኖች እንዳሉም አያለሁኝ። ከ100 ሚሊዮን ህዝብ አንድ የእሱ ነገር ይከነከናቸዋል። ዓይነ ጠባቦች። ስግብግቦች።

ቀድሞውንም እኮ „ድል ለዴሞክራሲ“ ፖለቲካ ነው። ዕውቀቱም ፖለቲካል ሳይንስ ነው። ተጽዕኖ ፈጣሪነቱ ይቀንሳል የሚሉም አሉ። ለተጽዕኖ ፈጣሪነት ነውን ሰው የሚታገለው? እንደዛ ከሆነ የነፃነት ትግል ለእኔ የገብያ ውሎ ነው፤ የነፍስ ሽያጭ እና ግዢ አድርጌ ነው እምመለከተው። 

ምንድን ነው ክብር? ምንድን ነው ዝና? ትውልድን ከማስቀጠል - ከሰባአዊነት - ከርህርህና - ከፈርኃ እግዚአብሄር፣ ፈርኃ አላህ ይበልጣል ወይ ይሄ ዝና፤ ተጽዕኖ ፈጣሪነት ወዘተ የሚባለው ጉድ? ለክብሩ ቢሳሳ ይህን ሁሉ ውርጅብኝ ሊሸከም ባልፈቀደ ነበር። ቤቱን ዘግቶ ይቀመጥ ነበር። 

ሌላው ህሊና ወዴት ነህ የሚያሰኜን ቁም ነገር እሱን ከአቶ ጃዋር መሃመድ ጋር የሚያፎካካሩት ብዕሮችና ብራናዎች ናቸው። ማለካካት የሚቻለው የሚመጣጠኑ ነገሮችን ነው። የማይገናኝን ነገር ማለካካት አይቻልም። ሰማይን መለካት ይቻላል፤ መመተርስ እንደ ጨርቅ ይቻላልን?! 
·        ቁምነገር።

የባልደራሱ ባለ አደራ ወደ ፖለቲካ ድርጅት መሻገሩ እራሱ ለአመራሩ ህልውናም ጥቃቱን ይቀንሳል። የደህንነቱም ዕውቅናውም ከፍ ይላል። ባለ ድምጽ ይሆናሉ። ድምጽ የሰው ህይወት ወሳኙ የነፍስ ጉዳይ ነው ለ21ኛው ምዕተ ዓመት። ከተናጠላዊ ትግልም ወላዊ ትግል ተመራጭ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ እሱ እራሱ ጋዜጠኛ አቶ እስክንድር ነጋ ይፈተናል። እስከ አሁን ፈተና ውስጥ አልነበረም ማለቴ አይደለም። በፖለቲካ መሪነት ማለቴ ነው። ባለፈውም ጽፌያለሁኝ። 

በደጋፊዎቹ፤ በአድናቂዎቹ ዘንድ በሁሉም መስመር በፖለቲካ መሪነት ተፈትኖ መውጣት ይኖርበታል። ጠሚር አብይ አህመድ ይሁኑልን አለን - ተመኜን፤ ጸለይን ቅኖች። ደከምንበት። ሆኑበት እና አዬናቸው። በቃ! አሁን በውስጤ የሉም። እንደ እኔ ስለ እሳቸው የሞገተ የለም። ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋም ዕድሉ ይሰጠው እና ይታይ። ፈተና ነው። ፈተናውን ከወደቀ በውስጥነት፤ በተስፋነት መታሰቡ ይሰናበታል። ልብ ጉዳዩ ነው ያሰናብተዋል በቆራጣ ሰንበሌጥ ቀላጤ። ብዙው የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች የጸሐይ ያህል ይታሰቡ ነበር። አገር ተገባ ታዩ። ማዬት መልካም ነገር ነው። የፖለቲካ ትግል የአዬር ላይ ውሎ አይደለም። ፖለቲካ በሞገድ ፕሮፖጋንዳ ወይንም እንደ ነፋስ ፍጥነት በአኒሞ ሜትር አይለካም።

የፖለቲካ ትግል መቀመጥን ይሻል። ቁጭ ብሎ አርቆ በጣም እርቆ ማሰብን ይጠይቃል። አዲስ ሃሳብን ማፍለቅ ይጠይቃል። መተንበይን ይጠይቃል። ማቀናጀትን ይጠይቃል፤ መፍትሄ መሆንን ይጠይቃል። አቅምን በአግባቡ ማስተዳደር ይጠይቃል። መንገድ መቀዬስን ይጠይቃል - ምህንድስና። መቻቻልን ይጠይቃል። ቀድሞ መገኜትን ይጠይቃል። ከሁሉ በላይ ሰው መሆንን ይጠይቃል። 

ሰው መሆን ገባርዲን መልበስ፣ ከረባት ማሳር አይደለም። ሰው መሆን እርህርህና ነው። ሰው መሆን ፈርኃ እግዚአብሄር፣ ፈርኃ አላህ ነው። እግዚአብሄርን ስታከብር ሰውን ማክበር ትችላለህ። አንድ የአገር መሪ እጩ አቻውን ተፎካካሪ አንተ እና አንቺ ሲል በቃ ከደረጃው ይወድቃል። ትናንት ስለሰው መብት ጥሰት ከቆረቆረህ ዛሬም ከጨረቃ የመጣ ሰው አይደለም ኢትዮጵያ ላይ በሚዘገንን ሁኔታ በአሮጌ ቆርቆሮ ተገዝግዞ እዬሞተ፤ እዬተንገላታ፤ እዬታሰረ፤ እዬታገተ ያለው። ግን ሰው መሆን በሰውኛ ከተፈጠረ ነው በሰውኛ መንፈስ ቋሚ ሰብዕነት መሆን የሚቻለው። ወዘተ …

·        አምልኮተ ሰው።

የኢትዮጵያ የፖለቲካ ድርጅቶች ሲመሠረቱ አምልኮተ ሰው ሆነው ነው። መሥራቹም የጸጋ ስግደት ካልተሰገደለት አይሆንለትም። ገና ሲፈጥረው ደርጅቱን አንባገነን በማድረግ ነው። ከእኔ በላይ ማን አለ ብሎ። የሰሞናቱን የ50በ60 የአብይዝም ቲወሪ ለናሙና መውሰድ ይቻላል። 

ይህን ያመለከ አንዲት ፈተና ብቅ ስትል እንኩትኩቱ ይወጣል ተጠላዩ ሁሉ። ኢሠፓ አምልኮተ ሰው ስለነበረበት ኮነሬል መንግሥቱ ኃይለማርያም አገር ጥለው ሲወጡ ለዘር ሳይተርፍ እራሱን አከሰመ፤ ቅንጅትም በመሰሉ ሁኔታ መራራ ስንብት አደረገ፤ ህወሃትም ቢሆን በሄሮድስ መለስ ዜናዊ አምልኮት ሥር ወድቆ ስለነበር እሳቸው ካለፉ በኋላ የሆነውን በማስተዋል ቢመረመረም ቁልቁል ነው የተጓዘው። አሁን በተመሰረተበት ቀዬ ላይ ብቻ ተውስኖ ቀረ።

 የወደፊት የአገር አውራ ሆኖ የመምራት ተስፋውም ጥንዙል ነው ለህወሃት። የህወሃት የሰሞናቱ የንብረት ክፍፍል ጥያቄ ላይ መቸከሉ እራሱ የፓለቲካዊ አቅሙን ሚዛን መክሳቱን ያሳያል። ጨርቅ ነው የሆነው። ቁስም ነው የሆነው። እንግዲህ በድርጅቱ ውስጥ የተሰዉትን የሚያውቁ እነሱ ናቸው። ክብሩን ለማስጠበቅ ዕቃ ከፈላ ላይ ወርደህ ስትገኝ ምን ይባላል? መርኽን - መንፈሳዊ ዕሴትን ትተህ። ቢያንስ በኢህዴግ በአውራ ፓርቲነት የተመራው የባድመ ጦርነት እና የጠፋው የሰው ህይወት እንዴት ትዝ አይልም? ሱማሌ ላይስ አገርን ወክለው ለሶልዳሪቲ የሄዱት ዜጎችስ እዛው የተሰዉት የት ይመደቡ?

የሆነ ሆኖ በኢትዮጵያ ፖለቲካ የጸደቀ፤ የዘለቀ፤ ያሸተ፤ ያፈራ፤ ያሰበለ የትውልድ ሮል ሞዴል የሆነ የፖለቲካ ሊሂቅም፤ የትውልድ ይሆናል የሚባል የፖለቲካ ድርጅትም አይተን አናውቅም። ተስፋ አያልቅም እና ተስፋ እራሱ ግን ምንግዜም ይጠበቃል።

ሌሎችንም ብታዮዋቸው እንዲዚሁ ነው …  አሁን የኦሮሞ ፖለቲካ በአቶ ጃዋር መሃመድ ሰብዕና ላይ የተገነባ ነው። እሱም ጊዜውን ቆጥሮ ለሽ ይላል። እሱ አንድ ነገር ቢሆን ያበቃለታል። ወይንም እሱ ትግሉን ትቶ ወደ ሌላ እራሱን ቢቀይርም እንዲሁ ክስመት ነው። ከሰሞናቱ ብልጽግና ነኝ ብሎ በተፋለሰ የፓርቲ የአደረጃጃት መርህ ተወለድኩ ያለውም ሙሽራው ኢህዴግ 50በ60 ቲወሪውን ስታስቡት ከላይ እንዳነሳሁት እኔን ብቻ አምልኩ ነው። 

ተመላኪው የሰይጣን ጆሮ ይደፈን እንጂ አንድ ነገር ቢሆኑ፤ እሳቸውን አምኖ የተጠለለው የቤተ - መንግሥት ቅልጠመኛውን ጨምሮ ሁሉም እንደ አውሮፓ የክረምት ቅጠል ይረግፋል። ሌላው ቀርቶ ዲስፕሊኑ ጠንካራ የነበረው ኢህአፓን እንኳን ስናይ ከስንት እንደ ተሰነጣጠቀ ታሪክ አስተምሮናል። የዚህ ችግሩ የራስ ንጉሥነት በሽታ ነው። ሰዋዊ አምልኮ ነው።

ሁሉም ንጉሥ ለመሆን፤ ለመመለክ ይሻል። በዚህ ማህል ትውልድ ይባክናል። ትውልድ መኖሩን ይቀማል። እስከ አሁንም በኢህዴግ እስር ቤት ያሉ ታጋዮች አሉት ኢህአፓ። ለሰውኛ አምልኮ ደግሞ እኛው ነን የሰብዕና ግንባታውን በገፍ እምናበጀው። ሲሚንቶ፤ አሽዋ፤ ኮርኒስ፤ ቀለም አቀባዮች እኛው ነን። በልክ አንይዘውም። ሰለዚህ ካለፈው ግድፈታችን ከተማርን ተቋማትን፤ ድርጅቶችን አጉልቶ በመርኽ፤ በዕውነት፤ በዓላማ እና በግባቸው ዙሪያ መጽናታቸውን፤ ለውጤት መብቃታቸውን የምንመዝንበት አዲስ ባህል መጀመር አለብን ብዬ አስባለሁኝ። የትውልድ ብክነትን ማስቆም የሚቻለው በዚህው ነው። እምናመልከው የድርጅቱን መርኽና የዕውነት አቅም መሆን ይኖርበታል። 

ስለዚህ የባልደራሱ ባለ አደራው ንቅናቄ በፍጹም ሁኔታ ከዚህ መሰል አመሰራረት እራሱን ማጽዳት ይጠበቅበታል። መሆን ያለበት፤ ሊሆን የሚገባው መሰረታዊ ጉዳይ ባለ አደራው ግልጽ በሆነ ዓላማው እና ግቡ ዙሪያ ብቻ አባላቱ፤ ደጋፊዎቹ እንዲተማመኑ አድርጎ መነሻውን ማሳመር የሚገባው ይመስለኛል። ሊታመን የሚገባው ተቋሙ፤ ፖለቲካ ድርጅቱ /ንቅናቄም፤ ፓርቲም ሆነ/  እንዲሆን አድርጎ መነሻ መሰረቱን ማሳመር ይገባዋል። 

በፍጹም ሁኔታ የባልደራሱ ባለ አደራው በግልሰቦች ተጽዕኖ ፈጣሪነት ብቻ ከተንጠለጠለ የትውልድ ፓርቲነቱ ሳይፈጠር ይመክናል። ከዚህ በራቀ፤ ከዚህ በቀደም፤ ከዚህ በበሰለ በአዲስ የፖለቲካ ባህል ሁኔታ መፈጠር አለበት። ይህ ቀላል ይመስላል እኔ ስጽፈው ነገር ግን 60 ዓመት ሙሉ የኢትዮጵያን ትውልድ አጭዶ፤ መቅኖ አሳጥቶ ያመከነ ጉዳይ ነው። እስከ አሁንም ያለ እናም መቋጫም ያልተበጀለት።

ሚዲያዎችም፣ ጸሐፊዎችም እባካችሁ ከሰብዕና ግንባታ ወጥታችሁ የድርጅቱን ተግባር እና ኃላፊነት እንዲሁም ውጤቱን እያያችሁ በእሱ ላይ ብቻ ሥሩ // እንሥራ። ይህ ችግርም ነው በዬዘመኑ የትውልዱ ተስፋ ካቴና እዬሆነ፤ ተተኪ እዬመከነ፤ አማራጭ እዬከሰለ ለዘር የሚጠራ፤ ተስፋ የሚጠጋበት ተቋማዊ አጥር ቅጥር መጠጊያ የታጣው። እንደ አገር ተዋርደናል። ኢትዮጵያ ከአፍጋኒስታን፤ ከዬመን ተራ ሦስተኛ ደረጃ ላይ ስንሆን ዕንቅልፍ ይወስዳልን?  እኔ አልቅሻለሁኝ። ይህ የባልደራሱ ባለ አደራ አንጎል ጉዳይ ሊሆነው ይገባል።

 ለመሞታችን መንገድ መጀመራችን ዓለም አወቀው። የኖቤል ሽልማቱ አልሸፈነውም ገመናችን። ውስጣችን እናዳምጥ። ሪፖርቱ ለብሄራዊ ምርጫ ቦርድም ትልቅ መዶሻ ነበር። ታአማኝነቱን ይቀንሰዋል።  

የባለ አደራው አድናቂ፤ ደጋፊ፤ አባላትም ቢሆኑ በዓላማው እና በግቡ ዙሪያ በተቋሙነቱ ጥራት እና ጥንካሬ፤ በይዘቱ ክህሎት እንጂ በሰው አምልኮ ከተጠመዱ የድርጅቱን ህይወት እራሳቸውን እራሳቸው ይንዱታል። ይህ ሊሠራበት የሚገባው ጉዳይ ነው። እራስን ማሸነፍ ይጠይቃል። አሁን አብሶ ዴያስፖራው የሰጠው ፍቅር እና አክብሮት እንዳይደፋ የባልደራሱ ባለ አዳራው በሚመሰረተው የፓርቲ ዲስፕሊን እራሱን ለማስገዛት እራሱን አሸንፎ አህዱ ማለት ይኖርበታል።

በተለይ የአባላት ምልመላ ሂደቱን ከብዛት ጥራት ላይ፤ ከቁጥር የህሊና አቅም ላይ፤ ከታይታ ይልቅ ውስጥነት ላይ ማተኮር ይኖርበታል። ይህ ማለት ግን ሰብዕናው የተሟላ፤ ዝልቅ ጽናት ያለው፤ ፈርኃ እግዚአብሄር የሰፈነበት፣ አንከር መታመን የሚችል መሪ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን የባልደራሱ ባለ አደራ ማግኘቱ ልዩ ሽልማት መሆኑን ዘንጉት አይደለም። መስጥሮ፤ ከድኖ መያዝ ይቻላል። 

በጸሎትም መርዳት። በልባችን ውስጥ ትንሽ ሙዳይ አለች። እዛ ይሁን ቦታው። ተገቢውን አክብሮት ለአገር ሃብት መስጠትም ይገባል። የፈቃደ እግዚአብሄርም ስጦታም ነው እኔ ሳስበው። ዜሮ ላይ ነው የነበርነው። ተስፋችን ፍሪጅ በረዶ ቤት ውስጥ ነው የነበረው። „አድርገህኛል እና አመሰግንህ አለሁ“ ይላል ልብ አምላክ ዳዊት።
  
የሆነ ሆኖ ያላፍንበትን ጉዞ ችግር ነቅሶ በማውጣት የትውልዱን መንፈስ ከብክነት ለማዳን፣ ማግሥት ሲታሰብ፣ ነገን ሊያዘልቅ በሚችል የትውልድ ፓርቲ ላይ አቅምን ማጠራቀም የተሻለ መንገድ ነው ከሚል ዕሳቤ ነው ሃሳቡን ያነሳሁት። አዲስ ባህል እንፍጠር። ያው ሙሉ ዕድሜዬን ያሳለፍኩበት፤ የሰለጠንኩበት፤ የሰራሁበትም ይኽው ነገረ ፓርቲ ስለሆነ ከውስጤ የታዘብኩትን ነው የገለጽኩት። ሃሳቡ ለሌሎችም የፖለቲካ ድርጅቶች ከተጠቀሙበት ያገለግላል። አገርም ትውልድም ማዳን የሚቻለው የሚችሉትን በማከፈል ነውና። አድማጭ ከተገኜ። 
·        መታመን።

በባልደራሱ ባለ አደራው ላይ ጥርጣሬ የሚፈጥሩ አስተያዬቶች ከዚህም ከዚያም አያለሁኝ። ባለ አደራው ሊጠለፍ ይችላል የሚሉ ነገሮችን አነባለሁኝ። ስለዚህ ባለ አደራው ግልጽ ጉዞውን ለህዝብ ባልተትበሰበሰ ሁኔታ ማሳወቅ ይገባዋል። ከማን ጋር ሊቀጥል እንደሚፈልግ። በስተቀር ግን ሁሉም የደረሰውን መለመላነት እሱም እንዳይደርስበት ከሚሰጉ ቅን ወገኖቼ ነው እኔ ይህን ዕይታ የማነበው። ምኞቱ ባይሳካ ከሁሉ በላይ የትውልዱ ተስፋ ይበርደዋል። ትውልዱ ስንት ጊዜ ይበደል? ስንት ጊዜስ ያልቅስ? ስንት ጊዜስ የእኔ የሚለውን መንፈስ ይዘረፍ? ስንት ጊዜስ ይቀጣ? ጥንቃቄ መልካም ነው። ያተርፋል።

ባለ አደራው ለህዝብ ታማኝ መሆን ካልቻለ ስኬቱም መክኖ ይቀራል። መታመን ለአንድ ድርጅት ቀይ የደም ሴሉ ነው። የባለ አደራው ተጋድሎ ቀደም ብዬ እንዳነሳሁት ሁለት ነገር አጣምሮ ነው የተነሳው የህልውና ተጋድሎ ትግል፤ የዴሞክራሲ ትግል። 

አብሶ የህልውና ተጋድሎ ትግል ከመደበኛው ለዴሞክራሲ ከሚደረገው ትግል በብዙ ሁኔታ ይለያል። ሁለቱም መስዋዕትነትን ቢጠይቁም የህልውና ተጋድሎ ትግል የሙሽርነት ሽርሽር አይደለም። የኬክ ቆረሳም ትግል አይደለም። የመወድስ የዜማ ቋትም አይደለም። መራራ ነው እጅግ። ይህን ጽዮናዊነት ማጥናት ይጠይቃል። አልታወቀም እንጂ አዲስ አበባ ወረራ ላይ ናት። ልክ እንደ ጠላት አገር ነው እርምጃ እዬተወሰደባት ያለው። እርግጥ አረቂቅ እና ጥልቅ፣ በከፍተኛ ሚስጢር የተያዘ ጉዳይ ነው። 

የሆነ ሆኖ በዚህ ውስጥ የሚሳተፉ ታጋዮች ከድርጅቱ የሚጠብቁት ወሳኝ ጉዳይ፤ ድርጅቱ ለተነሳበት ዓላማ እና ግብ እስከ መጨረሻው ሊያታግላቸው ስለመቻሉ የተግባር ማረጋገጫ ይሻሉ። ስለዚህም የባልደራሱ ባለ አደራው ይህን በመሆን መታመንን አፋፍቶመታመንን አጬግይቶ ሊያሳይ የሚገባው በኽረ ጉዳይ ሊሆን ይገባል። 

እስከ አሁን ባለው እኔ የሚሳማው ነገር አላዬሁም። እርማት ሲሰጠውም ያርማል። ለወደፊቱ ይመስለኛል ስጋቱ የአስተያዬት ሰጪዎች። ስጋት አለን ያሉ ወገኖች ሲገጥሙ ቀርብ አድርጎ ማወያዬት ይገባል። ሃሳቡን መፍራት አይገባም። እኔ ሁልጊዜ እማደርገው ይህንኑ ነው። በተረዳሁት ልክ አስረዳለሁኝ።

·        ጥንቃቄ በባልደራሱ የፖለቲካ አመሰራረቱ እና በቀጣይ ጉዞው ላይ።

(1)         በምንም ሁኔታ ለስብጥር ብሎ ውራጅ ማንነትን ቀይጦ ወይንም ደርቦ በማስጠጋት ድርጅቱ ከተፈጠረ - ሳይፈጠር ያከስማዋል። ይህ በቀላል አገለላጽ ዲዲቲ ነው። ለዚህም ለድርጅት ጉዳይ የሚመደበው ሰው ምርጫ ጠንቃቃነት እና ብቃት ሰፊ አትኩሮት መስጠት ይገባል። ድንግል መንፈስ ሊሆን ይገባል። ከዬትኛውም ድርጅት ያልነበረ፤ ያልተለካለከ መንፈስ ቢሆን ይመረጣል። ያ ካልሆነ ዲስፕሊኑን የመሸከም አቅም ያንሳል።

(2)         በፖለቲካ ሊሂቃን የማዬው የህዝብ ንቀት አለባቸው። ህዝብን ያቃላሉ። የባልደራሱ ባለ አደራው በታሪክ እራሱ ህዝብ ተሰብስቦ የፈጠረው ተቋም ነው። ወደ ፖለቲካ ድርጅት ሲቀዬር መነሻውን እንዳይረሳ በአጽህኖት ላሳስበው እሻለሁኝ።  የኢትዮጵያ ህዝብ ሁለመናውን የሰጠ ግን አንድም አደራውን አክብሮ የተወጣለት የቃልኪዳን ልጅ ያለገኜ፤ የተገፋ ህዝብ ነው። አይዞህ ባይ እንኳን ያለገኜ። አይዞህ ትልቅ ነገር ነው። 

    በመከፋቱ፤ በዕንባው፤ በመሰዋዕትነቱ፤ ኑሮውን በመቀማቱ ውስጥ ሆኖ አይዞህ፣ ቀኑን ተረዳድተን እናሳልፋለን ሳይሆን ንቀት ነው እማስተውለው። ውስጤ ያዝናል። ስለሆነም ባለ አደራው የዚህም አደራ እንዳለበት የቅድሚያ የህሊናው የቤት ሥራ ሊሆን ይገባል ብዬ አስባለሁኝ። ህዝብ ይከበር! 

(3)         የራስ የቀደመ ሃሳብ መኖር ግድ ይላል። የራስን ሃሳብን ለመግለጽ ደግሞ በማበከን ሊሆን አይገባም። ቆጥቦ ማስተዳደር ይገባል። ዝርግነት አዋጪ አይደለም። በተፈላጊ ቦታ፣ በተፈላጊ ጊዜ ብቻ መግለጥ። አሁን በዚህ ላይ አብን ተሸውዷል። ጥሩ ጥሩ ሃሳቦችን እንዲሁ ነበር በርካሽ ሲያቀና የነበረው ያለ ዋጋ - በነፃ። በፉክክር ጊዜ ቆጥቦ ማቅረብ ይገባው ነበር። በሌላ በኩል ሌሎች የወደቁበትን ሬሳ ሃሳብን አለማስተናገድ ይገባል። እያንዳንዱ ድርጅት የወደቀበትን መንስኤ ማጥናት የተገባ ነው። 

(4)         የትውስት አቅም ላይ ተጠማኝ ከሆነ ድርጅቱን ሳይፈጠር እንዲጨነግፍ ያደርገዋል። በራስ አቅም ላይ ብቻ ማቀድ መቻልን እንደ ባህል መውሰድ ይገባል። ይህ አሁን ተመሰረትኩ ያለው ብልጽግናም ሙሽራው ኢህዴግ ሆነ የቀድሞው ግንቦት 7 መሰረታዊ  የዓላማ ማስፈጸሚያ ወሳኝ ሞተር የነበረ ጉዳይ ነበር። ተጽዕኖ ፈጣሪን እያሳደዱ መልቀም። ተጽዕኖ ፈጣሪውን ከነጓዙ ትቀበላለህ፤ ያን የምትቆነጥጥበት መሳሪያ ስንዱነት ግን የለም፤ በቃ ተያይዞ ገደል። ተጽዕኖ ፈጣሪው ወይ ጥሎ ይወጣል ወይ የተገባው ክብር አልተሰጠኝም ብሎ አኩርፎ ተራራ ያክላል፤ ስለዚህም እሱን በማቆላመጥ ጊዜው ያልቃል። 

    ጥሎ ሲወጣም የተገነባው ቤት ቆርቆሮው ያፈሳል። ከዚያ ለፈሰሱ ውሃ ማጠራቀሚያ ፋጋ ወይንም ጢሽት ፍለጋ መባዘን። ስለሆነም መታመን በራስ አቅም ብቻ መሆን ይገባዋል ባልደራሱ። ተጽዕኖ ፈጣሪ ለቀማ ላይ ማተኮር አይኖርበትም። ዲስፕሊኑንም መሸከም አይችልም የሚጨመረው ተጽዕኖ ፈጣሪ። ብዙ ቀላዋጮች አዘናጊ መንፈሶችም አሉ። አብን በዚህ መስመር አለመሄዱ ያስመሰግነዋል። 

(5)         የባልደራሱ ባለ አደራ አመራር አካላት ከሌላ ድርጅት የኮበለሉ ሰዎችንም ካካተተም እንዲሁ ተስፋውን ያጠነዝለዋል። ምክንያቱም ሌላ ማንነት፤ ሌላ ዲስፕሊን ይዘው ስለሚመጡ የማንነት ቀውስ ይፈጠራል፤ ፈተናውንም ያበዘዋል። ከገቡ በኋላም ተጫኝ ወይንም አፈንጋጭ ይሆናሉ። አሁን የአብን ፈተና አንዱ ይሄ ነው። አብን አንጃ ያሰጋዋል ብዬ ሁሉ የጻፍኩት ከዚህ መሰረታዊ አመክንዮ ተነስቼ ነው። ይህን ሲመሰረትም ጽፌበት ነበር።

     አንድ የፖለቲካ ድርጅት ፓርቲ አመሰራረት ላይ እሸት በሆነ ሰብዕና እንጂ ተጠማኝ ሆኖ መሆን አይኖርበትም። የአዲስ አበባው የፖለቲካ ተፈጥሯዊ በባህሬው ልዩ ስለሆነ ብርቱ ጥንቃቄን ይሻል። ብዙ በጣም ብዙ አቅም ያላቸው ወገኖች አሉ። አዲስ አበባ የሁሉም አቅም መናህሪያ፤ ምንጭም ናት።

(6)         ሥነ - ምግባር በተለይ አመራር አካላቱ ምርጫ ላይ ሥነ - ምግባር፤ ሞራላዊ ዕሴት ወሳኙ መስፈርት ማድረግ ያለባቸው ይመስለኛል። የፖለቲካ ድርጅቱ የሰብዕና አቅም ተኮር ሊሆን ይገባል። አውሮፓ ላይ ከ10/ 15 ዓመት በፊት ሞዴሎች በቅርፃቸው እና የሞድ አቅማቸው ነበር የሚመረጡት፤ አሁን በሰብዕናቸው ነው የሚመረጡት። 

     ቃለ ምልልስ በማድረግ፤ የቡድኑ መሪ በማድረግ ይፈተኗቸዋል፤ ኃላፊነትን እንዴት እንደሚያስተናግዱ ይመዝኗቸዋል። ያው እኔ የዬትኛውንም አገር የትውልድ ተስፋ ላይ በሚሰሩ ቅን ተግባሮች ላይ አትኩሮት ሰላለኝ በመደበኛ ነው እምከታተላቸው። ስለዚህ ሰብዕና ዋንኛ መስፈርት ቢሆን የባልደራሱ ባለ አደራ የትውልድ ፓርቲ የመሆን ተስፋው መሰረት ይጣልለታል ማለት ነው። 
  
(7)         ወጣ ገብ አቋም ያላቸውን ድርጅቶች፤ ግለሰቦች ጋርም ጎጆ አብሮ መጀመር ያው የትውልድ ብክነት ሌላው መከራ ነው። በራሳቸው ዓላማ ያልጸኑ ሰዎች አትራፊ አይደሉም። ስለዚህ 27 ዓመት ቀላል ስላልሆነ ባልደራስ ከዛ 27 ዓመት ተመክሮ ተምሮ ጥንቃቄን፤ ጥራትን ቅደመኝ ማለት ይገባዋል። ጽኑ አቋም ነው ሰው ሊለካበት፤ ሊመዘንበት የሚገባ። በዚህ መስፈርት መቼም መውደቅን አልጠብቅም። ተመክሮው ሁሉ ለዚህ መሆን ያለበት ይመስለኛል።

(8)         ከፈረሰ ነገር ትምህርት አለ ግን አፍርሰኝ ብሎ በመፍቀድ አይደለም። የተጠጉት ሁሉ ሲፈርስ ከኖረ መንፈስ ጋርም ቢሆን ትርፈ ቢስ ድካም ነው። እራስን ለማስፈረስም አንዱ የቢዛ ፋስም ነው። ስለሆነም ገንቢ ከሆነ መንፈስ ጋር አቅምን ማቀናጀት አትራፊ ይሆናል። የክብር የመመጣጠን ጉዳይም አለ። በህሊና ውስጥ ያለ ዕባጭ ነገር አለ። ሁሉንም ፈትሾ በማስተዋል መራመድ የሚገባ ይመስለኛል። በቅንነት መለኪያነት

(9)         ከሌሎች ድርጅቶች በኩረጃ ላይ ከተነሳማ ውርጃ ይኖራል፤ ሌሎች ስላደረጉት እኔም ልሞክራው ዓይነት የተገባ አይደለም። ጨዋታው የዳማ አይደለም። ፖለቲካ ሰው በሥነ - መንግሥት ክህሎት የሚታነጽበት ፍልስፍና ነው። ስለዚህም ሰውን መሞከሪያ ጣቢያ ማድረግ ወንጀል ብቻ ሳይሆን ሃጢያትም ነው። በራስ ማንነት፤ በራስ ዲስፕሊን፤ በራስ ተፈጥሮ ውስጥ መቀጠል ነው ሊያዘልቅ የሚችለው።

(10)      የቅልጣን፤ የዘመናዊነት መንፈሶችን አስቀድሞ መቅጣት ካልተቸለም ዓላማው ከግብ ሳይደርስ ያሰናክልበታል። በፖለቲካ ድርጅቶች በጣም የባዛ ቅልጣን አያለሁኝ። የሰው ህይወት ቀሎ ነው እማዬው። ለሰው ልጅ ክብር የተገባው ቦታ የለውም የኢትዮጵያ ፖለቲካ። የሰው ልጅ እንደ ጌሾ በዬጓሮው የሚሸመጠጥ ነው የሚመስላቸው። 

    አሁን የጠሚር አብይ አህመድ የ11/11 የአዋሳ መከራ ተደቅኖ የኤርትራ ጉዞ፤ ለህዝቡ ምንም ዋስትና ሳያሰናዱ „የሁለት አገር ዜግነት“ ወቃሳ ክብሪት እናም የራሺያ ጉዞ፤ ወዘተ ሲታይ ለሰው ነፍስ ግድዬለሽ የመሆን ነው። ለተቋማት ውድመትም ደንታ ቢስነት ነው። ተቋማት የትውልድ ቅርስ ናቸው። የማግሥትም የቱሪዝም ኢንደስትሪ ዓይነተኛ መሰረቶች ናቸው። ትናንት እንዴት እንዳለፈም የሚያስተምሩ ቋሚ ሐዋርያት ናቸው ለቀጣዩ ትውልድ። ኃላፊነት እና ተጠያቂነት የሚሰማው መሪ ላለው ህዝብ። ኃላፊነት እና ተጠያቂነት ለሚሰማውም የፖለቲካ ሊሂቅ።

(11)      በጎሼ እሰጣ ገባ፤ በቆዬ ቁርሾ፤ በባጀ ቂም በቀል ከሌሎች ድርጅቶች እና ደጋፊዎቻቸው ጋር በተቃርኖ ውስጥ ከዳከረም ለራሱ ዓላማ ብክለትም፤ የጊዜ እጥረትም ይገጥመዋል። አቅምን፤ አዲስ ሃሳብንም ክስረትም ይፈትነዋል። መልስ መስጠትም አያስፈልግም። ሥራው እራሱ መልስ እንዲሰጥ አድርጎ አንጥሮ ማውጣት ያስፈልጋል። 

(12)      አቅምን የራስን ኮትኩቶ በማብቀል፤ በማጎልበት እረገድ በአቅም ፈጠራ ላይ አተኩሮ መስራት ይጠይቃል። አብሶ የህሊና ብቃት። ተተኪዎችን በዬጊዜው የማፍራት ጉዳይ ቸል ሊባል አይገባም። አሁን በዚህ ላይ ፕሮፌሰር መራራ ጉዲናን ማንሳት እሻለሁኝ። በዚህን ያህል ዘመን እሳቸውን የሚተካ አንድስም እንኳን ሊሂቅ ማፍራት አልቻሉም። 

     እሳቸውን እማነሳው የፖለቲካ ሳይንስ ሊሂቅ እና መምህርም ስለሆኑ ነው። አቅም ያላቸውን ነፍሶችን የባልደራሱ ባለ አደራ የፖለቲካ ድርጅት መፍራት አይኖርበትም። በዬትኛውም ሁኔታ የሚበልጡ ወጣቶች ሊኖሩ እንደሚችሉ አምኖ መቀበል ይገባል። ስለዚህ ለወጣቶች ዕድሉን እዬሰጡ ወደፊት ማምጣት ግድ ነው። ወጣቶች ተበድለዋል። 

     ሦስት ትውልድ ሲቀለድበት ነው የኖረው። መኖሩን እዬተቀማ። የአብይዝምን ዘመን እማልወቅስበት እማመሰግንበትም ቁምነገር ሚዲያ ላይ ያለው ፈቃድ የትውልዱን አቅም እንዳዬው አድርጎኛል። የት ላይ የሰከነ አቅም እንዳለ። የት ላይ ደግሞ ገለባ ላይ ሆኖ ፉከራ እንዳለ። 

     በዚህ ምክንያት ተኮፍሶ ጨረቃ ላይ የነበረው የተነፈሰ ጎማ ሲሆን፤ አንገተ ደፋታ አቅሞች ደግሞ የውስጥነት ሃብት ስለመሆናቸው ስናይ መጽናናትን ማግኜት ሁሉ አስችሎናል። ስለዚህ ለእነዚህ የአገር አቅሞች እውቅና እዬሰጡ፤ ሃላፊነት እዬሰጡ፣ በልጠው ቀድመው ይወጡ ዘንድ ሁኔታውን ማመቻቸት ይገባል። አገርም በአቅም ትጠቀማለች። አቅም እንዳይወጣ ቀዝፎ መያዝ  የኢትዮጵያ ፖለቲካ ባህል ወረርሽኝ ነው። በዚህ ላይ አብን ጥሩ ሞዴል ነው።

(13)      ሴቶችን በማሳተፍ እረገድ ሴት ስለሆኑ ብቻ መሆን የለበትም። አሁንም እማነሳቸው ፕሮፌሰር መራራ ጉዲናን ነው። በዚህ ሁሉ ዘመናቸው አንዲትም የምትታይ፤ የምትደመጥ ብቁ የሴት ሊሂቅ ማውጣት አልቻሉም። እኔ ስሞግታቸው ነበር። ይህ ትልቅ ሹልከት ነው። አለሁ ይላሉ ግን የሾለኩ ማሃን ናቸው። በሌላ በኩል በዘመነ አብይዝም የኢትዮጵያ ካቢኔ ዓለም ያጨበጨበለት 50/ 100 ሴቶች ናቸው። የተማሩም ናቸው። ተሰፋዬ ዝልቅ ነበር። ነገር ግን የእናትነት ጸጋን እንኳን በእነሱ የተግባር ማሳ ማዬት አልቻልኩም - እኔ። እርህርህና ነጥፎ ነው እማዬው። 

     በዚህ ጉዳይ ብዙ በጣም ብዙ ሞግቸበታለሁኝ፤ ሴቶች ወደፊት እንደሚመጡ ብቻ ሳይሆን ሴቶች መፍትሄ ናቸው ብዬም አምን ስለነበር። አሁን ግን ልፋቴ ከንቱ ሆኖ ነው ያዬሁት። ስለዚህ የባልደራስ ባለ አደራ ሴቶችን አሳትፋለሁኝ ካለ ሴት መሆናቸውን ብቻ ሳይሆን  አቅማቸውን፤ ብቃታቸው፤  ሰብዕናቸውን፤ በተለይም በተለይ እናታዊ ጸጋቸው አብሰንት አለመሆኑን አረጋግጦ መሆን ይኖርበታል። ሮል ሞዴል እያጡ ነው ተከታዮቹ ልጃገረዶች። በኢትዮጵያ መንግሥት በነበረው የሹመት አሰጣጥ ዘንጠረዥ ውስጥ  „የአጣርተን እንነግራችሁ አለን“ ቲያትር በአገር ውስጥ መንግሥት አለን የሚያሰኝም እጅግ አሸማቃቂ ጉዳይ ነበር።
 
(14)      በሌሎች የሙያ ዘርፎችም አቅም ተኮር ምርጫ ነው ሊሆን የሚገባው። አቅም ሲባል ለተዋፆ ተብሎ ከሚደረገው ፉክክር መውጣት በእጅጉ ያስፈልጋል።

(15)      በቅንጅትም፣ በአንድነትም ያዬሁት ነገር በጣም ብዙ ሥ/አ/ ኮሜቴ አባላት ነው የሚኖሩት። ይህ የተገባ አይደለም። ድርጅቱን በጣም ዘልዛላ እና የገረጀፈ ያደርገዋል። ቢያንስ 7 ቢበዛ 9 ቢሆን ለስራ ቅልጥፍናም፤ ለውሳኔ አሰጣጥም፤ የሥ/አስ/ ኮሜቴን አንድነትንም ጠብቆ ለማዝለቅም ይረዳል። ይኑር አይኑር አላውቅም ወ/ሮ ሙፍርያት ካሚል እንደሚመሩት እንደ የአዲስ አበባው የአብይዝም „የወሰን ኮሜቴ“ 8 እንዳይሆን አደራ። ኮሜቴ በጎደሎ ቁጥር ነው የሚዋቀረው፤ ምክንያት የድምጽ እኩልነት ቢመጣ ሰብሳቢው የሚሰጠው ድምጽ ወሳኝ ይሆናል። ይህ መርኽ ነው። አብይዝም ግን ይህም ጉዳዩ አይደለም። ለነገሩ በፓርቲ ህይወት አመሰራረት ሆነ መርኽ ልምድም ዕውቀትም የላቸውም። 
 
(16)      አመራሩን የማብቃት ጉዳይ በባለሙያዎች የተደገፈ አነስ፣ አነስ ያሉ ወርክ ሾፖችን፤ የቴሌ ኮንፈረሶችን እያሰናዱ በዚህ ላይ መሥራት የተገባ ይመስለኛል። ብዙ እማዬው ያለቀባቸው የፖለቲካ ሰዎችን ነው። ወሳኝ አገራዊ ጉዳዮችን እንደ ተረብ አድርገው የሚያቀርቡት የማጣት ችግር ይመስለኛል። ይህ መንገዳቸውን ሊያበሩት ቢፈልጉም በመጥፋት ላይ ያሉ ስለመሆናቸው እራሱ ያውጅባቸዋል። ከዚህ መዳን የሚቻለው ተከታታይ ስልጣና ማድረግን አቅምን መጥኖ መከወን ይገባል። የትውልድ ግንባታ በታቀደ ሥልጠና። በቴሌ ኮንፈረንስ ሁሉ ይቻላል። ያው የኢትዮጵያ የመብራት ችግር ካለ አስተጓጉለው።  

(17)      መቼም አንድ የፖለቲካ ድርጅት በዴያስፖራው አቅሙ ከተነሳ በጣም አስፈሪው ነገር ጣልቃ ገብነት ሊሆን ይችላል። ስለዚህ ሁሉም የመብቱን እና የግዴታውን ጣሪያና ግድግዳ ከውጥኑ አጥርቶ መጀመር ለቀጣዩ ፈተና መፍትሄ ይመስለኛል። የቅንጅት ፈተና፤ የአንድነት ፈተና፤ የሰማያዊ ፈተና የነበረው ይኽው ነው። የኦፌኮን አሁን ሄዶ ሄዶ የወደቀበትም ሸጎሬም ይኽው ጉዳይ ነው። ዋናው ነገር አመሰራረት ላይ ጥርት ባለ የኃላፊነት ወሰን እና ልክ ሊሆን ይገባዋል። ሥራ ክፍፍሉ በተገባ ሁኔታ ከጅምሩ ተግርቶ መሠራት አለበት። ዕውነት ለመናገር አብን በዚህ ዘርፍ ዕድለኛ ነው። 

     አቅሙ መሰረቱ አገር ውስጥ ስለሆነ ከዚህ መሰል ፈተና የዳነ ይመስለኛል። የወደፊቱን ባለውቀውም። እርግጥ የጠሚር ጽ/ቤት ይህም አስቀንቶት ካቴና ላይ ያሉ ወገኖችን በጥያቄ „የአብን የሃብት ምንጩ ምንድን ነው“ እያሉ ያጣድፉ የነበረበት ጉዳይም ይኸው መሆኑን ሳዳምጥ „እኔ ዲሞክራት መሪ ነኝን“ ውሃ የበላው ቅል መድረጉን አስተውዬበታለሁኝ። ይህን ያህል ታች መውረድ አያስፈልግም ነበር። ያልሰለጠነ ጮርቃ መንገድ ነው። ሊታፈርም ይገባል እንደ መንግሥት። ድርጅት በንፋስ ግፊት አይንቀሳቀሰም። ከአባላት ድጋፍ ማግኘት መርኽ ነው። አባላቶቹ፤ ደጋፊዎቹ ቢረዱት ኃጢያት አይደለም። ደንቡ ላይም ይኖራል። 
  
(18)      አላውቅም ሰው በምን ዓይነት የፖለቲካ ሂደት እንደሚበቅል። ፖለቲካ ድርጅት ውስጥ ዝርግነት ጥሩ አይደለም። አንድ የፖለቲካ ድርጅት ሚስጢር ሊኖረው ይችላል። ያን ካለ ጊዜው መዘርገፍ የተገባ አይደለም። አሁንም ማንሳት የምሻው አብን ነው። ቀደም ሲል ሰማያዊ ላይ አሁን ከሆነ በአብን ተስፋ ያደረጉ የዲፖሎማሲያዊ ነፍሶች የሚሰጡት ድጋፍ ካለ ጊዜው፤ ባልተገባ ሁኔታ ይፋ ማድረግ ፈጽሞ ያልተገባ ጉዳይ ነበር። 

     አይደለም ሳይጠዬቁ ቢጠዬቁም ያዝ አድርጎ ማቆዬት ብልህነት ነበር። አንድ የፖለቲካ ድርጅት አካላት በበዛ ሁኔታ መቆጠብ አለበት። እንዲህ መሰሉ መረጃ ለራስ አቅም ተቀናቃኝ ፈቅዶ መፍጠርም ነው። ጠሚር አብይ አህመድ ቆቅ ናቸው። በሩን ሁሉ ነው የሚያስከረችሙት። ሁሉንም ነገር ነው የሚከታተሉት። ለዛውም አማራ መንፈስ ላይ። ዝርግነት ጠላት ነው የሚያፈራው፤ ከዛም በላይ ለስኬቱም እንቅፋት ነው። ቀድሞ ብዙ ነገር ይቀጫል። አይጠቅምም። 

     ለዚህም ነበር በሰኔው 15/2011 ግርግር የአቶ ኽርማን ኮኽን ምስክርነት የተፈለገው። ጎንደሮች „ሙያ በልብ“ ይሉታል እንዲህ መሰሉን ጉዳይ። በጣም ጥበብ ያንሰዋል የኢትዮጵያ ፖለቲካ። ነገረ ተግባርን መለዬት ያስፈልጋል። ለህዝብ ይፋ የሚሆነው፤ ለሚዲያ ይፋ የሚሆነው፤ ለአባላቱ ይፋ የሚሆነው፤ ለደጋፊ ይፋ የሚሆነው፤ ለአካላቱ ይፋ የሚሆነው። „ሁሉ ተፈቅዶልኛል ሁሉ ግን አይጠቅምም“ ይህ የቃለ ወንጌል ጠቃሚ መልዕክት ነው። እንደዚህ መሰል ልቅነት ከትርፉ ኪሳራው ነው የሚያመዝነው። ችግሩ በሳል የፖለቲካ አማካሪም የለም።

(19)      እስከዛሬ በማዬው የአንድ ሰው አመራር ነው። የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ግንባር፤ ጥምረት፤ ውህደት ፈጠርን ሲሉ ለሁሉም ተወካዩ አንድ ሰው ነው። አንድ ሁለት ትሉና ሦስተኛ የሚጠራ ሰው አይገኝም። ለምን? በግል እና በጋራ ኃላፊነት ላይ ተመክሯቸው ወና ነው። አሁን በሙሽራውም ኢህዴግ አንድ ሰው ነው የሚታዬው። ሁሉም ኃላፊነት ላይ። አንድ ጊዜ የፖለቲካ ተንታኙ አቶ ኤርምያስ ለገሰ ጠቅላይ ሚኒስትሩ „በዙብኝ„ ሲል ሰምቸዋለሁኝ። ትክክለኛ አገላለጽ ነበር። ሁሉም ድርሻውን አውቆ እንዲሰራ ነፃነቱን መስጠት ያስፈልጋል። የሁሉንም ጭንቅላት እተካለሁ ማለት ግን ሰውን እንደ ሮቦት ማዬት ይመስለኛል።  

(20)      ልክን ማወቅ። ለዚህም ጎንደሮች ጥሩ አባባል አላቸው። „ልክን ማወቅ ከልክ ያደርሳል“ ይላሉ። በብዙ ድርጅቶች በጣም የተንጠራራ ነገር አያለሁኝ። ባላደራስ እራሱ በራስ የመተማመን አቅሙ ካለልኩ መሄድም፤ ከልኩ መውረድም እንዳይኖር ከአሁኑ ነው ተግርቶ መጀመር ያለበት። ተቋሙን በተመጣጠነ የራስ መተማመን ልኩን፣ ሚዛኑን፣ ደንበሩን እና ወሰኑን አውቆ መነሳት። ይህ የመጀመሪያው ሥራ ሊሆን ይገባል ለባልደራስ። 

    የግለሰቦችን ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ ድርጅቱ እራሱ ይህን መርኽ ሊከተል ይገባዋል። በተመጣጠነ ሙቀት ላይ የሰከነ ሚዛናዊ የራስ መተማመን ያለው የፖለቲካ ድርጅት ለትውልድም ሮል ሞዴል የመሆን አቅም አለው። እሰቡት የተመጣጠነ የራስ መተማመን ያልኩት ለአመራር አካላቱ ብቻ አይደለም ለራሱ ለባልደራስ ባለ አደራው ለሚፈጥረው አዲስ የፖለቲካ ድርጅትም ነው።

(21)      መቼም እንደ አብይወለማ ዘመን ሰባዕዊነትን ተስፋ ያደርግኩበት ዘመን አልነበረም። አልሆነም። የሆነ ሆኖ ባልደራስ መስፈርቱም አቅጣጫውም ሰው እና ተፈጥሮን ማዕከል እንዲሆን ማድረግ ይጠበቅበታል። ኢትዮጵያዊው ሰው ተንገላታ። እርግጥ አሁን አዲስ አበባ ላይ ብቻ እንደ ሆነ አትኩሮቱን አውቀለሁ። አብነቱ ግን ግሎባል ማድረግ ይቻላል። አዲስ አበባ  በዓለም አቀፍ ድርጅት መዲናነት 4ኛ ደረጃ ላይ ያለት ናት። አሁን ለኦሮምያ ብቻ ውርስ ቅርስ የተሸለመቸው ይህም አስጎምጅቶ ነው። የሆነ ሆኖ ዘመኑም ግሎባል ነው እና ደረጃውን ማሰጠበቅ ይጠይቃል። የመንፈስ ልዕልና።

(22)      ጸሎት። ፀሎት ጥሩ ነው። ግን ይፋዊ ሳይሆን ህሊናዊ ቢሆን ነው ምርጫዬ። በአደባባይ ሲሆን ረቂቅ የሆኑ ነገሮች አሉበት። ምክንያቱም አሁን የሚፈለጉ ክብሪቶች እና ቤንዚኖች አሉ። ለዛ መመቸት የተገባ አይመስለኝም። ሌላው ግን አንድ የፖለቲካ ድርጅት ሰውን ማዕከል አድርጎ ነው መፈጠር ያለበት ብዬ አምናለሁኝ። በሰው ውስጥ አማኝ እንዳለ ሁሉ የማያምንም የድርጅቱ አባል፤ የማያምን የድርጅቱ አካል ሊኖር ይችላል። ስለዚህ ጥንቃቄ ያስፈልጋል። ማጠቃለያ ላይ ግን እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይጠብቅ ማለት ይቻላል። ከዚህ ባለፈ መሄድ ግን ሰው ስስ ሆኗል።  

(23)      ሚዲያ አጠቃቀም። ይህን በሚመለከት ኢትዮ 360 „ፖለቲካችን“ ላይ ተነስቶ አዳምጬ ነበር። መነሻዬም የእነሱ ሃሳብ ነው። ባልደራስ / ባለ አደራው በተገኜው አጋጣሚ ሁሉ የሚዲያ ዕድሉን በቁጥብነት መጠቀም ይኖርበታል። ለምሳሌ የፖለቲካ ድርጅቶች ፉክክር ፋና፤ ዋልታ ቢያዘጋጅ የመንግሥት ናቸው ተብሎ ዕድሉ መታጠፍ የለበትም። ያ ከህዝብ ከሚሰበሰብ ቀረጥ ነው ድርጅቱ የሚተዳደረው። የራሳችን ሃብት ነው ብሎ ማስብም ይገባል። ስለዚህ ሃብቴ ነው ብሎ አምኖ መቀበል እና መሳተፍም። እርግጥ ነው ተልዕኮ ይዘው ኑ ውረዱ ኑ ተሰቀሉ የሚሉ ሚዲያዎች ላይ ክብርን ጠብቆ አለመሄድ ነው። 

    በኢትዮጵያዊነት ተፃራሪነት በቆሙት ሚዲያዎችም ላይ እንዲሁ ማዕቀብ መጣል ያስፈልጋል። በተጨማሪም በማጠልሸት፤ ህዝብ በማነሳሳት ላይ የሚያተኩሩትን ነጥሎ ማዬትም ይገባል። ነገር ግን በፌድራላዊ መንግሥት ሚዲያዎች ግን ዕድሉ ከተገኜ እኩል ተሳትፎ ማድርግ ይገባል። የግል የሚመስሉትም ብዙዎቹ ለተልዕኮ የተደራጁ ናቸው ሲቀዱ እማያቸው። 

     ለዛውም አቅም ያለውን ሰው ለማራገፍ፤ ለማዋራድ፤ መጠራቅቅ ውስጥ ለመጨመር፤ ከፎቅ ለመፈጥፈጥ ነው የተፈጠሩት። ስለዚህ በመንግሥት ከሚታወቁት ሚዲያዎች ጥሪን መቀበል ብልህነት ይመስለኛል። ዋልታ ለምርጫ ፉክክር አወያይ ሊሆን ይችላል። ልባም ሞራላዊ ሞጋች ስላለው። ለዛም መሰናዶ ይመስላል በቀደምት አሻም የተባለው ዕድል ሰሞኑን ተፈቅዶ ያዬሁት። የሆነ ሆኖ ሚዲያ አቅም ነው። ምርጫ ላይ ደግሞ ወሳኝ የነፍስ ጉዳይ ነው። 
     
(24)      ሰነድ ዝግጅት በደንቡ፤ በፕሮግራሙ እና በዕቅድ ንድፍ፤ በውስጥ አፈጻጻም መመሪያዎችም ላይ ቀላል እና ግልጽ አድርጎ ማዘጋጀት ያስፈልጋል። አደራ ዕቅድ እንዳይረሳ። የሰነዶቹ መሰናዶ የሥነ - ጹሁፍ ፉክክር መሆን አይገባውም። ኢትዮጵያ የገበሬ አገር ናት። በማዬው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ያው ገበሬውን አቅዶ የሚነሳ ውስጥነት ባይኖርም። ኢህዴግ ማህበራዊ መሰረቴ ገበሬ ነው ይላል። 

     ነገር ግን 27 ዓመት ሙሉ አንድም ገበሬ በፖለቲካ ውክልና የለውም። ሌላውም እንዲሁ። ኢትዮጵያ የከተሜ አገር ተደርጋ ነው እምትታዬው። በሌላ በኩል ባልደራስ አሁን ብሄራዊ ሆኖ ለመደራጀት አቅሙ ባይኖረውም ነገን አስቦ መነሳት ግን አለበት። የትውልድ ፓርቲነትን ጸንሶ። በመንፈስም ገበሬው እንዳለ በክብር ማሰብ ይገባል። 

     አዲስ አበባም ቢሆን ያልተማሩ ዜጎች ይኖራሉ። እሱ ብቻ ሳይሆን ተምረውም የማይገባቸው ፍጥረቶች አሉ። በተጨማሪ በተፈጥሯቸው ቀላል እና ያልተወሳሰብ ነገር የሚወዱ ሰዎችም አሉም። አብዛኞቹ ሲዊዞች እንደዛ ናቸው። ስለዚህ ሁሉም እኩል ሊረዳው በሚችል መልኩ ቀለል አድርጎ ሰነዶችን ማሰናዳት ይገባል። አዲስ አበባ ላይ የሚጠዬቁ ሰዎች ሳይ እንደ ተፈጠሩ የሆኑ ነፍሶችን ነው እማስተውለው። ስለዚህ ሰነዶቹ ሲዘጋጁ ለወጥ ኦዲዬንስ ሳይሆን ለቅይጥ ኦዲዬንስ መሆን ይኖርበታል። የዕውቀት፤ የግንዛቤ፤ የዕድሜ ልዩነቶችን አመጣጥኖ እኩል የመረዳት አቅምን በሚፈጥር መልኩ። ቀላል ማድረግ። 

(25)      ዓርማ ዕውነተኛ ከሆነ አታጋይ ነው። የባልደራስ ባለ አደራው ዛሬ ተፈጥሮ ነገ ከሰምኩኝ ብሎ መስዋዕትነትን ካላባከን በስተቀር እኔ የትውልድ ፓርቲ ሆኖ የሚቀጥልበትን መስመር መከተል ያለበት ይመስለኛል። ስለዚህም በጣም ቀላል፤ በጣም ግልጽ፤ አጭር ትርጓሜ ያለው ሁሉም ሊገባው የሚችል፤ ያልተወሳሰበ፤ ለተቃርኖ የማይጋብዝ ሆኖ መሰናዳት አለበት። 

     እኔ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ስንደቅ ዓላማን ሳስተውለው ውሳኔውን በውነቱ የቀደሙት አባቶቻችን ኢትዮጵያን ያበጇት ምን ያህል ልቅና፤ ምን ያህል ልዕልና፤ ምን ያህል ብጡልነት፤ ምን ያህል ሥልጣኔ እንዳላቸው የሚደንቀኝ ጉዳይ ነው። አረንጓዴ ቢጫ ቀይ። ምንም የሌለበት - ልሙጥ። ተስፋ፣ ጀግንነት እና ልምላሜ። የመኖር ሚስጢር በእነዚህ ህብረ ቀለማት ተመስጥሮ አለ አንድም ሳይቀር። ግን ቀላል ነው፤ ሲዩትም፤ ሲያጠኑትም። አፍ የፈታ ህፃን ልጅ በሚገባው፤ በሚያፍቅረው ሁኔታ። ሊቃውነት ረቂቅ ናቸው። ጥበቡ ስለተሰጣቸው። ስለዚህ ለባልደራስ አደራ አደራ የምለው ዓርማውን እንዳያወሳስበው ነው። ገበሬውን ይሰብ። ያልተማረውን ማህበረሰባችን ይሰብ፤ ልጆችን ይሰብ። የውጭ ዜጎችም ቢሆኑ በቀላሉ ሊረዱት እንዲችሉ ሊሆን ይገባል። የእኔ የእኛ እንዲባል።  

(26)      የማህበራዊ ሚዲያ ተሳትፎ አመራር አካላቱ ፍላጎታቸውን፤ ስሜታቸውን በድርጅታቸው ተቋማዊ በሆነ መልኩ ቢያደርጉ መልካም ነው። እርግጥ ነው ከሥልጣኔ ጎራ ጥፉ ማለት ሳይሆን አጀማመር ላይ ጥንቃቄ ይሻል። ለዚህ መስዋዕትነት ዝግጁ መሆንን ይጠይቃል። የብዙ የፖለቲካ ድርጅቶች መከራ የሆነው ይኽው ጉዳይ ይመስለኛል። የቆረጡ እና ቁጥቦችን ብቻ አመራራ ላይ ማምጣት የሚጠቅመው ለዚህ ነው። ለዲስፕሊን የተገዙ። 

     እራሱ ድርጅቱ በራሱ ፔጅ ላይ በሚለጥፋቸው ጉዳዮቹ ላይ ቢሆንም ዛሬ ስሜቱ የሁሉም ስስ ስለሆነ፤ ደጋግሞ አይቶ በጥንቃቄ መርምሮ ሊያደርገው ይገባል። ከጻፉት በኋላ ደግመው ሲዩት ብዙ ማስተካከል ይቻላል። ከታገሱት ደግሞ ሊወቅሱ የተነሱበት ነገር ሊለጥፉ ሲሄዱ ተስተካክሎ ይጠብቃል። አደብ ያስፈልጋል። 

    አክቲቢዝም እና የፖለቲካ ድርጅት መሪነት በውል መለዬት አለበት። በዚህ ላይ ህዝብ ግንኙነት የሚመደበው ሰው በጣም ስክነት ያለው ሰው ሊሆን ይገባል። ከስሜታዊነት በፍጹም ሁኔታ የጸዳ። አዲስ አበባ ሁሉም አላት። ተገለው የኖሩ ብዙ ብጡል ብቁ ሊሂቃን አሉ። የተከደኑ ሲሳዮች። እነሱም መሸሸት የለባቸውም። ቀረብ ብለው ባልደራሱን ምን እንርዳ ማለት ያለባቸው ይመስለኛል።

(27)      ባለ አደራው ሰርጎ ገቦች እንደሚኖረ ማሰብ ይኖርበታል። ስለዚህ ተግባርን በቁጥብነት ማቅለም ይጠበቅበታል። በማንኛውም ጊዜ አንጃ ሊፈጥሩ የሚችሉ ሰዎችም ተልዕኮ ተሰጥቷቸው ሊቀላቀሉ እንደሚችሉ ቀድሞ ማሰብ ይገባዋል። በዚህ ደግሞ ኢህዴግ የዶክትሬት ዲግሪውን የወሰደ ድርጅት ነው። 

    ህዝብ አማራጭ አልባ እንዲሆን በማድረግ በሰፊው ተሰርቶበታል። የጠሚር አብይ አህመድን አቅም ስታዩት ደግሞ ከጸሐይ ጉልበት በላይ ስልታዊ፤ ብልጣዊ፤ ዘመናዊ፤ ሰላቢያዊ፤ አማላያዊ ነው። እራሳቸው ነው አቅም ለተባለው ሰው ደውለው የሚያነጋግሩት፤ የሚያዘናጉትም። ወደ ቤተሰብም ጎራ ይላሉ። ሸብረክ ብሎ የምታዩት ሰው ሁሉ ከዛ ፈተና የመነጨ ነው። 

     ያልማረኩት ነፍስ የለም። ሁሉንም የሥጦታ ዓይነት ነው በልግስና የሚያቀርቡት። የተፎካካሪ/ የተቃዋሚ/ የተቀናቃኝ/ የተደማሪውን መንፈስ እንዴት ቁጭ አድርገው በጫጉላ ሽርሽር ሲቀልቡት እንደባጁ ማዬት ነው። እንዴት ጥበቃ መድበው እንደሚያንፈላስሱት፤ እንደምንስ የቤተ - መንግሥት ቤተኛ እንዳደረጉት፤ እንደምንስ የጸጋ ስግደት እንደሚያሰገዱ በዓይነት ነው። ስለዚህ በቀላል ሰንጥቆ ለመግባት እሳቸው ሁሉም አላቸው፤ በደህንቱም፤ በዲጅታሉም፤ በሚሊተሪውም ዕውቀትም ወዘተ … ስለዚህ በባልደራሱ ባለ አደራ የፖለቲካ ድርጅት አንጃ መፈጠርን፤ ፍንገጣ ሊኖር እንደሚችል ሊጠበቅ ይገባል፤ ቢፈጠርም አትደናገጡም። የህሊና መሰናዶ አስቀድማችሁ አድርጉ።

(28)       በሲቢክስ ቆይቶ ወደ ፖለቲካ ድርጅት ሲቀዬሩ ተወራራሽ ነገሮችን በመለዬት በጠራ የፖለቲካ አቅም መመስረት ይጠይቃል። ያው የሲቢክስ ድርጅት የውሳኔ አሰጣጥ እና የፖለቲካ ድርጅት የውሳኔ አሰጣጥ በጣም የተለያዬ ነው። ፖለቲካ ለስልጣን ነው ውድድሩ። ባላደራሱ ወደ ባህረ - ቢሮክራሲ ነው የሚገባውና። 

    ስለዚህ በሁለቱ መሃል ያለው ልዩነት በሚገባ በበሰለ፣ በሰለጠነ ሁኔታ አካላቱ በአጀንዳ ሊወያዩበት ይገባል። ምን አልባት የባልደራሱ አካል የነበረ የፖለቲካ ድርጅት አካል ሆኖ ለመቀጠል የማይፈልግ መኖሩም ተፈጥሯዊ ነው። እንደዚህም ሊገጥም ይችላል።

    የሆነ ሆኖ በሁለቱ የአደረጃጃት መርኽ ላይ ልዩነቱ እና እንድነቱ ላይ አስቀድሞ ግልጽ አቋም ሊወሰድበት ይገባል። ዲስፕሊኑም፤ ማንነቱም የተለዬ ነው። አሁን ባልደራስ የፖለቲካ ድርጅት ሲሆን አዲስ ማንነት ነው። አዲሱን ማንነት መሸከም የሚችል ዲስፕሊን ያስፈልገዋል ማለት ነው። ስለዚህ ይቅርብኝ የሚባል የግል የቀደሙ ማንነቶች ሁሉ ይኖራሉ። ሁለት ሦስት ነገር መውደድ አይቻልም። ስለዚህ መጀመሪያ በግል ቀጥሎ በጋራ እራስን ማሸነፍ ይገባል። ይህ ማለት ግን እራስን ማስተዳደር የሚቻልበት የግል ንግድ ድርጅት ካለ ይፍረስ ማለት አይደለም። ጉሮሮ ነዋ።

(29)      መርኽ እና ዕውነት በዚህ ድርጅት አህዱ ቢሉ ለትውልዱ ትልቅ ስጦታ ይሆናል።

(30)      ስህተት ሲኖር ይቅርታ መጠዬቅ። ተሳስቻለሁ የሚል ሊሂቅ የለም። ስለሆነም ይቅርታ ጠያቂ ይናፍቀናል።

(31)      ማሸነፍ እንዳለ ሁሉ መሸነፍም እንደሚኖር አምኖ መቀበል፤ ትርፍ እንዳለ ኪሳራም፤ ዘላቂነት እንዳለ መከዳትም፤ ወጥ ሆኖ መቀጠል እንዳለ አንጃ መፈጠርም፤ ተቀባይነት እንዳለ ተቃላይነትም፤  መመስገን እንዳለ ሁሉ መተቸትም፤ ጨለማ እንዳለ ገራጫማም፤ ብርሃናማም እንደሚኖሩ፤ ሳቅ እንዳለ ሲቃ እና ለቅሶ እንዳሉም፤ አብሮ መኖር እንዳለ መለያዬትም እንደሚኖር አምኖ መቀበል ግድ ይሆናል። ይህ ከሆነ ወጀብ በመጣ ቁጥር መፍረክረክ ይቀርና ተገቶ በጽናት የትውልድ ድርጅት ሆኖ መቀጠል ይቻላል።

(32)      የባልደራሱ ባለ አደራ ዕድል አመራሮቹ ካድሬ የነበሩ አይደሉም። ማንነቱን ስለማያውቁት በቀጥታ በአመራር አካልነት ሚና ላይ ነው ተግባራቸውን የሚጀምሩት። ስለዚህም መልካም አጋጣሚ ነው። ይህ የጠቅላይ ሚኒስተር አብይም፤ ሥልጣን ያሉትም የሙሽራው ኢህዴግ ሞጋች ፈተናም ነው።

·        ማሰተጋበሪያ።

ባልደራስ ወደ ፖለቲካ ድርጅት ከመቀዬሩ በፊት ሁሉም በዬዕምነቱ እግዚአብሄርን አላህን የሚጠይቅበት የጥሞና የግል ጊዜ ቢኖረው እመርጣለሁኝ። ያጣነው ይሄ ነው። ሁሉም ዘው ብሎ ነው የሚገባው። ለዚህም ነው የማይቀናን። ተስፋችን በዬዘመኑ ለድርቅ የሚቀለበውም በዚህ ምክንያት ነው። አሁን ዛሬ ከጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እንዳደመጥኩት ግን ዕድሉ እንደሌላ ነው። ቢያንስ ሦስት ቀን ታስቦበት ቢሆን ያተርፍ ነበር።  
  
በሌላ በኩል እንደ ተጨባጭ ሁኔታው በማንኛውም ጊዜ የፓርቲው መሰረታዊ ሰነዶች ደንቡ፤ ፕሮግራሙ እና ዕቅዱ ሊሻሻሉ፤ ሊቀዬሩ እንደሚችሉም ፍላጎትን ክፍት ማድረግ በጣም ይጠቅማል። አዲስ ሃሳብ ሲፈልቅ ድርጅትን ወደ ማክሰም አይኬድም። ለመንገዱ አስቀድሞ ግድፈትን የሚከላከል ክትባት ይሆንለታል።
·        ክወና።
የባልደራስ ባለ አደራ በፖለቲካ አደረጃጀት እና ጉዞም ራሱን በቻለ አመክንዮ ልምድ አግኝቶ የመጣ ስለሆነ ጥንካሬ የሚያመነጭለት ወይንም አቅሙ የሚቀዳበት ተደሞ እንዳለውም አስባለሁኝ። ፈተና ነው የፈጠረው። ማህበራዊ ንቃተ ህሊና ነው የወለደው። ባልደራስ የህዝብ ፈቃድ ያስገኜው ድርጅት ነው። ንቅናቄውም፤ ዕድገቱም ህዝባዊ ነው። 

እኔ ከመጋቢት አንድ ቀን 2011 ታምር በኋላ በፈቃደ እግዚአብሄር የተፈጠረ ድርጅት አድርጌ ነው እማዬው። ዕለቱ እራሱ በምልሰት እሰቡት። ምን እና ምን ተቀያይጠው እንደመጡ። ሰማያዊ ቁጣ እና ምድራዊ ፉክክር። ለዚህም ነው ይህን ያህል ሰፊ ጊዜ ወስጄ አድርጌው በማላውቀው ሁኔታ ረዘም ያለ አስተያዬት ለአዲስ ለሚመሠረት ፓርቲ የጻፍኩት። አዲስ ሊመሠረት ሲባል ዝም ብዬ ነው እማዬው የነበረው።

ለረጅም ጊዜ ሲናፍቀኝ የነበረ ጉልህ ምኞት አለኝ። የትውልዱ ብክነት ውስጤ ስለሆነ ሊሆን ይችላል። ቋሚ የሆነ የትውልድ ፓርቲ ልክ እንደ አሜሪካኖች የሪፓብሊካን እና የዴሞክራት ዓይነት ኢትዮጵያ ውስጥ የትውልድ ፓርቲ ቢፈጠር እል ነበር። ምን አልባት፤ ምንአልባት የባልደራስ ባለ አደራ የትውስት ዓላማ ይዞ፤ ወይንም የሻገተ ማንነት ተላብሶ ስለማይፈጠር የህሊና መሰናዶ ላይ ስላለ የትውልድ ፓርቲ ሆኖ ይዘልቅ ዘንድ በአመሠራረቱ ላይ ብርቱ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበት ስለ አሳሰበኝ ነው ይህን ዘለግ ያለ አስተያዬት የሰጠሁት። ለትውልድ ፓርቲነት የምኞቴ እጮኛ። ደህና መሠረት ነው ቤትን የሚያዘልቀው። ጥራት ነው ጎጆን የሚያቀናው።

አሁን የባልደራስ ባለ አደራው በመንፈስ ዲታ ነው። ዲታነቱን ማዝለቅ የሚቻለው ግን አመሠራረቱ ላይ በሚወሰደው ብርቱ ጥንቃቄ ነው። የባልደራስ ተቀናቃኞች አቅመ ያላቸውም ሆነ አቀምቢሶችም በማህበር ተደራጅተው፤ መንግሥትም እራሱ በይፋ እዬታገለው ያለው ስለሆነ ያን መቋቋም የሚችለው ደግሞ በጥራታዊ መስመሩ ጉዞው ነው። ይህ ማለት ግን ፍጽምና አይጠበቅም። ድክመት ነባሩን አልመደገም እንጂ በእንቅስቃሴ ላይ ያለ ተቋም የሰዎች ስብሰብ ስለሆነ ሁልጊዜ አዲስ ግድፈት ሊኖር ይገባል። ስህተት ሰውኛ ነው። ቁም ነገሩ አለመድገም፤ ለማረም መፍቅድ። ይቅርታም መጠዬቅ። ይቅርታ ክብር ነው።

ሌላው ባለ አደራው ሊያስብበት የሚገባው በኽረ ጉዳይ የተጋድሎ ታጋይ እና የትግልም ታጋይ ስለሆነ ጥምረቱም፣ ውህደቱም እንደ ተነሳበት ዓላማ ለህልውና ትግል ከሚያደርጉት ጋር ሊሆን ይገባል። የፋንታዚ ፓርቲ ስላይደለ። ብዙ ዘመናይ ነገሮችን ሳያስተናገድ በቀደመው የአባቶች ጥሞና፤ ልቅና፤ ልዕልና ልክ በጥበብ ለመመራት ስከነትን አስቀድሞ እራሱን ቢያሰናዳ ተስፋ የመሆን አቅም ይኖረዋል።

ፍላጎት በስማ በለው አይፈጸም። እራስ ተገኝቶ ነው ማስፈጸም የሚቻለው። በጣም መሰረታዊ ጉዳይ ነበር ባልደራስ ወደ ፖለቲካ ድርጅት የመቀዬሩ ጉዳይ። የእኔን ጉዳይ እኔ ነኝ እማስፈጽመው። ተመሳሳይ አቋም ያለን ሰዎች ብንሆን እንኳን ስብሰባ ላይ አዬሩን የሚለወጥ አመክንዮ ሲመጣ በሃሳብ ልዩነት የድምጽ አሰጣጡን ሂደት ሊቀይረው ይችላል። የአማራ ሊሂቃን ህልፈትም፤ የአቶ ክርስትያን ታደለ እስርም ይህ ተሰልቶ የተከወነ ነው። አንድ ጉልበታም ሃሳብ አቅራቢ የተቀናቃኙን ደጋፊዎች ሃሳብ ሙሉ በሙሉ የማስቀዬር አቅም ይኖረዋል። እራስ መሳተፍ እና በተወካይ መሳተፍ ፈጽሞ አንድ አይደለም።

የባልደራስን ባለ አደራ እግዚአብሄር እንዲረዳው እምሻው ቁመነገር ጽናቱን እንዲቀጥልበት ነው። ሸብረክ ባለ ቁጥር ዳጡ ብዙ ነውና። አብሶ ውህደት፤ ጥምረት፣ አብሮ መስራት ላይ ውራጅ ሬሳ መንፈስ ጋር ከተዋህደ የሚሊዮኖች ተሰፋ አሮ ይቀራል። ህልውናውን አስጠብቆ በሚያስማማው ላይ ከሆነ ደግሞ ያተርፋል። 

እልህኛ እና በሰጨኝ እንዳይሆንም አበክሬ አስገነዝባለሁኝ። በርትቶ ይጸልይ የባልደራሱ ባለ አደራ። የሮም አወዳደቅ እንዳይወድቅ። በተረፈ የእኔ ድንግል ትልቁ ጸሎቴ ህይወታችሁ ነው እና ጥላ እና ከለላ ትሁናችሁ። አሜን! የሰከነ ስኬት ላይ እንደምንገናኝ ተስፋ አደርጋለሁኝ እንደ እግዚአብሄር ፈቃድ። ይቅናችሁ። አሜን!


ማስተዋል ሰብሎ የማይበት ጊዜ ይናፍቀኛል።
የትውልድ ፓርቲም ይናፍቀኛል።
ህዝብ ይከበር!
ይቅርታ ክብር ነው!
ኢትዮጵያዊነት ከመፈጠሩ በፊት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር።

የኔዎቹ አብረን ቆዬን። ዘንከት ባለ ትህትና ልሰናበት ወደድኩኝ።
መሸቢያ ጊዜ።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።