ስለ ሶቆቃው አማራ፤

የቱ ይቅደም ስለ ሶቆቃው አማራ? ክፍል አንድ።  
ከሥርጉተ © ሥላሴ 28.06.2018
(ከገዳማዊቷ ሲዊዘርላንድ)

„አሌፍ። ህዝብ ሞልቶባት የነበረች ከተማ ብቻዋን እንዴት ተቀመጠች“ (ሰቆቃው ኤርምያስ ምዕራፍ ፩ ቁጥር ፪)



  • ·      መነሻ።

አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ስለወልቃይት እና ቅማንት ጉዳይ መልስ ሰጡ Part 2

  • ·      እፍታ።

ዛሬ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ከአማራ ቴሌቪዥን ጋር ያደረጉት ውይይት አዳመጥኩት። የአማራ ቴሌቪዥን ችግሩ ቀንጨብ እያደረገ የሦስት እና የሁለት ደቂቃ ቅርጥምጣሚ መረጃዎችን ከመለጠፍ የሽወዳ ፖለቲካ  ወጥቶ ሙሉውን ለቆታል። ስለሆነም ነው ዛሬ ጥዋት ሙሉን ለማድመጥ የፈቀድኩት። ቋረጥራጣውንማ ዞር ብዬም አይቼው አላውቅም።
  • ·      ደት።

በሁሉም ጉዳይ ነጥብ በነጥብ መሄድ አስፈለጊ አይመስለኝም ግን ወሳኝ የሆኑ ጉዳዮች ማንሳት ግን ግድ ይለኛል። በጣም ከአቶ ገዱ አንዳርጋቸው ጋር የምስማማበት የፌድራሊዝም የተገነባንበት መንፈሱ ብክል ነው የሚለውን ነው። አዎን የፌድራሊዚም አወቃቀር መንፈሱ ብክልነቱ ሁሉም መሰጥሮ የያዘው አማራውን ከኢትዮጵያ መልክዕምድራዊ ገጸ ምድር በፍጹም ሁኔታ ያገለለ ነበር። ለዚህም ነው ፌድራዚሙ ችግር የለውም የሚለውን ሞጥረው ሲሞግቱ የሚሰሙት። አማራን ዜጋ አይደለህም ብሎ ቆራርጦ፤ ሽንሽኖ ከመንፈስ ሰርዞ የሚያስጠብቅ ማገር ስለሆነ።

ይህ እንግዲህ ለ43 ዓመት በጠንካራ ሁኔታ የተሠራበት የሴራው ሰንሰለት ነው። የዛ ዘር ነው ተባይ አፍርቶ ይህን ሁሉ መከራ ያሸከመን። ዛሬም ሁሉም ተራው ድርሶታል። ዋናው አንኳሩ ጉዳይ አማራን በጠላትነት የመፈረጅ እና ከአማራ የጸዳ ሥርዓትና መንግሥት መፍጠር ነው የሚፈለገው የነበረው። ይህ በሁሉም ማንፌስቶ ውስጥ ተከድኖ የተያዘ የገመና ጉድ ነበር። በተሄደበት ሁሉ አማራ መንፈስ አለባቸው የተባሉ ድርጅቶች እስከ ማህበራዊ መሰረታቸው ድርስ እንዲመክኑ የሚደረገውም ለዚህ ነው። 

ተውጠው የሌላ መንፈስ ሃብት ንብረት ሆነው ቁልቁል ወርደው ለጠለፋቸው ፖለቲካ ግርድና እንዲቆሙ የሚደረገውም ቢዚህ መልክ ነው። በዚህ ላይ እከሌ ተከሌ የለውም። ሌላው ቀርቶ ህብረ ብሄር በሚባሉት ውስጥ የአማራ ሊሂቃን መሪ እንዲሆኑ አይደረገም። አንድ ነበሩ እሳቸውም የተገለሉ ናቸው።
  • ·      ምቅ።


እኛ አንድ ነገር ጠሽ ጥው ባለ ቁጥር ዘራፍ ስንል የቆዬነው ከመሠረቱ የነበረውን ሴራ ብልሃት ማግኘት ስለተሳነን እንጂ መሠረታዊ አመክንዮ አማራን በሁሉም መስክ ማምከን ነው። ይህ ተሳክቷል ወይ ቢባል፤ ተሳክቷ ግን አማራ ብቻውን ሳይሆን ለእሱ የተቃጠው ጦር ኢትዮጵያንም ጨምሮ አደቃቃት ከአገርም ከክብርም ከመኖርም ተፈታተናት። አዋረዳት ርቃኗን አስቀራት። ባዶ ሳጥን አደረጋት።
ይህን ቁልፍ የኢትዮጵያ ጥያቄ አጥንቶ መልስ ለመስጠት የደፈረው ኦህዴድ ብቻ ነው። 

ኦህዴድ ከችግሩ ሰበዝ መዞ ወይንም ጅራት ላይ ተንጠልጥሎ ሳይሆን ከችግሩ ማዕከላዊ አስኳል ነው የተነሳው። ለዚህም ነው ሚስጢሩ ስለተደረሰበት ጫጫታው በርክቶ የከረመው። ኢትዮጵያን በውስጣቸው ሲያሰቀምጡ የትኛውም የፖለቲካ ሊሂቅ አማራን ሰርዘው ነው። ከሥር እንኳን ለጸሐፊነት ታምኖ ቦታው አይሰጠውም።

አማራን ሰርዘህ ኢትዮጵያን ማሰብ ደግሞ ፍርድ እና ዳኝነቱ የእዮር ነው የሚሆነው። ምክንያቱም ፈጣሪ አምላክ ኢትዮጵያ የአድህኖ ማህደሩ ስለሆነች ጠበቃት እንጂ። ስለዚህም አልተሳካለቸውም በዚህ መስመር አህዱ ክለቱ ሠለስቱ እያሉ የተራመዱት የፖለቲካ ሆኑ የሲቢክስ ድርጅቶች ሆኑ ተቋማት፤ ግለሰቦችም ሳይቀር ሁሉም ሃሳባቸው እንደ ሎጥ የጨው ድንጋይ ሆነው ነው ያረፉት።

ፈጣሪ የሚረዳው ውስጥህን ጻዕዳ አድርገህ ስትጀምረው ብቻ ነው። በውስጥህ የሚጎረብጥ ነገር ተሸክመህ በልብጥ ጉዞ እጅምራለሁ ብትል ያው ነው በዬፌርማታው መንጠባጠብ ነው። በኖርክበት መቀመቀም ውስጥ ማርጀት ነው። ከግብህም ሳትድረስ፤ ተልዕኮህንም ሳታሳካ ተቋርጦ መቅረት።
  • ·      ንቅል።

በዚህ በአቶ ገዱ አንዳርጋቸው ቃለ ምልለስ ውስጥ ስለ ተፈናቃዮች ተነስቷል። መፈናቀል ለአማራ እኮ ኑሮው ህይወቱ ከነፍሱ ውስጥ ያለ ጉዳይ ነው። 27 ዓመት ሙሉ ከሁሉም ነገር ተገልሎ ባለመኖር ውስጥ በዕድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ሶቆቆኛ ነው አማራ። ሚሊዮኖች ፍልሰዋል። ሚሊዮኖች አንዳይወለዱ ሆነዋል፤ ሺዎች ታስረዋል፤ ተገድለዋል፤ አካላቸው ተገድሏል። የውሻ ነፍስ ደረጃ የተሰጠው ማህበርሰብ ቢኖር አማራ ነው።

ይህን ደግሞ የወያኔ ሃርነት ትግራይ እድሉን ስላገኜ ነው እንጂ ሌላውም አጋጣሚውን ቢያገኝ ይህ የማይቀር ነው የነበረው። ይሄው ከዚህ እዬተሳዳድን አይደለም ያለነው። ከዚህ የወያኔ ሃርነት ትግራይ ብቻ ነውን የሚያሳድን? ኢትዮጵያ ያለውን መንፈስ አፍርሶ እና ንዶ ከዚህ ደግሞ በግል እንኳን ለነጻነት በመንተጋው ላይ ስንት የሰቆቃ ዘመን ነው የታለፈው … አሁንም ይብቃ ቢባል በስንት ጣዕሙ። አሁንም ያሳዱናል… በዬሄድነበት ማዕቀብ ያስጠላሉ …
  • ·      ስለችግር የሰለጠነበት ህዝብ - አማራ።  

አማራን ዛሬ የተቸገረ አድርጎ ማቅረብ ሳይሆን አማራ በተፈጠረባት እና በመሠረታት አገሩ ውስጥ እንደ ፍልስጤም፤ እንደ ኩርድሾቹ ሁሉ የመኖሪያ ብትን አፈር መንፈሱ እንዳይኖረው የተደረገ ህዝብ ነው። ወደፊትም የሚፈለገው በዚህ መልክ እንዲቀጥል ነው። ለዚህ ነው አማራ ተደራጀ ሲባል ሁሉም አንበሳ ነኝ ብሎ የሚወጣው። ጸጉሩም የሚቆመው። በበታችነት ስሜት ስለሚናጥ።  
  • ·      የመርዝ ጆንያ።

በዚህ በተከዘነ በመርዝ በታጨቀ በቋንቋ ፌድራዚም ውስጥ ችግሩ አማራ ተወልደው ያደጉ ግን አማራ ያልሆኑ ሰዎች ናቸው አማራን እንዲመሩ፤ እንዲወክሉ የተደረገው፤ እንዲያሰተዳድሩም የሆነው። ይህን መሰረታዊ ጉዳይ አማራን ባለቤት አልባ በማድረግ ግን በተሻለ የጥምር ዕድል ባለቤት ሌላ ባለሁለት አፍ ስለት አማራዊ ሥነ ልቦናዎችን መበጫን ቀጭጨው እንዲቀሩ ማድረግ ነበር።

ይህ ማለት እነዚህ ሰዎች የሥልጣን አቅም አላቸው አማራው በራሱ ውስጥ በቅሎ እንዳይጸድቅ ይታገሉት። ከዚህ መንፈስ ያፈነገጠው „አሸባሪ“ በማለት ያስሩታል። ተፃራሪዎችን እንደ አሸን በማፍለት በዬቦታው አማረነትን አንቀው ይይዙታል።  ስለምን? አማራ በራሱ አቅም ውስጥ ከመጣ እነሱ ቦታ አይኖራቸውም። በውክልናው ውስጥ እጅግ በጥንቃቄ የሚሠረውም ወጥ የሆኑ አማራዎች እንዳይወጡ ነው።

ስለዚህ አማራውን ለማጥፋት ከአማራነት ውጪ ያሉትን ሰዎች መሪዎች በማድረግ በራሱ ቀይህ ነው ተብሎ በተሰጠው እራፊ መሬትም ላይ እንኳን በመንፈሱም በአካሉም ተሰዶ እንዲኖር ነው የተፈረደበት ሰቆቃው አማራ።

የማይውክሉት ሊዩት እንኳን የሚጠዬፉት ናቸው መሪዎቹ፤ እነሱ ደግሞ በሥልጣናቸው ተጠቅመው ለመመንጠር ተመቻቸላቸው፤ በቀላቸውን በፈለጉት መስክ ተወጡበት። እነ አቶ አዲሱ ለገሰ አይደለም መሪ የሆኑት? እና ሳጅን በረከት ስምዖን፤ እን አለምነህ መኮነን አይደለምን መሪህ ናቸው የተባሉት?

ስለሆነም አማራ በሙሉ አቅሙ ማደግ መበልጸግ ቀርቶበት መሬት አለህ መባልን ተነፍጎ የኖረ እጅግ አሳዛኝ ማህበረሰብ ነው። አዝናለሁኝ የአማራ ሊሂቃን እንዲህ ወለም ዘለም ሲሉ እና አማራ ነኝ ማለት እንደ ፖለቲካ ክስረት፤ ውርዴትም አድርገው ሲቆጥሩት። እውነት ለመናገር ግን በሌሉበት አለን ማለት ሳይጠሩት አቤትነት ነው። የለም እኮ አማራ፤ የተሰረዘ እኮ ነው አማራ። ለዚህም ነው እዬተለቀም መታስር የሚገባው መታሰር፤ መታረድ የሚገባው የታራደ፤ መሰወር የሚጋባው እንዲሰውር የተደረገው፤ መገድል የሚገባውም የተገደለው።
  • ·      ጭነት እና ተጫኙ።

አሁን ብዙ ጊዜ አቶ ደመቀ መኮነን ይነሳሉ። አቶ ደመቀ መኮነን ምን ያድርጉ? ምንስ ይፍጠሩ? ለፌድራል ሥራ ቅንነት አይባቸዋለሁኝ፤ አዎንታዊነት አይባቸዋለሁኝ፡ ግን አማራን ለመወከል ግን አቅም የላቸውም። ስለምን? የመሸከም አቅም ስለሌላቸው። አማራ ነህ መባል እና አማራ መሆን በፍጹም ሁኔታ የተለዬ ነው።

ስለዚህ አቶ ደመቀ መኮነን ኦህዴድ እንዳደረገው በቀጥታ ልክ እንደ ዶር ወርቅነህ ገበዬሁ ለፌድራሉ ውክል መላክ ብቻ ነው ያለባቸው። ምን አደረጉ እኒህ ሰው ካለ ፍዳቸው ፍዳቸውን እምናበላው። ያው እነሳጅን በረከትም እኮ የነበረባቸው ችግር ይሄው ነው። አማራ ሳይሆኑ አማራ ሁን፤ ለአማራ ተቆርቆር፤ ለአማራ ባለቤት ሁን ማለትም የተገባ አይደለም።

እኔ አሁን ወንድ ሁኚ ብባል ይሆናልን? አይሆንም። እንደዛ ነው እሳቸው ይህን መሰል መከራ ተሸከም ተብለው የተገደዱት። የማይችሉትን የሥነ - ልቦና አቅም፤ የማንነት አቅም ነው እንዲሸከሙ የተደረጉት። አቶ ደመቀ መኮነን እንደ አማራ አሰብ፤ ለአማራ ብቸኛው ተቆርቋሪ ሁን ማለት ይህ መቼም ፍርደ ገምድልነት ነው።

ስለዚህ ለእኔ ግብረ ምላሹ የሚሰጠኝ ነገር ከሳቸው እራስ አማራ መወርድ አለበትም ኢህአድግም እንደ ድርጅት መንግሥትም እንደ መንግሥት ፌድራል ላይ አማራ ውክልና የሌለው መሆኑን መቀበል ግድ ይለዋል። ስንት ወጣቶች ነው የሚታዩት ፌድራል ላይ የትናንሽ ብህረሰብ ተወካዮች ናቸው ቁልፍ ቦታ ላይ ያሉት። አማራ ግን የለም ስርዙ ነው።
አቶ ደመቀ መኮነን ያደጉበት ቀዬ ሰለሆነ ትዝታው ሊኖራቸው ቢችልም እኛን አማራዎችን ይወክሉ የሚለው ጉዳይ ግን በፍጹም ሁኔታ ከአመክንዮ ውጪ ነው። 

ውሃ ያዘለ ተራራ ተሸከም እንደማለት ነው። አማራነት የሚጫን ክሰል አይደለም። አማራነት የደም ሥር ርስትነት ነው። አማራ መሆን በቃላት መጥበቅ እና መላላት ሳይሆን አማራ ከሆነ ቤተሰብ የዘር ሐረግን መወለድን ይመለከታል።
ስለዚህም አቶ ደመቀ መኮነነም ካለ አቅማቸው ጭነቱን ከምናበዛባቸው እሳቸውን በፌድራል ደረጃ እንዳለ እደን አንድ ኢትዮጵያው መሪ አይተን የአማራነት ማልያውን ግን ከባላያቸው አንስተን አማራ ለሆኑ መስጠት ግድ ይላል።
  • ·      ልብ ካዘኑ፤

በድርጅታዊ ሂደት ከታች ጀምሮ በማምጣት የሚቻልበት ብዙ መነገዶች አሉ። በአስቸኳይ ስበስባዎች አማካኝነት። አሁን ረ/ ፕ/ አባባው አያሌው እና መሰል የ አማራ ልጆች ለአማራነት ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያዊነት ሰቅ ናቸው። አማረነትም ኢትዮጵያዊነትም ሳይጎዳ እኛም ወኪል የለንም ብለን ሳናቆስል ቢያንስ በሥነ - ልቦና አቅም ሙሉ የመሆን ጉዳይ ሊኖር ይችላል። ሥነ - ልቦናችን እኮ ይጎዳል።

አማራ አገር አልቦሽ ስለሆነ አንድ ሁለት ሰው ቢያንስ ፌድራል ላይ መኖሩ ማዕከላዊ በሆነ ሁኔታ በሌሎች ክልሎች ለሚኖሩት አማራዎችም ዋቢ፤ ጠበቃ አለኝ የሚሉት መንፈስ ይኖራቸዋል። ተስፋ ያውላል፤ ተስፋ ያሳድራል። ተስፋም ያዘምራል። እንደዚህ ባሉ አገራዊ ጉዳይ ላይም አንድ የእኔ የሚባል ሲጣፋ ያሳዝናል። ለዘውም ለተቀጠቀጠ መህብረሰብ። ሁሉም ወፍራም ውክልና አለው አማራ ግን በክፍትነት የተተወ … ነው።

ቁስለኛው ነው ቁስሉ የሚሰማው። ሰፊ ማህበረስብ ነው የተዘዘለው ይህ ደግሞ ነገን አያበረክትም ታይቷል ። ጉልበታም ሃይማኖትንም በሚመለከት በፖለቲካ ውሳኔ ላይ ባይተዋር ብቻ ሳይሆን 27 ዓመት ሙሉ ጭራሽ የተረሳ ነው።

ይህ ሂደት ለነገ ሳይሆንም ለዛሬም አይበጅም። እህ እያልን ቀጣዩን ዘመን መግፋት የለብንም። „እውነቱን ተናግሮ ከመሸበት ማደር“ ግድ ይላል። ይቀጥላል …

„አማራነት ይከበር!“

የኔዎቹ ኑሩልኝ። መሸቢያ ጊዜ። 

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።