ህይወት እራሷ ጥያቄ እና መልስ ናት። ትጠይቃለች ወይ ትምለሳለች።


 

ዕለተ ሮቡ ዕለተ ማዕዶተ ተናኜ
በከበቡሽ ቁራሽ እንጀራ
በቢሆነኝ ብራ
በሰብለ ህይወት አዝመራ
ለራህብ የሚራራ።
„ሰነፍ ሰው ቁጣውን ያወጣዋል
ጠቢብ ግን በውስጡ ያስቀረዋል።“
(ምሳሌ 29 ቁጥር 14)
 

 
ዕለተ ማዕዶተ ተናኜ ፈንገጥ ያሉ ዕይታዎቼ የሚቀርቡበት ነው።
የሃሳብ ቀን። ከዚህ ቀደም የሠራኋቸው ያደሩ ጉዳዮችን በቋሚነት
በዬዕለቱ የምሠራባቸው ዘርፎችን ነው። አሁን ወደ መደበኛው ተግባር።፡
ዛሬ አንድ የራሴ የሆነ ነገር ላቀርብ ፈለግሁኝ። ምን ስለምን?
ህይወት የጥያቄ እና የመልስ ጭማቂ ናት በእኔ ፍልስፍና።
ህይወት እራሷ ጥያቄ እና መልስ ናት። ትጠይቃለች ወይ ትምለሳለች። ህይወት ኑሯዋ ጥያቄና መልስ ነው። ኑሯዋ ብቻ ሳይሆን የመኖሯ ዛይቢያ መተንፈሻ ቧንቧዋ ጥያቄ እና መልሰ ነው። ኦክስጅኗ። እህል አብስሎ ለመብላት እሳት፤ ፈጭቶ ለመብላት ወፍጮ፤ ለመጓጓዝ የየብስ - የሰማይ እና የባቡር መጓጓዣ።
እህል ለማምረት ማረስ - መዝራት - ማረም - ማብቀል - ማጨድ - መከመር፤ መውቃት - በመንሹ መለዬት። ከዛ ማስቀመጫሳ? ሲባል እንደ አካባቢው ሁኔታ ዕቃ እንዲህ እንዲህ እያለ አቤቱ ህይወት ለራሱ እራሱን እዬጠዬቀ ኑሮውን የሚያቃልል መሳሪያ ፈለሰመ። ፍልስፍናው ምንጩ ህይወት የሚያቀርበውን ጥያቄ ለመመለስ ነው።
እኛ የምንወድቀው ወይንም አልሆነ ቦታ እምንቀረቅረው የህይወትን ጥያቄ መመለስ ሲሳነን ወይንም ስንዘለው ነው። መጀመሪያ የራሳቸውን የመኖር ጥያቄ የመለሱ ሰዎች ደልዳላ መኖር ይኖራቸዋል። ለምን እሰደዳለሁኝ? ለማን እሰደዳለሁኝ? እንዴትስ ተሰደድኩ? ስሰደድ ምን ላተርፍ ምን ልከሰር? ብከስር አማራጭ የህይወት መስመሬ ምን ይሆናል?
ከጥቂቶች በስተቀር ያልመለሰነው ጥያቄ ውስጥ ተዘፍቀን ህይወት እና እኛ አራባ እና ቆቦ። ብንማረው፤ ብንለብሰው፤ ብናጌጠው፤ ገንዘቡ ቢሞላ ቢተርፍ አንድ የራሱን የመኖር ጥያቄ ከመለሰ ደሃ ከሚያገኜው ሐሤት በላይ መኖር የለም። ለምን ብትሉ አድራሻ በሌለው መርከብ ስለሆነ የመኖር ጉዞ።
ሁልጊዜም፤ ምንጊዜም ህይወት በጥያቄ ውስጥ ነው። ህይወት በጥያቄ ውስጥ ነው የተፈጠረም ብዬ አስባለሁኝ። ፈጣሪ አምላክ የሚያመሰግነው ፈለገ እኛን ፈጠረ። አዳም አንድ ብቻ ሲሆንበት ማባዛቱን እንደምን ላድርገው ብሎ ሲያስብ ከአካሉ አካል ፈጠረለት።
ህይወት ለሰከንድ ከጥያቄ እና ከመልስ ውጪ ሆነ አታውቅም በሥርጉትሻ ፍልስፍና። እንዲያውም ህይወትን የፈጠረው ጥያቄ እና መልስ ነው ብላ ታምናለች ሥርጉትሻ። እናንተስ ውዶቹ? ምን ትላላችሁ?
ማስታወሻ።
ፎቶው ሥርጉትሻ ናት፤ አንሺዋ ጋዜጠኛ ብያንካ ናት። ቦታው ሉዘርን ነው።
(Media macht Media) "ሚዲያን ሚዲያ ይሠራዋል" የሚል አንድ የጀርመንኛ ተናጋሪዎች የፓናል ውይይት ነበር። በወል እና በግል።
የጸጋዬ ድህረ ገጽ እና የጸጋዬ ራዲዮ ልምዱን እንዲያካፍል ካለው የኮምኒቴ ሚዲያ ተመርጦ ተጋብዞ ነበር። በዛ ጉባኤ መላ የፕሬስ ባለሙያ መንግሥታዊም መንግሥታዊ ያልሆኑ ነበሩ ከሊቅ አስከ ደቂቅ። በጣም ትልልቅ ሰዎች።
የዩንሴፍ መሥራች ቤተሰቦች፤ የሁለተኛው ዓለም ጦርነት ወቅት ጋዜጠኛ አባቷ የነበረች ሴትም አግኝቼ ነበር። ዬእኔን ሩም መርጠው መጥተው ነው ነበር። ጥሩ ጊዜ ነበር። ግንቦት 7 የሚባል እፉኝት ድርጀት ያን ገናና ዕውቅና ታገለው እንጂ። ዕድሉ ለአገር አቅም የመሆን ሚስጢራዊ ሥጦታ ነበር። እንዲህ ዙሪያው ገደል ሲሆን ስንት ጥቅም ነበረው። አሁንም አገር ገብቶ ባያምስ ምንኛ መታደል ነበር። ፈቅዶ እራሱን ቢያገል። ትውልዱን ጢባ ጢቦሽ ባይጫወትበት።
ሥርጉተ©ሥላሴ
Sergut©Selassie
17.03.2021
ጎዳናዬ የሃሳብ ልቅና ነው።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።