አሉታዊው ስስት እና ገፈፋ ጠንቅ ነው። ድዌም። ፖርሳ ዬሰከነ መስከንን በእጃችን እንሥራው።

 

አሉታዊው ስስት እና ገፈፋ ጠንቅ ነው። ድዌም።
#ፖርሳ ዬሰከነ መስከንን በእጃችን እንሥራው።
ስስት ሰፊ ትርጉም አለው። እኔ አሉታዊ ስስት ላይ ነው ማተኮር እምሻው።
"ለመብል ሁሉ አትሰስት ላዬኽውም እህል
ሁሉ አትሰስት፤ ብዙ መብላት ደዌ ይሆናልና
ስስትም ጓታን ያበዛዋል እና አትሰስት፤
ስስት የገደላቸው ሰወች ብዙ ናቸው፤
መጥኖ ዬሚበላ ግንሰውነቱ ጤና ነው።"
 

 
ስስታም ዓይኑ ጠባብ ነው። ይቅበዘበዛል። ጎላ ብሎ በወጣው ላይ አንቴናውን ይዘረጋል። የእህል ስስት ለቁንጣን ይዳርጋል። የሥልጣን ስስት ደግሞ ለፋሺዝም። ስስት የህሊና ቀውስም ያስከትላል። ቀውሱ #ማናንሼ እለዋለሁኝ እኔው። የማንነት ቀውስ ያለበት ሰብዕና ውስጡ ሰላም የለውም። ይናደፋል። ይቦጭራል። ሁልጊዜ ግስላ፤ አራስ ነበር ነው።
ሥልጣን ኖረውም አልኖረው ቅምጥ ፍላጎቱን ለማስቀጥል ሩጫው አጋጣሚውን በመጠቀም ይሆናል። አድብቶ ይጠብቃል። ብቅ ብሎ ይሰወራል። አረሳስቶም ጠቀራውን ያንዶለዱለዋል። እሳቱን ጫጭሮም ዞር ይላል። ገባ ወጣ ነው። ለምዱ እስቲገለጥ። አክ እስኪባል። መነገጃው ግን ያው የፈረደበት ኢትዮጵያዊነት ነው። እያከሰለ በምራቁ ቀለም ቀቢነት ያጎሳቁለዋል።
እርግጥ ጠንቀኛውን ዬአንድ ለአንድ አጋበስባሽ ስስቱን አምቀው የያዙ ጊዜ ራዲዮሎጂ ሆኖ እስኪያጋልጣቸው ብዙ ማገዶ ይጠይቃል። ሰብዕናቸው #ግራጫ #በሲቃ ነው። አካሄዳቸው #ተርገብጋቢ እና #ገርበብ ያለ ነው። አልፎ አልፎ ፍንጭ ቢሰጡም ለሰከኑ ዬሰብዕና አጥኝወች ካልሆነ በስተቀር ተሎ ለማዬት ያስቸግራሉ።
የሆነ ሆኖ አቅም፤ አቅል፤ ብቃት፤ ታሪክ ላለው ማህበረሰብ ስስታም ግለሰቦችም፤ ስስታም ተቋማትም የትውልድ ጠንቅ ናቸው። ካንፓቸው እና ካንፓሳቸው #ጥላቻ ነው። ምርታቸው ዲዲቲ ነው። ከሚጠሉት ዘለግ ብሎ የሚወጣ ዬሃሳብ ልቅና ከኖረ ጦር ያዘምቱበታል። ስለምን? መርኽ እና መርኋቸው #ጥላቻ ነውና። ወይንም መስለው ገብተው ያራግፋታል። መለመላውን ያስቀሩታል።
"እግዚአብሄር በአንድም በሌላም
ይናገራል፤ ሰው ግን አያስተውለውም።"
ስስታም #አድራሻ ዬለውም።
ስስታም የሚወክለው #ቀለም ዬለም።
ስስታም #ወካይ ማህበረሰብ የለውም።
ስስታም ወካይ #ሃይማኖት ዬለውም።
ስስታም ወካይ #አገር የለውም።
ስስታም ወካይ #አህጉር የለውም።
ስስታምን ችላው የምንኖር መሬት ብቻ ናት።
///ስስታም መለያው ዬሰብዕና ቀውስ ነው። መነሻው የበታችነት ዝንቅንቅ ስሜት ነው። ሃኪም ዬለውም። ///
ስስታም ከእህል ዘር፤ ስስታም ከአትክልት ዘር፤ ስስታም ከፍራፍሬ ዘር፤ ስስታም ከልብስ ዘር፤ ስስታም ከገንዘብ ዘር፤ ስስታም ከሥልጣን ዘር ሁሉንም ስጠው #አይጠግብም#በቃኝን አያውቅም። በቃህ ዬሚለው የቆረጠ መንፈስግን ያስፈልገዋል። ምክንያት? ከፈነዳ አገር ምድሩን ስለሚያበላሽ፤ አገር ምድሩን ስለሚያውክ፤ ለአገር ምድሩን ወረርሽኙን ስለሚያጋባ። በተለይ ሚዲያ ላይ ቁንጮ ከሆነ፤ ሥልጣን ላይ ቁንጮ ከሆነ፤ በንግግር ጥበብ ክህሎት ከተሰጠው አደጋው ግዙፍ ነው።
ሙሶሎኒም ናዚም ያን ሁሉ ህዝብ በጥላቻ በተወጠረ ስሜት በገፍ የነዱት በንግግር ጥበባቸው እና በአገኙት የሥልጣን አጋጣሚ ነው። ሁለቱም ኢትዮጵያ ላይ ተከስተዋል። በአደብ በተደሞ ጨምቶ ለሚያዳምጥ፤ ምራቁን ለዋጠ ንጥር የሃሳብ ልቅና።
ስስታም ሰብዕና ሆና ስስታም ተቋም አሳማ ነው። ዬሚቀረው የለም። ገዳፊም ነው። ውጥረቱ፤ መንጠራራቱ፤ ትምክህቱ ሁሉም ምንጩ ጥጋቡን ካለመቻሉ የመጣ ነው። አቅል ዬለውም። ቱግታ - ያበዛል። አደብ የለውም ገረጭራጫ ነው። ርህርህና የለውም ብስጩ ነው። አይዟችሁን አያውቅም ግለኛ ነው። ቁንጥንጥ ነው የውሳኔ ሰብዕና ዬለውም። ክልፍልፍም ነው እርጋታ ያነሰው።
ታላቋን ኢትዮጵያ፤ ዬኔታዋን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶን፤ ዬአማርኛ ቋንቋን፤ ዬአማራን #ሊቃናት ክህሎት፤ የስሜን ቀደምትነት፤ የጉራጌን፤ የወላይታን፤ የጉጂን፤ የቦረናን፤ የአማሮን ዛሬ ፍዳ ምንጩ የስስታሞች ሂደት ያመጣው ነው። በተናጠልም በተደራጅም ኩነት። ነገ የሃድያን፤ ዬአፋርን፤ ዬጋሞን፤ ዬጋንቤላን ህዝብ በቀጣይ የሚገጥማቸው ዘለግ ያለ ፈተናም ማህበረ ስስታም ዬሚፈጥሩት ብሄራዊ ጦሮ ይሆናል።
#ጦሮ መንጦላይት ንፋስ ነው። መንጦላይት ማለት ክፋት እና ጭካኔ ያዬለበት ሰብዕና ማለት ነው። ጦሮው ማለት ደግሞ አቧራ ከኃይለኛ ወጀብ ጋር ተዘንቆ ቤት እያፈረሰ፤ ቆርቆሮ እዬነቃቀለ ጦር የሚያውጅ እንደ ልቡ የሆነ የመርገምት ዬንፋስ ዓይነት ነው።
በዚህ ልቅ እና አናርኪዝም ዘመን ዬምናዬው የምድር መንጦላይት ጦሮ ከማህበረ ስስታም አብራክ ዬተቀዳ ነው።
ምን እናድርግ?
1) ስስታምነት ድዌ በመሆኑ ማህበርተኛ ላለመሆን መወሰን።
2) ስስታምን ከማድመጥከማድነቅም መጠበቅ።
3) ዬእኛ አቅም ላይ ስላወጣው ያን በገፍ የሰጠነውን አቅም መንጠቅ። ከዛ ሽፋኑን ከልቶ በአደባባይ ማህበረ ስስታምን ይቀላቀላል።
ቅን አቅም ይመግባል። እናም ያወጣል። ግን ማውረጃው ይሳናል። ኢትዮጵያን ለዚህ የምፃዕት ቀን ያበቃናት እኛው ነን። አሁንም በግልም በጋራም ያለውን ምጣት ማስቆም መቻል ባይቻለን እድገቱ እንዳይጨምር ለማድረግ መጋለቡን አቁሞ ተግ ብሎ ማድመጥን ግዛኝ፤ ንዳኝ ማለት ተገቢ ይሆናል።
ተመሳስለው ያሉ ስስታሞችን #አክ ለማለትም መሳሪያው #አድምጦ መነሳት ነው። በአንድም በሌላም ገባ ወጣ እያሉ፤ አጋጣሚ እዬጠበቁ የሚያጠቁ ተናዳፊ ስስታሞች ናቸው። ያን ዬሚጠሉትን ባዩ፤ ባደመጡ ቁጥር ቀንዳቸው ሲቆም ታያላችሁ፤ በአንድም በሌላም። ምንጩን ማጥናት፤ ከአጠኑ ፈውሱን መፈወስ ያስፈልጋል።
ፈውሱ በገፍ ዬሰጠኽውን አቅም ካለምንም ቅድመ ሁኔታ መንጠቅ እና ማራገፍ። በቃ፤ በቃኽኝ ማለት በድርጊት ማስጌጥ። ፈረንጆች ተግባር ሁለንም ነው ይሉ የለ። እንደዛ። አለማድመጥ እራሱ መዳህኒትም ነው። ያን ካለ አቅም እና ወርዱ የተንጠለጠለውን ስውሩንም ግልጡንም በበታችነት ስሜት ዬሚዳክረውን ማራገፍ ይቻላል። ባዶ ወና ቤት ማስቀመጥ። ዕውነት፤ መርህ ሁልጊዜም ይዳኛሉና።
#ሲከወን ………
ጎንደሮች ሙያ በልብን ያመሳጥራሉ። እንሁንበት። ክድን አድርጎ፤ ክድን ብሎ መስራት። ድሉ አደባባይ ሲናኝ እንኳንስ ለሌላው ለባለቤቱም እንግዳ ይሆናል። ማን አደረገው? ስለምን ሆነ አድራሻ ዬለውም። ግን መልካም ነገር ሁኗል። ሲጠነሰስ በቀንጣ ሲከወን ደግሞ ቀንጣው የለለበት የአደባባይ አጃቢ የሚጎርፍበት ይሆናል።
በዚህ መልክ ከቅንጣት እስከ ገዘፈው ተጋድሎ ከግርግር፤ ከታይታ፤ ከፕሮፖጋንዲስትነት፤ ከአክቲቢስትነት በላይ የሰከነ መስከንን በእጃችን እንስራው። ማህበረ ስስታም ለውሻ ሥጋ እንደሚሰጠው በዙር ብጣቂ ቆሽቋሽ ደም አንተክታኪ ጉዳዮችን እዬነካኩ ግን እነሱ ደርዝ ያለው ተግባር ያዋጣናል ባሉት መንገድ ቀጥለዋል። ግልፁ ማህበረ ኦነግ፤ ስውሩ ማህበረ ኦህዴ። መቀደምን ለመቅደም ስለመቅደም መቀዳደም ጥናት። በወረት ቅርሻ መጠለፍ ሽንፈት ነው።
ላም እረኛ ምን አለ ለተቋማት ብቻ አይደለም ለዜጋውም ነው። እሺ። እሺ ትበልልኝ ዬእኔ ድንግል። አሜን።
እግዚአብሄር ይስጥልኝ።
ሥርጉተ©ሥላሴ
Sergure©Selassie
17/03/2023
ጊዜ ራዲዮሎጂ ነው።
የሰከነ መስከንን በእጃችን እንሥራው።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።