ዬአማራ እናት ከስድስት ልጆቿ ጋር ተገደለች። 07/11/2022

 

ዬአማራ እናት ከስድስት ልጆቿ ጋር ተገደለች።No photo description available.
 
 
ዬአሪሲዋ ሁሩርታም አዬሯ በስጋት እዬተናጠች ነው።
"የቤትህ ቅናት በላኝ።"
እያዘንኩ ነው እምጽፈው። በጢቾ ሮቤ መስመር ሌሊቱን ሁሉ ስትሄዱ ብታድሩ ምንም ንክች የሚያደርጋችሁ የደረቅ ወንጀል ፈፃሚ እንኳን አልነበረም። አይደለም የአማፂ ድርጅት አባላት።
አሁን ግን የበዛ ስጋት ሙሉ አርሲ አንዣቧል። ከተሞች ለጊዜው ሰላም ቢመስሉም የገጠር ቀበሌወች ግን ኦነጋውያን በዛው በመከረኛው አማራ ላይ ጥቃታቸውን ቀጥለዋል።
አንዲት እናት ከስድስት ልጆች ጋር፣ 9 አማራውያን ከሦስት ቀን በፊት ተመሳሳይ 5 ዬአማራውያን የንፁኃን ግድያ በገበሬ መንደሮች እዬተከወነ ነው። በአርሲ ጀጁ ……በመንበረ ሕይወት፣ በአዲስ ህይወት መንደሮች። ከገጠር ጀምረው ነው የዘር ማጽዳት ዘመቻው የተወጠነው።
የዘመኑ የፖለቲካ ባህሬ ተረኝነት ሲባል አይደለም ይህ እጭ ላይ ያለ የፖለቲካ ዕሳቤ ነው። አሉታዊ ዴሞግራፊ ላይ ተቀምጦ ይህ መሰል የፖለቲካ ትንታኔ አዘናጊ፣ ትጥቅ አስፈቺ፣ አልዛዢ ነው።
ዘመኑ የገዳ ወረራ፣ የገዳ፣ መስፋፋት፣ የገዳ አስምሌሽን፣ የገዳ ዲስክርምኔሽን ነው በማለት አዲስ አበባን ናሙና አድርጌ አራት ዓመት ሙሉ፣ ጽፌያለሁ ተናግሬያለሁ።
የችግር መፍቻ አቅም የምታመነጨው፣ የችግሩን ዕውነተኛ ፍላጎት ስታውቀው ነው። በደራሽ እና በጭፍጫፊ አጀንዳ አቅም ሲባክን ባጁ። አሁን ነገረ አማራ ተራግፎ ሙት መሬት ላይ ይገኛል።
አይነ ስውራን፣ አቅመ ደካሞች፣ አረጋውያን፣ ሴቶች፣ ህፃናት ካለምንም ሃግ ባይ ሰፊ ጥቃት እዬተፈፀመባቸው ይገኛል።
ለዚህም ነበር አበክሬ በተከታታይ
1) ዓለም ዓቀፍ ጠበቃ ቀጥረን መጤም፣ ሰፋሪም ከተሆነ ህግ ይበይንብን። ሪፈረንስ የኔታ ፕ/ ዶር ሃብታሙ ተገኜ፣ ዬኔታ አቻምዬለህ ታምሩ የሠሩት ጥናታዊ ጽሁፍ ይሆናል። እያንዳንዳችን በዬወር እያዋጣን እርስታችን ዕውቅና የማሰጠት ህጋዊ ሂደት ይጀመር ብዬ በአጽህኖት ለመንኩኝ። ሰሚ ዬለም።
በደራሽ ጉዳይ እፍግብ ከማለት በስተቀር። አክሰሱ ያላቸው፣ ሁሉ ያላቸው አማራ ልጆች አሉት ግን ገነገነበት። ዛሬ እንዲህ የተሆነ የዛሬ 20/30/40 ዓመት ሲታሰብ ይበርዳል።
2) የአማራ ህፃናትን መብት የሚያስከብር ከፖለቲካ ጉዳዮች ጋር ንክኪ ዬሌለው ግብረ ሰናይም፣ ጠባቂም ተቋም ይፈጠር ብዬ በአንድ ወቅት መምህርት እና ፀሐፊ መሰደረም አበራ ብትይዥው ይህን ፕሮጀክት ብዬ በይፋ ጽፌያለሁኝ።
ተቋሙ መምህራን፣ የህክምና ሰወች፣ የማህበራዊ ኑሮ ሙሁራን፣ የህግ ባለሙያወች፣ የሥነ ልቦና አዋቂወችን ሊያካትን እንደሚገባ የመነሻ ሃሳብ አቅርቤ ነበር። እንደ ዩኒሴፍ ያለ። ተጽዕኖ ፈጣሪ ሲለቅሙ ውለው ለሚያድሩ ሚዲያወች ይህን መሰል ሃሳብ እንደ ትቢያ ዬሚታይ ነው።
3) ለአማራ ህዝብ እራሱን ዬቻለም የሰባዕዊ መብት ሞጋች ድርጅትም ስለሚያስፈልገው የምትችሉ ባሊህ በሉት ብዬ ነበር።
ዬአማራ ህዝብ እስራኤሎች ባለፋበት የትግል መሥመር ማለፍ ካልቻለ ተበትኖ የመቅረት ዕጣው ሰፊ ይሆናል። ቀስ በቀስ በዬለቱ 5 ዓመት ሙሉ የአማራ ሞት ያልተመዘገበት ማዕልት ከቶም ዬለም።
የሚገርመው አሜሪካን አገር የጽዮናዊነት ትግልን የመሩ ድርጅቶች፣ ተቋማት እያሉ በአማራ ሥም የተደራጁ ተቋማት እስከ ዛሬውዕለት ጆይን አላደረጓቸውም። ህወሃት ግን ገና ይፈፀምብኛል ብሎ ምን እንደ ሠራ ተመልክተናል። እንዲህ ዓይነት ከፕላን ኤ እስከ ዜድ ድረስ፣ ከፕላን ሀ እስከ ፕላን ፐ ድረስ የሚመራ ተቋም በስለትም የአማራ ህዝብ ካገኜ ሽልማት በሆነ ነበር።
ትግል በአንድ ወቅታዊ ጉዳይ ብቻ አይደለም። የገዘፋ ሁለት ተጋድሎ ነው የአማራው። የማንነት እና የህልውና ተጋድሎ። ይህን ለመምራት በደራሽ ጉዳይ ተጠምዶ አይሆንም። ሥራን ኃላፊነትን ማከፋፈል ይገባል።
ከልዩ ኃይል ወደ ፋኖ፣ ከፋኖ በቀጥታ ወደ ነገረ ድርድር? አሁን "እኔም ፋኖ ነኝ" ተረስቷል። ዬዛሬ ዓመት የኔታ ጎዳና ያዕቆብ ለድርድር መነሻ ሰነድ አዘጋጁ፣ ተደራዳሪ አካል ሰይሙ ብለው ጽዋ ሚዲያ ላይ አቅርበዋል።
ይህም ብቻ ሳይሆን በስሜት ሳይሆን በስሌት ዬአማራ ትግል ቢመራ ጥሩ ነው። አማራ ይከዳል በማለት አቅሙን ቆጥቦ እንዲያስተዳድር የፃፋትን በፀጋዬ ራዲዮም፣ በዩቱብ ቻናሌም ጹሁፋን አንብቤዋለሁኝ።
የህልውና ተጋድሎ፣ የማንነት ተጋድሎ መጠነ ሰፊ ነው። ለዛው ጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ በሚመሩት አገር። እሳቸው አሳቻ ናቸው። አለን የሚባል የአማራ ህዝብ ተቆርቋሪ ድርጅት ሚዲያውን ሁሉ ሞልቶት ነበር። ዛሬ የማን ነው አለን?
ሌሎች አማራ በብዛት የሚሳተፍባቸው የፖለቲካ ድርጅቶች አብን፣ ባልደራስ የማን ናቸው። የውጭ የድጋፍ አካሎቻቸውስ? ዶር አብይ አህመድን ለመታገል ብዙ በጣም ብዙ ጥበብን፣ ስልትን ተደሞን፣ ጥሞናን ይጠይቃል።
አሁንም የኦነጋዊው ኦህዴድ ሙሉ አቅም አማራው ነው። ለምን? ኦነጋውያኑ ምራቅ ላይ ያስቀመጧት ኢትዮጵያ እስረኛ ነውና አማራው።
ከዚህ ውጪም ልሁን ቢል ማን አለ? ምን አለ? ከሥር መሬት ላይ ማለቴ ነው። የግለሰቦች አቅም አስተዋፆ ነው።
የዳኝነት ሚና ያለው የተቋም ብቃት ነው። ግለሰቦች ለሽ ሲሉ ሁሉም ምርኮ ይሆናል። ውጥኑ ይበርደዋል። ወደ መቃብር ይከዘናል። ተቋማዊ ሲሆን ግን ይመክታል። ይዳኛል።
እግዚአብሔር ይስጥልኝ።
ሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
07/11/2022
ጊዜ ራዲዮሎጂ ነው።
"ተረኝነት" ብቻ ሰለመሆኑም ነገ ቁምነገር አለው ይጋፈጣችኋል፣ ለዚህ አደንዛዥ ዕፅ የፖለቲካ ተንታኞች።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።