ስለአዲሱ ኮሮና ቫይረስ ማወቅ የሚገባዎ ነጥቦች /ከቢቢሲ የተጋራ/


እንኳን ወደ ቀንበጥ ብሎግ በሰላም መጡልኝ።

„አቤቱ ሰውነቶቼን አሁንም ለአንተ ሰጠሁኝ።“
(መጽሐፈ ጦቢት ምዕራፍ 4 ቁጥር 12)

ከሥርጉተ©ሥላሴ
Sergute©Selassie
25.01.2020
ከጭምቷ ሲዊዘርላንድ።


ስለአዲሱ ኮሮና ቫይረስ
ማወቅ የሚገባዎ ነጥቦች
 እንዴት ናችሁ ቅኔዎቹ የአገሬ ልጆች ደህና ናችሁ ወይ? እኔ ደህና ነኝ። ቢቢሲ የአማርኛው ክፍል ዛሬ ወሳኝ ነጥብ አንስቷል። ስለ አዲሱ ኮሮና በሽታ። ጤናችሁም፤ ደህንነታችሁም አጀንዳዬ ስለሆነ እነሆ ሼር አድርጌያለሁኝ። እናንተምስ ሳትደክሙ መልዕክቱን ሼር አድርጉት።  
„በቻይናዋ ዉሃን ግዛት የተከሰው ኖቭል ኮሮና ቫይረስ ከቻይና ውጪ ወደ በርካታ አገራት እየተዛመተ ይገኛል።
አሜሪካ፣ ፈረንሳይ፣ ጃፓን፣ ደቡብ ኮሪያ፣ ታይዋን፣ አውስትራሊያ በሽታው መታየቱን ሪፖርት ካደረጉ አገራት መካከል ይገኙበታል።
የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ቫይረሱ ወደ ኢትዮጵያ እንዳይዛመት እየወሰደ ስላለው እርምጃ እና ስለ ቫይረሱ የሚከተለውን መረጃ አስተላልፏል።
·       ኮሮና ቫይረስ ምንድነው?
የኮሮና ቫይረስ ከቀላል እስከ ከባድ የመተንፈሻ አካል ሕመም የሚያስከትል የቫይረስ ዝርያ ሲሆን ሞትን ሊያስከትል የሚችል ህመም ነው።
የቫይረሱ መተላለፊያ መንገዶች
በሽታው ያለበት ሰው ሲያስነጥስ፣ ባልበሰሉ ምግቦች፣ ከታማሚው ሰው ጋር በሚደረግ የቅርብ ንክኪ ይተላለፋሉ።
·       የበሽታው ምልክቶች
በበሽታው የተያዙ ሰዎች ትኩሳት፣ ሳል፣ የትንፋሽ መቆራረጥ እና የመተንፈስ ችግር ምልክቶች ይታይባቸዋል።
በሽታው የጠናባቸው ሰዎች ላይ ደግሞ እንደ የሳምባ ምች እና ከባድ የመተንፈሻ አካላት ህመም ይስተዋላል።
·       በበሽታው መያዛቸውን የጠረጠሩ ሰዎች ምን ማድረግ አለባቸው?
ከላይ የተጠቀሱት ምልክቶች ካለብዎ ወዲያውኑ በአቅራቢያዎ ወደሚገኝ የጤና ተቋም ይሂዱ።
የበሽታው ስሜት ከመፈጠሩ አስራ አራት ቀናት በፊት በሽታውን ሪፖርት ወዳደረጉ አገራት ሄደው ከነበረም ይህንንም ለጤና ባለሙያ ያሳውቁ።
በሚያስሉበት እና በሚያስነጥሱበት ጊዜ በሽታው ወደ ጤነኛ ሰው እንዳይተላለፍ አፍና አፍንጫን በክንድ፣ በመሃረብ ወይም በሶፍት ይሸፍኑ።
አፍን አፍንጫን ለመሸፈን የተጠቀምንበትን ሶፍት በአግባቡ በቆሻሻ መጣያ ውስጥ ማስወገድ እና እጅን ሁልጊዜ በውሃ እና በሳሙና መታጠብ ያስፈልጋል።
በበሽታው መያዝዎን ሪፖርት ለማድረግ በነጻ የስልክ መስመር 8335 ወይም የመደበኛ ስልክ 0112765340 መጠቀም ይችላሉ።
·       በሽታው ወዳለባቸው ሃገራት ሲጓዙ ሊወሰዱ የሚገቡ ጥንቃቄዎች
ትኩሳት እና የሳል ምልክት ከሚያሳዩ ሰዎች ጋር ንክኪ አለማድረግ
በተለይ ደግሞ ከታመሙ ሰዎች ወይም ከአካባቢያቸው ጋር ንክኪ ከፈጠሩ እጅን በሳሙናና ውሃ መታጠብ
ያልበሰሉ የእንስሳት ተዋጽኦዎችን አለመመገብ
በሕይወት ካሉም ሆነ ከሞቱ የቤት እና የዱር እንስሳት ጋር ንክኪ አለማድረግ
ስለ በሽታው በቂ መረጃ እንዲኖረዎ የሚመለከታቸውን ይጠይቁ
የመከላከልና የዝግጁነት ሥራዎች
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቤጂንግ፣ ሆንግ ኮንግ፣ ሻንጋይ፣ ቸንዱ እና ጓንዡ እንደሚበር ይታወቃል። ይህ ቫይረስ ከተሰራጨባቸው ከተሞች መካከል ደግሞ ቤጂንግ እና ሆንግ ኮንግ ተጠቃሽ ናቸው።
ከዚህ በተጨማሪም ቦሌ ዓለም አቀፍ አየርማረፊያ በርካታ መንገደኞች አቋርጠውት የሚያልፉት በርካታ ናቸው።
የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በዓለም ጤና ድርጅት ምክረ ሀሳብ መሠረት ለሁሉም መንገደኞች የሰውነት ሙቀት የመለካት ሥራ መጀመሩን አስታውቋል።“

መሸቢያ ጊዜ። ኑሩልኝ።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።