• #ብሄዊ የምህረት ዓዋጅ አስፈላጊነት እና፤ ለአፈፃጸሙ አክብሮትን ስለመመገብ።
የምህረት ዓዋጁ ዱርቤቴ ላሉት ብቻ አይደለም፤ ተንሳፎ ላለው የብልጽግና አካላቱ ጭምር ነው። በጣም ውስብስብ፤ የተፍተለተለ ችግር ውስጥ ነው ክልሉ ያለው። እንደ አገር ኢትዮጵያም የአማራን ህዝብ ቅንነት፤ ገራገርነት ልታጣ አይገባትም። አክብሮ መነሳት፤ ጠንክሮ በማስተዋል መትጋት፤ በብልህነት መከራውን እያዬ ያለውን ህዝብ አለሁልህ ማለት ይገባል። በጥልቀት እንሰበው። በሰፊነትም እንመርምረው።
"አቤቱ ንጹህ ልብ ፍጠርልኝ።" አሜን።
ምዕራፍ ፲፯። በዚህ ዘለግ ባለ የወግ ገበታዬ ምዕራፍ ፲፯ ይጠናቀቃል። ከጥቂት የጥሞና ቀናት በኋላ ምዕራፍ ፲፰ ይመጣል።
#መኽራዊ አትኩሮት።
ጤና ይስጥልኝ ማህበረ ቅንነት፦ እንዴት አደራችሁ? እንደምንስ - አረፈዳችሁ። እኔ አምላኬ ክብሩ ይስፋ ደህና ነኝ። በክሪስማስ ሰሞናት ለእኔ አሸወይና ነበር። የመጸሐፍቶቼን ስክሪፕት እማርምበት። በዚህ ሰሞን ነፍስ በምድር ላይ ሥራውን ያቆመ ያህል ጸጥ ስለሚል በርካታ ያላጠናቀቅኳቸውን የአዕምሮ ተግባራት የምከውንበት የመኽር ወቅቴ ነው። በዚህ ዓመት ደግሞ በተለያዩ ሚዲያወች የወጡ የአማራ ህዝብ ድምጾችን ለማድመጥ ፈቀድሁኝ። ዜናወችንም ውይይቶችንም በእኔነት ሙሉ ስሜት ተከታተልኩ።
#ውስጤ።
ገና ቀንበጥ ሳለሁኝ ሰፊ ዕድል አግኝቼ ምን ላድርግልሽ ስባል ወደ ገበሬዬ መልሱኝ ነበር ያልኩት። እኔ ጎንደር ከተማ ተወልጄ ነው ያደግኩት። ቤተሰቦቼም እንደ እኔው። የከተማ ልጅ ሆኜ ገበሬን እንደ ነፍሴ የመውደዴ ሚስጢር የገበሬው ተፈጥሯዊነት ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድ 100 ቀናታቸው ሳይጠናቀቅ ከፃፍኩላቸው ሙግት መሰል የወግ ገበታዬ አንዱ የገበሬው የፖለቲካ ውክልና ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ መንግሥታቸው እያንዳንዱን መንደር ሊጠብቅ ስለማይችል የአማራ ህዝብ ራስዘብን ትውፊታዊ የትጥቅ እና አገር የመጠበቅ ይተባህሉን ጉዳይ እንዳያውኩት፤ ይልቁንም ጥበቃ እንዲያደርጉለት በትህትና አሳስቤያቸው ነበር።
ሁለቱም ከአማራ ገበሬ የትጥቅ እና ተፈጥሯዊ ይተባህል ጋር የተያያዘ ነበር። ያን ጊዜ ጹሁፌን ይከታተሉ ነበር ብዬ አምን ስለነበር ዘለግ አድርጌ ነበር ሃሳቤን ያቀረብኩት።።
የሆነ ሆኖ ለእኔ ነገረ ገበሬ ከድምጹ፤ ከአኗኗሩ ዘይቤ፤ ከቅንነቱ፤ ከፈርኃ እግዚአብሄር እና ፈርኃ አላህነቱ፤ ለሰው ልጅ እና ለተፈጥሮ ከሚሰጠው ትሁት ደግነት፤ ንጹህ አክብሮቱ፤ ከተፈጥሮ ጋር ካለው የመግባባት ውህድ ማንነቱ ጋር የሚመስጠኝ ህዝብ ቢኖር ገበሬው ነው። ገበሬውን በሚመለከት አደራጁ ሁኜ አብሬው ህይወቱን ስለኖርኩኝ መፈጠር እንደ ገበሬ መጽደቅ ነው ብዬ አምናለሁኝ።
ይህ የማርክሲስት ሌኒኒስት ርዕዮት ብስጭት እና ገበሬ መንደሮች ለዚህ ዓላማ መዋላቸው በብዙ ሁኔታ የአማራን ገበሬ ፈተና ውስጥ ያስገባ የመከራ፤ የሰቆቃ፤ የጭንቅ ህይወት ይኖር ዘንድ የተገደደበት ህይወት እንደተፈጠረበት አስባለሁኝ። ውስጤ ሁልጊዜም፤ ለምንጊዜም ለዚህ ንጹህ ማህበረሰብ ይጨነቃል።
#የአማራ ክልል ውይይቶች።
ያው ልደት ሲደርስ፤ ልደትን አስታኮ ብልጽግና የተለያዩ ስብሰባወችን በአማራ ክልል ያሰናዳል። የልደት ዋዜማም በብሄራዊ ያደርገውና አትኩሮትን ሻሞ ይይዛል። ምክንያታዊ ነው። ለጊዜው ይህን ልተው እና የሰሞናቱ ህዝባዊ ስብሰባ ገበሬወችም ስላሉበት ከውስጤ ሆኜ ተከታትዬዋለሁ። እንደ ጸሐፊ ትንቢተኛው አቤ ጉበኛ አልወለድም፤ ትንሳኤውን አግኝቶ "ባልፈጠር ይሻለኛል" የሚል ቃል አዳመጥኩኝ። የአማራ ገበሬ ምርር ብሎታል። አንገፍግፎታል፤ አንገሽግሾታልም።
በብዙ ሁኔታ የጎጃም ገበሬ ከአርበኛ በላይ ዘለቀ ንቅናቄ እና ብሄራዊ ሁነት ባሻገር የሰላም ቀጠና ነበር። ኤርትራ፤ ትግራይ፤ ጎንደር እና ወሎ ነበሩ ከንጉሳዊ ሥርዓት መውደቅ ጋር ዱር ቤቴ ላለ የዘመኑ ወጣቶች ምሽግ ሆነው አሳራቸውን ያዩት። ጎጃም ምድረ ገነት ነበር። አሁን ደግሞ ስቃይ። እጅግ አሳዛኝ ክስተቶችን አዳመጥኩኝ።
ጯሂት ትንሽዬ ከተማ ናት። የቅቤ ከተማ ናት። የጎንደር ከተማ ነዋሪ የዓመቱን ቅቤ የሚገዛው ቅቤ ጯሂት ነው። ከጯሂት ቆላድባ፤ ከቆላድባ ጎርጎራ፤ ከአዘዞ ቆላድባ መሄድ ጋዳ ሆኗል። ጯሂትን ያነሳሁት ስለማውቀው እንጂ በጎጃም በብዙ ቦታወች፤ በወሎም መሰሉ ህዝብ ጭንቅ ላይ መሆኑን አዳመጥኩኝ። እኔ ወሎ በዚህ ልክ ይሆናል ብዬ አላሰብኩም ነበር።
"#ሁሉም ልጃችን ነው።"
እንደ አዳመጥኩት ፋኖም፤ መከላከያም፤ የአማራ ክልል ሚኒሻም፤ የአማራ ክልል አድማ በታኝም ልጃችን ነው ጎልቶ የወጣ የሁሉም ጉባኤወች ድምጽ ነው። ስለዚህ ምን ሊደረግ ይገባል ብዬ ሳወጣ ሳወረድ #ብሄራዊ #የምህረት #ዓዋጅ አስፈላጊነት ጎልቶ ታየኝ።
2) ከፋኖ የተመለሱም፤ ከመንግሥት ጋር ያሉትም የጠቀሱት ጉዳይ መንግሥታዊ መዋቅሩም ውስጥ የዱር ቤቴ መንፈስ እንደ አለ፤ አንድ ወጣት ሲገልጽ እንደ ሰማሁት የወረዳውን፤ የዞኑን የመንግሥት ስብሰባ የፋኖ መሪወች ያደምጡት ዘንድ እንደሚደረግ አድምጫለሁኝ። ይሄ ከፖለቲካዊ ዕድምታ አንፃር ከባዱ ሁነት ነው። የገዘፈውም። ስለምን መዋቅራዊ ኃላፊነት እያሉ ይህን መሰል ኃላፊነት ሊወስዱ ፈቀዱ? ምን ጎድሎባቸው? ምንስ አጥተው። ቁጣ አያስፈልገውም። ቁንጥጫም አያስፈልገውም። የልብ መሸፈትን መንስኤ አጥንቶ ዘላቂ መፍትሄ መስጠት የአመራር ብቃትን ይጠይቃል።
3) በመንግሥት መዋቅሩ እና በፋኖ የመሻት ማዕከል ውስጥ ልጥፍ ሳይሆን ውህደት ድልድይ እንዳለ ፍንጮቹ ይጠቁማሉ።
4) የዱር ቤቴ ጽንሰ ሃሳብ ከተማንም እንዳካተተ የሚያስረዱ ፖለቲካዊ ዕድምታወች አሉ። ዋና ከተሞች #ደሴት ሆነዋል። ደብረማርቆስ፤ ፍኖተሰላም፤ ደብረታቦር፤ ጋይንት፤ ባህርዳር፤ እብናት፤ አዲስ ዘመን፤ ሐይቅ፤ ወልዲያ፤ ደሴ፤ ዳባት፤ ደባርቅ፤ አጣዬ፤ ጎንደር፤ ደብረብርሃን፤ ሽዋሮቢት፤ አንባጊዮርጊስ ወዘተ ……… ፋኖ በጫካ አለ።
ፋኖ በመንግሥት መዋቅርም አለ። በራሱ በብልጽግና አመራር ውስጥም እንደ አለ ተመላሽ የፋኖ መሪወች ሲገልጡ ሰማሁኝ። ከቀጠናቸው ውጪ በሞፈር ዘመት ሂደው ተመላሽ ታጣቂወች እጅ የሚሰጡበት ዓይነተኛ ምክንያትም ይኽው ጉዳይ ነው። መተማመን፤ መታመን አማራ ክልል ውስጥ ስደት ላይ እንዳሉ ምልክቶችን አስተውያለሁኝ።
5) ካፒቴን ፻አለቃ ማስረሻ ሰጤ ሰርተናል፤ አሳክተናል ካላቸው ወሳኙ "የኃይል መዛባት ፈጥረናል ነው።" እእ። የሃይል መዛባት የተፈጠረ ነገር የለም። የፋኖ መሠረቱ ህዝባዊ ነው። ህዝባዊ ስለሆነ ማዕከላዊ አመራር ለመፍጠር እስካሁን ያልተቻለው የፋኖ የአፈጣጠር ተፈጥሮ ስለማይፈቅድ ነው። ጽፌበታለሁም አውዲዮ ሠርቸበታለሁኝ።
ከዚህ በኋላ 20/40 ዓመት ቢቆይ ፋኖን ማዕከላዊ አመራር ፈጥሮ ማስተዳደር አይቻልም። ስለሆነም የታጠቀ ኃይል ማዕከላዊ አመራር ከሌለው አደጋው ብዙ ነው። የሰማናቸው መከራወች ሁሉ ከፋኖ የአደረጃጀት አፈጣጠር መርህ ጋር ግጭት ስላለ ነው። የፋኖን ተፈጥሮ ሳያውቁም፤ ሳያድጉበትም የከተማ ልጆች ፋኖን እንምራ ሲሉ ያልቻሉበት መሰረታዊው አመክንዮ ይህ ነው። ከዚህ ስንነሳ የፋኖ አመራር በሰላምም፤ ይሁን በምህረት ሲገባ የሚዛባ የኃይል ሚዛን አይኖርም። እራሱን እና ጥቂት ተከታዮቹን ይዞ ነው ሊገባ የሚችለው። ይህ የሚሠራው እንደ ህወሃት ላለ ድርጅት ነው።
መሠረቱ ከመሠረቱ ነው ነገረ ፋኖ። መሬት ላይ በቀበሌ ገበሬ መንደር ላይ ነው ያለው ፋኖ። በሌላ በኩል የፋኖ አደረጃጀት የጎበዝ አለቃ ለመምረጥ ማን ቢወልድ ማን አለበት?
በሌላ በኩል ፋንኖ በትግል መቆየትም አይቻልም። ፋኖ ለደራሽ ችግር ደራሽ መፍትሄ ሰጪ እንጂ ለረጅም ተጋድሎ የሚሆን የአደረጃጀት ተፈጥሮ የለውም። ገብያ ላይ አይዋልም አይታደርም። ገብያው ሲፈታ ገብያተኛው ወደ ቤቱ ይመለሳል። የፋኖ ተልዕኮም የተመጠነ፤ ቆይታው ለአጭር ጊዜ እና ስኬታማ ነው።
ለረጅም ጊዜ ከሆነ ፋኗዊ ትግል ይከብደዋል። ይህን አልተረዱም ጀማሪ መሪወቹ። አሁን ባለው ውይይት የፋኖ ትግል በተራዘመ ቁጥር የህዝብን ሙሉ መንፈሳዊ፤ ቁሳዊ፤ ሎጅስቲክስ እየሳሳ ይሃዳል። ፋኖነን የግንባሩን ከውኖ ተሎ ወደ መደበኛ ህይወት መመለስ ነው ተፈጥሮው።
በሌላ በኩል ማዕከላዊ የአወቃቀር ሁነት ከሌለ የሚዛባ የኃይል ሚዛን አይኖርም። ያ ቢሆን ኖሮ መሪው ሲገባ ከጫፍ እስከ ጫፍ ሆ! ብሎ ተንዶ ይገባ ነበር። የራሱን ድርጅት ከአንገት ላይ ይሁን ቁርጭምጭሚት ላይ ወለምታ ሊፈጥር ይችላል። ከዛ በተረፈ ግን ካፒቴኑ ባሰበው ልክ የሚፈጠር ፊኖሚናል ሁነት አይኖርም።
#በዚህ ውስጥ።
በዚህ ውስጥ የአማራ ክልል ህዝብ ተሰቃዬ። የተሰቃየው በግራ ቀኙ በኩል ነው። በመንግሥት በኩል ይሁን በፋኖ በኩል "የመንታ እናት ተንጋላ ሞተች" እንደሚባለው ነው የአማራ ህዝብ የሆነው። ይህን ለመፍታት ብሄራዊ የምህረት ዓዋጅ ያስፈልጋል። በጣም ሰፊነት ብልሃዊ ጉዞ ይጠይቃል።
#አቅሎ ማየት እና ጢሱ።
በአለፈው የፓርላማ ውሏቸው ጠቅላይ ሚር አብይ አህመድ አሊ "ሁለት ሦስት ሽፍታ" ሲሉ አዳምጫለሁኝ። ይህን ያሉበት ምክንያት እኔ ሳስበው
1) ለዲፕሎማሲው ማህበረሰብ የፋኖ አቅመቢስነትን ለማመላከት።
2) ፋኖ ዓለም ዓቀፍ ዕውቅናውን እንዳይፋፋ።
3) ፋኖን ተስፋ የሚያደርጉ ከኖሩ ተስፋ ለማስቆረጥ አስበውበት ነው የተናገሩት።
ለነገሩ አማራዊ ጉዳዮችን አቅሎ ማየት ዶር አብይ አህመድ ያዘወትራሉ። እሳቸው እንዳሉት ጉዳዩ "የሁለት ሦስት ሽፍታ" አይደለም። የተሳሳተ ብያኔ ነው። ማን ምን እንደሆነ የሚታወቅ ነገር የለም። ነጭ ጤፍ፤ ሰርገኛ፤ ቀይ ጤፍ ብሎ መለየት አይቻልም። መዋቅሩ የብልጽግናም እንዲሁ ዋልሎ ነው ያለው።
ለመሆኑ የአማራ ክልል ብልጽግና የማን ነው??? ይህ እራሱ ምህረት ያስፈልገዋል። የአማራ ክልል መንግሥታዊ መዋቅር ይሁን የአማራ ክልል የብልጽግና መዋቅራዊ ሰንሰለቶች የምህረት ዓዋጁ እንደሚመለከተው ማሰቡ ይጠቅማል። ቂም አያስፈልግም። በቀልም አያስፈልግም። እያንዳንዱ ቢያንስ አምስት ቤተሰብ ያስተዳድራል። ስለዚህ ቤተሰባዊ አዲስ ቀውስ ማምረት አያስፈልግም። ያለው ቀውስ በቂ ነው።
አንድ በሙሉ ዕድሜ ያሉ የፍኖተሰላም ተሰብሳቤ "የራቀ ቤተሰብ ከተባለ የአክስት እና የአጎት ልጅ ነው፥ … እንጂ ልጁ፤ ወንድሞ ፋኖ ዱር ቤቴ ያላለ የለም። ሲጀመርማ እኛም ይሁንታ ሰጥተንበታል" " ፋኖ ተልዕኮው ለአጭር ጊዜ ብቻ ስለሆነ ይሆናል አጀማመሩ ላዬ ፈቅደን ነበር የሚሉት። ፋኖ ተሎ ተልዕኮውን ያሳካል በሚል ሊሆን ይችላል። የ፬ ኪሎ ዓዋጅ አድምጠንም ነበር።
በሌላ አደረጃጀት ቢሆን አንድ ዱርቤቴ ያለ የከፋኝ ኃይል የተረዘመ ተጋድሎን መቋቋም ይቻላል። በፋኖ ግን ተፈጥሮ አይፈቅድም። ማዕከላዊ አመራር ለመፍጠር ስለማይቻልም ከቁጥጥር ውጭ ይሆናል። የታጠቀን ኃይል ማዕከላዊ አመራር ካላገኛ ከህግ ውጪ የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው። ከዚህ ከሰማነውም የሃዘን መከራም በባሰ። አንድ ነገር ከተፈጠረበት ውጪ ከሆነ ኃላፊነቱን እና ተጠያቂነቱን መሸከም አይችልም። ከአንድ መንደር በላይ ሊወጣ አይችልም። ቢበዛ ወረዳ እንጂ ተፈጥሮው ለማዕከላዊ አመራር ይከብዳል።
#የብልጽግና መዋቅር።
ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ነው የሚባለው። አካል የለውም። መነሻ መሠረትም የለውም። የአደረጃጀት መርህም አይገዛውም። በዚህ ውስጥ ህዝብን ለመምራት አይቻልም። የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ዕውቅና ሲሰጠው ለብልጽግና እኔ ሞግቼ ነበር። የህዝብ ጉዳት ታይቶኝ፤ ስለ ሠራሁበትም ነው። ካለ ዲስፕሊን የፓርቲ መዋቅርን መምራት አይቻልም። ተንሳፎ ያለ ጉድ ነው። ብልጽግና የፖለቲካ ፓርቲ የአደረጃጀት መርሆችን ተከትሎ አልተደራጀም።
ጨለማ እና ጢሱ ጉዳይ አባላቱ፤ አካላቱ ውርሰ ህወሃት ነው። ህውሃትም ቀንቶት ልብ አሸፍቶ ተስፋን መሠነቅ የቻለው የራሱ ልጆች፤ የገዛ የልጅ ልጆች ባለሥልጣን ስለሆኑለት ነው። ሚስጢር የባቄላ ወፍጮ ነው የሆነለት። አደጋው ኢትዮጵያን እንደ አገር ማስቀጠል ላይም ነው። የህወኃትን መንፈስ የተወረጄ መዋቅር ሁልጊዜም ኢትዮጵያ ኢመርጀንሲ ሩም እንድትሆን ያደርጋታል። ህወሃት የሚባል የፖለቲካ ድርጅትን የመሰለ በመከራ ማምረቻ ዓለም አስተናግዳ አታውቅም። ሊድንም የሚችል አይደለም።
የብዙ ቀውሶች ጠንሳሽ የህወሃት መንፈስ ነው። ለዛ ነው አቅም በገፍ እየተዋጣ የሚገኜው። ህወኃት ሲፈጠርም፤ ሲጠናቀቅም ኢትዮጵያ አጀንዳው አይደለችም። ይህን ለማስቀጠል ሙሉ አባላቱን መረከብ ዛሬ ዳገት በዳጥ ሆነ ለብልጽግና። ይህም ሆኖ ሙቀቱ ከኖርማሉ ውጭ ሆኖ ቋያ ስለመፍጠሩ አጀንዳው አይደለም ብልጽግና። አለሁም ይላል አቤቱ ብልጽግና መሪ መንፈሱ ህወሃት በአሻው ልክ አካሉን እየዘወረው።
ጠበቃ ፋኖ አስረስ ማረ 80% አማራ ክልልን እየመራን ነው ሲል የተሳለቁ ነበሩ። ዕውነቱ ግን ዕውነት ነው። አገርን ፕሮፖጋንዳ ይምራት ካልተባለ በስተቀር አቤቱ ብልጽግና አማራ ክልል ላይ መውደቁን አምኖ፤ ድክመቱን ተቀብሎ፤ የአማራ ህዝብን ይቅርታ ጠይቆ፤ እናም አክብሮ የምህረት ዓዋጅ ዓውጆ አንፃራዊ መረጋጋት ለአማራ ህዝብ ሊፈጥር ይገባል። የብልጽግና የአመራር ጥበብ የተሸበሸበ ስለሆነ ነው ይህን መሰል መከራ የአማራ ህዝብ እየተቀለበ የሚገኜው።
የፖለቲካ ፓርቲ መሪነት በሠርግ መልስ፤ በለርግ ቅልቅልና ግጥግጥ አይደለም። ቢሮ እያደሩ የሚሠራ በትጋት እና በተከታታይነት የሚከወን እንጂ ፍሬም ተሠርቶ ከግድግዳ ላይ የሚለጠፍ ዓርማ አይደለም። ስንፍና፤ ዝለት፤ ንቀት የትም አያደርስም። ኢትዮጵያ እንደ አገር ትቀጥል ዘንድ አቤቱ ብልጽግና ከረባቱን፤ ገበርዲኑን፤ ሴቶችም የፋሽን ትዕይንታቸውን ገትተው ወደ ሥራ ሊገቡ ይገባል። ሁልጊዜ ጉዞ? ሁልጊዜ ሽርሽር መሸርሸርን እያስተናገዱ መጨረሻው ያላማረ ይሆናል።
ይህ ሁሉ መፈናቀል፤ ይህ ሁሉ የተቋማት ውድመት፤ ይህ ሁሉ ፍርሃት እና ስጋት ለአማራ ህዝብ እንዲጋፈጥ መደረጉ የግፍ ግፍ ነው። ሙሉ ድምጽን ሰጥቶ ለኖቤል ያበቃ ህዝብ ፈንግጠው የተገባ ፖለቲካዊ አካሄድ አይደለም። ብዛት ሳይሆን ጥራት። የፖለቲካ ድርጅት አባልነት የገብያ ውሎ፤ የኢቤንት ሽብሸባ፤ የልብስ ፋሽን ትዕይንት አይደለም።
አንድ የፖለቲካ ድርጅት የቆረጡ፤ ትጉኃን በታማኝነት በድንግል እና በንጽህና ተወደው፤ ተከብረው የህዝብን ኑሮውን እየኖሩ ዝቅ ብለው ሊያገለግሉ የሚችሉ ጠንካራ ሠራተኞች ማዕከል ነው። የአማራ ክልል ብዙ በጣም ጎድሎበታል። የጠቅላይ ሚር ቢሮ አትኩሮት ለአማራ ልጆች ስስ ነው።
በጠቅላይ ሚር ጽህፈት ቤት ውስጥ ታማኝነት፤ ተቀባይነት እና ተደማጭነት በሚመለከት ሚዛኑንም የጠበቀ አይደለም። ለኦርቶዶክስ ተዋህዶ በምንም ደረጃ ላይ ነው። የፖለቲካ ውክልና ላይ ኢትዮጵያ መሬት ላይ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ግብር ከፋይ መሆኗ ተሰርዟል። ይህ በራሱ የውስጥ መከፋትን ያባብሳል። ሊታረምም - ይገባዋል። ሁሉም እኩል መሳቅ አለበት። ለአንዱ ቅርብ ለሌላው ሩቅ የወላጅ ጸጋው አይደለም። መንግሥትን እኔ እንደ ጎረቤት ሳይሆን እንደ ወላጅ ነው እማየው።
#አባ ገዳወች።
ሰሞኑን የአማራ ክልል መንግሥት ስብሰባ ላይ ነው። አባ ገዳወች፤ የአገር ሽማግሌወች ተገኝተዋል።" #ጣና ኬኛ" ይሳካ ዘንድ ብዙ ደክመንበታል። ለአማራ ህዝብ ግን መከራ የታጨበት ነው። እና ያ መንፈስ ተመልሶ የሚገኝ አይደለም። ያተረፈው ስሌለ። ምነው በኦሮምያ ክልል ያለውን የአማራን መፈናቀል፤ ወላጅ አልባ ልጆች መበራከት፤ ተሳቆ መኖር፤ #መስቃ መከራ #ተው ለምን አይሉም አባ ገዳወች። አላየነም አልሰማንም። ተጋሩን ያዳኑ እነሱው ናቸው። ይህ ያስመሰግናል።
ጠቅላይ ሚር አብይን ለሥልጣን ያበቃ የአማራ ህዝብ ነው። በክብርም የተቀበለ። አማራ ውለታ ለፈጸመ ግን አባ ገዳወች፤ የኦሮሞ የፖለቲካ ሊቃናት በአማራ ችግር ዙሪያ አጀንዳቸው ሆኖ አያውቅም። የአማራ ህዝብ ድምጽ እንደ አልባሌ ነው የተወረወረው። ዕድልን ሰክኖ የማስተዳደር አቅም ሊኖር ይገባ ነበር።
አሁን አባ ገዳወች ባህርዳር ሲገኙ የክልሉ መንግሥት ካባ በቦንዳ ስለሚያከፋፍል የዛ በረከት ይድረሰን ካልሆነ በስተቀር የሚያሳኩት ቀንጣ ጉዳይ አይኖርም። ከቅርባቸው ያለውን የአማራ ህዝብ ሰቀቀን፤ የተዋህዶ ልጆችን የፍርሃት ቆፈን እና ቀንበር ሊያስወግዱላቸው ይገባ ነበር።
የአማራ ልጅ አዲስ አበባ እንዳይገባ ሲታገድ ማስቆም ይችሉ ነበር አባ ገዳወች። ትውፊታዊ ሥልጣንም ተደማጭነትም አላቸው። ኦሮምያ ጉባኤ ላይ ይገኙ እና ከመሸም ቢሆን ይሞክሩት። ይምከሩ ልጆቻቸውን። ወግ አይቀርም በኦሮምያ ጉባኤም የአማራ የአገር ሽማግሌወች እንዲገኙ ሊደረግ ይችል ይሆናል። የችግሩ መፍቻ ቁልፍ ይህ መሥመር በፍጹም አይደለም።
የአማራን አብዛኛው ህዝብ ምን አስከፋው የሚል ጥልቅ ጥናት ይጠይቃል። ግድፈት አውቆ እና ተቀብሎም፤ ለእርምትም ፈቃደኝነት ይጠይቃል። በእጅ ያለ ነገር ነው።
እንደ አደባባይ ሚዲያ ዘገባ ከቅድስት ኦርቶዶክ ተዋህዶ የጸዱ ቀበሌወች አርሲ ውስጥ መፈጠሩን ሰምቻለሁ። ሰቆቃውም ቀጥሏል። ያን ለማስታገስ ለምን አልጣሩም አባ ገዳወች ሆኑ የአገር ሽማግሌወች ባህርዳር ከመጓጓዝ ይልቅ። ወጪውም ቀላል ነው።
#አክብሮት። ሰላም - በግልምጫ? ሰላም - በእርግጫ አይገኝም። ሰላም በፍጥጫ አይገኝም።
በአንድ በኩል ኑ ግቡ። በራችን ክፍት ነው። በዛው መድረክ "ሽፍታ፥ ጃዊሳ፥ ዘራፊ፥ ጽንፈኛ፥ ቀማኛ" ይህ አያቀራርብም። በተለይ #የሠራዊቱ ከፍተኛ መኮንኖች አካላት አገላለጽ ይቆጠቁጣል። ግሳፄም ነው። ይህ የተገባ አይደለም። በፋኖ በኩልም ለሰላማዊ ሁነት "ከእብድ ጋር አንደራደርም፤ መደራደር ከፖለቲካ ዘርፍ ተቆጥሮ፤ አንድ ሃሙስ የቀረው" ይህም ትክክለኛ መንገድ አይደለም። በጥራት ጥያቄወችን ሰንዶ ለድርድር ተፈቃቅዶ መጀመር ይገባል። ህዝብ ተሰቃይቷል። ያላየው የመከራ ዓይነት የለም። ደመ ከልብ ሆኗል።
ትርፍ ነገር ለምን? ፋኖ የሚቃለል ኃይል አይደለም። እእ። ብልጽግናም ዓለም ዓቀፍ ዕውቅና ያለው መንግሥት ነው። የአማራ ህዝብም የተከበረ ሰው አክባሪ ህዝብ ነው። የትኛውም የጸጥታ አካል የአማራ እናት እና አባት የወለዷቸው ናቸው። ቢያንስ የአማራ ወላጆችን ማክበር ለምን አቃተ????
1) አሁን ለአማራ ህዝብ ቅርቡ ማነው?
2) ማን አለልኝ ይበል?
3) ማን አይዞህ ይበለው?
5) ማን ያጽናናው። የአማራ ህዝብ መሽቶ እስኪነጋ እርግጠኛ የሚያደርግ የሰላም ዋስትና የለውም? መሪነት እኮ ይህን ማስቻል ነው።
#ሁለቱ የግንባር ሥጋ ወጣቶች እና ነገረ መምህርት የሺ። በዚህ አጋጣሚ መምህርቷን እግዚአብሄር ያጽናወት ልላቸው እፈልጋለሁኝ።
1) አንድ ፋኖ ፍኖተ ሰላም ላይ፤
2) ሌላ የሠራዊቱ አባል የነበረ ፋኖ ዱር ቤቴ ላይ የሰጡት አስተያዬትን ተከትሎ አጥቂው የማይታወቅ ይሆናል። በግልጽነት፤ በቀጥተኝነት የተናገሩ ወጣቶች ስለሆነ በማንኛውም ጊዜ አደጋ ሊደርስባቸው ስለሚችል ወደ ማዕከላዊ መንግሥት ቢወሰዱ መልካም ነው። የግንባር ሥጋነት ብዙ ይጎዳል።
3) የመምህር ደረጄ ባለቤት መምህርት ወይዘሮ የሺም መራዊ ላይ ለልጆቻቸው ይኖሩላቸው ዘንድ የእሳቸው ህይወትም ልዩ ጥበቃ የሚሻው ሆኖ አግኝቸዋለሁኝ። ልጆች አባታቸውን አጥተው እናታቸውን ሊያጡ ስለማይገባ። ይህን መሰል ጉዳይም በአጀንዳ ተይዞ ተከታታይ ተግባር ሊፈጸምበት ይገባል። ጥግ ለሌላቸው ወገኖች ጥግ የመሆን።
በሌላ በኩል አስተያዬት የሰጡ ወገኖችን በመንግሥት መዋቅር ባሉ ይሁን በፋኖ አመራሮች ተጨማሪ ጥቃት እንዳይኖር ግራ ቀኙ እንደዬአደረጃጀታቸው ይርጋ ሊሰጡበት ይገባል። በቃው! የአማራ ህዝብ። ነፃ ሆኖ ተፈጥሮ ነፃነቱ አደጋ ውስጥ ነው ያለውና።
#የአማራ ህዝብ ሥነ - ልቦና በራስ መተማመኑ የተፈተነበት ዘመን።
የአማራ ህዝብ በራስ የመተማመን ተፈጥሯዊ አቅሙ የተመጣጠነ ነው። ከፍም ዝቅም ሳይል በልኩ ለልኩ። አሁን ግን ጭንቅ ላይ ነው። ፍኖተ ሰላም ላይ ወንበሩ ቢውጣቸው የወደዱ ሰወች አይቻለሁኝ። በቢዲዮ እንዳይቀረፁ ሲደበቁ ነበር።
የተሳታፊወችን ሙሉ አትኩሮት እና የስሜታቸውን ሁነት ተከታትዬዋለሁኝ። ግብረ መልሱ ደፈር ያለ አስተያዬት ሲሰጥ የሚደነግጡ፤ በትዝብት የሚዩ፤ በጋቢያቸው እራሳቸውን የጋረዱ፤ ያዘኑ፤ የተበሳጩ፤ የፈዘዙ ታዳያ።ሚወችን ወዘተ አይቻለሁኝ። ይህ ነው ውስጤን ያሳዘነው። የአማራ ህዝብ በራስ የመተማመን ሙሉ አቅም የነበረው ህዝብ ነው። የአማራ ህዝብ ጸጋ በራስ የመተማመን አቅሙ እና ክህሎቱ ፈተና ላይ መሆኑን አይቻለሁኝ። መራራ ጎምዛዛ ነው።
የስብሰባ ተሳታፊወች አስተያያት ሲሰጡ "ሁሉነገሬን አጥቻለሁ፤ የፈለገ ያድርጉኝ" የሚሉም ጉልህ ድምፆችንም አዳምጫለሁኝ። ከሁሉ የሚከፋው ስልጣን ላይ ያሉ ጫካወች የበቀል እርምጃ እንዳይወስዱባቸው በእጅጉ አሳስቦኛል። እኔ ይህን ሰምቶ መጀመሪያ ይህን መሰል የትጥቅ ትግል ያስወሰነው ሰብዕና በምን ሁነት ህየወቱ እንደምትቀጥል አላውቅም። የአማራ ህዝብ ጭንቅ ላይ ነው።
ከዚህ ጋር በተያያዘ ጥሪ ተደርጎላቸው በፍጹም ለስብሰባ ሊመጡ የማይፈቅዱ መንደሮች እንዳሉም ሰምቻለሁ። ስለሆነም የአማራ ክልል ችግርን ለመፍታት የጨመተ፤ የአማራ ህዝብን ተፈጥሮ ከልብ ያከበረ፤ ሰብአዊነት ያለው #ብሄራዊ ግብረ ኃይል ያስፈልገዋል። በለብ ለብ፤ በግብግብ፤ በዝንጥፍጣፊ ልል እና ልቅ መንገድ የአማራን ህዝብ ዘላቂ ሰላም ማስከበር አይቻልም። በሳል የፖለቲካ ትጋት ይጠይቃል። ሥነ ልቦናውም ተጎድቷል።
በጣም ስጋቴ ብልጽግና መዋቅር ውስጥ ያሉ መንታ መንገድ መራጮች በአማራ ህዝብ ላይ ሌላ የበቀል ጅራፍ እንዳይሰነዝሩ ብርቱ ጥንቃቄ ያስፈልጋል። በሌላ በኩል ምርጫ መጣሁ መጣሁ እያለ ነው። ተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲወች አማራ ክልል ያለበትን ደመመን የተጫነው አትሞስፌር ተረድተው፤ ምንም ዓይነት ተጨማሪ ጫና እንዳያደርጉበት በትህትና እና በአክብሮት እጠይቃቸዋለሁኝ። ግፍም ነው። አማራ ክልል ቢሮ ከፍተው ምረጡኝ??? በቃው! የአማራ ህዝብ። እለፋት።
አማራ ክልል ያለው ችግር የከፋ ነው። አየሩ በሙሉ ተወጥሯል። መንተንፈሻ አየር ያስፈልገዋል። የእያንዳንዱ የነፍስ ወከፍ መኖሪያ ቤት ግድግዳ ሳይቀር መተንፈስ ይፈልጋል።
#እራስን ስለመግለጥ።
በቀል ይኖራል ብየ አስባለሁኝ። ተባቃዩ ባለቤት አይኖረውም። ዝንቅንቅ ስብጥርጥር ስለአለ። ስለዚህ እራስን የመግለጽ ህዝባዊ ሁነት ቢኖር መልካም ነው። ብልጽግናም አለሁ ካለ አካላቶቹ እራሳቸውን ይገልጡ ዘንድ መድረክ ሊያመቻችላቸው ይገባል። ሙሉ ህዝብን መበቀልም፤ ማሰርም አይቻልም እና። የተጎዳ ህዝብ ላይ ተጨማሪ ምንም ዓይነት ፈተና ሊገጥመው አይገባም።
#ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶን በሚመለከት።
ልዩ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የሚያስፈልጋት ይመስለኛል። ከፖለቲካ ሙሉለሙለ መገለሏ፥ ልጆቿ በማተባቸው ምክንያት ችግርን ማስተናገዳቸው ዱር ቤቴ እንዲሉ ካስገደዳቸው በኽረ ጉዳይ አንዱ ሆኖ በውይይቱ አዳሜጫለሁኝ። በዚህ ምክንያት የተጎዱ የካህን ቤተሰቦች የመኖራቸውን ያህል መርቀው የሸኙም የሃይማኖት አቨው እንደ አሉ አዳምጫለሁኝ። ካህናት ሌላ የእስር ዘመቻ እንዳይገጥማቸው ቅድስት ተዋህዶ ችግሩን የእኔ ብላ መላ እና ጥበብ ብትቀርጽ መልካም ይመስለኛል። ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋርም ፊት ለፊት መወያዬት የሚገባት ይመስለኛል።
1) የአማራ ህዝብ ጥያቄወች የብልጽግና አጀንዳ ሊሆን ይገባል።
2) የጥያቄወች ዕውቅና ማግኜት መሠረታዊ ጉዳይ ነው።
3) ዕውቅና መስጠት ብቻ ሳይሆን የተግባር ሰሌዳም ሊወጣለት ይገባል። በአጭር፤ በመካከለኛ ጊዜ በረጅም ጊዜ ሊፈቱ የሚችሉ በኽረ ጉዳዮች ተለይተው ወደ ተግባር የሚገባበት መሥመር ሊኖር ይገባል።
4) የአማራ ህዝብ ጥልቅ ችግር ከክልሉ መንግሥት፤ ከክልሉ ብልጽግና ጽህፈት ቤት፤ ከአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በላይ ነው። የአማራ ክልልን ችግር በበላይነት በማዕከላዊ መንግሥት ዘንድ ብልህነት፤ በጭምትነት፤ በሰፊነትን የመምራት አቅምን አብዝቶ ይሻል። ዕውነተኛ የሆነ፤ ቅብ ያልሆነ የህዝብ እና የመንግሥት ግንኙነት ለመፍጠር ቅን የሆነ ድልድይ ሊዘረጋ ይገባል።
5) የፖለቲካ ውክልና በሚመለከት የአማራ ሊቃናትን፤ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማንያን ሊቀ - ሊቃውንታት በሚመለከት የካቢኔ አባላትን ዝርዝር፤ ብሄራዊ ጉባኤወች ላይ ያለው የፕሮቶኮል ተዋረድ ሳይው ተመጣጣኝ አይደለም። ማመዛዘንም እንኳን አይቻልም። የሚመዛዘን ሲኖር ነው ማመጣጠን የሚቻለው።
የኢትዮጵያ የመንግሥት አወቃቀር ሥርዓቱ ሃይማኖታዊ ካልሆነ ለሁሉም አቅም እስከአለው ድረስ እኩል ውክልና ያስፈልጋል። ሚዛኑን ያልጠበቀ ከሆነ ብሶት ሲፈነዳ ዛሬ ሥራ ላይ ያሉ ህጎች ሁሉ ተፈፃሚ አይሆኑም። ሲከር ይበጠሳል፤ ሲሞላም ይፈሳል። ዕውነቱን ለመናገር የአማራ ሊቃናት - ቃና እና ክህሎት፤ በቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ዊዝደምን በማሳደዱ ነው ህወሃት መንበሩን ያጣው። ይህ እንዳይደገም ያስተዋለ የእርምት እርምጃ በብልጽግና መንግሥት በእጅጉ ያስፈልጋል።
#አፍቅሮተ ህወሃት በአማራ ህዝብ አክ! ሊባል የሚገባው ፖለቲካዊ ዕውነት ነው።
"እግዚአብሄር በአንድም በሌላም ይናገራል፤ ሰው ግን አያስተውለውም።" ብዙ አሳዛኝ ክስተቶች መፈጣራቸው፤ ህወሃትን ደግሞ ከመሻት የመነጩ ስለመሆናቸው እኔ ከገባኝ ቆዬ። በህይወት እያለሁኝ ህወሃትን ጠግኖ፤ ደልዞ እና ጣጥፍ እንደ ገና ለመንበረ ሥልጣን ለማብቃት የሚደረገውን ትርምስ በሚመመለከት በአትኩሮት እና በጥንቃቄ የምከታተለው ጉዳይ ነው። የጃርት ጉባኤ ካልተናፈቀ በስተቀር ህወሃት የሚናፈቅ ተቋም አይደለም። መናፈቅ መብትም ቢሆን የአማራ ህዝብ ጥቅጥቅ ጨለማ ናፋቂ ሊሆን አይገባም።
#ልማት።
ብዙ ቦታ ልማት ተጠይቋል። የተጀመረው ይጠናቀቅልንም። ሰላም ስሌለ የመንግሥት ግብር መሰብሰብ አይቻልም። በሌላ በኩል ነባሩን ለማስቀጠል፤ አዲስ ፕሮጀክት ለመጀመር ሰላም ከሌለ እንደምን ይሆናል? ጥያቄው ተገቢ ቢሆንም እስኪ መጀመሪያ የአማራ ህዝብ በሰላም ውሎ ለማደር ይብቃ።
#የሰላም ጥሪ እና አፈፃጸሙ።
የአማራ ትግል ከውይይቱ እንደተረዳሁት ህዝባዊ ሆኗል። ይህን ህዝባዊ የውስጥነት ጥያቄ አክብሮ ደረጃውን የጠበቀ ብሄራዊ ድርድር ማድረግ የተገባ ነው። ይህም ሆኖ ህዝብ ጋር ለመታረቅ የሚያስችል ስኩን የፖለቲካ ተግባር ይጠይቃል። እራሱ የብልጽግና መዋቅር ተንሳፎ ነው ያዬሁት። መሪነት መሪነት እንጂ ጅራትነት አይደለምና። ብልጽግና አልቻለም። ዋልካ መሬት ውሃ ሲያጣ እንደሚሆን ሆኖ ነው ያዬሁት።
#ትምህርት ቤት። እንደ መከወኛ።
መምህራን እና የፋኖ ንቅናቄን በሚመለከት እንደ አዳመጣችሁት ነው። የጎጃም የቀለም ትምህርት ልቅና አይደለም ለኢትዮጵያ ለአህጉሩም፤ ለዓለምም ልዩ ነው። የአሳ ተመግቦቱ ልቅና ይመስለኛል የጎጃም ልጆች ትምህርት ዘርፍ ላይ ላቂያ የሚሆኑት። እራሱን የቻለ ጥናት እና ምርምር ይጠይቃል። ይሄ ተስተጓጉሏል። ስለሆነም ምህረትን እመኝለታለሁኝ።
የተዘጉት ትምህርት ቤቶች ብቻ ሳይሆኑ ሥራ ላይ ያሉት በቂ ትምህርት የማይሰጥባቸው ስለመሆኑ ነው ያዳመጥኩት። ትምህርት ስኬቱ የረጅም ጊዜ ነው። አማራ ክልል በዚህ የጊዜ ማዕቀፍ ውስጥ እንደ ሾለከ ነው ያዳመጥኩት። በጣም በቁጭት ሊታሰብበት የሚገባ መሠረታዊ ጉዳዬ ነው። ለይደር ሊቀጠርም አይገባም። ቢያንስ ትምህርት ላይ ያሉት ተማሪወች የተሟላ የትምህርት ክፍለጊዜ እንዲኖራቸው፤ ጥራት ያለው ክትትል ሊደረግ ይገባል። ይህን ንቅናቄ የጀመሩ ሁሉ፤ በዚህ ጉዳይ ተሳትፎ የነበራቸው ሁሉ አማራ ነገስ የሚለውን ቢያስቡበት በትህትና እጠይቃቸዋለሁኝ።
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አገልግሎትም እረገድ ከአገልግሎት ውጪ የሆኑ አብያተ ቤተክርስትያናት እንዳሉም አድምጫለሁኝ። ደጀሰላሙ ከተዘጋ ከፈጣሪ ጋር መገናኛው ድልድዩ እንደምን ይሆን?
በሙሉ ያዳመጥኳቸውን ሊንኮች ለጥፌያለሁኝ። ከዜና ጋር የተሠሩትን አዳምጫለሁ ግን ሊንኮቹ አላስፈለጉኝም። ቆራጣ ቆራጣ ስለሆኑ።
• «መከላከያውም ፋኖውም ልጃችን ነው› የሰላም ናፍቆትና የህዝብ ብሶት:- ታህሳስ «13/2018#Ethioskymedia"
• «በሰሜን ጎጃም ዞን የሰሜን ሜጫና መራዊ ከተማ ነዋሪዎች ጋር የተደረገ ውይይት»
• ስለአማራ ክልሉ ጦርነት ያልተሰሙ አነጋጋሪ ጉዳዮች; የሃይማኖት አባቶችና ባለስልጣናት ውግዘት ገጠማቸው- ታህሳስ 6/2018#Ethioskymedia" auf YouTube
• "አወዛጋቢው ጦርነትና የህዝቡ ለቅሶ: ‹ለሚሊሻም ለፋኖም ሞት እናለቅሳለን› - ታህሳስ 6/2018#Ethioskymedia"
• "ከፍኖተ ሰላም ከተማ፣ ጃቢጠህናን ወረዳ እና ጅጋ ከተማ ነዋሪዎች ጋር በፍኖተ ሰላም ከተማ የተደረገ ሕዝባዊ ውይይት"
• "ሕዝባዊ ውይይት በደቡብ ሜጫ መሐል ገነት ከተማ"
• "ሕዝባዊ ውይይት በደቡብ ሜጫ መሐል ገነት ከተማ"
• "የኪንፋዝ በገላ ወረዳ የሕዝብ ውይይት"
• " የሕዝብ ውይይት በቆላ ድባ "
• "ሰላም ለሁሉም ሁሉም ለሰላም" በጯሂት የተደረገ ውይይት"
• "ሕዝባችን ላይ የጋለ የብረት ቀንበር ጭነንበት ቆይተናል"
• " ከመርጡለማርያም ከተማ እና ከእነብሴ ሳር ምድር ወረዳ ነዋሪዎች ጋር የተደረገ ሕዝባዊ ውይይት"
• "በደብረ ማርቆስ ከተማ አካባቢ ታጥቀው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የመንግሥትን የሰላም ጥሪ የተቀበሉ "
ቸር አስበን፤ ቸር እንሁን። አሜን።
ቅን አስበን፤ ቀና እንሁን። አሜን።
ኑሩልኝ። አሜን።
የማከብራችሁ የአገሬ ልጆች ሆይ!
ከጥቂት ቀናት የጥሞና ጊዜ በኋላ ተመልሰን እስክንገናኝ ድረስ ምዕራፍ ፲፯ በዚህው ተጠናቋል። የፊደል እርማቱን ተከታትዬ እሠራለሁኝ። ምዕራፍ ፲፯ እና የአውሮፓውያኑ አዲስ ዘመን 2026 ጋር አብሮ ይመጣል። ቀጣዩም የእኛ የቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ የልደት በዓል ይመጣል። ለዛ ክብረቶቼን በሰላም ያድርስልኝ። አሜን። ጥር እና አስተርዬም ይከተላሉ። ሰላምን ይዘው ይመጡልን ዘንድ ምኞቴ ነው።
እግዚአብሄር ይስጥልኝ። አሜን።
ሥርጉተ©ሥላሴ
Sergure©Selassie
29/12/2025
ጊዜ ራዲዮሎጂ ነው።
አቤቱ አምላካችን ሆይ! ሠላም ለአገራችን፤ ሠላም ለዓለም ህዝብ ይሁንልን ዘንድ እለምንኃለሁ። አሜን።

አስተያየቶች
አስተያየት ይለጥፉ