ፐ!

የመርህ ሰው እንሁን።
„በንጉሡ ውስጥ የነበረው ጃንደረባው ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክ 
     ኤርምያስን በጉድጓዱ ውስጥ እንዳኖሩት ሰማ።“
 ትንቢተ ኤርምያስ ምዕራፍ ፴ ቁጥር ፰፯
ከሥርጉተ© ሥላሴ 18.08.2018



ትናንት አንድ ዜና አደምጥኩኝ የአማራ ክልል መስተዳድር የኤርትራን መንግስት ፕሬዚዳንት ፕ/ ኢሳአስ አፈወርቂን ወደ ክልሉ እንደ ጋበዘ። ቀኑ አልታወቀም ግን ይሁንታ እንዳገኜ አዳምጫለሁኝ።

ፕሬዚዳንት ኢሳያስ የሚመሩት የልዑካን ቡድን ወደ አማራ ብሔራዊ ክልል እንዲሚመጣ ተስማምተናልንጉሱ ጥላሁን

አላውቅም እኔ ይህን ያህል ከውጪ መንግሥታት ጋር ክልሎች ሥልጣን እንዳላቸው፤ ህጋቸውንም አለነብኩኝም። መቼም ይሄ ሥልጣን ከተሰጣቸው ለእኔ ሥርዓተ አልበኝነት ነው። ወይንም ኢትዮጵያ የምትባል ማዕካለዊ መንግሥት ያላት አገር አለመኖሯን የሚያውጅልን ነው። በመንፈስ እንዳልነበረች ባውቅም ይህን ያክል ግን ገሃድ የወጣ ጉድ ይኖራል ብዬ አላስብም። 

እርግጥ ነው የአባይ ኬኛ ግንኙት የሰጠን ግብረ ምላሽ ነበር በዬክሎች የነበረው የተካተረ ግንኙት ከውጭ መንግሥት ጋር የሚመስል ነበር። ልክ አልባንያ፤ ከአዘርባጃን፤ አዘርበጃን ከቦስንያ፤ ቦስንያ ኮከራዚ ወዘተ ... 

ይሄ የአሁን ደግሞ ግርም የሚያደርግ ነገር ነው። ፉክክር ነው ወይ የተያዘው ወይንስ አገር እዬተመራ ነው ያሰኛል። ወይንስ የ አብይን ጥረት ማክስም እና ማክሰል? ነገሩን ሁሉ እኮ የልጆች ጨዋታ አድርገውት አረፉ። የውሃ ላይ ኩበት … አንዱን መሰረት ሳያስዙት በዬደረሱበት ጉብ እያሉ እራሳቸውንም እዬናዱት ነው። ግንባሩ እራሱ ንደት ላይ ነው …

ከዬትኛው ስብሰባ ላይ እንደሆን አላስታውስም ብቻ  በአሜሪካኑ ጉብኝት ጠ/ ሚር አብይ አህመድ „ፕ/ ኢሳያስ አንድ ነገር ከሚሆኑብኝ እኔ ብለው እንንተው ጨርሱት“ ብለው ነበር።

ይህም ብቻ አይደለም „እንቅልፍ አጥቼ እንደ ህጻን ልጅ ነበር ስጠብቃቸው የነበረው“ ብለዋል። ይሄ ኢትዮጵያ ውስጥ በቅጡ የተደራጀ የማፍያ ቡድን እንዳለ ይገለጣል። ይህ ቡድን እራሱ ከአቅም በላይ መሆኑ ብቻ ሳይሆን፤ በማንኛውም ጊዜ የፈለገውን ነገር ማድረግ እንደሚችልም ያመለክታል። የማፍያ ቡድኑን የእዝ ሰንሰለቱን ሰብሮ ለመቆጣጠር አለመቻሉን ሁሉ ያመልከታል።

እንግዲህ ይሄ ጠ/ ሚር፤ መሪም፤ መንግሥትም አለን ስንል በነበረበት ጊዜ ነው ከመጋቢት 24 ቀን እስከ ሀምሌ 19 ቀን። የአብይ ካቤኔ ሥልጣን ላይ የቆዬው እስከዚህ ቀን ድረስ ነው። ሊመራችሁ ይችላል ግን እውነቱ ይሄው ነው። ከደረሱ በዋላ በዲያስፖራ ለሚገኙ ኢትዮጵውያን ሹመት ሰጡ የሚለው ዜና ፌክ ነው ፈንድ ራይዚንጉንም ለማስቀጠል እና ለማዘናጋትም ነው።  

አሁን ለእኔ መንገዳችን የት ላይ እንደሆነ ማን ኢትዮጵያን እዬመራት እንደሆን አላውቅም። እርግጥ ነው በድርጅት ደረጃ ግጥም አድርጎ የወያኔ ሃርነት ትግራይ እዬመራት ቤተ መንግሥቱን እንደተቆጧጠረ ይረዳኛል፤ አንጃዎችም የደመሩልኝ እና። የአኩራፊዎች ማህበር።

 በዚህ ሁኔታ ነው እንግዲህ ሌላ ላሞኛችሁ አዲስ ድራማ ደግሞ የተጀመረው። የአማራ ክልል ስንት ወዘተረፈ ችግር ተሸክሞ ፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂን ይፋዊ ጉብኝት እንዲያደርጉ ጋበዘ። ፐ! ፐ! ፐ! 

ምን ተፈልጎ? ፍቅሩ? ወይንስ የደህንነት ችግር ተፈጥሮ ሌላ ትርምስ ናፍቆን? በአገር አቀፍ ደረጃ፤ በብሄረዊ ደረጃ እኛ ባሰብነው ሳይሆን ልዑል እግዚአበሄር በፈቀደው በረቂቅ ስልጣኑ ባደረገው የውስጣችን የልዩነት ቆሻሻ ነገር አስወግዱ ፍጹም ደስ የሚል ጊዜ አሳልፈናል።

እኔ ሞገደኛ ነኝ። እኔ እንኳን ገና ቦሌ ሲገቡ ነበር ልዑኩ በኤርትራ መንግሥት ላይ ስለነበረው ጥርጣሬዬ፤ ስለነበረው ስጋቴ ሁሉ እርግፍ አድርጌ የተውኩት። 

ስለምን? እማላውቀው ናፍቆት ስለነበረብኝ እሱ ገዛኝ እና ሁሉንም ነገር በመልካም ከመቀበል ውጪ ልዑል እግዚአብሄርን ላስቀይም፤ ላስከፋ አልፈለግኩኝም ወደፊትም አልፈልግም። ኤርትራ እንኳን ያን የህዝብ አደራ እና የፍቅር ዕዳ ክዳ አብይን አላውቅህም ብትል? ሰው ስንት ጊዜ ይገላበጣል?

በዶር አብይ ካቢኔ አብዛኛው ባያምንበትም እኔ ከጅምሩ መፈንቅለ መንፈስ እንደ ተደረገበት በሚገባ አውቃለሁኝ። ብህልሜም አዬሁኝ፤ እንደገናም የቁም እሰረኛ ሆኜ ስለማውቀው የቁም እስረኛ እንደሆነም አምናለሁ ግን ኤርትራ አለችበት በዚህ ሴራ ውስጥ የሚል ስጋት የለብኝም። ምክንያቱም የነበረው ግንኙነት እዮራዊ ነበርና። በተገኘው ዕድል ግን አትጠቀመም የምልም ጅል አይደለሁኝም። ነገረ አብይ ለኤርትራም ሚራክል ነበር እና። 

ያን ፍሰሃ አሁን ለማጠልሸት ነው አሁን የተጀመረው ጥረት። ምክንያቱም አይደለም አማራ ክልል በማዕክላዊ መንግሥት ደረጃ በጠራራ ጸሐይ አንድ የአገር ኮከብ ተገድሎ ውሾን ያነሳ ውሾ በሆነበት ሁኔታ ኢትዮጵያ መንግሥት አላት የላትም በሚያስብል ደረጃ በጠራራ ጸሐይ ሰው ተገድሎ በሚንጠለጠለበት ሰዓት፤ የተቀናቃኙ ቡድን ሙሉ ወታደራዊ የሰልፍ ትርኢት በይፋ እና በአደባባይ ሚታይበት ሰዓት ጠ/ ሚር አብይ እና ቤተሰባቸው በምን ሁኔታ እንዳለ በማይታወቅበት ሰዓት የአሁኑ የአማራ ክልል የፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ ግብዣ እና የሳቸው እሽታ ግርም ብሎኛል። 

ደህንነቱ አስተማማኝ ሁኔታ የትኛው አካል ነው የሚሰጠው፤ አንጃው ወይንስ አፍንጋጩ የወያኔ ሃርነት ትግራይ? አንድ ነገረ ተፈጥሮ ኤርትራ እና አማራ ደግሞ ሌላ ጉግስ ልክ እንደ አሁን ከጃዋረውያን ጋር እንደተገባው ለመፈጠር ቀልብን፤ መንፈስን አቅጣጫውን ለማስለወጥ ነው እዬሆነ ያለው። ስንት የጭቃ እሾኽ ይሆን ያቺ አላዛሯ ኢትዮጵያ የተሸከመችው? 

ደጋግሜ ተናግሬዋለሁኝ። ፕ/ ኢሳያስ አፈውርቂ አቅም ያላቸው መሪ ናቸው። በዝምታቸው ወስጥ ብዙ ነገር አለ። በዛ ላይ በደህንነት ዘርፍ አንቱ ናቸው። ይህ ሆኖ አማራ ክልልን አምነው ብቻ ለመሄድ ለመጎብኘት ማሰባቸው እጅግ የሚገርም ጉዳይ ነው። በውስጡ ምን አለበት?

ይሄ ልክ የሰኔ 16ቱ የድጋፍ ሰልፍ የጥድፊያ፤ ልክ የሰሜን አሜሪካኑ ጉብኝ የጥድፊያ "የእነቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ" እንደሆነው ዓይነት ነው ሆኖ የታዬኝ። ወይንም ሌላ የተዘጋ በር አለ? ሊደርስ የሚችለው አደጋ ብቻ ሳይሆን ለምን ተፈለገ? አገራዊ እርቅ እኮ ተፈጽሟል። ከተፈለገ እግር ኳስ ውድድር ማድረግ ይቻል ነበር። ወይንም የማህበረ ምዕማናን ጉዞ ወዘተ ...አንድ ብሄራዊ  መንግሥት ወርዶ ክልል ላይ ...? ይጨንቃል ያስፈራልም ... 

ድንቄም ነጻነት? በፍጹም በባዶ አዬር በተሞላ ሠረጋላ ነው እዬተገላበ ያለው። አህጉራዊ እና ሀገራዊ ችግሮችን ባላጤነ ሁኔታ ዘው እዬተባለ ህዝቡ ለዳግም ጥቃት እና ለዳግም መከራ እየተዳረገ ነው ያለው። ለዳግም ውርዴትም፤ አንዲት ነገር በልዑኩ ላይ ቢፈጠር የሚመጣውን እሰቡት? ኤርትራ ጦሯን አዝምታ ቅርጥም ነው የምታደረገው። የቀደመው የፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂ እና የዶር አብይ አህመድ የ ዓለም አቀፉ ዕውቅና ጉዳይም አፈር ድሜ ይግጣል። መንገዱ እና ጉዞው ወደ ዛው ነው ... ምነው አቶ ንጉሡ ጥላሁን ለ አብይ ካቢኔ አሉታዊነት እንዲህ እንቅልፍ አሳጣቸው? አልገባኝም እንዲገባኝም አልፈልግም።  

አንድ በእርጋታ፤ በስክንት፤ በውስጥነት ምን እዬተደረገ ነው ያለው ብሎ የሚያስብ ሰው አልተገኘም። ወይ ኢትዮጵያ ለካንስ እንዲህ ነሽ? ሲሞቅ ብቻ?

አሁን የሚገርመው ነገር ስለ አብን እና ስለ ግንቦት 7 ይጨንቀናል ይጠበናል ሰው በዛ ደግሞ አዲስ የጦር ቀጠና ተከፍቷል። ለነገሩ ግንቦት ከስንቱ ጋር ተጣልቶ እንደሚዘልቀው፤ ሌላውም ከግንቦት 7 ጋር ጉጉሱ የማይደክመው ስለምን እንደሆን አላውቅም?

 በመኖር ውስጥ ሞታችን ታውጆልን። ያለንበትን የቆምንበትን መመርመር ቀርቶ የለውጥ ሂደቱ አድርሻው ምን እንደ ሆነ ሊገባን ከቶም አልቻለም። 

እርግጥ ነው "የሌባ ግርግር ከሆነም" አቋራጭ ባቋራጭ ሊሰላ ስለሚችል ነገረ አብይ ቢዳፍን የሚሹ የወንበር ሱሰኞች ይኖራሉ።

የሆነ ሆኖ አቅጣጫ የለሹ ያልታወቀው መንገድ ላይ ተሆኖ አሁንም ስለ ሌላ ጉዳይ አጀንዳችን ሆኗል። አገር የገቡት የተለያዩ የኦነግ ቅርንጫፎች፤ ኦብነግ ነገ በነጻ መሬት ምን ሊያመጡ እንደሚችሉ አይታወቅም። ግቡ ተብለው ገብተዋል፤ አንድ ኦነግ ብቻ አይደለም ያለው ብዙ ናቸው። ነፃ መሬት አግኝተዋል። ህዝቡን በቀጥታ ያገኛሉ በመሃል ጠ/ ሚሩ ከሥራ ውጭ ናቸው ጠባቂ በሌለባት ሁኔታ በዬሰከንዱ ምን ሊፈጠር እንደሚችል አይታወቅም።

በዚህ ሁኔታ ነው አቅመ ቢሱ ብአዴን "የራሷ ሲያርባት" ሆኖ ያን በጤናማ ጊዜ የተገኘውን አደራ እና ተልዕኮውን በቅጡ የተከወነውን የዲፕሎማሲ ጥረት ለማጠልሽት ይሁን ጣልቃ ገብነት ይሁን ለማለምልም ብቻ ባልተገባ ጊዜ፤ ባልተገባ ሁኔታ፤ በሌለ አቅም ይህን መሰል ክልላዊ ውል የተዋወለው።

ሌላው ቀርቶ እንቁጣጣሽ አርቲስቶች ኤርትራ ሊሄዱ እንደሚችሉ ሁሉ መርሃ ግብር ተነድፎ ነበር፤ አሁን  የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አርቲስቶችን በተገኙበት እንዴት ባዕሉን እዛው ማሳለፍ እንደሚችሉ በምን ዓይነት የበጎ ተግባርት ላይ ማተኮር እንደሚገባ የትውውቅም ጉባኤ አድርጎ ነበር።

ፕሮግራም መሪው ረ/ ፕ ነብዩ ባዬ ነበር። ያው  የኤርትራ እና የኢትዮጵያን ሙሉ የግንኙነት ሴሪሞኒ የመራ ያደራጀ እሱ ነበር። ጀንበሯ እንዴት እያዘቀዘቀች እንደሆን ተመልከቱት … የአብይ ሌጋሲ እንዴት በሁሉም አቅጣጫ እርቃኑን በግልበጣ ላይ እንደሆነ አስተውሉት … አንዱ ኤርትራ እና ኢትዮጵያን ነጥሎ ክላላዊ ለማድረግ ይታትራል፤ ሌላው በብሄራዊ ደረጃ የታቀደውን ከተማዊ አድርጎታል። ሁለቱም መሃል የተሰቀዘው የአብይ ካቤኔ ነው። መልካምነቱ ትቢያ እዬለበሰ ነው ... እዬተሸረሸረ ነው።

የሚገርመው የአማራ ክልል መስተዳድር ሹሞች ሁለት ብቻ ናቸው። ዶር ገዱ አንዳርጋቸው እና አቶ ነጉሡ ጥላሁን። ሌላ ሰው የለም ከእነሱ በስተቀር። አሁንም ቅድምም እነሱው ናቸው። ሌላው ቁጥር ብቻ ነው። ማያስፈልጉት ቀደመው በሞት ተሸኝተዋል።

ይህም ሆኖ ስለራሳቸው በዬደቂቃው ምን ሊፈጠር እንደሚችል ሳያውቁ ነው አሁን ፕ/ ኢሳያስ አፈወርቂን ግብዣ ያደረጉት። የሃይል አሰላለፉ በማንኛውም ጊዜ ሊቀየር ይችላል። 

ክልሎች እንደ መንግሥት እራሳቸውን ችለው ይሄን ያህል መራመድ ከቻሉ 27 ዓመት ሙሉ በሱዳን እና  በኢትዮጵያ የደንበር ጉዳይ ስላለቀው ወገናቸው ስለምን ተቆርቋሪ አልሆኑም ነበር እነ ብአዴን? ስለምን ከሱዳን ጋር ሄደው አልተደራደሩም ነበር? ሌላው ቀርቶ በዬክልሉ ባለቤት አልባ የህግ ጥበቃ አልባ ለሚንገላታው የ አማራ ልጅ ስለምን አቅሙ አልነበራቸውም። ይህን ያህል ከውጪ መንግሥታት ጋር የመደራደር አቅሙ ከኖራቸው።

ህሊና ያለው ከወረቀት አምልኮ የወጣ የዬትኛውም ድርጅት አባል ያልሆነ ቅን ዜጋ እንደዚህ አይነት መላ የለሹ የትርምስ ዓውዶችን ባሊህ ቢሉት መልካም ነው።

የአማራ ክልል „ጅብ ከማያውቁት አገር ሄዶ ቆርበት አንጥፉልኝ“ ሆነው ጃዋርውያን አሸኮኮ አድርገው ሲባዝኑ ሰነበቱ፤ ስለ ዶር አብይ አህመድ ህዝብ ትክለኛውን ሁኔታ እንዳያውቅ በዚያ ሸበቡት፤ ግርዶሽ ፈጠሩለት፤ መንፈሱን ቀለበሱት።

በሌላ በኩል ደግሞ ህዝብ ሌላ አምኮተ አምላክ ፈጥረው ተቀበል የነገ መከራህን ተሸከም ብለው ፍዳውን አሳዩት፤ ጋረዱት።

ዛሬ ደግሞ አዲስ ሽብሸባ ጀምረዋል። ይህም ያው የዶር አብይ አህመድ ህልም እዬከሰመ እዬደበዘዘ ሥማቸው እዬተረሳ እንዲሄድ የማድረግ ተልዕኮ ነው ለእኔ።

የፈረደበት ቀይ ጃኖ ከትናንት በስትያ ለአብይ፤ ትናንት  ለንጉሥ ጃዋር¡ ነገ ደግሞ ለኢሱ ተሰናድቷል።

ድራማው፤ ትወናው በግራ በቀኝ ወጀብ በወጀብ ያ ምስኪን፤ ያ ቅን፤ ያ ቸር፤ ያ ሩህሩህ፤ ያ ሰው አማኝ፤ ያ ታታሪ፤  ደግሞ ባሊህ ባይ አጥቶ እነዛ የክፉ ነገር ፋፍሪካዎች አግተው ይሳለቁበታል። ይተፉበታል።

ሲፈልግ ብቻ ሱፍ አልበሰው፤ ከረባት አክለው እንደ እቃ ይጫወቱበታል። እስረኛው ጠ/ ሚር አሁን ለእኔ ቤተ መንግሥት ነው ብዬ በፍጹም አላስብም። 

እርግጥ ነው ዛሬ ትንሽዬ ከሰሞናቱ የጭቃ ቤት ገዳዳ የተጋደሙ አዲዳዲ ምርጊት ህልም ሻል ያለች ነገር ብመለከትም አሁን ወንበሩን ሰው ቁጭ ብሎበት አላዬሁም፤

እኔ እንደሚገባኝ ችግራችን የመርህ ሰው አለመሆናችን ይመስለኛል። ሌላው ችግራችን ደግሞ የሚቀድመውን አለማወቅ።

ለምሳሌ አሁን የአብን እና የግንቦት 7 ጉግስ አብይ ከሌላ አፍር ድሜ ይግጣል። ዴሚክራሲያዊ ምርጫ ለዘላለሙ ይዘጋል። ነፃነቱም ተሰጥቶ ታይቷል።

ተገኜ የተባለው ለውጥ ከሦስት ከአራት ተሸንሽኖ መና ይሆናል። ወያኔ ሃርነት ትግራይ ለጋሸ ጃግሬው ለኢዴፓም፤ ለአቶ ልደቱ አያሌውም አልሆነም እንኳንስ ለሌላው። እሰከ ፈለገው ድረስ ጢባ ጢባ ተጫወተበት ዛሬ እንደ አሮጌ አካፋ እና ዶማ ወረውረው …

በሌላ በኩል በበርካታ ቅንጫፍ የተባዛው ኦነግ እና ኦብነግ በሰከንድ ውስጥ ጥምረት ፈጥረው ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ አይታወቅም። 

ለዚህም ኦቦ ለማ መገርሳ ህዝብን ተማጽነዋል። „ወይ ባልዘፈንሽ  ከዘፈንሽም ባላፈርሽ ነው“ የአገርን አደራ የተረከበው እኮ ኦህዴድ ነው። 
መንግስት የህግ የበላይነትን የማስከበር ግዴታ አለበት ለዚህም ህብረተሰቡ ሊተባበር ይገባልአቶ ለማ መገርሳ
ስለዚህ ገና መሠረት ሳይዝ አስገባ አስገባ ተደራደረ አሁን ወገቤን ቢል ጉዳዩ አቅሙን መጠዬቅ ነው። ይሄ የራሱ  የኦህዴድ ጉዳይ ነው። "ህብረተሰቡ ሊተባባር ይገባል" ምን ብሎ?ምኔስ ብሎ? ኦህዴድ ተሸንፌያለሁኝ ብሎ ኦነጋውያን መሆኑን ነው ለዛ ነውን የሚተበባረው? 

እጅግ ለምሳሳለቸው ዶር ለማ መገርሳ እምለው እኔ በግሌ ሚኒያ ላይ ያደረጉት ንግግር በወኔ፤ ሚሊዬንም ላይ የታዬው የኦነግ አሸነፊነት ትእይንት ያ አቅም አመንጭቶ ለውጡን እንዲድን ከማድረግ ውጪ ያ ቅን በአደባባይ ደሙን እና አካሉን የገበረውማ ምን ይሰማዋል እኮ አልተባለም፤ ሌላው ቀርቶ እንዴት ያ ድል እንደተገኘ እኮ ፍንጭ አልተሰጠም። ቄሮ አሸነፈ ነው የተባለው። ይህም ይሂን ህብረተሰቡ ባዶ እጁን ነው፤ ባዶ ሆዱንም ነው። 

መጀመሪያ በጠራራ ጸሐይ ድፍት ስላለው አገራዊ ምልክት ጭንቀት ይኑረን? ምን እንዲያደርግ ይሆን የሚፈለገው ያ መከረኛ ህዝብ? ኦህዴድን ማመን እና መቀበል ነው አድርጎታል፤ አድርገነዋል። ጫናውን ሁሉ ችለን። መከራውን ሁሉ ታግሰን። ግን ያዬነውን አይተናል። የታዘበውነውም ታዝበናል። 

ለጆዋር ንግሥና አልነበረም ቀን ከሌት የተተጋው …  እራሳቸው በዛ ስብሰባ ላይ መገኘታቸው ካልቀረ ህጋዊ አድርገው ነበር መገኘት የነበረባቸው። ምን አልባት አሁንም እሳቸው ነፃ ከሆኑ ካልተጋቱም ማለቴ ነው ... ሚኒያ ላይ ያን ያህል እንኳን ለ እኔስ ኖራችሁልኝ ዓይነት መንፈስ በወኔ ሱናገሩ ለዚህ ቀን አማራም አድርሶናል ማለት ነበረባቸው። ባልተስረከረከ ባልትዠጎረጎረ ቁርጥ እና ግልጽ ቋንቋ ግን አልሰማንም። 

ወስጣችን አዝኗል። ይህ የእኔ ስሜት ብቻ አይደለም፤ ባይተዋር እኛ አድርገናቸው አናውቅም፤ ስሜቱ ግን ያን ያመለክት ነበር።  በእኛ ውስጥ ታቦታችን ናቸው እሳቸው ቢቀበሉትም ባይቀበሉትም፤ የሆነ ሆኖ አገራችን ከ27 ዓመቱ በላይ ችግር ውስጥ ናት ሥርዓት አልበኝነቱ ገዢ ሆኗል።  

ሌላው ማፍያው አጋቹ ቡድንም እንዲሁ በሙሉ አቅም ላይ ነው፤ ሙሉው የወያኔ ሃርነት ትግራይ ከአዲስ ክልሎች ጋር በጥምረት ውህደት ፈጥሮ ምን ዓይነት ህብረ ብሄራዊ ፓርቲ ሊያደራጅ እንደሚችል አላሰብነውም፤ ለነገሩ ድሮም አዬር ላይ ነበርን አሁንም አዬር ላይ እንዋዥቃለን …
ሌላው በፍጹም ሁኔታ የአብይን ሌጋሲ አንቀበለም ያሉት ደግሞ አማራጭ መንገዳቸውን ይዘው የመጣውን መከራ ለመቋቋም አቅም አልፈጠሩም። ምክንያቱም አሁን አብይ ተወግዶላቸዋል እና። የሚያሞቅ፤ የሚያበረታታ የትግል መስመር ነድፍው ህዝብን ለማዳን ምንም ላይ ናቸው። ብቻ እኛ ዝብረቆች ነን።

ጠቅላይ ሚ/ሩ ጉድጓድ ውስጥ ነው ያሉት።

ነፃነት ለአብይ እና ለቤተሰቡ!


የኔዎቹ ኑሩልኝ። 
መሸቢያ ጊዜ። 

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።