"የኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው" መባቻ።

መባቻሥርጉተሥላሴ
ከሥርጉተ  © ሥላሴ (Sergute©Sselassie)
09.11.2017 (ከገዳማዊዋ ሲዊዘርላንድ ዙሪክ)
„ግሩም ድንቅ ሁኜ ተፈጥሬያለሁ እና አመሰግንሃለሁ፤ ሥራህ ድንቅ ነው ፣ ነፍሴም እጅግ ታውቀዋለች።“
(መዝመረ ዳዊት ምዕራፍ ፻፴፰ ቁጥር ፲፬)
መቅድም
የጹሑፌ አንባቢዎች እንዳብራራው የተጠዬቁኝ ነገር በግል አለኝ። የሌሎችም ሊሆን ስለሚችል ትንሽ ልበልለት። በዩቱብ ባንኬ ላይ እዬሠራሁ በማስቀምጣቸው የፍቅራዊነት (LoveIsm) አዎንታዊ አነቃቂ የቃላት ፖስተር ፕሮግራም ላይ ነው ትንሽ እንዳብራራው የተጠዬኩት። ዝግጅቱ ለመነሻነት ብቻ ነው የሚያገለግለው። የፍቅር ተፈጥሮ መርህ ውቅያኖስ ነውና። መንፈሱ የሰው ልጆችን የተፈጥሮ ልዩ ጸጋ የሆነውን ፍቅርን በአንድ መሥመር ብቻ ያማከለ አይደለም። የተለያዩ ደወሎችን፤ የህብረ ቀለማት ህብር ነው። ሙሽራው የሰው ልጅ ነው። ስለፍቅር ተፈጥሮ ሲገለጽ የፍቅር ተፈጥሮ በርካታ ልዑካኖች አሉት። ማህበራዊ ኑሮው፤ መኖር ራሱ፤ ነፍስ እራሱ፤ ከዚህም ባሻገር ጋራው፤ ሸንተረሩ፤ ተራራው፤ ወንዙ፤ ዝናቡ፤ ፕላኔቶች፤ ህዋው፤ አዝዕርቱ፤ ቅጠላ ቅጠሉ፤ ነፍሳቱ፤ እንሰሳት፤ እነኝህን ሁሉ ያካትታል። እነሱም በእኛ ውስጥ ያሉ የፍቅር ታቦቶች ሲሆኑ፤ ሰላማቸውን ግን ታውኳል ስለሆነም እንደ ሰው ልጅ የደማናማው ዘመን የመከራው ተጋሪዎች ናቸው። ስጋት ዓለምን ውጧታል። ሁሎችም እረፍት ያጡ ናቸው። ፍቅራዊነት ለእኔ ሃይማኖቱ የተከፈተ ቅን ልቦና ብቻ ነው። የፍቅራዊነት (LoveIsm) ቀለሙ ደግነት ነው። የፍቅራዊነት ፊደሉ ሰብዕዊነትና ተፈጥሯዊነት ነው፤የፍቅራዊነት ዶግማው መቻቻል ነው። የፍቅራዊነት የይዘቱ ተክለ ሰውነት ውቡን የምርቃት አንባን ተፈጥሮን በሙሉ ማዕከል ማድረግ ነው። አሁን ሰው „አድናቆትን“ እንደ ተራ ነገር ሊያው ይችላል። „አድናቆት“ ግን የተራራቁ መንፈሶችን በጥበቡ በአሃቲነት የሚያስደምም የክህሎት ሥነ – ጥበብ ነው። „ምስጋና“ ምስጋና ሰጪው በውስጡ ፍቅር ሲኖር ብቻ ነው ንፉግ የማይሆነው። እራሱ ጌታችን መዳህኒታችን እዬሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ የፈጠረው ለምስጋና ነው።
ፍቅራዊነት የጥንዶችን የኑሮ ሥነ – ምግባር ወጥና ውበታዊ በማድረግ እረገድ በአዲስ ትውልድ የሞራላዊ የግንባታ ሂደት ላይም ያተኩራል። አዲስ የኑሮ ጥበብም ነው። ማህበረሰብ ት/ቤቱ ቤተሰብ ነው እና። የሆነ ሆኖ ስጀምረው ይህን ያክል ጥራት ይኖረዋል ብዬ አላሰብኩትም ነበር። አስር /10/ ብቻ የፍቅራዊነትን ህልም ፓስተሮችን ሠርቼ ዩቱቤ ላይ ለመለጠፍ ነበር ዓላማዬ። በፊልም መልክ። ለዚህ በባለሙያ የተጠዬቁከት ከ2.00.00 /ከሁለት ሺህ/ የሲዊዝ ፍራንክ በላይ ነበር። ፖስተሩን ይዤው ሁለት ዓመት ተቀመጥኩ። ትንሳኤ ትንሳዔውን ዓውጆለት አሁን ከመቶ በላይ ፕሮግራሞችን እራሴው ሠርቼ ተለጥፈዋል። አጭር ነው ዝግጅቱ። የአዕምሮ ቴራፒ የሚያደርግ ሙዚቃም አለው። ደወልም ሊሆን ይችላል። እንንቃ፤ እንሰብ አርቀን ነጋዊነትን እናስተውለው ለማለት። ግራፊክ አለው። የጹሑፍ አርቱ አሰልቺ አይደለም። ቆይታውም እንዲሁ አሰልቺ አይደለም። አሁን እዬሠራሁት ያለው „የፍቅራዊነት ተፈጥሮ ረቂቅነትን ነው“ ለመነሻ የሚሆኑ ዋና ሃሳቦች ወደ 35 የሚሆኑ ምዕራፎች ይኖሩታል። እነኝህ ምዕራፎች በኮምፓክት conpact በክለሳ ይጠቃለላሉ። ኮንፓክቶች ደግሞ በአንድ ፕሮግራምsummary ይቋጫል። ስለዚህ ከሥር ተነስቶ ማዬቱ ነው የሚበጀው። ለምሳሌ „የፍቅራዊነት ራዕይ“ የሃሳቡ ሆድ ዕቃ ነው። የጽንሰ ሃሳቡ አንጎል ነው። ከእሱ መነሳቱ መልካም ይመስለኛል። አያያዥ ሰለሆነ። ሌላው የተደጋገመ ቃል ይኖራል ለምሳሌ „መቻቻል።“  ከ„ውሃ“ ጋር በቀን እኛ ስንት ጊዜ እንገናኛለን? በዚህ ስሌት እሰቡት ዬአንዳንድ ቃሎች መደጋገሙን። በፍቅራዊነት ተምሳሌት የሆነው የጥበባኛው ቴዲ አፍሮንም በአማርኛ አንድ የፖስተር ፕሮግራም ሠርቼ አስቀምጬለታለሁ። ታሪኩ ነው። እምታገኙት ግን ሥሜን በእንግሊዘኛ ከጻፋችሁት ብቻ ነው Seregute Selassie ፎቶዬ በኢትዮጵያ ሰንደቅዓላማ ያለው ነው። ከዚህኛው ጋር ሌላ ጉዳይ ሊቀላቀልበት ስለማይገባ ሁለት ዩቱብ ነው ያለኝ። ሁለተኛው በአማርኛ የተለያዩ ዝግጅቶችን ልሠራበት ያሰብኩት ገና ውጥን ነው። ቀድሜ መጨረስ ያለብኝን ቅምጥ ጥሪት ከጨረስኩ በኋዋላ እሠራበታለሁ። አሁን ወደ ተነሳሁበት የጉዳዬ የዛሬ ዘር ….
  • ሰሞናቱ።
  • ሰሞናቱ በአንድ መሥረታዊ ብሄራዊ ጉዳይ ላይ የሁላችንም ተመስጦ ተገዝቶል።

ቀደምቱን ወላዊ መሪ ቅን መንፈሶችን በምለሰት ለናሙና ስንቃኘው፤
·         „ወይ ተባበሩ ወይ ተሰባበሩ!“
·         „መርህ ይከበር!“
·         „ዝም አንልም“
·         „ድምጻችን ይሰማ!“
·         „የሚለዮኖች ድምጽ!“
·         „የእሪታ ቀን!“
  • ቀደምቱን ቀንጣዊ ቅን መንፈሶች ለናሙና በምልሰት ….

·         „ቅንጅት መንፈስ ነው!“ የአንዲት ወጣት ፖለቲካ አንስት ጽርሃ መንፈስ ነበር።
·         „አሁንም እንደ ገና!፤ አሁንም እንደ ገና!“ በአቅማችን ላይ እንሁን እንደማለት። ለትውልዱ የመጀመሪያዋ አንስት የአንድ ብሄራዊ ፓረቲ ሊቀመንበር ንዑድ መንፈስ ነበር።
·         „በቃ!“ ይህ ሃይለ ቃል የአንድ ካናዳ የሚኖር ድንቅ ወጣት ዘር ነበር። በ“በቃ!“ ቲ ሸርት በራሱ ወጪ ያሠራ። አሁን አገር ቤት ያለውን አብዮት የሚመራው ይህ ጉልበታም ቃል ነው። ብሄራዊነቱ ታሪካዊነቱ ብጡል ነው።
·         „የፈራ ይመለስ!“ የአንድ ድንቅ ወጣት ጋዜጠኛ ዘመን አሻጋሪ የተግባር አርበኝነትን ያወጀ ነው።
·         „የሚታይ ነገርን ለማሳዬት የማይታይ ነገር ቀድሞ መሠራት አለበት!“ የአንድ ዕውቅ የፖለቲካ መሪ „ሰከን“ በሉ፤ አደብ ግዙ፤ ገና ምን አይታችሁ፤ የሚል ተስፋ ሰናቂ ነው።
·         „… ከእንግዲህ ሰው ሰብስቤ ማነጋገርን ላቆም ነው!“ የእኒሁ ፖለቲካኛ እና የኢኮኖሚ ሊቀ – ሊቃውንት የአርበኝነትን መንፈስ ያነቃቃ ልብ የተሸለመው መርኽ።
·         „ኢትዮጵዊነት ሱስ ነው“ የአንድ ወጣት ፖለቲከኛ አሁንም ልብ የተሸለመው አቅጣጫ መሪ ለጋ ወቅታዊ ፖሊሲ ነው።
  • ወደ እኛ ሲመጡ።

እነኝህ ቅን መንፈሶች ወደ እኛ ሲመጡ ለአፍቅሮተ ማልያ፤ ለቂም፤ ለበቀል፤ ለሴራ ፖለቲካ፤ ለቅናት፤ ለምቀኝነት ልባችን ያልሸለምን አብዛኞቹ ኢትዮጵውያን ደስታን አንጥፈን፤ ተስፋን ጎዝጉዘን፤ ነገን በብርሃን ሰንቀን ነበር አቀባበል ያደረግንላቸው። በዛን ጊዜ ለዬትኛውም ወላዊ ይሁን ቀንጣ አቅጣጫ አመልካች መርሆዎች ወይንም ብሄራዊ የፖሊሲ አቅጣጫዎች ምንም ቅደመ ሁኔታ አልሠራንለትም። በፐርሰንትም አልሸነሸነውም። ደረጃም አላወጣንለትም። ወይንም ዞጋዊ ፍተሻ አልደረግንም ወይንም ውጤቱ ካላዬን ሞተን እንገኛለን አላልንም። ልባችን ከፍተን አድናቆታችን መጠን በሌለው ልግስና እና ቸርነት ፍቅርን ሸለምነው። ከሴራ ፖለቲካ ጋር ንክኪ የሌለን ወገኖች። ተቀናቃኝ መንፈሶችንም በግልጽነት፤ በድፍረትና ልባችነን ሞልተን ፊት – ለፊት ወጥተን ተሟገትንለት። ለሀገር በቀሉ ጠቃሚ ቅን መንፈስ። ከብዙዎች ጋር በዬዘመኑ አዲስ ጠላት እያፈራንም ተቃቃርን። አብሶ እኔ። ለብዙ ጥቃት ተጋለጥኩኝ። በእኛ ሐገር የፖለቲካ ሙግት ጠላት የሚፈራበት፤ ግት የሚታወጅበት፤ ቂም የሚቋጠርበት፤ ሰው እንዳሻው የሚፈረጅበት፤ ታኮ የሚመረትበት፤ የአሉባልታ ሊኳንዳ ቤት የሚሰናደበት ነው። በዕውነቱ ዴሞክራሲ ቃሏን እንደ ዳዊት እዬደገምን በዕውኑ ዓለም ግን ሥልጣኔ አብዝቶ ይጎድለናል። የሙግቶች ግብዕቶች ህሊናን ለማጎልበት፤ አቅምን በአግባቡ ለመጠቀም፤ ስልትን ለመጠበብ እንዲያገለግል አይፈቀድለትም። የሆነ ሆኖ ሳይጀመር ግብ የለም። ለማናቸውም ውጥን ህዝበ – ጠቀም መባቻዎች እንክብካቤ፤ ድጋፍ፤ በጥንቃቄ መስጠት ያተርፋል። ድካማችን ይቀንሳል። ቅንነትን ሳንሰት አጠጥተን በመስኖው እንዲለማ ካለደረግነው፤ ያው ነው እንደለመደብን አቅማችነን ፍልስ እናደርገዋለን። አፍሰን መለቀም፤ አቀዝቅዘን ለማሞቅ ሰው መገበር። አይዋ ማህበረ ደራጎን ደግሞ በእኛ ተዛነፍ ድከመት ተንጠራርቶ አጎልብቶ ቀዳዳዎችን ወታትፎ በአዲስ ተውኔት ብቅ ይላል፤ ያው የተለመደው ሰውን እንደ ጥሬ ዕቃ ባልተቋረጠ የማቅረቡ ሂደትም ይቀጥላል … እኛ የገፋነውን፤ እኛ ፊት የነሳነውን አቅም ብልሆቹ ይጠቀሙበታል። „ባለቤት ያቀለለውን አሞሌ ባለ ዕዳ …“ እንደሚባለው ….

የሆነ ሆኖ ሌላው ቅዱስ አሰባሳቢ ሃሳብ ቅደመ ሁኔታ አልተሰራለትም ነበር። ስለምን ይሆን ዛሬ „ኢትዮጵዊነት ሱስ ነው“በቅድም ሁኔታ እንዲታሠር/ እንዲቀፈደድ ያስፈለገበት ብዬ እራሴን ስጠዬቅ ወያኔ ሃርነት ትግራይ አህያ እዬገደለ የገባበት አዚም ወይንም የሰማይ እርግማን ይሆናል ብዬ አሰብኩ። አንዲት አንስት ጽንስ በማህጸኗ ሲያደር ያረጋ ደም ነው የሚሆነው። አሁን ለዛ ያረጋ ደም ሙሉ ጽንስ ስትሆን፤ ስትወልድም 900 ውሃ ያዘለ ተራራ ተሸክመህ ካለዬሁህ አሁንም ጽንስ ነህ ብዬ አልቀበልህም ነው – ሙግቱ። የፈጣሪን ሰማያዊ ጥበብ በመጋፋት። ይህን ለዛውም ባለቤት በሌላት ሐገር ላይ፤ አዛዡ እውር ድንብሱ በጠፋበት ሁኔታ፤ ሊጠፉ ከሚችሉ ሐገሮች ዝርዝር ውስጥ ለምትገኝ ሐገር እንዲህ ለ„ኢትዮጵዊነት ሱስ ነው“ ቅድመ ሁኔታው ይደረደርለታል። መጣህፍም ይገለጥለታል። እኔ ሳስበው የ አቶ ለማ መገርሳ የጉዞ ትልም እና እራሱ የ ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው ገጠመኝ ላሳቸውም ለራሳቸው ድንገተኛ surprise ነገር ይመስለኛል። ባልጠበቁት ውስጥ አልፎ ያዩት አቅም ነው ኢትዮጵያዊነት የተመስጧቸው ንጉሥ የሆነው። እሳቸው የሄዱት አቅምን ወደ እራስ የማምጣት ስበትን ለመፍጠር፤ ተጽዕኖ ለመፍጠር ይመስለኛል። ግን የአማራ ፍቅር ተፈጥሯዊ ቀለም ያለው መሆኑ ነው እሳቸውን ለዚህ ታላቅ የታሪክ ገድል ያሸጋገራቸው ብዬ አስባለሁ። ባለውለታቸውም ነው ይህ ጉዞ። የተወለዱበት ቀን ልደታቸው። እሳቸው እራሳቸው አላሰቡትም በዚህ ውስጥ እምሰጣለሁ ብለው። ይህ የብልህንታቸውን ዲካ ልቅናቸውን ያሳዬል። ለዬትኛውም ጫካ ለተመኘ ቡድን አማራ የሰጠውን ቀለማም መሳጭ ተፈጥሯዊ ፍቅር ተርጓሚ አግኝቶ አያውቅም። ባክኖ ነው የቀረው። እንዲያውም የጥቃት ሰለባ ነው ያደረገው። ያ ፍቅር ይህን ያህል ጉልበታም ሆኖ ታቦት የሆነው በአማራ ውስጥ ያለው ለኢትዮጵያዊነት የታማኝነት የፍቅር ደረጃ ነው። ወደ ጥልቅ የፍቅር ተፈጥሮ ጉዞ አቶ ለማ መገርሳን የወሰዳቸው። ነገን እኔ የምጠብቀው እሳቸውን በዚህ ጥልቅ የሚስጢር ልቅና ነው … ዘልቀው እንዲያፈሩ ነው።
  • ተጠዬቅ

ይህ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው ተጠዬቅ፡ እዬተባለ ነው። ይገባልም ድንገተኛ እንግዳ ስለሆነ – ሊመረመር – ሊፈተሽ። ሌላው የገረመኝ ግን አንዱ አኖሌን አፍረሰው ያሳዩን የሚል መንፈስ ታጥቆ ከች ይላል። ሌላው ደግሞ የኢትዮጵያዊነት አለት የሆኑትን እና የንጎሦች ንጉሥ አጤ ሚኒሊከን ያለውን ዕይታ ማወቅ እሻለሁ ይላል። አነ ድንቅ አርበኛ ዲነግዴ፤ እነ ድንቅ አርበኛ ጉባና ካልተነሱ በጅ አልልም ይላል። አሁን ይሄ ሁሉ ጉዳይ አሁን ላለው የጭንቅ ቀን ምጥ ገላጋይ ሊሆን ይችላልን? ሐውልት መፍረስ ያለበትስ በልቦናችን የቀረጽናቸው የማንፌስቶ ጣዖታት ናቸው። የሥነ – ልቦና ዝግጅታችን ገና የሙቀቱ መጠን ከዕንባ ጋር ለመዋህድ ጊዜ  ያስፈልጋል። ሐዘኑ የላይ ነው ዕሳቤው። በሚሊዮኖች የራሮት ድምጽ ያለከተመ ነው። ሃሳብ፤ ትልም፤ ራዕይ እኮ አቅጣጫ ነው። ወደ ድርጊት ሊሸጋገር የሚችለው ሁሉም ያለውን የመንፈስ ድጋፍ ካዋጣለት ብቻ ይሆናል። ያ ደግሞ የሂደት ውጤት ነው። ስኒ ላይ የተለያዩ የባዕድ የሆኑ አመክንዮች ቡና ተቀድቶ በፌስታ ይጠጣል። ስኒ ላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ሠንደቅ ዓለማ ሲኖር ከሰው ቤት ተሂዶ እንኳን አሳብዶ ያሰነሳል …. ይህ ባለበት ሁኔታ ነው „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ የተደመጠው። „ኢትዮጵያ“ የሚለው ቃል እኮ ከዬትም ቦታ እንዲገለል የተፈረደበት እኮ ነው። እስኪ ለኦነጋውያን „ኢትዮጵዊነት ሱስ ነውን“ በሉት አይደለም ከጹሑፉ ውስጥ ቢገኝ ሊያነቡት አይፈቅዱም፤ ሊያዳምጡትም አይፈቅዱም። ያማቸዋል። በውስጣቸው ያለው ነገር ይህን ቃል ለማድመጥ አይመቸውም። ስለምን? ያለሠራናቸው አምክንዮዎች ስላሉ። መጣን የሚሉትም ሥር ነቀል ከልብ የሚገባ የለውጥ ሐዋርያነትን አልፈቀዱትም። ያልተነካ ድንግል መሬት ነበር ውስጥን ገልጦ ማሳዬት መሬት ላይ ዘመኑ ላልተፈቀደለት ኢትዮጵያዊነት። እንሆ ዛሬ ጥግ አገኘ። ሚሊዮኖች ይከተሉታል። መዳኛ ነው ለሚሊዮኖች የራሮት ድምጽ።
አንድ ነገር ትዝ አለኝ። የአገልግሎት ዘመናቸውን ያጠናቀቁት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የተከበሩ ፕ/ባራክ ኦባማ ሲወዳደሩ „ አዎን! አንችላለን“ የሚል ነበር። ታዲያ መቻልህን አሁን ቁጭ እንዳልን ዘርተህ – አብቅለህ – አፍርተህ አሳዬን ተባሉን? ሌላው ቀርቶ ይህ መንፈስ ለሁለተኛ ዙር ምርጫ እንኳን የሠሩትና የቀረው ተማጣጥኖ የተጀመሩት አንዲቋጩ ተጨማሪ ጊዜ ነው የተሰጣቸው። ሥልጣኔ ማለት ይሄው ነው፤ ከተፈጥሮ አምክንዮ አለማፈንገጥ። ልጅ በአንድ ቀን ተጸንሶ፤ ተወልዶ፤ ለቁም ነገር አይበቃም። ፈጣሪ መሬት ወርዶ ታምር ካልሠራ በስተቀር። የወቅቱ ፕሬዚዳንት/ ፕሬዚዳንት ትራንምፕ „አሜሪካ ትቅደም“ አሉ። መቼም የነበረው ጊዜ በውዝግብ የሰመጠ ነበር። አስቀድምህ አሜሪካ ስትቀድም አሳዬን አልተባሉም። በዚህ መሪ ቃል አብላጫውን ድምጽ ይዘው በዛ አወዛገቢ ሙግት ውስጥ አልፈው ይሄው ፕሬዚዳንት ሆኑ። የምርጫ ዘመናቸውን በዚህው ይቀጥሉ ወይንም ይቋረጥ/ ወይንም ተጫማሪ ዘመን ይጨመርላቸው በሂደት የሚታይ ነው። ኢትዮጵያ ላይ ግን ሰነሰለት ይዘጋጅለታል። የመፍትሄ መንገድ … አዲስ ራዕይ ያለው፤ አቅም ያለው ሰው ብቅ ሲል በውጥረት ንጦ ከጨዋታ ውጪ ማድረግ  … ቧልት።
  • ሁሉንም በጠላትነት መፈረጅ – የብልህነት ድርቀት ነው።

አቅም እንዴት ሊደመጥ ይገባዋል? አቅም እንዴት ይያዛል? አቅም እንዴት ሊመራ ይገባዋል? አቅም እንዴት በሥርዓት ሊደለደል ይገባዋል? አቅም እንዴት በቁጠባ ሊያዝ ይገባዋል? አቅም እንዴት በተቀማጭ ሃብትንት ሊታይ ይገባዋል? አይደለም አቅም ላይ ራሱ ፈቅዶ በራሱ ጊዜ አቅም ሲታደም ቀርቶ ሲያመለጠን እንኳን አናስተውለውም እንኳንስ አስቀድመን ጥንቃቄ ልናደርግበት። እንኳንስ በቅጡ ልናስተዳድረው። እንኳንስ ሃብታችን ልንለው። እንኳንስ ልናቀርበው። መደረጀት እኮ ውጪያዊ አይደለም። ወስጣዊ ነው። ምንግዜም በህሊና ውስጥ፤ በራስ ውስጥ ድርጁ/ ስንዱ ሆኖ መገኘትን ያስፈልጋል ለአንድ የነፃነት ራህብተኛ። ፍላጎቱን የማይናወጽ ጽኑ አመክንዮ ሊኖረው ይገባል። ነፋስ በመጣ ቁጥር የማይወዛወዝ፤ በወጀብ የማይናጥ። በቁልፍ ያልተከረቸመ … ቅንነትን የሰነቀ መሆን አለበት። ለሀገር ክፍት እምሮና ለዘላቂ ሰላም ፍጹም ታማኝ መሆንን ይጠይቃል። የትውልድ ጉዳይ አጀንዳችን ከሆነ።
በአንድ ሥርዓት ውስጥ የህዝብ ኑሮ የሚመሠረተው በሥርዓቱ በተረቀቁ እና ይሁናታ ባገኙ ህገ መንግሥቶች፤ በተጨማሪ ህግታት፤ እንዲሁም የአፈጻጻም መመሪያዎችም ይሆናል። ዛሬ ያለው ትውልድ በወያኔ ማንፌስቶ እጅ ባለው ህገ መንግሥት ሥር መውደቁ ግድ ነው። የትኛው ዕጣ ነፍስ ነው ከዚህ አምልጦ ኢትኦጵያ ውስጥ የሚኖረው? ይቻለዋልን? አሁን ዛሬ የጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴን የኒወርክ ታይመስን የአቶ ታከለ አለነ የመንፈስ ካቢኔ ይዞታ ትዝብት አዳምጬው ነበር። የመዋቅሩ ሰንሰለት መተንፈሻ ጭላንጭን እንኳን የለውም። ካህኑ ራሳቸው ካድሬ ናቸው። በዚህ ሂደት ውስጥ መኖር በማንኛውም የኑሮ ዘርፍ ያሉ ወገኖቻችን ግዴታ ነው። ስለምን አብራችሁ ኖራችሁ ብሎ መውቀስ አይገባም /የአማራ ተጋድሎ የኔታዎች ስለሚብጠለጠሉበት።/ ምን ምርጫ ነበራቸው። ሰው እኮ ኑሮውን ታግሎ ማሸነፍ ካልቻለ መኖር አይችልም። መኖርን ለማኖር አስገዳጅ ሁኔታዎችን ሁሉ ሳይወድ ተቀብሎ እንዲኖር ይገደዳል። ይህ የሶሻሊዝም ርዕዮት ደግሞ መርሁ ይሄው ነው። የመንፈስ ነፃነትን በፍጹም ሁኔታ የሚገፍ። በቤት ውስጥ እንኳን የቤት ነፃነት የሌለበት ነው።
የሚገርመኝ በዛ ሥርዓት ውስጥ የነበረ ወገን የአቶ ለማ መገርሳ ነገር ያንገሸግሸዋል፤ ያበሳጨዋል፤ ይጎመዝዘዋል። ሰከን ያሉት ረጋ እንዲል ቢያስተውሉትም አልቻለም። ረጋ ብሎ እራሱ የነበረበትን ሁኔታ ሊመረምር አልፈቀደም። ጥፋት ካለ ጊዜ አለ – ለመወቃቀሱ። ሥርዓት ከተዘረጋ እኮ ክፍት ነው ለፍትህ። ዛሬ ግን ከግለሰቦች ጥፋት በላይ ሐገር ልትጠፋ ነው። ህዝብ ሊተላለቅ ቋፍ ላይ ነው። በቀል ሊነግስ እያኮበኮበ ነው። ዛሬ የምንቀናጣበት፤ ቀይና አልጫ የምንልበት አይደለም። በእጅ በሌለ አቅም ዘራፍ ማለት ከጭብጡ አናት መውጣት ነው። ቀድሞ ነገር በዛ ሥር በሰደደ የካድሬ ትብትብ ሁኔታም አንድን ነፍስ አባል የነፃነት አርበኛ ለማድረግ በፍጹም አይቻልም። ከአምክንዮ ውጪ ነው። ይህን ሁሉ ድጦ የወጣው ዕንባ ብቻ ነው። ይህ የህዝብ ማዕበል እኮ መሪ ያስፈልገዋል። በስተቀር ይከሽፋል። ለበለጠ አደጋ ይጋለጣል። ለመሆኑ ማነው ከወያኔ ሃርነት ትግራይ ጋር በግልም ይሁን በተደራጀ ሁኔታ ለመሥራት ያልፈቀደው? ያልሠራውስ፤ ለመሥራትስ ያልሻተው? ሻብያ፤ ኦነግ፤ ኢህአፓ፤ አማራጭ ሃይሎች፤ ህብረት፤ ቅንጅት፤ መደረክ፤ ሸንጎ ማን? ሻብያ ሀገር ያድናል ብለን ተጠግተን እዬመረቅን፤ አፋችን ቁርጥ እስኪል ድረስ ስለሁለመናው በውዳሴ እዬዘከርን፤ በዓለም ተቀባይነቱ እያደገ መጣ ብለን የተለዬ አድናቆትን ይቸርን፤ እያጀገን ነገር ግን የራሳችን ወገን ግን ገሸሽ እንደርጋልን። ምን ማለት ነው ይሄ? አይገባኝም። እንዲገባኝም አልፈቅድም። እኛ የምንመካበት መሬት ላይ ምን አለን በተለይ አማራው? በድርጅት ይሁን በግል ጥንካሬ የመንመካበት። ዛሬን ነው ማዬት ያለብን። … በዛሬ ውስጥ እንሁን።ቀደም ባለው ጊዜማ ከማህበረ ደራጎን ውጪ ሆኖ ተሁኖ  መሬት ላይ ያሉ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ቅድመ መወያያ ሊፈራራሙ ነው ብለን ውግዝ ተ-አርዮስ ብለን ነበር እኮ። የዛሬ 6/7 ዓመት ልበ ሙሉ ሆነን ተስፋችን ጥግ የሰጠነው ስለነበረን። ስንት ዓመት ተቆጠረ …. እና ብልህ እንሁን። ከእጅ የገባ ነገር ካመለጠ አይገኝም። ወርቅ ይቀልጣል፤ መቅለጡ ብቻ ሳይሆን ይፈሳልም ….
  • ብድር ቀረማ።

ለመሆኑ እኛ እራሳችን ኢትዮጵያን ያሰቀደመ ሥያሜ ያለው ምን ያህል ፓርቲ አለን? በዬጊዜው የሚፈጠሩ የስበስብ ዓይነቶስ ኢትዮጵያን ይገልጻሉን? „አገር“ ነው የሚባለው? የኢትዮጵያዊነት ሥያሜ ለመሆኑ የነፍሱ መንፈስ ከሥልጣን ሹም ሽር ባሻገር እናስበዋለን? መንፈሱ እኔ የማዬው ከኢትዮጵያ ሥያሜ መንፈስ ወጥተን ብድር ነው የምንቃርመው። „ኢትዮጵያ“ የሚለውን የጥቁር ህዝብ የነፃነት ዓርማ ሥሙን እራሱ መድፈር አልተቻለም። እንኳንስ „ኢትዮጵያነት ልብ ውስጥ የሚቀመጥ ሱስ ነው“ ልንል ቀርቶ። ወደ ዛ ንኪኪ ከኖረው እኛ ለምናስበው፤ ከሌሎች ጋር ለምናደርገው ድርድር እንቅፋት ይሆናል በማለት ስንገፋው ነበር የኖርነው ሥያሜውን፤ ዕውነቱ ይሄ ነው። ከነበራቸው ጋር እንኳን ስንዋህድ ሥሙን ለመቀበል አቅም አልነበረንም። ስለሆነም ይህን ቅዱስ መንፈስ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነውን“ የማጣጣል የሞራል አቅሙን ሰፋሪ ሆኖ ለመቅረብ ይከብዳል። በፍጹም ሁኔታ ከይፈርሳሉ ሐገሮች ዝርዝር ውስጥ ዕድምተኛ ለሆነችው ሐገር ኢትዮጵያ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ የቀደመ፤ የሰለጠነ፤ ብልህ መንፈስ ነው። ታቦት ነው።
ሥራ።
ሥራ የሁለት ፊደላት ቅምር ነው። ሥራ ሁለመና ነው። አንድ ቅን መንፈስ ተንከባካቢ ይሻል – በሥራ። እረዳት ይሻል – በሥራ። አይዞህ ባይ ይሻል – በሥራ። የእኛነትን ይሻል – በሥራ ። ተነሳሽነትን ይሻል – በሥራ። አትኩሮትን ይሻል – በሥራ። ምራቅን መዋጥ ይሻል – በሥራ። አደብን ይሻል – በሥራ። ሰከን ማለትን ይሻል – በሥራ። ማዳመጥን ይሻል – በሥራ።
አንድ ቅን መንፈስ ብልህነትን ይራባል፤ ቅርበት ይጠማዋል። ከራስ መንፈስ ጋር መሆንን ይሻል፤ የውስጥ ለውጥን ይመኛል። መፈለግ በራሱ ግብ አይደለም። ለግብ የሚያደርሱ አሰባሳቢ ቅን መንፈሶች ናቸው ለግብ የሚያደርሱ። በዚህ ቀውጢ ጊዜ፤ መንፈስ ህልቆ ማሳፍርት በሌለው ስጋት በተወጠረበት ሰዓት አንድ ያልተጠበቀ፤ ፈጽሞም ያልታለመ መንፈስ ወደ እኛ ይመጣ ዘንድ እግዚአብሄር አምላክ ወደደ። በዬትኛውም ዘመን፤ ከዬትኛውም ወገን ይምጣ ቅን መንፈስን ቅንነትን መመገብ ያስፈልጋል። እነዚህ ቅን መንፈሶች ከወርቅ በላይ የፈለቁ ናቸው። ከዕንቁ /ዳዬመንድ/ በላይ የደመቁ ናቸው። ሀገር፤ ትውልድ፤ ዘመን አዳኞች ናቸው።
ለመሆኑ ዕንባ ዕለታዊ ህይወት በሆነባት እመቤት ኢትዮጵያ ላይ የምርጫ ሞድ ቤት፤ የምግብ ቡፌ ቤት፤ የሂሳብ ስሌት ጥቁር ሰሌዳ ውስጥ መግባት ይኖርበታልን ወይንስ ዕንባን የሚያስታግስ መንፈስን መከብከብ አለበት?  ምርጫው አንድ ነው። ከሊቅ አስከ ደቂቅ የሐገሬ ጉዳይ ያገባኛል፤ „ለሥልጣን አይደለም የምታገለው“ ለሚለው ዜጋ/ድርጅት ሁሉ ፈተናው ይሄው ነው። እራህብ ላይ ያለ ሰው ስለ ዴሞክራሲ ለማደመጥ አቅም የለውም። ሬሳ ታቅፋ ላለች እናት ዴሞክራሴ ምኗ ነው? ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ/ ጠ/ሚርዊ መርጫ ምኗ ነው? አካሏ በሰላም እጦት በራህብ ዝሏል። አይደለም ነገን ዛሬን አታምነውም። ዛሬ የሞተባት እናት እኮ ናት ያለችን። ዋስትና የላትም። መንፈሷ በባይታወርነት ጠውልጓል እና …. አይዞህ/ አይዞሽ የሚለው ነው የሚያስፈልገው/ት/ … „ኢትዮጵዊነት ሱስ ነው“ ለራሱ ለማህበረ ደራጎን የምሽግ ማህበረተኛም መድህኑ ነው። ነገ የወዬ ቀን ናት። የተቆጣ ህዝብ ህግ የለውም። ሲከር ይበጠሳል ሲሞላም ይፈሳል። ስለሆነም ለእኔ ለሥርጉተ ሥላሴ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ በመንፈስ ውስጥ አጥንት ሆኖ የኖረውን ዕጸ በለስ ምጥ ገላጋይ ነው፤ ፈዋሽም ነው። ለኢትዮጵያም አጽናኝ መንፈስ ነው። አደብ ገዝቶ ወደ ራስ ወደ ውስጥ መመልከት ያስፈልጋል። አድናቆቱ ቢቀርበት ሰላሙ ይጠበቅለት።
  • ተመክሮ።

የንደፈ ሃሳብ ተመክሮ እና የመሬት ላይ የተግባር ተመክሮ እኩል መመዘን ከባድ ነው። ንድፈ ሃሳብ ቤቱ አዬር ላይ ነው። መተማመኛውም ሞቅ ያለው ህዝባዊ የበቃኝ ንፋስ በርቀት ነው። ተግባር ደግሞ እልፍኙ መሬት ላይ ነው። መተማማኛውም በቅርቡ ያለው የህዝብ የቁጣ ወላፈን ነው። መሬት ላይ ያለ ሰው ችግሩን ለማድመጥ ከፈቀደ፤ ይሁንታ ከሰጠ የተሻለ አማራጭ ነው። ቅርብም ነው። ጊዜ ይቆጥባል። ብክነትንም ይታደጋል፤ በቀልን መስመር ያስይዛል፤ የእኛ ነገር አፍርሶ መጀመር ስለሆነ በዚህ ሂደት ግን የሚጠቅሙትን ከማይጠቅሙት ለመለዬት በቂ አቅል እና አደብ ይኖራል። አፍርሶ ከዜሮ መጀመርም ይሰናበታል። እርሾ ይኖራል። ሂሳብ እንዲወራረድ የሚያስጠይቅ የውጪ ሐገር ምኞትም በልኩ እንዲራመድ ይሆናል። ምን አልባት ስጋቴ ለእኔ አጋጣሚውን ሌላው ሲያገኝ ደግሞ በራሱ ውስጥ ላሉት ነገሮች እንደ ወያኔ ካነገሠ ከድጡ ወደ ማጡ እንዳይሆን ነው። ጥገትነትን ለሁሉም በእኩልነትና በፍታህዊነት ስለመሆኑ ግን ጊዜ ሰጥቶ ማዬት ከተቻለ አማራጭ መንገድ ነው „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ ግን አሁንም አቅሙን አክበረን ከተነሳን። ድጋፉን ካልሰሰትንለት። የጎደለውን ክፍተት በቅንነት ከመገብነው። መልካም ጉዞዎቹን  ከአደነቅንለት …. በስተቀር እንደ ተለመደው „የዝብሪት ቤት ይሆናል“ ….
በተጫማሪነት ለሙግቴ እንዲረዳኝ … ሁለት ምሳሌዎችን ላንሳ የኢህአፓ ፖለቲከኞች እና የደርግ ፖለቲከኞች በቲወሪ አኩል ናቸው። ርዕዮታቸውም ተመሳሳይ ነው። ተግባር ላይ ግን ኢህአፓ ከህዝቡ ጋር መንግሥት ሆኖ ለመሥራት ዕድሉን ስላላገኘ አቅሙ አልተፈተሸም። ለዚህም ነው እኔ በኢህአፓ ወቀሳ ላይ ብዙም እምልሳተፈው። ተጠያቂ የሚሆንባቸው አምክንዮች ለእኔ ሚዛን አይደፉም። ምክንያቱም መንግሥት የመሆን ዕድሉን አላገኘም እና። መንግሥት አልነበረም። ህይወቱ የጫካና፤ የስደት ነው። ስለሆነም ነው እንደ መንግሥት ሊወቀስ፤ ሊነቀስ አይገባም የሚል ዕድምታ ነው ያለኝ። በመሬት ላይ የተደራጁ ቢሯዊ ተግባራት ላይ ኢህአፓ ዕድለቢስ ነው። የሥልጠና ዕድልም አልነበረውም። አቅሙን ጥቅም ላይ ሊያውልበት የሚችል ማሳ አልነበረውም።  ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋርም ህጋዊ ሆኖ አልሠራም። መንፈሱን አያወቀውም። የውጊያ አውዶች ተመክሮዎች ነው ያሉት። ስለዚህም የሚጎድለው የተመክሮ ንጥረ ነገር አለው ማለት ነው።
እርግጥ የተለዬ ጸጋ ያላቸውን ወገኖች ገጥመውኛል። ዕድሉን ሳያገኙ። አንዲት የኢህአፓ አባል የነበረች አንስት አንድ ጊዜ በአንድ አምክንዮ ዙሪያ የጻፈችውን ደብዳቤ ልካልኝ ሳነበው ድንቅ ነው ያለኝ። ያ አቅም ከህዝብ ጋር ህጋዊ ሆኖ በፓርቲ ህይወት ውስጥ ሲመጡ የሚገኝ ረቂቅ ብቃት ነው። እና እሷ ግን የተለዬ ጸጋ እንዳላት ለማዬት ችያለሁ። ሌሎችም እንደዚህ ጸጋው የተለዬ ያላቸው ሊኖሩ ይችላሉ የሚል ስዕል ሰጥቶኛል። የሆነ ሆኖ መሬትን ለማድመጥ መሬት ላይ መገኘት አትራፊ ነው። ከህዝቡ ጋር ኑሮውን መኖር። ነፍሱን ማድመጥ። ችግሩ ይህን ዕድል ለማግኘት ከሰማይ በላይ እሩቅ ስለሆነ ነው። አሁን ግን ከዛው፤ በዛው ማህበረ ደራጎን ሥር ከወደቀ ነፍስ አንድ መንፈስ ለግልግል ወጥቷል። ይህን እንደ ዕድል ልንቆጥረው ይገባል ባይ ነኝ። እራህብ የነፃነት ከአንገረገበን፤ የህዝብ የሰቆቃ ትንፋሽ ካባከነን፤ ከገረፈንም።
እኔ በሥር – ነቀል ለውጥ ጽኑ አማኝ ነኝ። ፖሊሲው የወያኔ የጣሊያን ነው። ለዚህም ነው ምርጫ በመጣ ቁጥር ተሳትፎ የይሰሙላ ነው፤ የልግጫ ነው፤ የርግጫ ስል የነበርኩት። „ድርድርም“ የሚባለው እንዲሁ። አሁን ግን የተለዬ ነገር ነው የተፈጠረው። ኦሮሚያዊ መንፈሱ ወደ ብሄራዊ ደረጃ ያደገ ውጥን ጅምር ማሳዬቱ እኔ እንደ ሰው ሠራሽ አድርጌ ልቆጥረው አላስቻለኝም። ሌላ ኮተት ካልተሸከመ ሰማያዊ ታምር ነው ለእኔ። በፍጹም አላሰብኩትም። በጣም በጥርጣሬ የተወጠሩ ዕይታዎችን አዳምጫለሁ፤ አንብቤያለሁ። ይገባልም። አመጣጡና አጠባበቁ ያልተገናኙ ስለነበሩ። ግን „ለእግዚአብሄር የሚሳነው የለም።“ በተለይ ለአሰባሳቢ መርሆዎች ከወል ይምጣ ከግል በመንፈሴ ገና ይሆናል ብዬ ተጠራጥሬ አላውቅም። እንደ ወረደ ነው የምቀበለው። ኤዲት አላደርገውም። በጥርጣሬ ስንጥር አልቀርበውም። ቅን መንፈስን የውጤቱን ዕድሜ በሂደት ሚዛን ገምግሜ ነው በቃህኝ የምለው። ጥርጣሬን ምራኝ ማለትን እግዚአብሄርም አይወደውም። ፈጣሪ አምላካችን በእጅጉ ተጣራጣሪነትን ይጸዬፈዋል። ጤናማነትም አይደለም።
  • ጥንቃቄ።

የባህርዳሩ እንኮሸሽሌን በሚመለከት ጥንቃቄ ማድረግ ግን ይገባል። „ኢህአድግ“ የሚባለው ነገር ልብስ ነው። ቆንጆ የተዋበ ልብስ።  በማንኛውም ጊዜ ሊቀደድ የሚችል ቅብ ልብስ። በማንኛውም ጊዜ ሊያረጅ የሚችል የተውሶ ልብስ። በማንኛውም ጊዜ ወልቆ ሊጣል የሚችል የይስሙላ ልብስ። የውጭ ሀገር መንግሥታትን ለማባጨል በቅብ ሥሙ ይጠራ። እኔ ግን አንድም ቀን በጹሑፌ ይሁን በድህረ ገፄ፤ በድህረ ገፄ ይሁን በራዲዮ ፕሮግራሜ ተጠቅሜበት አላውቅም። ሥርጉተን ሥርጉት የሚያደርጋት ልብሱ ሳይሆን ውስጧ ነው። ስለሆነም „ኢህአድግ“ ለእኛ  ያልነበረ ሮቦት ነው። ልብሱ ሲወልቅ ገላው የወያኔ ሃርነት ትግራይ ሀገር፤ ህዝብ፤ አብሮነት፤ ፍቅር፤ ታሪክ፤ ዕሴት፤ ሃይማኖት፤ ትውፊት ገዳይ ማንፌስቶ ነው። የታላቋ ትግራይ ህልመኛ ነው። ይህን ልብ ነው ሱሪያቸውን ግጨው ላይ በአደባባይ – በጠሃይ ያወለቁት የአቶ ገዱ አንዳርጋቸው/ አስቃቸው ካቢኔ የተገጠመለት። ንግግራቸው እራሱ ቀፎ ነበር። መወቀስ የሚጋባውን ግጣሙን ልብ መሆን ሲገባው በድንበር ዘለል ስደት በሚገርፈው ወገናቸው ላይ ነበር የስድቡን ወጨፎ ያሸከሙት። በአሁኑ ስብሰባም ውስጣቸውን ለማዘረፍ ምቹ ናቸው። የአማራ ጉዳይ ምንአቸው ነው? የሉበትም። „አህያውን ሲፈሩ“ እንደሚባለው የጎንደሩ ሥብሰባም ይሄው ነው። ወጥ ዲያብሎሲያዊ ልቦች መረዛቸውን የሚረጩበት፤ ተነቃቂ የነፃነት መንፈሶችን የሚዝሉበት፤ ለሌላ ጥቃት የሚመቻችበት ነው የማህበረ ደራጎን የፈንድሻው ቀን – በጎንደር። ትግራይ ምን መጓዝ ያስፈልገዋል። ጎንደርን በወረራ ይዞት የለ። ደግሞስ ጉሮሮ፤ ቤቱ የራህብ መዳህኒቱ ነው – ጎንደር። የናፈቀውን ሁሉ በሌብነት ዘርፏል። ምን አውቶብስ ያጫጭናል? ለኳስ ጨዋታ የሄዱትን ዓለም ዐቀፉን የፊፋን ህግ ጥሶ ደብድቦል። አስሯል። ለነገሩ ሲስተናገዱ እንጂ ማነን ሲያስተናግዱ። ተዚህ ላይስ አይፈረድም። … ማስተናገድ አልተነኖረበት የት የሚያታወቀውን … ማን ወደ ትግራይ ተሰዶ ያውቅና፤ ፍቅር ከፈንጅ ጭስ አይታፈስም፤ ከንጹህ ጻድቃን ልብ አንጂ።
በነገራችን ላይ ሂደቶች በሙሉ ከማህበረ ደራጎን ዕቅድ ውጪ አይደለም የሚሉ ወገኖች አሉ። በዚህ እስማማለሁ። እኔ እንዲያውም ከስውራኑ የትግራይ ሊቃውንታት የፈለቅ አዘናጊ ትልም መሆኑን ለአፍታም ቸል አልለውም። ነገር ግን አንድ የቀደመ አምክንዮ ነበር። የኦሮሞ ቴሌቪዥን ባህርዳር ሄዶ የሠራው ቅን ተግባር ነበር። ተነሳሽነቱን ልባዊ የሚያደርገውም ይህም ነው። በዚህ ትልም ውስጥ ወያኔ ማትረፍ ከቻለ ምስላቸው የተጎለተውን ጠ/ሚ ሐይለማርያም ደስላኝንም ቁጭ ብለው እንዲመለከቱ የመንፈስ ቅጣት መሰናዶም ሊሆንም ይችላል ብዬ አስባለሁ። በራሳቸው እራሳቸውን ገለል እንዲያደርጉ ጫና ለመፍጠር፤ ባይሆንም በሂደት ከዚህ የታላቋ ትግራይ ህልመኝነት ማስቀጠያ ጉዞ አመቺ ባይሆንም ይሻላል ላሉት በትረ ሥልጣኑን ለመባረክ። ነገር ግን በሚገርም ሁኔታ ባልታሰበ አኳኋውን ግን አፈንግጦ የወጣ ቅዱሰ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው።“ ይህ በአቶ ገዱ መንፈስ ውስጥ አይደለም „ኢትዮጵያዊነት“  „አማራነት“ እንኳን ብንኙ የለም። አማራ ተቆርቋሪ የለውም በፍጹም። በሌላ በኩል የኦሮሚያ ፕሬዚዳን አቶ ለማ መግርሳ ውጪ የሚገኘውን ወገናቸውን በመንፈሳቸው ውስጥ አስቀምጠው በአክብሮት ሲያመሰግኑ፤ በማህበረ ደራጎን ልብ የተገጠመላቸው አቶ ገዱ አንዳርጋቸው/ አስቃቸው ደግሞ ወገናቸውን በደንበር ዘለልነት ወረፉ … ሌላም በቀጣይ የምናዬው ምንጣፍነት ይኖራል።
  • ወጣትነት እና አቅሙ።

ወጣትነት የአቅም ጥሪት ነው። ወጣት በዬትኛውም ዘመን፤ በዬትኛውም ሐገር የለወጥ ሐዋርያ ነው። ተሎ ይቀበላል አዲስ ሃሳብ። አዲስ ሃሳብም አፍላቂም ነው። ወጣትነት ትጉህነት ነው። ወጣትነት ታታሪነት ነው። ወጣትነት ሥልጣኔም ነው፤ ማለት ዘመንን እንደ ዘመኑ የመተርጎም አቅም ወጣት አለው። ወጣትነት ጉልበት ነው። አሁን አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ ከ65% ያለነሰ ወጣት ነው ይባላል። ለዚህ ሥነ – ልቦና ቅርብነትም ደልዳለ ያለ ኮረቻ ነው አጋጣሚውን ወያኔ አዝብጦ ካልጋለበው፤ ወይንም የአቶ ለማ መገርሳ ካቢኔ ለወያኔ መንፈስ ካልተንበረከከ፤ ይህን የመሰለ አዲስ ምዕራፍ ቀበቶውን ፈትቶ ለሄሮድስ መለስ እርቃኑን ለቀረ ሙት መንፈስ ካልሸለመ። ወይንም ከዚህ መንፈስ ሸሽቶ የራሱን የብሄር መወጣጫ እንደ ታቦት ካልከበከበ፤ ሁሉም በር ክፍት ነው „ለኦሮምያ ክልል“ ፕሬዚዳንት ለአቶ ለማ መገርሳ። ምርጫው የሳቸው ነው። ጊዜ ታሪክ ይሠራል። ኢትዮጵያን ማዳን ወይንም መግደል። ትውልዱን መታደግ ወይንም ለተጨማሪ ፍልሰት ቦንብ መሆን። አማራን አንበርክኮ መግዛት ወይንም በፍጹም ተቆርቋሪነት አክብሮ እኩል ተጠቃሚ ለማድረግ ጠበቃ መሆን። መፍትሄ መሆን ወይንም የበለጠ ችግር አምራች መሆን።
  • „አጀንዳ ተቀማ።“

ይህ ሰፊ የመንፈስ ሽፋን ያገኜ ጉዳይ ነው። የህዝቡን አጀንዳ ለመቀማት ማነው ያላቀደው? ማነውስ ያላለመው? ማነውስ ያልማሰነው? ማነውስ ለራሱ ማንፌስቶ ጥንግ ድርብ እንዲሆን ያልከጀለው? ማነውስ ይህን ሞገዳማ የህዝብ ከመከራው የበቀለ የበቃኝ አቅም መሸጋገሪያ ለማድረግ ያልቋመጠው? እከሌ ተከሌ ሳይባል – ሁሉም። አንድ ሰሞን እማ ቋቅ አስኪል ድርስ ድርጅት ምስረታ በደቦ አና ብሎ ነበር። ስለዚህ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ“ ነው ይህን አቅም ቢመኝ ከሁሉ ህልመኛ እንደ አንዱ ነው ሊታይ የሚገባው። ዜጋ ነዋ ኢትዮጵያዊ። እንዲያውም ቅርብ ነው – ለስሜቱ ሐገር ቤት ስላለ። በዛ ላይ እንደ ሌሎች የነፃነት ብሄራዊ ይሁኑ የጎሳ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ህጋዊ የሆነ መዋቅራዊ የጫና ችግር የለበትም። አንጻራዊ ነፃነት አለው። አንድ „ክልል“ ሊኖረው የሚገባ ማናቸውም፤ የመንግሥት፤ የመንፈስ ይሁን የመዋዕለ ንዋይ እንዲሁም የመዋቅር ሙሉዑ አቅም አለው። ስለሆነም ባለው ላይ ተጫማሪ አቅም ደግሞ ተፈጠረለት፤ እግዚአብሄር ያቀበለው መሰላል „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ አሰኘው። ይህ በደቂቃዎች መጠነ ሰፊ የመንፈስ ሃብታትን አፍርቶለታል። ከሌሎች የአዬር ላይ ዘመን ጠገብ ፕሮፖጋናዳዎች በላይ ባለጥሪት ሆኗል ዛሬ የነገን መተንበይ የሚቻለው በተግባሩ ልክ ይሆናል። ከዬትኛውም የፖለቲካ ልሂቃን ያልተሰማ በር ከፋች ቅዱስ ስንኝ ነው „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው።“ ይህ ስንኝ „ከቅንጅት መንፈስ“ በላይም ነው ለእኔ። „ቅንጅት መንፈስ ነው“ የአንድን እጅግ ለጋ፤ በቅጡም ያልተዋሃደ ድርጅት ማንፌስቶ መሠረት አድርጎ ነው የተነሳው። ይህ ግን ሞት የተፈረደበትን ተምሳሌያዊ ማንነትን ትንሳዔ ማዕከል አድርጎ ነው የተነሳው። ኢትዮጵያ ፍርሰት ከሚያሰጋቸው ሐገሮች ተርታ ነው ያለችው እያሉ ነጮቹ ይዘግባሉ። ስለዚህ ለእኔ ያለውን የበቃኝ ማህበራዊ አቅም  „ለኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ አቅም ቢሆን የሚያስከፋ አይሆንም። ህዝባዊ ንቅናቄው በቅርብም ሆኖ የሚመራው ወጥ ባለቤት የለውም።  „ኢትዮጵያዊነት ሱስ“ ነው ለእኔ ፖሊሲ ነው። በ40 ዓመት ውስጥ በጦርነት ቀጣና ሲባክን ለኖረው „ኢትዮጵያዊነት“ ቅኝ ግዛት ለተፈረደበት „ኢትዮጵያዊነት“ በጎሪጥ ለሚታዬው „ኢትዮጵያዊነት“ ገዢ መሬት ነው። የብሥራት መባቻ ነው። አሁንም እኩል መስዋዕትነት እዬገበረ ላለው የአማራ ተጋድሎ ግን የሚመጥን አቅም አማራዊ አቅም እና ክህሎት በፍጹም ሁኔታ ምድረ ባዳ ነው። በዚህ እኔ ታላቅ ስጋት አለኝ። የዚህ ተጋድሎን በቅርብ የሆነ ሁነኛ አቅም ያለው መንፈስ የለም ካልተመጣጠነ ጉብጠት በጉጠት ይሆናል።
  • ንጽጽር።

በሁለቱም መካካል ትልቅ ልዩነት አለ። በአቶ ገዱ አንዳርጋቸው/አስጠቃቸው/ እና በአቶ ለማ መግረሳ። ልዩነቱን በጨረፍታ ….
·         የመሪነት አቅም፤ ዲፕሎማሲያዊ የመሆን ችሎታ ክህሎታዊ ነው፤
·         የአምክንዮ አቅም ሙሉዑነት መንፈስን ሊገዛና ሊያስተዳድር የመቻል አዎንታዊነቱ ተጋባቢ ነው፤
·         ኢትዮጵያን አክብሮ በመነሳት ተመስጦዖ ልዩ ማዕዛና ጠረን ያለው ሳቢ ነው፤
·         በርቀት የማሰብ አቅም ጉልበቱ ትውልድ ላይ ለመነሳት ፈቃዱ ትሁት ነው፤ „ኦሮሞነትን“ ብብልጫ ካላስቀደመ።
·         ህዝብን እንደ ህዝብ የመቀበል የቅንነት አቅም በተወሰነ ደረጃ መታዬቱ፤ ውጪም ሐገርም የሚኖረውን ወገን የራስ አካል አድርጎ የእኔ ብሎ አቅርቦ የመመልከቱ ብቃት አሁን ባለው ዕድሜው አበረታች ነው፤
·         ጠላትን ያለማበራከት ልዩ ስልት ወይንም ሥነ – ጥበቡ ብልህነትን የጎረሰ ነው፤ የውስጥ አጀንዳን ቅደመኝ ካለለ።
·         ከህዝብ የችግር ልብ ለመነሳት የታዬው ተነሳሽነት መልካም ነው ሉሁሉም ኢትዮጵያዊ ተጎጂዎች እኩልነትን በነገው ከቀለበ፤
·         የመንፈስ ጥገኝነትን አለመፍቀድ፤ በሚያምኑበት መንፈስ ውስጥ የመቆዬት፤ በተቀበሉት መንፈስ ላይ የመርጋት አቅሙ ስንኞቹ ተወራራሽ እና ማግስታዊነትን ያነገሱ መሆናቸው „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው!“
·         በራስ የመተማመን መንፈሱ ጥሩ ደረጃ ላይ ነው ያለው።
·         ያጣጣለው፤ ወይንም ከግምት ውጪ ያደረገው፤ ወይንም የተኮፈሰበት አንድም መንፈስ የለም።

በእነዚህ መጠነኛ መስፈርቶች በዚያች ባዬናት የቆይታ ጊዜ ውስጥ ማዳመጥ ይቻላል። ማለት የእኔ ካልነው የኢትዮጵያን ችግር።በቆዬንባቸው የሴራ ፖለቲካ ውጥንቅጥ ትርምስ ውስጥም ይህን የአቶ ለማ መገርሳ ላይ የታዬው አቅም ለንጽጽር ከሌሎች ጊዜያቶች ጋር  ለማቀራረብ ይቸግራል። በብልጫ ነው የማዬው እኔ … ጊዜውና አጋጣሚውን ካገኙ የተሻለ የሽግግር ዘመናዊ ድርሻ ሊያበረክቱ ይችሉ ይሁናል። አሁንም „ታላቋን ኦሮምያን“ ብቻን አጀንዳቸው ካለደረጉ። ይህ የጣሊያን ምሽግ ነው የጥፋት ሁሉ አንጎሉ። ለነገሩ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ እራሱ ቦታው ደግሞ የሚሰጠው አቅምና አቅል ይኖራዋል። መቼም ሰው ድንጋይ ካልሆነ እያንዳንዷ የመሪነት ደቂቃ ዩንቨርስቲ ናት … ከሁሉ በላይ ብረት መዝጊያ የሆኑ አቅሞች በአጠገባቸው አሉ። በባዶ ላይ የሰመጠው አማራው ብቻ ነው። አሁንም ትክሻውን ለሌላ የጥፋት ዘመን እንዳይሆንበት ስጋቴ እጅግ ሰፊ ነው። ባለቤት የለውም። በዚህም ላይ ነው 40 ዓመት የተሠራበት። አማራው ደግሞ 40 ዓመት ተኝቶ መኖሩ ላይገርም አሁንም ቫልዬም እያሰኘው ነው …

„ከዛው ስለምን አማራን አልሰበሰቡም፤ ምን ጎጃም መሄድ አስፈለጋቸው ….“
„ኦሮምያ ውስጥ ያሉትን አማራዎች መሰብሰብ ሲችሉ ባህርዳር ስለምን አስጓዛቸው“ የሚል ጹሑፍም፤ ውይይትም አዳምጫለሁ። ባልነበሩበት ሕይወት ውስጥ ለመኖር ሰው ሲፈቅድ ሊሆን የሚገባውን ነው የተደረገው። ልታስተውሉት ያልፈቀዳችሁት አምክንዮ ይሄው ነው። ኦሮምያንማ ያውቋታል። ያለቸው ነገር አላቸው። ሰዉም ያው ሰው ነው። አፈሩም ያው አፈር ነው። ወንዙም ያው ወንዝ ነው። ያላዩት መንፈስን ናፋቂ ናቸው ወጣቱ ፖለቲከኛ። ባላቸው ላይ መጨመር ፈለጉ። ምን አልባት ሌላም እርስት ነገር – የመንፈስ። በቅንነት ሲታይ ግን ከሁሉ በላይ „ፊት/ገጽ“ ብዙ ነገር ይገልጣል። „ፊት/ ገጽ“ ውስጥን ያሳያል። „ፊት/ ገጽ“ ውስጥን ይተረጉማል። „ፊት/ ገጽ“ የነፍስ ጉባኤ አናባቢ መስታውት ነው። „የፊት/ የገጽ“ አገላለጾች በራሳቸው የመፍቻ መዝገበ ቃላት ናቸው። „ፊት/ገጽ“ የስሜት ካታሎግ ነው። ሰው ሳይናገር በማዬት ብቻ የአንድን ሰው ወስጡን ፎቶ ማንሳት ይቻላል። ፊት ለፊት በመገናኘት የሚገኘውም ፍቅር አልፋና ኦሜጋ ነው። „ነገር በዓይን ይገባል“ እኔ ዬክብርት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳ አድናቂ የሆንኩት ካዬኋዋት በኋላ ነበር። የእሷ ነገር እንደ እብድ ነው የሚያደርገኝ። አሜሪካን ሀገር እህቴ እኔን ልትጠይቅ ስትመጣ ፎቶዋ ነበር ከቤቴ በፍሬም ሆኖ። እና ቪዲዮ ስትቀርጽ „እሳት እንዳይነድብኝ ከብርቴ ልጀምር“ ትል ነበር። እህቴ የበዛ ሃይማኖተኛ ናት። በህይወቷ ሰው አስቀይማ አታውቅም። በምትኖርበት ሀገር „መላዕክ“ ነው የምትባለው/ ወንድሜም ከመላዕክ ጋር ነው የምኖረው ይለኝ ነበረው። ግን ፖለቲካ ፈጽሞ አትወድም። ይህን ያነሳሁት ማዬት፤ በአካል መገናኘት ተጽዕኖው ከእኔ አልፎ የፖለቲካ ጉዳዮች ለማያገባት እህቴም ለብርቴ ያለው የፍቅር አክብሮት ተጋባባት። ቅድሚያ ለእሷ ፎቶ ነበር የምትሰጠው። እንዲያው ከነፍሬሙ አውርዳ አይታዋለች።

ስለሆነም „የኦሮሞ ካድሬዎችም“ በሏቸው ምን፤ ባሻችሁ ሥያሜ ጥሯቸው እኔ ደሜና ሥጋዬ ነው የምላቸው ይህን ያክል በአንድ ሐገር እዬኖሩ የተሠራውን የሄሮድስ መለስ ዜናዊ አናገናኝ ወንዝ ተሻግረው ለመሄድ ማሰባቸው በራሱ ከድል በላይ ነው። አይደለም እነኛ አዛውንታት የሐገር አድባሮች አውቶብሱ እራሱ ያን አይጠገቤ የጎጃም ለጥ ያለ የጤፍ አማልማሎ እያዬ ሲሄድ፤ ያ ነፍስን በፍሰሃ በሚያዘናክተው ውብ አዬር ሲመጡ፤ ያን የማንኩሳ ኮክ ሲገምጥ፤ ያን የጎጃምን ሙዝ ሲላጥ፤ ያ ማር ጠገብ ከአፍ ላይ የሚቀረው የ6ወር ጠላ ሲጎነጩት፤ ያ የታሪክ ዕንብርት የአባይ በርሃን መጪ ሲባልበት የሚፈጥረው ስሜት የጥበብ፤ የሃይማኖት ያህል ጉልበት አለው። መጽሐፍ ያጻፍል። እዛው እያሉ አማራዎችን ቢያነጋግሩ ከተለመደው ተግባር ውጪ ዕዝነ ልቦናን ከእነሱ አልፎ እኛንም እንዲህ የውስጥ ሰላማችን ሊያስጠብቅ፤ ሊመስጥም አይችልም ነበር። ማለት አይተው ከሄዱ በኋዋላ እኔ እምጠብቃቸው ሰፊ ነፍስ ያላቸው የተግባር ማሳዎች አሉ። እነኛ „ኦሮምያ“ በሚባለው የሚኖሩ „መጤ“ የሚባሉት አገር አልባ አማራዎች/ አማርኛ ተናጋሪዎች፤ መጠጊያ ቁራጭ እራፊ ነገር ያልነበራቸው ያላቸውን ረቂቅ ተፈጥሯዊ ሙሉዑ አቅም እንዲመሰጡበት አቅል ሰጥቷል።

ሰንቀው የሚመለሱት ቀና የመንፈስ ሃብት ለክርስትና አማንያን እዬሩሳሌም፤ ለእስልምና እምነት ተካታዮች የመካ መዲና ያህል ነው። በፍቅር ቆርበው ነው የሚመለሱት። ልብሳቸው እራሱ ሸምቶት የሚሄደው ጠረኑ የተለዬ ነው። አርሲን እኔ ስለቅ ከፍቅር ዕንባ ጋር የተሰጡኝ ውድ እቃዎች ነበሩ፤ የወተት ማለቢያ እና የጭኮ መያዣ /ቆሬ/ ነበር። ተጎንብሳችሁ ስታሸቱት ማጠንቱ፤ የተጠለፈበት ጥበቡ ጠረኑ የተለዬ ነው። ስንድዱ እራሱ የጠረኑ መስህብ ይማስጥ ነበር። እራሱ ስንዴው የአርሲ የተለዬ ነው። 25 ኪሎ ስንዴ አርሲ እያለሁ ለእናቴ ልኬላታለሁ። እንደኛ ዱቄት ልም አይሆንም። ነጭም አይደለም የዱቄቱ ቀለሙ። መተያዬት ልዩ ነው። ትርፉ  አይታይም፤ አይዳሰስም ፍጹም ረቂቅ ነው። እኔም ሄጄ ስላዬሁ ነው፤ በዬአጋጣሚው በሚነሱ ጉዳዮች ላይ ደፍሬ እምጽፈው። ለማንኛውም ዕይታዎች ሲደመሩ ከዛው ያሉ የአማራ ተወላጆችን ማነጋገር እና ወገኖቻቸው በትውልድ ቦታቸው ምን እንደሚመስሉ ማዬት ልዩነቱን ለማዬት የተጨነቅንበት፤ የቤት ሥራችን የሠራንበት፤ የእኔ ብለን አትኩሮት መሰጠተችን ምን ያህል እንደሆነ ያሳያል። በእውነቱ ስስ ሆኖ ከስቶ ነው ያገኘሁት። እንደ ተራ የፕሮፓጋንድ ብጫቂ እንጂ እንደ መንፈሳዊ የፍቅር ጉዞ ሆኖ አልታዬም። እነዚህ ሰዎች እኮ በሄሮድስ መለስ ዜናዊ ፈርዖናዊ መንፈስ በፍጹም ሁኔታ እንዳይገናኙ የበርሊን ግንብ የተገነባባቸው እኮ ናቸው። እንደ ጠላት እንዲተያዩ እኮ ነው ቦንብ የተጠመደባቸው። 40 ዓመት ሙሉ በልዩነት ጡብ የተሠራበት፤ በትጋት፤ በጥንቃቄ፤ በቋሚነት የታመቀ ድፍን የጥላቻ ባሩድ አለሎ የተዋቀረበት ነበር እኮ። ያውቃሉ አቶ መለስ የሁለቱ ህዝቦች የደም ትስስር አቅም ሆኖ ከወጣ ኢትዮጵያ አይደለም ለራሷ ለአፍሪካም የሚያስመካ የብቃት/ የአቅም ጉልላት እንደሚኖራት። ስለዚህም ነው አቶ መለስ ሰው ሰራሽ „አናገናኝ ወንዝን“ ድልድይ አልቦሽ አድርገው ቆፍረው የፈጠሩት … ከሞት ቢነሱ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነውን“ ቢሰሙ ጨርቃቸውን ጥለው ያብዳሉ፤ ወይንም ራሳቸውን ያንቃሉ/ ያንጠለጥላሉ …. ይሄ ነው እኛ ያልገባን የተዋህዶ ሚስጥረ አዕማድ። ሌላው ያ በመስቃ ሲሳቀቅ የነበረው አማራ/ አማርኛ ተናጋሪ ወገናቸው ኑሮው እና ህይወቱን በቀዬው ተገኝቶ ማዬት የተለዬ አክብሮትን ያመነጫል። ውስጥን ይገራል። ውስጥን በጸጸት ያነዳል። የራስህን አካልህን ባይታዋር አድርገህ የቆዬህበት መንፈስ እግር እሳት ነው የሚሆነው፤ ከጉዞው በኋላ። ለእኔ በትረ መፍትሄ ነው። በተለይ ለዛ ምስኪን አማራ እኛ ለማንደርስለት። አይዞህ ባይ ለሌለው ተገላይ/ ተጨፍጫፊ/ተወቃሽ ቅን እና ፍጹም ደግ ህዝብ ጉዞው ተጽዕኖ ፈጣሪ ይሆናል ብዬ አስባለሁ። እርግጥ ትርፉን በትርፍ ማመጣጠን የሚችል ብልጥነት ሳይሆን ብልህነት ከተገኘ።

  • ጉዞ።

ህይወት ጉዞ ነው። ፍቅርም ጉዞ ነው። ነገም ጉዞ ነው። ትውልድም ጉዞ ነው። ራዕይም ጉዞ ነው። ምኞትም ጉዞ ነው። ዘመንም ጉዞ ነው። በጉዞ ማዕቀፍ ውስጥ ቅንነት ከላ ትርፋማነት ይዛቃል። ይልቅስ …. አዲስ የማይሆነው የወያኔ ሃርነት ትግራይ ማንፌስቶ ልብ የተገጠመለት የአቶ ገዱ አንድአርጋቸው /በናቸው/ አስቃቸው/ ካብኔ እና የአባ ጨጓሬውየአቶ አባይ ወልዱ የፈንድሻ ጨዋታ ነው። መሬቱን ለጉልበት ሥራ እዬመጡ አሳምረው ያውቁታል – ትግሬዎቹ። መጎምጀቱና ስስቱ ነው ዘራፋውንም እንዳያቆም ያደረገው። ይልቅ ማህበረ ፈርዖን የጎንደርን ማህበራዊ ሰላም ይመልሱለት። በግፍ ያሰሯቸውንም ይፍቷቸው። መሬቱንም ይመልሱ። „የሰው ወርቅ አያደምቅም እምና“ … እዛው ከርዕሰ መዲናዋ ሁለተኛ ከተማ ከሆነችው ደማቋ ትግራይ ላይ ሆነው ይህን መልካም ነገር ቢጀምሩ በቂ ነው። ትውልድን ያተርፋል። የእነሱ ጉዞ ለወረራ ነው። መቼስ ዘርፈው፤ ሰርቀው፤ ዋሽተው አይጠግቡም። ጉዞው ለመንፈስ ወረራ፤ ለቅርስ ወረራ ነው። በዕውነቱ ትርፍ የለውም ከኪሳራ በስተቀር። „ገድሎ እግዚአብሄር ይማርህ“ ጥጋባቸውን እዛው ከንግሥ ከተማቸው ቢያስታግስቱ ነው ልጅ የሚያወጣው ለነተጋሩ። ምናቸው ይናፈቃል? ፍቅሩ እኮ ብን ብሎ ደርቋል። ጠፍ መሬት ነው። ግፉ ከሚቻለው በላይ ነው … ይልቅ የደም ጸዋ ለጤናችን ከመባባል ግዞት ውስጥ ያሉትን የወልቃይት፤ የጠገዴ፤ የራያን ህዝቦች ወላዊ የጥቃት ሰለባነት ያቁሙ።
  • ዓይን ማረፊያነት።

ለዚህ የታደለ ነው አይዋ አማራ። አማራው የዓይን ማረፊያ ነው። አቅሙ ለሎሌነት አገልግሎት እንዲውል መታጨት።ይህን አማራው ልብ ሊለው ይገባል። ሁሉም ጎብጦ እንዲቀር ነው የሚሻው። አሁን በአቶ ለማ ካቢኔ ውስጥ እሳቸውን የሚተካ ሙሉ ሃይል አለ። አያድርገውና አንድ ነገር ቢፈጠር። እጅግ ተመስጧቸው የሚስብና እና የሚማርከው ነገር ተተኪዎቹ እንደ እርሳቸው ወጣቶች መሆናቸው ናቸው። ሁለተኛ ሙሉዑ አቅሙ መሬት ያያዘ ነው። ሦስተኛ መዳኛውን ብልሃት በህሊና አቅማቸው ልቅና አግኝተውታል። አራተኛው ተተኪዎች ተሰልፈዋል ልክ እንደ ጀርመን የእግር ኳስ አደረጃጃት ተተኪ በሽ ነው። በዓይነት። ብዙ ያልተነገረላቸው፤ ብዙም በአድናቆታችን ውስጥ ያልከተብናቸው አሁን አቶ አብይ የመንፈስ እርጋታቸው እራሱ ትውልድ ይገነባል። ለዛ አላቸው። የውስጥ ቀላማቸው ይመስጣል – ሌላውን ትቼ። በዛች በተመጠነች ስንኝ ውስጥ ቁም ነገር ሰፍኖበታል። የአምክንዮው ጽኑ ድሃ ጠ/ሚር ሐይለማርያም ደሳለኝ ታዲያ እንዴት አድርገው ነው እነዚህን ወጣት የተረጋጉ ሊሂቃን ሊመሩ የሚችሉት። ፈጽሞ አይገናኙም። ኮፒና ኦርጅናል።
ሌላው ብዙ ጥረት ተደርጎበት መክኖ ዬሚታዬው በብሄራዊ የመሪነት አቅም የትግራይ ጉዳይ ነው። ልዑላኑ ሾልከዋል። ግን ሌላ ምንጣፍ አላቸው። በዬትኛውም የሙያ ዘርፍ ዕውቀትን መሰረት ያደረገ ንጣፍ እነሱው ናቸው። 26 ዓመት ዕድሉን ያለተቀናቃኝ ዋኝተውበታል። ያልተደፈረው የሥነ – ሥዕል ዓወደ ምህረት ብቻ ነው። የሥነ – ስዕል ጸጋ በግብር ይውጣ አሸሼ ገዳሜ ስለማይደፈር። ጸጋው ለተሰጣቸው ጥቂት ምሩቃን ብቻ ነው። ከሥነ – ጥበባት ዘርፍ ለታላቋ ትግራይ ራዕይ አጋፋሪነት መረጋገጫ ያልሆነ አለ ቢባል ሥነ – ሥዕል ብቻ ነው። ከዚህ ሁኔታ ጋር ኢትዮጵያዊነቱን መስጥሮ የያዘው የተከበረው የደቡብ ህዝቦች እራሱ አማርኛ ቋንቋን ስለተቀበሉ፤ ደህና ሰዎችም ከላይ ስላሏቸው ብዙም በጥሰት የሚሰምጡ አይሆኑም። ሌሎቹ ወያኔ ክልል ባላቸው አዲሶቹ አፋር፤ ጋንቤላ ቤንሻጉል፤ እንደ አቅማቸው የራሳቸውን ሰው ያጣሉ የሚል ዕሳቤ የለኝም። ከአማራው በተሻለ ለእነሱ በሩ ክፍት እና ልዩ አትኩሮት 26 ዓመት ሙሉ ነበር። ሁሎችም በተለያዩ የሙያ ዘርፎች በዕውቀት ላይ የተመሠረተ የተመጣጠነ አቅም ይኖራቸዋል ብዬ አስባለሁ … የጉራጌ ብሄረስብ ግን ጸጋው በሆነው የኤኮኖሚ ዘርፍ እንኳን ተላይ ነው። ቀን ያልወጣለት ማህበረሰብ ነው – ጉራጌው። ብዙም አናተኩርበትም እንጂ የመሥራት ተነሳሽነቱ እንዲቀበር የተበዬነበት የተገፋ ህዝብ ነው።
  • የተደፈጠጠው/ የተጣሰው።

ባለፈው የወሎ ወጣቶች ጣናን ለመታደግ ሲሄዱ እግረ መንገዳቸውን ወደ ጎንደር ጎራ ብለው ነበር። ይገርማል። ሲገናኙ የነበረውን የውስጥ ስሜት ሲገልጹ የሚገርም ነበር „ተለያይቶ የተገናኘ ቤተሰብ ሲገናኝ ነበር“ ነው ያሉት። አማራ ሥሙብቻ ነው ያለው። እንኳንስ ከሌላው ወገኑ ጋር ሊገናኝ ቀርቶ ከራሱ ከአማራው ጋር እንኳን እንዳይገናኝ የተሴረው ሴራ እጅግ ጥልቅ ነው። ይህንን ጥቃት ለመቋቋም የሚችል ብልህ ዬሥነ – ልቦና አቅምን ነው አማራው አምጦ፤ ተመጣጣኝ አድርጎ የማውጣት ተከታታይ ተግባር መከወን ያለበት። ሙሁሩ፤ ሊቁ፤ የጥበብ ሰው። የራስን የቤት ሥራ መሥራት ይገባል፤ በሌላ እሰጣ ገባ ጉዳዮች ላይ ተጠዬቅ ከማለት … ጥቃቱ ከጎረበጠ፤ ነገም እንዲህ አሮ እንዳይቀጥል ልብ ገዝቶ ጠንክሮ መውጣት። ከዚህ በመለስ፤ ከዚያ በመለስ ሳይባል አቅምን ቀጥ አድርጎ ሊመራ የሚችል ወጥ አማራዊ የሥን – ልቦና አቅምን አቅል ሰጥቶ መገንባት። ተጋድሎው መክኗል የሚሉ ሁሉ እኮ አሉ።

አዎን! የተጣሰው አማራ ነው። የተጨፈለቀው አማራ ነው። በመጀመሪያ ነገር አማራ ለቁልፍ ቦታ አይታጭም። አሁን ባለፈው ዓመት አዲስ ሚኒስተሮች ሲሾሙ ከኦሮሞ 9 ሚኒሰተሮች ዕድሉ ሲሰጣቸው አንደስም እንኳ አማራ ሚ/ር ሆኖ አልተሾመም። የተናቀ ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ ማዕቀፍ ውስጥ የተሰረዘ ነው – አማራው። የጎንደሩ ጉባኤ የፈንድሻ ሞዴል ትዕይንት ይህን ከግንዛቤ ማስገባት ይኖርበታል። ምን ያህል በሁሉም ዘርፍ ከካርታ ውጪ እንደሆነ አማራው ከልቡ ሆኖ ሊታደምበት ይገባል። ውጪ ሐገርም ይሄው ነው። የሆነ ሆኖ የአቶ ገዱ ካቢኔ ሁለመናው አማራዊ አይደለም። መንፈሱ ሙት ነው። ተተኪ ማውጣትም አልቻለም። ላውጣ ቢልም አይችልም የሴራው ቸረቸራ አቶ በረከት ስሞዖን ምን ሆነ እና ተልዕኳቸው። ተግባሩ ላይ አቅም የሌላቸው ሽባዎች ናቸው ሁሉም ቦታ በተተኪነት ላይ ያሉት፤ ወይንም የነገሥታቱ ዘር፤ ሌላ ቦታ ይህን ያህል ጥሰት ቀርቶ የሃሳብ ድፍረት እንኳን የለም። እርቃኑን የቆመ የግራር እሾህ ነው የአቶ ገዱ አንዳርጋቸው/ አስቃቸው ካቢኔ። ለምንም ቦታ እጮኛ ሊሆን የማይችል ደመ-ነፍስ። በዬትም ቦታና ሁኔታ የመንፈስ አቅም ለአማራው ጥግ የለውም። ወና ምደረ በዳ ላይ ያለ ነው – አማራው። የትም ቦታ ውጪም። በምንም ሁኔታ አቅም ያለው አማራ/አቅም ያላት አማራ የጦር አውድማ ነው/ ናት። ቃጠሎው ነዶ አናቱ ላይ አናቷ ላይ አመድ የሚሆንበት/ የሚሆንባት። ስለሆነም አሁን ባለው የሃይል ሚዛን ውስጥ ደመ ነፍሱን ያለው የአቶ ገዱ አንዳርጋቸው/ እስቃቸው የሙት መንፈስ ግዑዝ ካቢኔ ከቁጥር የሚገባ አይደለም፤ አጀንዳችንም ሊሆን አይችልም። አገልግሎቱ ልቡን ለገጠመለት ለወያኔ ሃርነት ትግራይ ጸረ አማራ ፖሊሲ ነው። አማራ ከሥሩ መድረቅ አለበት ከነትውፊቱ፤ ከነዕሴቱ ነው የሴራው ድር። ከትናንት በላይ ዛሬ እንኳን ሴራውን ለማድመጥ ፈቃዱ የለም በአማራ ሊቃናት።

እኔ አብክሬ መግለጽ እምሻው ለአቶ ለማ መገርሳ ካቢኔ አሁን ባለው ሁኔታ አብሶ በእጃቸው ባለው ካቢኔ ውስጥ በወያኔ የሴራ ፖለቲካ በበቀል የተከተከተውን፤ በመከራ የዳሸቀውን የአማራን ህዝብ/ አማርኛ ተናጋሪውን ከጥቃት መከላከል፤ ከብክቦ መያዝ፤ የኑሮ ዋስትን መስጠት አዳዲስ ወጣቶችን ደግፎ የማውጣት፤ በእድሎች ላይ እኩል ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ሁኔታ ማመቻቸት ይኖርበታል። በተለይ በባይታወርነት የተቀጠቀጠበት ዘመኑ ሊከትምልት ይገባል። እንደ ራሱ ሆኖ እንዲኖርም ይለፍ ሊሰጠው ይገባል። የዚህ መግለጫ የሆኑ ዕሳቤዎችን እንደራሱ አድርጎ ለመጓዝ ነፃነታቸው ሊጠበቅላቸው ይገባል። አማራ ውስጥ ተወለደው አድገው በኢትዮጵያ ም/ጠ ሚር የሆኑት እኮ ኦሮሞው አቶ ደመቀ መኮነን ናቸው። አማራ ግን አይደለም ከዚህ ደረጃ ለአንድ ተራ ቦታ እንኳን ፈጽሞ ቦታ ያልነበረው በሞቱ ውስጥ እዬገበረ የኖረ እጅግ ጭቁን ነው አማራው/ አማርኛ ተናጋሪው። የማከብረዎት አቶ ለማ መገርሳ ይህ ፖለቲከኝነትን አይጠይቅም ሰብዕዊነትን እንጂ።
የወያኔ የጥቃት ስልት ዘርፈ ብዙ ነው። ወያኔ አማራ „ክልል“ ብሎ በሰዬመው በወል አይደለም በዬቀኑ አማራን ነጥሎ ገድሎ ጫካ ውስጥ ይጥላል። በሃኪም ቤት ያለው የአያያዝ ሁኔታም ሌላ ጉድ ነው፤ በተዛባ የመዳህኒት አጠቃቃም የሚያልቀው ህዝብ።  ከአማራ „ክልል“ ውጪ ያሉት አማራዎችን ብቻ ሳይሆን አማርኛ ቋንቋም እንዲጠፋ ስለሚፈለግ አማርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎችም ሰለባዎች ናቸው። የሚላከከውም በኦነግ ነው። ይህ የታክቲክና የስትራቴጂ አማራን በሁሉም ዘርፍ ሰቅዞ ቀስ እያደረጉ ማጥፋት ክህነቱ ነው ለወያኔ። ለዚህም ነው አማርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎችን ዛሬ የጨመርኩት። አማርኛ ቋንቋም በጠላትነት የተፈረጀ ነው። ሊያሸንፈው ያልቻለ ጉልበታም ማንነት ያለው ነው።
የሆነ ሆኖ የአቶ ለማ መገርሳ ካቢኔ ለእነዚህ የጥቃት ሰለባ ለሆኑት ወገኖቻቸው እኩልነትን መቀለብ፤ አይዟችሁን መቀለብ፤ አለንላችሁን ማጠጣት፤ ከ26 ዓመት በኋላ ፍትህን በእኩልነት እንዲያዮት ካለስጋት፤ ካለአድሎ እንዲኖሩ፤ የውስጥ ሰላማቸው እንዲጠበቅ ተከታታይ የሆነ ተግባር መከወን ይኖርበታል። እኔ ከመሬት እንዲነሳ የምፈልገው ሞት ላይ ላለው ወገኔ/ ልድርስለት ለማልችለው ወገኔ የመንፈስ ቅርበት እንጂ የአኖሌ ሃውልት መፍረስ ወይንም የታሪክ ውርርድ አይደለም። ምሳሌነቱ በዚህ ነው ተካክሶ ማዬት የምሻው፤ አብነቱ በዚህ መልክ ነው ተመጣጥኖ ማዬት እምፈልገው። ወያኔ „ኦሮምያ“ ብሎ በከለለው ቦታ አማራ/ አማርኛ ተናጋሪውም ግብር እየከፈለ፤ ግዴታውን እዬተወጣ ግን በድርብርብ ጭቆና ውስጥ ሰምጦ ስለሚገኝ፤ ሁነኛ አልባም ስለሆነ፤ የህግ ጥበቃም ስለማያገኝ፤ ለብዙሃኑ የአማራ/ አማርኛ ተናጋሪም ወገን ወኪል ሊሆኑለት ይገባል የተከበሩ አቶ ለማ መገርሳ። ይህ ሰብዕዊነትም ነው። ይህ ፍቅራዊነትም ነው። ይህ ተፈጥሯዊነትም ነው። ይህ ሰዋዊነትም ነው። ይህ ፍትሃዊነትም ነው። ይህ ተጠያቂነትንና ሚዛናዊነትን የሚያስተጋብር ነው። መድረሻ አልባ ነው አማራው በቀዬው መኖር ያልተፈቀደለት። እንዲወልድ ያልተፈቀደለት። ገጠር እኮ ከብት የሚያቆሙ ታዳጊ ወጣቶች የሉም፤ ታሪና ቁንጮ ያላት ታዳጊ ጉብል የለችም፤ መክኗል። አባ ወራው እና/ እማ ወራዋ የልጆቻቸውን ወልዶ – አሳድጎ – ድሮ – ኩሎ ማዬት አልተፈቀደለትም። ናዚዝም እኮ ነው …
እርግጥ ነው ዛሬ አይደለም አሁን ገና ያረጋ ደም ነው፤ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ አሁን ላለው ሁኔታ ይህ ሙቀት ለጋሽ መንፈሱ እራሱ በቂ ነው። ምንም ተጫማሪ ሃላፊነት በዚህ ለጋ መንፈስ ውስጥ ሊጫኑ አይገባም። ግን በፖሊሲ ደረጃ እንዲጠፋ የታወጀበትን ወገኖቾዎትን ሰቆቃ የእኔ የቤት ሥራ እንዲሉት አደራ ማለት እሻለሁ፤ በዚህ አጀንዳ ላይ ስለማልመለስበት። በዐዕምሮዎት ሰሌዳ በፕላን ያስቀምጡት ዘንድ በአክብሮት ላስታውሰዎት እሻለሁ። በክልለዎት፤ በሚያዙበት ቦታ የውስጡን ሰላሙን ያውጁለት እባክዎትን ለአማራ/ አማርኛ ለሚናገረው ወገኖዎት። ሰብስበው ያነጋግሩት፤ ከስሜቱ ጋር ይተዋወቁ፤ ካቢኔዎት በአጀንዳ በተመስጦ ሊወያይበት፤ ሊመክርበት እና ከውሳኔ ላይ ሊደርስበት የሚገባ የአምክንዮ ጭንቅላት ነው ነገረ አማራ/ ነገረ አማርኛ ቋንቋ።
  • የኢትዮጵያ ታሪክ ጉስቁልና የአማራ ብቻ አይደለም።

ሌላው እኔ አገር ቤት ሁለገብ የሆኑ ጉዳዮችን የተወሰኑትን ሚዲያ ላይ እከታተላለሁ። የክፍተቱ ዲካ ከ – እስከ የለውም። ይህን ሚስጢር ለገባው ነገረ አማራ ዛሬ ብቻ ሳይሆን ነገም የመንፈስ አቅም ዘር አልባነቱ ሥነ – ልቦናው የተራቆተ መሆኑን ልብ ሊለው ይገባል። በዬቦታው ያለው ማነቆ ትብትብ ነው። መፍቻውን ሰክኖ ማድመጥ ይገባል። …. ሊቃናቱ የአማራ፤ ነገን እታደጋለሁ ብሎ የተነሳውን „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ አዲስ አሰባሳቢ ምዕራፍ ከፋች ፖሊሲ በአማራ ዙሪያ እጅግ ሰፊ ጥልቅ ተግባር እና ተልዕኮ ጋር እንዲቆራኝ መትጋት ይጠበቅባቸዋል። አብሶ የአማራ ወጣት ታጋዮች አሁንም ደግሜ ላስገነዝባችሁ የሚገባው ቁም ነገር በታሪክ ዙሪያ የምታደርጉትን እሰጣ ግባ ተግ አድርጋችሁ፤  እንዲሁም እንደ መያዦ የሰነቃችሁትን የነገር ማነሳሻ ጉዳዮችን ተዎት አድርጋችሁ ሞት ላይ ላለው፤ ተቆርቋሪ ለሌለው፤ ከካርታ ውጪ ለሆነው የአማራ ትውልድን የማስቀጠል ተግባርር ላይ ትኩረት ብተሰጡት ነው የሚመረጠው። የኢትዮጵያ ታሪክ ጉስቁልና የአማራ ብቻ አይደለም። አማራ ብቻውን የኢትዮጵያን ታሪክ አልሠራም። ሁሉም ባለድርሻ ነው። አማራ መንግሥት አይደለም። ያለው መንግስት የማህበረ ተጋሩ ነው። በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ታሪክ ጉስቅልና የመላ ኢትዮጵውያን የቤት ሥራ ነው። አሁን የምታደርጉት ግን የኢትዮጵያ ታሪክ ጉስቁልና ባለቤትነቱን እራሱን የአማራ ታገድሎው አንዲሸከም የሚያስደረግ ዕድምታ አለው። ሌላ ጫና፤ ሌላ ተከሳሽነት እዬፈጠራችሁ ነው። በፍጹም ሁኔታ ያልተገባ መንገድ ነው። የራሳችሁን የቤት ሥራ ሥሩ አቅም ካላችሁ። ሌላ ነገርም እያቆጠቆጠ ነው። „አማራ ያልተረጋጋ ማህበረሰብ ነው፤ አማራን በወጥነት ማዬት አይችልም፤ አማራ ግለኛ ነው“ ወዘተ ይህ አዲሱ ምላጭ ነው። ለዛውም የሰላ። ከመደበኛ የተጋድሎው ደንበር ውጪ መንፈሱ እንዲባክን፤ በውስጠ ሰላም እጦት ተንጦ ተግባራቱን በአትኩሮት እንዳይከውን የታሰበ የሴራ ድር ነው። ሆን ተብሎ የተጫረ እሳት … ስለዚህ „ልብ ያለው ሸብን“ ታጠቁ።
  • ባርነትን ለመታደግ ቅንነትን አቤት ማለት

ሌላው ያ የአማራ ገድለኛ አብዮት ያልተደገፈበትን ምክንያት ከልብ ሆናችሁ ድምጹን ልታዳምጡት ይገባል። ለሌላ ተለጣፊ ታኮ የታጨበትንም እሰቡት። ተጋድሎ በነቀፌታ የታጠረበትን፤ በውጋት እንዲሰቀዝ የተደረገበትን፤ መክኖ እንዲቀር ያተለመለትን ሴራ ሁሉ ከልብ ሆናችሁ እሰቡት። የእኔ ብላችሁ ደጋግማችሁ አዳምጡት። እያላችሁ የሌላችሁ ስለምን ትሆናላችሁ? የአማራ ታገድሎውም ያልተደገፈበት ምክንያት የአማራ የህልውና ቀጣይነት በስጋት ተወጥሮ፤ ማህበራዊ ሰላሙን አጥቶ ግን አንገቱን ደፍቶ ለመናጆ አገልጋይነት፤ አቅሙ ለሌላ መወጣጫ ስለሚፈለግ ብቻ ነው። አማራ እኮ አሁን ኢትዮጵያ መሬት ላይ „ባሪያ“ ነው። ይህን የሚታደግ በእጅ ያለ የተደራጀ አቅም፤ ልብ የሚጣልበት አቅም አማራው የለውም። ስለሆነም ቢያንስ ቅን መንፈሶችን በቅንነት ለማዬት፤ ለማስተናገድ የሚችል ወጥ የሥነ – ልቦና አቅምን መገንባት ያስፈልጋል። ብልህነት። የ አያያዝና የአቀራርብ ጥበብ ቢያንስ ኦሮምያ በሚባለው „ክልል“ የሚኖሩት አማራዎች/ አማርኛ ተናጋሪዎች የኑሮ ዋስትና የሚገኙበት ጥሩ አጋጣሚዎችን ማመቻቸት ታላቁና ቀዳሚው ዓውራ ተግባራችሁ ሊሆን ይገባል። ይህን ማግኘት የሚቻለው ማናቸውንም ቅን መንገዶች ከልብ አክብሮ በመነሳት ብቻ ይሆናል።
ይህ መንፈስ የሚጎረብጣቸው፤ የሚቆረቁራቸው፤ በእነሱ ካልተፈተለ ሸማ የማይመስላቸው በግልም ይሁን የተደራጁ ሃይሎች ይኖራሉ። ከእነሱ መንፈስ ጋር የአማራን ተጋድሎ ማዳበል ልንደርስለት ለማንችለው ህዝብ የሞት ስንቅ፤ የስጋት ጥሪት እያስቀመጥንለት መሆኑን ልብ ልንለው ይገባል። ከሁሉ በላይ ዘሩ ጨርሶ ሊጠፋ ለተፈለገው አማራ የመተንፈሻ ቧንቧው ሊሆን ይገባል „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው።“ በዚህ መንፈስ ውስጥ ባለቤት አልባው አማራም፤ የኔባይ እንዲያገኝ ጥረት ማድረጉ ነው ተግባር ሊሆን የሚገባ። የኃይል አሰላለፍ እና የቅራኔ አያያዞችን ትንሽ ፊደል መቁጠር የሚያስፈልግ ይመስለኛል። በዬቦታው አማራዊውን መንፈሱን ለማስጠጋት የሚፈቅድ የለም … ይህን ከውስጣችን ሆነን እንዬው።
  • እንደ እርገት … 

… ሌላው መንፈስን እንደ ቅል የሚያንጠለጥለው፤ እረፍትም የሚነሳው አመክንዮ የአዲስ አበባ ኗሪዎች ጉዳይ ነው።ባለቤት የለውም። ስለሆነም የውስጥ ሰላማቸውን እንዲረጋጋ የሚያደርግ ነው ይህ „ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ መሪ መንፈስ። አብሶ ለህፃናት። ስለዚህም ይህን መንፈስ አቅም እንዲሆን እንክብካቤን ሳይሰቱ መስጠት ይገባል። በሰጠነው ልክ ነው ተጠቃሚ መሆን የሚቻለው። ሁሉም በትጋት የቻለ ቢያንስ የጸሎት አጥር ቅጥር ሊሠራለትም ይገባል ለ„ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው“ አዲስ ብቱን መንፈስን ሰብሳቢ ፖሊሲ።
ለመባቻ የሚሆን ፓን አፍሪካውያን የተፍነሸነሹበት የአዲስ ዓመት ዝግጅት … እንሆ //
 የፈንዲቃ ፕሬዚዳንት የአቶ ታከለ አለነ/ አለነ ታከለ አንዳዊ አንቀጥቅጥ ካቢኔን በኒወርክ ታይም ዕይታ/ ጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴ እንደ ተረጎመው እና እንደ አነበበው ….

ሰው እንደ „ሰው“ የሚቆጠርበት ዘመን አማላካችን ያምጣልን። አሜን!
እግዚአብሄር ይስጥልኝ። መሸቢያ ጊዜ። ደህና ሁኑልኝ – በትሁት ልቦና።





አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።

አብይ ኬኛ መቅድም።