#እፎይታዬ አጤ ዝናብ #ዜማዬ #ፍቅሬ ነው።

 


"አዋቂ ንጉሥ ሠራዊት ይመክራል፤
አዋቂ ዳኛም ሥራት ይሠራል።"
 
(መጽሐፈ ሲራክ ምዕራፍ ፲ ቁጥር ፩)
 
ዝናብ #ሲዘንብ ማዬት እጅግ ያስደስተኛል። ኮንሰርት ጉብቼ አላውቅም። ደስታዬን ስለማይሰጠኝ። ለእኔ የተፈጥሮ ኮንሰርት እምመሰጥበት ዜማዬ፤ ዝማሪዬ ነው።
 
በተለይ #ዠርከክ ብሎ ካለ ወጀብ ሰላማዊ ግርማ ሞገስ ተላብሶ #ሲያዠከዥከው ማህሌት ላይ ያለሁ እስኪመስለኝ ድረስ ሐሤት ይሰጠኛል።
 
የዝናብ ውሃ አቁቼ መጠጣትም በጣም ዕውዳለሁኝ። ቅዱስ ሆኖ ይሰማኛል። ንጹህ ሆኖ ይሰማኛል። ፈዋሽ ሆኖ ይሰማኛል። #ለጸጋዬ ራዲዮም ሲዲውን ገዝቼ ብዙ ራዲዮ ፕሮግራሞችን ሠርቸበታለሁኝ።
 
ዝናብ ፈውስ፤ መድህን እና ህይወት #አዳሽም ነው። እረፍት የወጣሁ ያህል ይሰማኛል። የምትናፍቀኝ ኢትዮጵያ ውስጥም እንዳለሁ ይሰማኛል። የኢትዮጵያ እየትገተለተለ፤ ያገኜውን ትርምስምሱ አውጥቶ እያግበሰበሰ የሚሄደው #ጎርፍ ሳይቀር ይናፍቀኛል። 
 
ዝናብ እና ጸሐይ ሲቀላቀሉ ደግሞ ልጅ እያለሁኝ "#ጅብ ወለደ" ይባል ስለነበር ያን አይጠገቤ የልጅነት ትዝታን ስለሚጠራልኝ ውስጤ #ፍንሽንሽ ይላል። አጤ ዝናብን ከልብ እወደዋለሁኝ፤ ከልብም ይናፍቀኛል። መንገድ ላይ ከሆንኩኝ ጥላም አልይዝም። እዮራዊ #ጸበሌ ነው። መድህን አገኛለሁኝ። ተፈጥሯዊ የውስጥ ጥራቱ እኮ ድንቅ ነው።
 
ዝናብ እየዘነበ መተኛት እራሱ ልዩ #ቴራፒ ነው። እወዳለሁኝ። ቤት ሆኜ ዝናብ ከመጣ የጀመርኩትን ሥራ ይሁን ምግብ #አቁሜ ቁሜ ሂደቱን በተመስጦ አያለሁኝ። አንዳንድ ጊዜ እቀርጸዋለሁኝ። በነገራችን ላይ ጥዋት ስነሳ የማዬው ቀዳሚ ነገር ሰማይን ማየት ነው። 
 
#የጉም #ጉዞ፤ የጉም #ፔንቲግም እጅግ የምወደው እዮራዊ ስጦታ ነው። ብዙ አለኝ። እግዚአብሄር አምላክ ውስጣችን #ሰውኛ#ተፈጥሮኛ ብናደርግለቴ ምን ያልሰጠን #ድንቃ ድንቅ ጸጋወች አሉና። 
 
BBC ስለ አጤ ዝናብ ጠቃሚነቱን ዘግቧል። እስኪ አንብቡት በረከቱን።
 
ግን ውዶቼ እንዴት ናችሁልኝ? እኔ አምላኬ ክብሩ ይስፋ ደህና ነኝ።
 
ቸር አስበን፤ ቸር እንሁን። አሜን።
ቅን አስበን፤ ቀና እንሁን። አሜን።
ኑሩልኝ። አሜን።
እግዚአብሄር ይስጥልኝ። አሜን።
 
ሥርጉተ©ሥላሴ።
Sergute©Selassie.
06/08/026.
 
ተፈጥሮዬ ኑርልን የእፎይታ መጠለያችን ነህና።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

የእኔ እማ ልዕልቴ እንዴት ነሽ?

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።