#ለነውር ሌላ #ነውር መመከቻ ሊሆን አይችልም።

 

#ለነውር ሌላ #ነውር መመከቻ ሊሆን አይችልም።
 
"ምድርን ሰንጥቀህ ፈሳሾችን አወጣህ።"
(ትንቢተ ዕንባቆም ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፱።)
 
#ምዕራፍ ፲፱።
 
ነውር ነውር ነው። ለነውር #ደረጃ ማውጣት አይቻልም።
በነውር ውስጥም ትምክህት ቦታ አይኖረውም። ነውረኝነት
ምኑ ያስመካ እና?
 
ለነውር ሌላ የነውር ዓይነት ለማነፃጸሪያ ሊቀርብ አይገባም።
ማነፃጸር መልካም ነገርን // ከመልካም ነገር ጋር ከሆነ የተገባ ነው።
በሌላ በኩል ነውር ይለፍ ከተሰጠው #ወራሪ ነው።
 
ነውር ከተፈቀደለት #ተስፋፊም ነው።
ለነውር የሚሰጠው ጊዜ ዕድሜን ይዘርፋል። ከነውር
ጋር መኖር የዕድሜ ብክነት በብክለት ነውና።
 
በነውር ውስጥ መኖር አፍ ባለው መቃብር
ውስጥ የመኖር ያህል ከባድ ነው። #ለምን?
ህሊናዊ ነፃነትን ስለሚፈትን።
 
ነውር ሲወጠን #እራስን ይገድላል። ነውር
ከመሰራጨቱ በፊት የራስን ሰብዕና #ቃሬዛ
ላይ አስቀምጦ ነው ወረራውን አህዱ የሚለው።
 
የነወር ካፒቴኑ #ክፋ ሃሳብ ነው። ክፋ ሃሳብ ስንቁ
የሰውን ልጅ መዋለ ህይወት መበርበር፤ መቦርቦር፤
በመጨረሻም ከጥቅም ውጪ ማድረግ ነው።
 
ያለ ነወር መኖር ይቻላል። #ቁጥቦች ይፈጽሙታል።
አማንያን የዕምነት ዶግማና ቀኖናቸውን ከተከተሉ
ያለ ነውር መኖር ይቻላል።
 
ነውር የሚጠጋው ሲፈቀድለት ብቻ ነው።
ነውር #አክ ከተባለ ድርሽ አይልም።
 
የነውር ዓይነቱ ብዙ ነው። አንዱ ክህደት ነው። መካድ።
ክህደቱ አፈፃጸሙ፤ አድራጊው እና ተደራጊው ቢለያይም
የነውርነቱን ተፈጥሮ ግን አይቀይረውም።
 
የሁሉም የህግ ትልልፍ ሁነቶች በሙሉ #ነውር ናቸው።
ህግ ጣሽነት። ትዳር - ሲከዳ፤ ቤተሳባዊነት - ሲከዳ፤
ጓደኝነት - ሲከዳ፤ ልጅነት - ሲከዳ፤ እህት - ወንድምነት
ሲከዳ፤ እናት አባታዊነት - ሲከዳ፤ አገር ሲከዳ ይሁን ኃላፊነት
ሲጣስ የድርጊቱ ዓውራ #ክህደት ነው።
 
ክህደት ሚዛን የለውም፤ በወቄት በኪሎ፤ ወይም በሜትር
በኪሎ ሜትር፤ ወይንም በጋሻ በክንድ #አይከነዳም። ረቂቅ
ነውና። መንፈስ ይለካልን? እእ።
 
ለዚህም ነው አንድን ነውር ከሌላ ነውር ጋር #መመዘን ይሁን ማፎካከር፤
ወይንም ማነፃጸር አይቻልም የምለው።
 
እናቱን የከዳ አባቱን ከከዳ ጋር ማነፃጸር አይገባም። ክህደቱንም
ማፎካከር አይገባም።
 
ክህደቱ ሲታሰብ ገና ፈፃሚው አቶ #ሀ የነውር ቤተሰብ ይሆናል።
ነውረኝነት እክልን መፍጠር ነው በራስ ተፈጥሮ ላይ።
 
እንደ ወርቅ የነውር ደረጃ ሊያወጡ የሚሹ ሰብዕናወች ይገርሙኛል።
አይቻልም።
 
ሌላው ምንጊዜም ነውር #መሃን ነው። መሃንነቱ ለራሱም ነው። በነውር
ውስጥ ለመኖር መወሰን #የአረጠ የኑሮ ዘይቤ በመሆኑ።
 
እርግጥ ነው የተሰጣቸው፤ በልካቸው ለመኖር የፈቀዱ፤ ከነውር
እራሳቸውን #ያቀቡ ይኖራሉ። በእነሱ ንጽህና ነው ዓለም ጸንታ የኖረችው።
 
"እናንተ ነውርና ነቀፋ የሌላችሁና ቅዱሳን አድርጎ
በእርሱ ፊት ያቀረባችሁ ዘንድ በፊት የተለያችሁትን
ክፋ ሥራችሁንም በማድረግ፤ በአሳባችሁ ጠላቶች
የነበራችሁትን አሁን በሥጋው ሰውነት በሞቱ በኩል
አስታረቃችሁ።"
 
 (ቆላስያስ ምዕራፍ ፩ ቁ ፳፩ - ፳፪)
 
ቸር አስበን፤ ቸር እንሁን። አሜን።
ቅን አስበን፤ ቀና እንሁን። አሜን።
ኑሩልኝ። አሜን።
 
እግዚአብሄር ይስጥልኝ። አሜን።
ሥርጉተ©ሥላሴ።
Sergute©Selassie.
03/08/026.
ጊዜ ራዲዮሎጂ ነው።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

ዛሬ ያለው ነገር „ፈረቃም፤ ተረኝነትም“ አይደለም።

የእኔ እማ ልዕልቴ እንዴት ነሽ?

እህት አጊቱ ጉደታ አገር ነበረች።